በርካታ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በተለያየ የአፍሪካ ሀገራት እየታሰሩ መሆኑ ቢታወቅም፤ በርካታ ወጣቶች አሁንም በመሰደድ ላይ መሆናቸውን ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት አስታወቀ
በተለያዩ የምዕራብና ደቡባዊ አፍሪካ ሀገራት ቁጥራችዉ በትክክል ሊታወቅ ያልቻለ ስደተኛ ኢትዮጵያውያን በእስር ላይ መሆናቸውንና በርካታ ወጣቶች ከሀገሪቱ በመሰደድ ላይ እንደሚገኙ የአለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት (IOM) ሐሙስ አስታወቀ ። ባለፉት ስድስት ወራቶች ብቻ በተለያዩ 10 የአፍሪካ ሀገራት ለዚሁ ችግር ተጋለጠዉ የነበሩ 1ሺ 657 ኢትዮጵያዉያንን ወደ ሀገር ቤት መመለስ እንደቻለም ድርጅቱ ገልጿል።
የዓለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት ስደተኞቹን ወደ ሀገር ለማመላለስ ጥረትን ቢያደርግም አሁንም ድረስ በርካታ ወጣቶች ከሀገሪቱ በመሰደድ ላይ መሆናቸው ስጋትን እየፈጠረ መምጣቱን አክሎ አመልክቷል።

በተያዘዉ ሳምንት በዛሚቢያ በህገ-ወጥ መንገድ ገብታችኋል ተብለዉ የተላለፋባቸዉን የእስር ቅጣት የጨረሱና ወደ ሀገር መመለስ ያልቻሉ 14 ታዳጊ ህፃናት ወደ ኢትዮጵያ መመለሱን የስደተኞች ተቋም ገልጿል። በማላዊ ፣ ዛሚቢያ ፣ ታንዛኒያ እና ሌሎች ሀገራት ቁጥራቸዉ በትክክል ሊታወቅ ያልቻለ ስደተኞች በእስር ላይ የሚገኙ ሲሆን የእስር ጊዜያቸውን ያጠናቀቁ ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸዉ የሚመልሳቸዉ ባለመኖሩ ለችግር ተጋልጠዋል ። የማላዊ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾ ድርጅቶችና ግለሰቦች ከ120 የሚበልጡ ኢትዮጵያዉያን በእስር ቤት እየደረሰባቸዉ ያለን ስቃይ በመቃወም ስደተኞቹ ወደ ሀገራቸዉ እንዲመለሱ በመጠየቅ ዘመቻን መክፈታቸዉ ይታወሳል።
የምዕራብና ደቡባዊ አፍሪካ ሀገራትን በመጠቀም ስደተኛ ኢትዮጵያውያኑ ወደ ደቡብ አፍሪካ የመግባት እቅድ እንዳላቸዉ የተለያዩ አካላት ይገልፃሉ። ሰሞኑን የአለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት (IOM) ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት ታዳጊ ህፃናት በርካታ ኢትዮጵያዉያን በተለያዩ ሀገራት በሚገኙ እስር ቤቶች በስቃይ ላይ መሆናቸዉን እንዳስታውቁ ድርጅቱ በችግሩ ዙሪያ ባወጣዉ ሪፖርት አመልክቷል።
የስደተኛ ድርጅቱ ለችግር ተጋልጠዉ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገር ለመመለስ እያደረገ ባለዉ ጥረት ባለፉት 6 ወራቶች ብቻ 1 ሺ 657 ስደተኞች ከ10 የፍሪካ ሀገራት ሊጓጓዙ ችለዋል። መንግስት በተለያዩ ሀገራት ለችግር ተጋልጠዉ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን በተመለከተ እስካሁን ድረስ የሰጠው ምላሽ የለም ።
ምንጭ፡- ኢሳት
በጎንደር በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 ያላነሱ ሰዎች ሲገደሉ፤ በአካባቢው ውጥረቱ እንደቀጠለ ነው
በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን በሚገኘው ጎንደር ከተማ፤ በያዝነው ሳምንት ማክሰኞ ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት ጀምሮ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 ያላነሱ ዜጎች መገደላቸው ተጠቆመ፡፡ መረጃዎች እንደሚመለክቱት ከሆኑ፤ 10 ያህል ንፁሃን ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ርምጃ መገደላቸውን ተከትሎ፤ ህዝቡ በወሰደው የአፀፋ እርምጃ 9 የፌደራል ፖሊስ እና 1 የመከላከያ ሰራዊት አባል ተገድለዋል፡፡
በስፍረው የሚገኙ የዓይን እማኞች በበኩላቸው የተገደሉ ሶወች ቁጥር ከተጠቀሰው እንደሚልቅ ይናገራሉ፡፡ ይሁን እንጂ በግጭቱ የተገደሉ ሰዎችን ቁጥር በተመለከተ እስካሁን ከገለልተኛ አካልም ሆነ ከመንግሥት የተሰጠ ማረጋገጫ የለም፡፡

ባለፈው ማክሰኞ ሐምሌ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረ ግጭት በጎንደር ለሁለት ተከታተይ ቀናት የነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ ወደሌሎች አጎራባች ከተሞች መዛመቱ ተሰምቷል፡፡ ህዝባዊ ተቃውሞውም ሐሙስ ወደ ዳባርቅ ከተማ የተዛመተ ሲሆን፤ አሁን ደግሞ ወደ ሳንጃ ወረዳ እና ወደ ሌሎች አጎራባች ከተሞችና ወረዳዎች መዛመቱ እየተነገረ ነው፡፡

በተፈጠረው ግጭትም የሰው ህይወትን ጨምሮ የህወሃት እና የደጋፊው ናቸው የተባሉ ንብረቶች መውደምንም አስከትሏል፡፡
የግጭቱ መንስኤ የወልቃይት ጠገዴ ህዝብ የአማራ ማንነትና ተያያዥ መብታቶቻችን ይከበሩልን የሚል ጥያቄን ለትግራይ ክልላዊ መስተዳደርና ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ሲያቀርቡ የነበሩ ተወካይ ኮሚቴዎችን ከሚኖሩበት ጎንደር ከተማ የትግራይ ክልልና የፌደራሉ መንግሥት የፀጥታ ኃይሎችና የደህንነት አባላት ለማፈን እና ለማሰር በወሰዱት የኃይል እርምጃ በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑ ይታወቃል፡፡
በተለይ ከወልቃይት የአማራ ማንነት ተወካይ ኮሚቴዎች መካከል ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ፤ ሊያግቷቸው የመጡ የፀጥታ ኃይሎችን “ህጋዊ ከሆናችሁ በቀን መምጣት ትችላላችሁ፤ ካልሆነ በሌሊት እኔ እጄን ለማንም አልሰጥም” ማለታቸውን ተከትሎ በተፈጠረው አለመግባባት፤ ህዝቡ የመንግሥት ኃይሎችን የሌሊት እገታና ሌሎች 4 የኮሚቴ አባላትን እስርና እገታ በመቃወም ከመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ጋር ግጭት እንደተፈጠረ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡
በጎንደር በተፈጠረው አለመረጋጋት የተባበሩት መንግሥታትን ጨምሮ የአሜሪካና የእንግሊዝ መንግሥታት ዜጎቻቸው ወደጎንደርና አቅራቢያው ከመሄድ እንዲቆጠቡ አስጠንቅቀዋል፡፡ እስራኤል በበኩሏ በጎንደር የሚገኙ 6 ሺህ ቤተ እስራኤላውያንን እና በስፍራው የሚገኙ በኢትዮጵያ የእስራኤል ኤምባሲ ተወካዮችን ደህንነት በተመለከተ ከፍተኛ ቁጥጥር ወደሚደረግበት ስፍራ ጥበቃ እያደረገችላቸው መሆኑን የኢየሩሳሌም ፖስት ዘገባ አመልክቷል፡፡
በጎንደር ግጭቱ ለጊዜው የተረጋጋ ቢመስልም፤ አሁንም በአካባቢው በመንግሥትና በህዝቡ መካከል ከፍተኛ ውጥረት መኖሩ እየተገለፀ ነው፡፡
በጎንደር ህዝባዊ ተቃውሞ እና ውጥረቱ ቀጥሏል
(አዲስ ሚዲያ) በጎንደር ከተማ የወልቃይት የማንነት ጥያቄን የሚመሩ የኮሜቴ አባላትን ለማሰር በተወስደ እርምጃ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ከፍተኛ ግጭት አስከተለ። ግጭቱ የተከሰተው ትናንት ሰኞ ሐምሌ 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ሌሊት ጀምሮ እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
የመንግሥት ደህነት እና የፀጥታ ኃይሎች የወልቃይት ማንነት ጥያቄ የሚመሩ ኮሜቴ አባላት መካከል አቶ አታላይ ዘርፌ፣ አቶ ጌታቸው አደመ፣ አቶ መብራቱ ጌታሁንና አቶ አለነ ሻማ በቁጥጥር ስር ያደረገ ሲሆን፣ ኮሎኔል ደመቀ ዘውዴ በህግ የምትፈልጉኝ ከሆነ ሲነጋ መምጣት ትችላላችሁ በማለታቸው በተፈጠረው አለመግባባትና ግጭት በግድ እጅ እንዲሰጡ በኃይል በመንቀሳቀሳቸው ኮሎኔሉ እርምጃ መውሰዳቸው ተሰምቷል። ለምንግሥት የፀታ ኃይል እጃቸውን እንዲሰጡ በኃይል የተጠየቁት ኮሎኔል ደመቀ ዘውዴ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው፤ ቤታቸው በፀጥታ ኃይል መከበቡን ተሰምቷል፡፡ በተፈጠረው አለመግባባት ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት በመገደላቸው በህዝቡ በተወሰደ የአፀፋ እርምጃ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎችም መገደላቸውን የኢሳት ዘገባ አመልክቷል፡፡

መንግሥት ማክሰኞ ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጎንደርና ወልቃይት አካባቢን በተመለከተ ማምሻውን በሰጠው መግለጫ በተፈጠረው አለመግባባት 3 የልዩ ሃይል ፖሊሶች ሲገደሉ፣ 5 መቁሰላቸውን አስታውቋል። ይሁን እንጂ መንግሥት ለግጭቱ መንስኤ የወልቃይት ማንነት መብት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላትን በቁጥጥር ስር ለማዋል መሆኑን ከመግለፅ በመቆጠብ በቁጥጥር ስር ያዋላቸውን እና ለማዋል የፈለጋቸውን የወለወቃይት ማንነት መብት አስተባባሪ ኮሚቴ አባላትን ከኤርትራ መንግሥት ጋር በማያያዘ ሲወነጅል ተሰምቷል፡፡
በያዝነው 2008 ዓ.ም. ቀደም ሲል የወልቃይት ማንነት መብት ጥያቄ አቅራቢ ኮሚቴ አባላት መካከል አቶ ሲሳይ ሊላይ የሚባሉ የኮሚቴ አባል በትግራይ ክልል ልዩ ኃይል ታግተው ከተሰወሩ በኋላ በአካባቢው ውጥረት መንገሡን ተከትሎ ወህኒ ቤት በማሰር ለፍርድ ማቅረባቸው አይዘነጋም፡፡ የእስርና ፍርድ ጉዳያቸውም በሰቲት ሁመራ መቀጠሉ ታውቋል፡፡
ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ፤ በጎንደር የመንግሥት የኃይል ርምጃን በመቃወም ህዝቡ ንብረትነቱ የህወሓት/ኢህአዴግ የሆነውን ሰላም የህዝብ ማመላለሻ አውቶቡስ፣ በተጨማሪ ሌላ መለስተኛ የፀጥታ ኃይሉ ተሽከርካሪ እና በጎንደር ከሚገኙ የህወሓት የንግድ ኩባንያ መደብሮች መካከል የተወሰኑት ላይ የማቃጠል ርምጃ መወሰዱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በተቃውሞው ከጎንደር አዲስ አበባ ያሉ መንገዶችም በድንጋይ ተዘግተው ታይተዋል፡፡
መንግሥት በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 አካባቢ 6 ያህል ነዋሪዎች ገድሎ ከ3 ሺህ ያላነሱ ነዋሪዎችን ቤት አፈረሰ
(አዲስ ሚዲያ) በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፈለ ከተማ ወረዳ 1 በተለምዶ ሐና ማርያም፣ ፉሪ፣ ቀርሳ፣ ኮንቱማ እና ማንጎ ጨፌ አካባቢ ነዋሪዎች ላይ መንግሥት በወሰደው የኃይል ርምጃ አንዲት ነፍሰጡር እናት እና አንድ ቄስን ጨምሮ 6 ያህል ሰዎች ሲገደሉ፤ ከ 3 ሺህ ያላነሱ የመኖሪያ ቤቶች በዶዘር እየፈረሰ መሆኑ ተጠቆመ፡፡ መንግሥት የኃይል ርምጃውን የወሰደው ሐሙስ ሰኔ 23 እና ትናንት አርብ ሰኔ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ሲሆን፤ በአካባቢው ህፃናት፣ ሴቶች እና ነፍሰጡር የሆኑ እናቶችን ጨምሮ በርካታ ሰዎች መፈናቀላቸው ታውቋል፡፡ በተለይ አንዲት ነፍሰጡር እናት በቤቷ ተኝታ እያለ፤ ቤቷ በዶዘር ሲፈርስ እዛው መገደሏም ተሰምቷል፡፡

የቤቶቻቸውን በክረምት መፍረስና የመንግሥትን የኃይል ርምጃ የተቃወሙና በጉዳዩ ዙሪያ የሌሉትን ጨምሮ በርካታ ሰዎች መታሰራቸውም የተገለፀ ሲሆን፤ የአካባቢው ወንዶች እየፈረሱ ባሉ ቤቶች አካባቢ እንዳይገኙ አካባቢው በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ስር መውደቁ ታውቋል፡፡ በዚህም ምክንያት የአካባቢው ነዋሪዎች ከቤቶቻቸው መፍረስ በተጨማሪ የመንግሥትን ግድያ እና እስር በመፍራት ከአካባቢው መሰደዳቸው ተጠቁሟል፡፡
መንግሥት የነዋሪዎቹን ቤት በክረምቱ የዝናብ ወቅት ጠብቆ ለምን ማፍረስ እንደወሰና እንደጀመረ ባይታወቅም፤ እንዲፈርሱ የተወሰኑ ቤቶችን የማፍረስ ስራው እንደሚቀጥል አስታውቋል፡፡ በአካባቢውም ቤቶቻቸው በዶዘር እንዲረስ የተደረጉባቸው ሰዎች ንበርትም አብሮ ከጥቅም ውጭ እንዲሆን መደረጉን የአካባቢው ሴቶች ይናገራሉ፡፡
ቀደም ሲል ረቡዕ ሰኔ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. መንግሥት ወደ 30 ሺህ የሚጠጋ የነዋሪዎችን ቤት “ህገወጥ ነው፣ መፍረስ አለበት” በሚል መወሰኑን ተከትሎ ቅሬታ በመቅረቡ፣ የአካባቢው ወረዳ 1 አስተዳደር ነዋሪውን በቦታውና በቤቶቹ ጉዳይ እንነጋገር ብሎ ሰብስቦ እያወያየ ሳለ፤ በጎን አፍራሽ ግብረ ኃይልና የፀጥታ ኃይል ልኮ ማፍረስ በመጀመሩ በተፈጠረ አለመግባባት የወረዳው ስራ አስፈፃሚ እና ፖሊሶች መገደላቸውን፣ ከነዋሪዎችም ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሰዎች መገደላቸውን እና መቁሰላቸው ይታወሳል፡፡
ከቤቶቹ መፍረስ ጋር በተያያዘ የሰብዓዊ መብት ጉባዔ (ሰመጉ)፤ መንግሥት ከ19 ሺህ ያላነሱ ቤቶችን ማፍረሱን በመጠቆም፤ እየተወሰደ ያለውን የኃይል እርምጃ እንዲያቆምና ቤቶቹን አፍርሶ ነዋሪዎቹን ለጎዳና ህይወት ከመዳረግ ይልቅ መፍትሄ ሊበጅለት እንደሚገባ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ጠይቋል፡፡
በምሥራቅ ሐረርጌ ዞን አወዳይ ከተማ በተቀሰቀሰ ግጭት 4 ሰዎች ተገደሉ
(አዲስ ሚዲያ)በምስራቅ ሐረርጌ ዞን አወዳይ ከተማ ትናንት ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት በመንግሥት ኃይሎች እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረ ግጭት የ9 ዓመት ህፃንን ጨምሮ 4 ያህል ነዋሪዎች በከተማው አስተዳደርና በፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡ በአካባቢው የሚገኘው የሐሮማያ ሆስፒታል በበኩሉ የተገደሉት ሰዎች ቁጥር 4 መሆኑን እና የቆሰሉ 3 ሰዎች በሆስፒታሉ የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው ተጠቁሟል፡፡ የአካባቢው ነዋሪዎች እንደሚሉት ከሆነ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 6 እንደሆነ እና በፅኑ የቆሰሉት ደግሞ 4 እንደነበሩ ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡

በዕለቱ የግጭቱ መነሻ እንደሆነ የተነገረው በአወዳይ ከተማ ውስጥ ያለ አንድ የሞባይል ስልክ መሸጫ ሱቅና አጠገቡ ያለው የፍራሽ መሸጫ ሱቅ ባልታወቀ ምክንያት በመቃጠላቸው የተነሣ የአከባቢው ህዝብ እሳቱን ለማጥፋት ጥረት ቢያደርግም ሊሳካ ባለመቻሉ በአከባቢው ያሉትን የባለሥልጣናት ለእርዳታ ቢማፀኑም ቆመው ከመሳቅ ባለፈ ምንም እርዳታ ባለማድረጋቸው የተበሳጩ ነዋሪዎች “ድሮም እናንተ የምታደርጉልን ነገር የለም” ስለዚህ ከዚህ ሂዱ ብለው በመናገራቸው የፀጥታ ኃይሎች በስልክ ወደ ቦታው መጠራታቸውንና ግጭቱ መከሰቱን የአካባቢውን ነዋሪ ዋቢ በማድረግ የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የነጋዴዎቹን ሱቅ ቃጠሎ ተከትሎ በህዝቡና በመንግሥት በተለይም በአካባቢው አስተዳደር አካለትና የፀጥታ ኃይሎች ጋር በተፈጠረ አለመግባባት የአወዳይ ቀበሌ 02 ሊቀመንበር አቶ አብዲ ኢድሪስ በቃጠሎው ስፍራ የነበሩ ነዋሪዎች ላይ በከፈቱት ተኩስ የ9 እና የ13 ዓመት ህፃናት ቆሰሉ፡፡ በሊቀመንበሩ የቆሰሉ ህፃናትም ወደ አካባቢው የጤና ተቋም ቢወሰዱም ወዲያው ህይወታቸው ማለፉ ታውቋል፡፡ በዚህም ምክንያት በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች በቁጣና በጩኸት ወደቆሰሉ ህፃናት ሲመጡ የኦሮሚያ ልዩ ፖሊስ እና የፌደራል ፖሊስ በድንገት ወደስፍራው በመምጣት፣ አንድ የፌደራል ፖሊስ አባል ተኩስ ከፍቶ 3 ወጣቶች ወዲያው ሲገደሉ፤ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ሰዎችም በፅኑ መቁሰላቸውን በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኝ ተናግረዋል፡፡

በመንግሥትና በህዝቡ መካከል በተፈጠረው ግጭት ምክንያት በአወዳይ የሐረር መንገድ ዝግ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ይሁን እንጂ በግጭቱ ዙሪያ እስካሁን ከመንግሥት አካል የተሰጠ መግለጫም ሆነ ማብራሪያ ማግኘት አልተቻለም፡፡