በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉት “ፀረ- ሰላም ህፃናት”
ጌታቸው ሽፈራው
አቶ ቀኖ የሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት ውስጥ በጥበቃነት ይሰራሉ፡፡ አቶ ቀኖና ጎረቤቶቻቸው ሰብሰብ ሲሉ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ በተለይ ኢህአዴግ ስለሚወስዳቸው ህገ ወጥ እርምጃዎች፣ ስለተቃዋሚዎች ጥንካሬና ድክመት… የመሳሰሉት ጉዳዮች ላይ ያወራሉ፣ ይወያያሉ፣ በሚያከራክሯቸው ነገሮችም ይከራከራሉ፡፡ ይህ የእነ አቶ ቀኖ ሰፈር ሰዎች የውይይት መድረክ በእነሱ ብቻ ተወስኖ አልቀረም፡፡ ጉዳዩ በመደጋገሙ ህፃናት ልጆቻቸው ሳይቀር ‹‹ሰማያዊ፣ አንድነት፣ መድረክ፣ ኢህአዴግ…..›› እያሉ የአቅማቸውንና የገባቸውን ያህል ያወራሉ፡፡ ቤተሰቦቻቸው ሲከራከሩና ሲያወሩ ከሰሙት! በዚህ አቋማቸውም ህፃናቱ ‹‹ፀረ ሰላም›› ተብለው ታስረውበታል፣ ተደብድበውና ይቅርታ ጠይቀውም ተለቀዋል፡፡
ማክሰኞ ጥር 19 ቀን 2007 ዓ.ም ነው፡፡ ከቀኑ 11፡30 አካባቢ አራዳ ክፍለ ከተማ የሚገኘው መስከረም 2 ት/ቤት ተማሪዎች የሆኑት 14 ያህል ህጻናት ወደ ቤታቸው እየተመለሱ ነው፡፡ ህፃናቱ እንደወትሯቸው ከት/ቤተ መልስ እየተጨዋወቱ፣ እየተቀላለዱ፣ እየተሯሯጡ ወደ ቤታቸው በመመለስ ላይ ናቸው፡፡ መሃል ላይ ግን ቤተሰቦቻቸው በተደጋጋሚ የሚያነሱትን ጉዳይ አንስተው መከራከር ጀምረዋል፡፡ የ13 አመት እድሜ ያለውና የ6ኛ ክፍል ተማሪ የሆነው የአቶ ቀኖ ልጅ ‹‹ኢህአዴግኮ ፈሪ ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲን ይፈራዋል›› ይላል፡፡ ጓደኛው ደግሞ ‹‹ኢህአዴግማ የሚፈራው አንድነትን ነው፡፡›› ይላል፡፡ ሌላኛው ደግሞ ‹‹መድረክ የሚባል ፓርቲምኮ አለ፡፡ እሱንም ይፈራዋል፡፡ ኢህአዴግ ፈሪ ነው!›› ይላል፡፡ ሌሎቹም ቤተሰቦቻቸው ውሃ፣ መብራትና ኔትዎርክ ሲጠፋ፣ ኑሮ ሲወደድ፣ ሙስና ሲያስመርራቸው በስርዓቱ ላይ ከሚያሰሙት ሮሮ መካከል የሚያስታውሱትን እየጠቀሱ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ይከራከራሉ፣ ያወራሉ፡፡ ይቀልዳሉ!
ይህኔ ነው አስገራሚው ነገር የተከሰተው፡፡ ፖሊስ 14ቱንም ህፃናት በ‹‹ፀረ ሰላም›› እንቅስቃሴያቸው ከእነ ሙሉ የትምህርት መሳሪያቸው በቁጥጥር ስራ ካዋላቸው በኋላ በጥፊና በእርግጫ እያለ ወደ ወረዳ 7 ፖሊስ ጣቢያ ይወስዳቸዋል፡፡ ፖሊስ ጣቢያ ከደረሱ በኋላም ‹‹ተንበርከክ!›› ተብለው ‹‹ማን ነው ሰማያዊ፣ አንድነት፣ መድረክ እያለ ሲያወራ የነበረው?›› እየተባሉ ህፃናት ላይ ይፈፀማል ተብሎ የማይታሰብ ድብድባ ይፈፀምባቸዋል፡፡ ህፃናቱ ‹‹ፀረ ሰላም›› ለተባለው እንቅስቃሴያቸው ቅጣትና ማስፈራሪያ ከተደረገባቸው በኋላ ‹‹ከአሁን በኋላ አይደግመንም›› ብለው ይቅርታ ጠይቀው በ‹‹ፖሊስ ሆደ ሰፊነት›› ከምሽቱ 1 ሰዓት አካባቢ ከእስር ተለቀዋል፡፡
እነዚህ ህጻናት ‹‹ዳግመኛ አይለምደንም!›› ብለው ይቅርታ ባይጠይቁ ኖሮ ታስረው ሊያድሩም ይችሉ ነበር፡፡ ምን አልባትም ፖሊስ ‹‹ያልተፈቀደ ቅስቀሳ አድርገዋል፣ ህገ መንግስቱን ለመናድ ጥረዋል፣ ህዝብን ለማናወፅና አመጽ ለመቀስቀስ ተደራጅተው ተንቀሳቅሰዋል፣ ምርጫው ሰላማዊ እንዳይሆን እየሰሩ ነው….›› የሚል ክስ እንደማይመሰርት እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ እስካሁን ፖሊስ ሲያቀርባቸው ካየናቸው አስቂኝ የቀጠሮ ማራዘሚያ ‹‹ምክንያቶች›› አንጻር ‹‹አብረዋቸው የሚማሩት ሌሎች ግብረ አበሮቻቸው አልተያዙም፣ ቢወጡ አሁንም ተመሳሳይ ‹ፀረ ሰላም› ተግባር ይፈፅማሉ፣ መረጃ ይደብቁብኛል›› በሚል ተጨማሪ ቀን ይሰጠኝ ላለማለቱ እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡
ስርዓቱን ለመከላከል ሲባል እስሩ እዚህ ደርሷል!
የአንድነት ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት በፖሊስ ቁጥጥር ስር ዋለ
አዲስ አበባ ቀበና የሚገኘው የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዋና ጽህፈት ቤት በፖሊስ እና ደህንነቶች ቁጥጥር ስር ዋለ፡፡ የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት በቁጥጥር ስራ የዋለው ምርቻ ቦርድ ለእኔ ይታዘዘኛል በሚል የፓርቲውን ስምና ህልውና ለነ አቶ ትዕግስቱ አወሉ ማስረከቡን ተከትሎ ነው፡፡ ፖሊስ አርብ ጥር 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ጽህፈት ቤቱን ከመቆጣጠሩ በፊት የፓርቲው ስራ አስፈፃሚዎች ስብሰባ ተቀምጠው እንደነበርና በዕለቱ ከሰዓት በኋላ የፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት በምርጫ ቦርድ ውሳኔ ጉዳይ ለመምከር ወደ ጽህፈት ቤቱ ሲያመሩ በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉ ተረጋግጣል፡፡ በዕለቱ ጠዋት ስራ አስፈፃሚው በጉዳዩ ዙሪያ ከመከረና ከተወያየ በኋላ ለምሳ ወጥተው ለምክር ቤቱ ስብሰባ ሲመለሱ ወደ ቢሮው መግባት የተከለከሉ ሲሆን፤ ቢሮው በፖለስ ቁጥጥር ስር በመዋሉ ቀጠሮ የተያዘለት የፓርቲው ምክር ቤት ስብሰባም ሳይካሄድ መቅረቱ ታውቋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ የፓርቲው ስራ አስፈፃሚዎች ለምሳ ሲወጡ ትተዋቸው የሄዷቸውን ተሸከርካሪም ሆነ ማንኛውንም ወረቀት ይዘው እንዳይወጡ ከታገዱ በኋላ ፖሊሶቹ በስልክ በተሰጣቸው ትዕዛዝ ስራ አስፈፃሚዎቹ መኪናቸው ብቻ ተፈትሾ እንዲወጣ መደረጉን የፓርቲው ምክትል ፕሬዘዳንት አቶ ግርማ ሰይፉ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ተናግረዋል፡፡ ፖሊስ ቢሮውን ሲቆጣጠር ከስራ አስፈፃሚው ውጭ በቢሮ ያሉ የፅህፈት ቤት ሰራተኞችና ሌሎች የፓርቲው አባላትና አመራሮች ላልተወሰነ ጊዜ ከቢሮ እንዳይወጡ፣ከግቢ ውጭ የነበሩትም እንዳይገቡ መደረጉን የአይን እማኞች ለአዲስ ሚዲያ ገልፀዋል፡፡ ፖሊስ ቢሮውን በኃይል ሲቆጣጠር ምንም ዓይነት የፍርድ ቤት ትዕዛዝ አለመያዙ ታውቋል፡፡ የአንድነት ፓርቲ ዋና ፅህፈት ቤት በምርጫ ቦርድ እነ ትዕግስቱ አወሉ ከተመረጡ በኋላ አሁንም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ይገኛል፡፡
በተመሳሳይ ዜና አዲስ አበባ ቸርችል ጎዳና አካባቢ የሚገኘው የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ዋና ጽህፈት ቤትም በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉ ተጠቁሟል፡፡ ፖሊስ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ የፓርቲዎቹን ዋና ጽህፈት ቤት ለምን እንደተቆጣጠረ እስካሁን የተገለፀ ነገር የለም፡፡ የአዲስ ሚዲያ ፖሊስ ምንጮች እንዳረጋገጡት ከሆነ፤ፖሊሶችም የፓርቲዎቹን ቢሮዎች ተቆጣጠሩ የሚል ትዕዛዝ ከመሰጠቱ በስተቀር ለምን እንደተቆጣጠሩ ራሳቸውም ምክንያቱን እንደማያውቁ ተጠቁሟል፡፡ ምርጫ ቦርድ መጪውን ምርጫ 2007 ዓ.ም. ሂደትን ተክትሎ በዋዜማው ሁለት አንድነት እና መኢአድ ፓርቲዎችን በማፍረስ ሌላ አዲስ ታሪክ አስመዝግቧል፡፡ ቀደም ሲል “የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ” ከህወሓት/ኢህአዴግ የተሰጠውን ትዕዛዝ ከማስፈፀም ውጭ ነፃና ገለልተኛ አይደለም፣ቦርዱን የሚመሩት ስራ አስፈፃሚዎችም ተቋሙን ለመምራት የሚያስችል አቅምና ቁርጠኝነት ስለሌላቸው ለተቋሙ አይመጥኑም፣..በሚል በተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተደጋጋሚ ትችት ይቀርብበት እንደነበር አይዘነጋም፡፡
አሁን ያለው የቦርዱ እንቅስቃሴ በቀጣይ ቀናትም ከምርጫው ዋዜማ እስከ ድህረ ምርጫ አዳዲስ ውሳኔዎችን እና እንቅስቃሴዎችን ሊያሳይ እንደሚችል ይጠበቃል፡፡
ሰበር ዜና፤ ምርጫ ቦርድ አንድነትና መኢአድን ፓርቲን ለእነ ትግስቱ አወሉና ለእነ አበባው መሐሪ ሰጠ
- ‹‹እውቅናውን የሰጠነው ለቦርዱ ለሚታዘዘው ነው›› -ፕሮፌሰር መርጋ በቃና
ምርጫ ቦርድ አንድነትን ለእነ ትግስቱ አወሉ፣ እንዲሁም መኢአድን ለእነ አበባው መሃሪ መስጠቱን ዛሬ ጥር 21 ቀን 2007 ዓ.ም በሂልተን ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አሳወቀ፡፡ ምርጫ ቦርድ በመግለጫው ‹‹የእነ በላይ በፍቃዱ ቡድን›› በጠቅላላ ጉባኤ እንዳልተመረጠ፣ አምስት አባላት ያሉት አስመራጭ ኮሚቴ አባላት እንዳልመረጠ፣ የተመረጡበትም 51 ሲደመር አንድ መርህ አለመሆኑን፣ ጠቅላላ ጉባኤ ሲያደርግ ሪፖርት አለማድረጉንና ለአባላቱና ለፓርቲው ክብር የሌለው በመሆኑ ፓርቲውን ማስቀጠል እንደማይችል ገልጾአል፡፡
በሌላ በኩል የትግስቱ አወሉ ቡድን መርህ ይከበር እያለ እየታገለ በመሆኑ፣ የኢ/ር ግዛቸው ካቤኔ አባላት ተገፍተው የወጡ በመሆናቸው፣ ጠቅላላ ጉባኤ አድርገው ለቦርዱ ሪፖርት እንዳደረጉ፣ ‹‹የእነ በላይ ቡድን›› ፈቃደኛ ባለመሆኑ እንጂ እነሱ ችግራቸውን በውይይት ለመፍታት ፈቃደኛ በመሆናቸው እንዲሁም ለአባላቶቻቸውና ለፓርቲው ክብር ስላላቸው እውቅናውን ለእነሱ ሰጥቻለው ብሏል፡፡ ምርጫ ቦርድ በመግለጫው ‹‹ምርጫ የሚገባ ፓርቲ በማስፈለጉ፣ ‹‹የእነ በላይ ቡድን ፓርቲውን የሚያስቀጥለው ባለመሆኑና ፓርቲውን እንደ ፓርቲ እንዲቆይ ስለሚፈለግ ዛሬ ጥር 21 ቦርዱ ባደረው አስቸኳይ ስብሰባ እነ ትግስቱ አወሉ ወደ ምርጫ እንዲገቡ ወስኗል›› ብሏል፡፡
የቦርዱ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና ‹‹የእነ ትግስቱ አወሉ ቡድን ያካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ የተሟላ ስለመሆኑ በምን ታረጋግጡልናላችሁ?›› በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ ‹‹ሁለቱም ችግር አለባቸው፡፡ እኛ ያየነው በአንጻራዊነት ነው፡፡ የእነ ትግስቱ አወሉ ቡድን ችግር ቢኖርበትም ከዛኛው የተሻለ ነው፡፡ እውቅናውን የሰጠነው ለቦርዱ ለሚታዘዘው ነው፡፡›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ እነ ማሙሸት አማረ በጠቅላላ ጉባኤ ባለመመረጣቸው፣ ለተከታታይ 3 ወራት ወርሃዊ መዋጮ ያላወጣ አባል ከአባልነት የሚሰረዝ በመሆኑና ከፓርቲ አባልነትም ስለተባረሩ እንዲሁም ህገ ወጥ ማህተም በማሳተማቸው እውቅና እንዳልሰጣቸው ገልጾአል፡፡ በሌላ በኩል 2005 ዓ.ም ላይ አበባው መሃሪ የተመረጡበት ጠቅላላ ጉባኤ የተሟላ እንዳልነበር ቢታመንም በተደረገ ምርመራ የተሟላ መሆኑ በመታወቁ፣ በትክክለኛው ማህተም ስለሚጠቀም፣ ጠቅላላ ጉባኤ አድርጉ በተባለበት ወቅት ጠቅላላ ጉባኤ በማድረጉና ሪፖርቱንም ስላቀረበ ወደ ምርጫው እንዲገባ ወስኛለሁ ማለቱን ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡
ይሁን እንጂ ፓርቲዎቹ ምርጫ 2007 ዓ.ም. ለመሳተፍ መወሰናቸውን ተከትሎ ህወሓት/ኢህአዴግ በምርጫ ቦርድ አማካኝነት ሊያፈርሳቸው የተለያየ ህገወጥ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው፣ ቦርዱ ገለልተኛ እና ነፃ አለመሆኑን በድርጊቱ እየገለፀ ነው ሲሉ በተደጋጋሚ ተቃውሞና ቅሬታ እያቀረቡ መሆናቸው ይታወቃል፡፡
ፍርድ ቤቱ በብሎገሮቹና በጋዜጠኞች ላይ ተሻሻለ የተባለውን የአቃቤ ህግ ክስ ተቀበለ
ባለፉት 9 ወራት በፖሊስ ቁትጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ሲታይ የነበሩት 6 የዞን 9 ጦማርያንና 3 ጋዜጠኞች ላይ አቃቤ ህግ በዛሬው ዕለት ጥር 20 ቀን 2007 ዓ.ም. አሻሽዬ አቅርቤዋለሁ ያለውን የክስ ቻርጅ የልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ የወንጀል ችሎት ተቀባይ አድርጎታል፡፡
በዚህም መሰረት ተከሳሾቹ በአሸባሪነት ወንጀል እንደሚጠየቁና ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ የእምነት ክህደት ቃላቸውን እንዲሰጡ ዛሬ ጠዋት በነበረው የክስ ሂደት ወቅት ጠይቋቸው ጉዳዩን ለከሰዓት አስተላልፎት ነበር፡፡ ነገር ግን ከጥቂት ሰዓታት በፊት በነበረው የክስ ሂደት ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን ለ17ኛ ጊዜ ለሚቀጥለው ማክሰኞ ጥር 26 ቀን ቀጠሮ በመስጠት ተበትኗል፡፡
ስድስቱ የዞን 9 ጦማርያንና ሦስቱ ጋዜጠኞች ከባለፈው ዓመት ሚያዚያ 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ሲታይ የከረመ ቢሆንም የክስ ሂደቱ ላይ ግን በርከት ያሉ የህግ ሂደትን ያልተከተሉ ሁኔታዎች ሲስተዋሉ መቆየቱን አዲስ ስታንዳርድ ዘግቧል፡፡
አንድነት ፓርቲ የጠራው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ በፖሊስ ድብደባ ሲጠናቀቅ፤በርካታ ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል
-“የፍትህና የነፃነት ጥያቄያችን ደም በማፍሰስ አይቀለበስም!”- አንድነት
-በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞችም ተከታታይ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች እንዲቀጥሉ ተወስኗል
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዛሬ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ አራት የክልል ከተሞች የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ በፖሊስ ድብደባ ተጠናቀቀ፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ የነበረው የተቃውሞ ሰልፍ መነሻውን ቀበና ከሚገኘው የፓርቲው ዋና ጽህፈት ቤት በማድረግ መዳረሻውን ጥቁር አንበሳ አካባቢ በሚገኘው ኢትዮ-ኩባ አደባባይ ሲንቀሳቀስ የነበረው ሰልፍ በፅህፈት ቤቱ አካባቢ በተፈፀመ የፖሊስ ድብደባና እገታ ሊቋረጥ ችሏል፡፡
የተቃውሞ ሰልፉ ዋነኛ ዓላማም ምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ አንድነት ወደ ምርጫው መግባቱን በመወሰን በመላ ሀገሪቱ ከ450 በላይ ዕጩዎቹን ማቅረቡን ይፋ ማድረጉን ተክትሎ ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ፓርቲው ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ በሚል ፓርቲውን ከምርጫ ውድድር ለማስወጣት የሚደረገውን ተግባር ለመቃወም መሆኑን ቀደም ሲል ይፋ ማድረጉ ይታወቃል፡፡ ከተጠቀሰው ዓላመ በተጨማሪ በዜጎች ላይ የሚደርስ ህገወጥ እና የግፍ እስር እንዲቆም፣ የታሰሩ የህሊና እስረኞች እንዲፈጡ፣ ነፃና ገለልተኛ ምርጫ ቦርድ እንዲኖር፣…የሚሉ ጥያቄዎች ይገኙበታል፡፡
መረጃዎች ከስፍራው እንደጠቆሙት ከሆነ፤ የተቃውሞ ሰልፉ ቀበና ከሚገኘው የአንድነት ፓርቲ ጽ/ቤት የተነሳው ከ 150 በላይ የሚሆን ሰልፈኛ ከጽህፈት ቤቱ 100 ሜትር ርቀት ላይ ከሚጠብቁ ከ500 በላይ ሰልፈኞች ጋር ከመቀላቀላቀላቸው አስቀድሞ ፖሊሶች ቆርጠው በመግባት ከባድ ድብደባ አድርሰዋል፡፡ አራት ኪሎ፣ በፒያሳና የሰልፉ ማጠናቀቂያ በሆነው ኢቲዮ -ኩባ አደባባይ ይጠባበቅ የነበረው ሰልፈኛ ሊበተን መቻሉንም ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
በተፈፀመው የፖሊስ ድብደባም ከ26 በላይ የፓርቲው አባላትና አመራሮች ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን፤ ከሰልፉ ጋር ምንም ንክኪ ያልነበራቸውና ቀበና መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን የነበሩ የ70 ዓመት አዛውንትም ከፍተና ጉዳት ደርሶባቸው በአቅራቢያው በሚገኝ የጤና ተቋም የህክምና ዕርዳታ ሲደረግላቸው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት በክልል ከተደረጉት የተቃውሞ ሰልፎች መካከል ፓርቲው በደብረማርቆስ፣ በሸዋሮቢት እና በጋሞጎፋ ከምባ የተሳካ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መደረጉ ተጠቁሟል፡፡
በአዲስ አበባው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጉዳት ከደረሰባቸው የአንድነት አባላት መካከል የሚሊዮኖች ድምፅ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ስለሺ ሐጎስና የፓርቲው ኦዲትና ኢንስፔክሽን ኃላፊ ዳግማዊ ተሰማ ከፍተኛ ጉዳት ስለደረሰባቸው ራሳቸውን ስተው እንደነበርና ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው እንደነበር የዓይን እማኞች ከስፍራው አስታውቀዋል፡፡ በተመሳሳይም ……የተባሉ ነፍሰጡር በፖሊስ ድብደባ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው የተጠቆመ ሲሆን፤በፖሊስ ድብደባ ከተፈፀመባቸውና ጉዳት ከደረሰባቸው የፓርቲው ስራ አስፈፃሚና አባላት መካከል፡-
- አቶ አስራት አብርሃም (የህዝብ ግንኙነት ተጠባባቂ ሃላፊ)
2. አቶ ዳንኤል ተፈራ (የውጭ ጉዳይ ሃላፊ)
3. አቶ ብሩ ብርመጅ (የፖለቲካ ጉዳይ ሃላፊ)
4. አቶ ፀጋየ አላምረው (ምክትል አፈ-ጉባኤ)
5. አቶ አሻግሬ መሸሻ (የሰሜን ቀጠና ሃላፊ)
6. አቶ ሰለሞን ስዩም (የኤዲቶሪያል ቦርድ ሰብሳቢ)
7. ወ/ት ልዕልና ጉግሳ (የም/ቤት አባል)
8. አቶ ዳግማዊ ተሰማ (የም/ቤት አባል)
9. ጋዜጠኛ ስለሺ ሀጎስ (የም/ቤት አባል)
10. አቶ ስንታየሁ ቸኮል (የአዲስ አበባ የወጣቶች ጉዳይ ሃላፊ)
11. አቶ አሸናፊ አሳምረው (የወረዳ አመራር)
12. አቶ ኢሳያስ ቱሉ (አባል)
13. ወ/ት መስከረም ያረጋል (አባል)
14. አቶ ሃይሉ ግዛው (የወረዳ ሰብሳቢ)
15. አቶ አዲሱ መኮንን (የወረዳ ሰብሳቢ)
16. አቶ ሲሳይ ካሴ (አባል)
17. አቶ ወጋየሁ አድማሴ (አባል)
18. አቶ ክብረት ሃይሉ (የም/ቤት አባል)
19. አቶ ስለሺ ደቻሳ (አባል)
20. አቶ ማሩ አካሉ (አባል)
21. አቶ ክፍሉ በዳኔ (አባል)
22. አቶ ፋሲካ አዱኛ (የወረዳ አመራር)
23. ወ/ሮ ገነት ሞገስ (የወረዳ አመራር)
24. ተስፋየ ብዙነህ (አባል)
25. ሙሉጌታ ተፈራ
26.ኤፍሬም ሰለሞን(የአዲስ አበባ ስራ አስፈፃሚ)
በተቃውሞ ሰልፉ ፖሊሶች ያደረሱትን ጉዳት በቅርብ ሲከታተሉ የነበሩት የተለያዩ ሀገራት ዲፕሎማቶች የአንድነት አመራሮችን እና ጉዳት ደርሶባቸው በየሆስፒታሉ የሚገኙ የአንድነት አባላትና ደጋፊዎችን አነጋግረዋል፡፡ የፓርቲው አመራሮች ከአባላትና ከደጋፊዎች ጋር ውይይት ያደረጉ ሲሆን አንድነት በአዲስ አበባ ተከታታይ የተቃውሞ ሰልፎችን እንደሚያደርግ ይፋ ተደርጓል፡፡ ይህንንም በተመለከተ ፓርቲው መግለጫ ያወጣ ሲሆን፤ ሙሉ መግለጫውን ከዚህ በታች ይመልከቱ፡-
የፍትህና የነፃነት ጥያቄያችን ደም በማፍሰስ አይቀለበስም!!!
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ
ፓርቲያችን አንድነት ገዥው ፓርቲ፣ ምርጫ ቦርድና የገዥው ፓርቲ ልሳን በመሆን እያገለገሉ ያሉ ሚዲያዎች በመተባበር ከምርጫ ለማስወጣትና ተለጣፊ አንድነት ለመፍጠር የሚደረገውን ጥረት በመቃወም የተቃውሞ ሰልፍ መጥራቱ የሚታወቅ ነው፡፡
የተቃውሞ ሰልፉን ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም እንደምናከናውን ለአዲስ አበባ መስተዳድር ብናሳውቅም መስተዳድሩ በ12 ሰዓት ውስጥ በፅሁፍ ምላሽ መስጠት ባለመቻሉ ሰልፉ እውቅና አለው፡፡ መስተዳድሩ ግን የተጣለበትን ሃላፊነት ከመወጣት ይልቅ ወደ ጎን በመግፋት የተወሰኑና የማይታወቁ ግለሰቦች ፔቲሽን ተፈራርመው አምጥተዋል በማለት ብዥታ ለመፍጠር ሞክሯል፡፡ ፓርቲያችን ህጉን ጠብቆ ህጋዊ የሆነ ሰልፍ ለማካሄድ ቢሞክርም አሁንም ሃላፊነት በጎደለው ሁኔታ የፓርቲያችን ከፍተኛ አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ጭካኔ በተመላበት ሁኔታ ከፍተኛ ድብደባ ተፈፅሞባቸዋል፡፡ በተደጋጋሚ እንዳየነው ፖሊስ ደንብ ማስከበር ሲገባው አድሎ ለፈፀመው አካል በመወገን ድብደባ መፈፀሙ ከወገንተኝነት ያልፀዳ መሆኑን እንድናረጋግጥ አድርጎናል፡፡
ጥያቄያችን አሁንም የፍትህ፣ የእኩልነትና ህግ እንዲጠበቅ የማድረግ ነው፡፡ ገዥው ፓርቲ የመንግስትነት ስልጣኑን በመጠቀም የስልጣን ዘመኑን ለማስረዘም እየከወነ ያለውን ሴራ ማስቆም ነው፡፡ ጥያቄያችን የነፃነትና ያልተሸራረፈ ዴሞክራሲ ይረጋገጥ የሚል ነው፡፡ ጥቄያችን ምርጫ ቦርድ የገዥው ፓርቲ አጋር መሆኑ ቀርቶ ገለልተኛ ሚናውን ይወጣ የሚል ነው፡፡ እነዚህ ጥያቄዎቻችን ደግሞ ደም በማሰስ፤ በድብደባም ሆነ በእስር ፈፅሞ አይቆሙም፡፡
በሚቀጥለው ሳምንትም በተለያዩ ከተሞችና በአዲስ አበባ የሰላማዊ ተቃውሞ ድምፃችንን ከፍ አድርገን እናሰማለን፡፡ ትግሉ ይቀጥላል፡፡
ድል የህዝብ ነው!!
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም.
አዲስ አበባ










