Tag Archives: TPLF/EPRDF democracy

ሰማያዊ ፓርቲ ይቅርታ እንደማይጠይቅ አስታወቀ

የሰማያዊ ፓርቲ ዓርማ

የሰማያዊ ፓርቲ ዓርማ

ሰማያዊ ፓርቲ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጽሕፈት ቤትን እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ በጽሑፍ ይቅርታ ይጠይቅ በማለት የተላለፈው ውሳኔ ከሕግ አግባብ ውጪ ስለሆነ ተቃውሞውን በመግለጽ ይቅርታ እንደማይጠይቅ አስታወቀ፡፡

የቦርዱ የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ደምሰው በንቲ ባለፈው ሐሙስ በጽሕፈት ቤታቸው በሰጡት መግለጫ፣ ሰማያዊ ፓርቲ የምርጫ ቦርድን ስም አጥፍቷል ብለዋል፡፡ ‹‹በተሻሻለው የምርጫ ሕግ አንቀጽ 102 (4)ሀ፣ ለ እና ሠ እንዲሁም 102 (6) ሐ መሠረት የፖለቲካ ፓርቲዎች የቦርዱን ሥልጣን መቀበል፣ ሕጋዊ ትዕዛዙንና መመርያውን የማክበር ግዴታ እንዳለባቸው፣ እንዲሁም ቦርዱ በሚያዘጋጃቸው የጋራ የምክክር መድረኮች ወይም ሌሎች መድረኮች ላይ ወኪል የመላክ ኃላፊነት እንዳለባቸውና በሐሰት ስም ከማጥፋት መቆጠብ እንዳለባቸው ያመለክታሉ፤›› ብለዋል፡፡

‹‹ሰማያዊ ፓርቲ ግን ቦርዱ በተለያዩ ጊዜያት ያዘጋጃቸውን የጋራ ምክክሮች እንዲበተኑ ሙከራ አድርጓል፣ እየረገጠ ወጥቷል፣ በሐሰት ቦርዱን ወንጅሏል፡፡ እንዲሁም የስም ማጥፋት ዘመቻ አድርጓል፤›› በማለት ፓርቲው በጽሑፍ ይቅርታ እንዲጠይቅ ቦርዱ ወስኗል በማለት አስታውቀዋል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ውሳኔውን አስመልክቶ፣ ‹‹እኛ ይህን የምንረዳው የምርጫ ቦርድ የራሱ አቋም ሳይሆን ኢሕአዴግ በቦርዱ ውስጥ ምን ያህል ሚና እንዳለው ያጋለጠ ውሳኔ መሆኑን ነው፤›› በማለት ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡

‹‹ቀደም ባሉት ጊዜያት የሰጠነው አስተያየትና ስብሰባ ረግጠን መውጣታችን ዘለፋ መስሎ ከተሰማቸው አትዝለፉን እንነጋገር ማለት መልካም ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ ጊዜ ውስጥ ይቅርታ ጠይቁኝ ብሎ ማስፈራራት አገራችንን አሳፋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚከት ነው፡፡ ይቅርታ መቀለጃ አይደለም፡፡ እኛም በዚህ ምክንያት አናስተናግደውም፤›› ብለዋል፡፡

‹‹በተጨማሪም በመሠረቱ እኛ አንድ ድርጅት ነን፡፡ ምርጫ ቦርድም እንዲሁ አንድ ድርጅት ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ድርጅቶች ሊግባቡ የሚችሉት ደግሞ በሕግና በደንብ ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ካጠፋ ወይ ወደ ፍርድ ቤት ይሄዳል፣ ወይም ቦርዱ ባለው ሥልጣን ችግሩ ይፈታል፡፡ ቦርዱም ካጠፋ እንዲሁ፡፡ ከዚህ ውጪ ይቅርታ ጠይቀኝ ብሎ መጠየቅ ፍፁም ተቋማዊ አሠራር አይደለም፤›› በማለት ውሳኔውን ፓርቲያቸው እንደሚቃወም አስታውቀዋል፡፡

አንድነት ፓርቲ በድጋሚ በጠራው አስቸኳይ ልዩ ጠቅላላ ጉባዔ ፕሬዘዳንቱን በመምረጥ ተጠናቀቀ

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዓርማ

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዓርማ

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በመጪው ምርጫ ግንቦት 2007 ዓ.ም. ለመሳተፍ መወሰኑን እና ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚወዳደሩ 450 ዕጩዎቹን በአራቱም የሀገሪቱ አቅጣጫ ማቅረቡን ይፋ ካደረገ በኋላ ምርጫ ቦርድ ፓርቲው እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ በድጋሚ ጠቅላላ ጉባዔ አድርጎ የፓርቲውን ፕሬዘዳንቱን ካለተመረጠ ምርጫው ላይ እንዳይሳተፍ አደርጋለሁ ባለው መሰረት ዛሬ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. አዲስ አበባ ቀበና በሚገኘው የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት አዳራሽ ጠቅላላ ጉባዔው መካሄዱ ታውቋል፡፡ ፓርቲውን ለመምራት በዕጩነት ቀርበው የተወዳደሩት አቶ በላይ ፈቃዱ፣ አቶ አለነ ማህፀንቱ እና አቶ ዳግማዊ ተሰማ መሆናቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ከተደረገው የአንድነት ጠቅላላ ጉባዔ በከፊል

ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ከተደረገው የአንድነት ጠቅላላ ጉባዔ በከፊል

ለፕሬዘዳንትነት የተወዳደሩት ሶስቱም ዕጩዎች በወጣትነት የዕድሜ ክልል ላይ የሚገኙ ሲሆን፤ በትምህርታቸው የማስተርስ ድግሪ፣ በፖለቲካ ተሳትፎ ሶስቱም በአንድነት ፓርቲ በተለያየ ከፍተኛ አመራርነት ያገለገሉ ሲሆን፣ በሙያቸውም የተለያዩ ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ተቋማት ላይ ማገልገላቸው ተጠቁሟል፡፡ በመጨረሻም በነበረው ውድድር አቶ አለነ ማህፀንቱ ራሳቸውን በገዛ ፈቃዳቸው ከውድድሩ ውጭ በማድረግ በአቶ በላይ ፈቃዱና በአቶ ዳግማዊ ተሰማ መካከል በተደረገ የምረጡኝ ቅስቀሳና ውድድር የጠቅላላ ጉባዔው አባላት ባደረጉት የምስጢር ድምፅ አሰጣጥ መሰረት አቶ በላይ 183 ድምፅ በማግኘት የአንድነት ፕሬዘዳንት ሆነው ተመርጠዋል፡፡ አንድነት መተዳደሪያ ደንብ መሰረት የጠቅላላ ጉባዔው አባላት 320 ሲሆን፤አቶ በላይም የአባላቱን 57.2 በመቶ ድምፅ በማግኘት አሸንፈዋል፡፡

ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ከተደረገው የአንድነት ጠቅላላ ጉባዔ በከፊል

ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ከተደረገው የአንድነት ጠቅላላ ጉባዔ በከፊል

ውጤቱን ተከትሎም ተፎካካሪያቸው የነበሩት አቶ ዳግማዊ ተሰማ ለአቶ በላይ ፈቃዱ የእንኳን ደስ ያሎት መልዕክት በማስተላለፍ መጪውን ምርጫ አንድነት ፓርቲ አሸናፊ ሆኖ እንዲወጣ በጋራ ጠንክረው መስራት እንዳለባቸውና ለዚህም በፓርቲው የሚሰጣቸውን የስራ ድርሸና ተልዕኮ ለመወጣት ዝግጁ እንደሆኑ መግለፃቸውን ከስፍራው የአዲስሚዲያ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በመጨረሻም አቶ በላይ ፈቃዱ ፓርቲውን በፕሬዘዳንትነት ለመምራት ቃለ መሐላ መፈፃማቸው ታውቋል፡፡

አዲሱ የአንድነት ፓርቲ ተመራጭ ፕሬዘዳንት አቶ በላይ ፈቃዱ ቃለ መሐላ ሲፈፅሙ

አዲሱ የአንድነት ፓርቲ ተመራጭ ፕሬዘዳንት አቶ በላይ ፈቃዱ ቃለ መሐላ ሲፈፅሙ

በጉባዔው ላይ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ዲፕሎማቶችና ጋዜጠኞች እንዲሁም ሌሎች ተጋባዦች የተገኙ ሲሆን፤ በሀገሪቱ የምርጫ ቦርድ ህግ መሰረት ሂደቱን መታዘብ የነበረበት ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሂደቱን ለመታዘብ እንደማይገኝና ወኪልም እንደማይልክ ቀደም ሲል ከፓርቲው ለተደረገለት ጥሪ በደብዳቤ ማሳወቁ ተጠቁሟል፡፡ ቀደም ሲል ታህሳስ 2006 ዓ.ም. የፓርቲው ፕሬዘዳንት የነበሩት ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው ስልጣናቸውን በገዛ ፈቃዳቸው በመልቀቅ ለፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት ካስረከቡ በኋላ አቶ በላይ ፈቃዱ ያለፉት 3 ወራት የፓርቲው ፕሬዘዳንት ሆነው ማገልገላቸው አይዘነጋም፡፡

በምርጫ 2007 ዓ.ም. ኢህአዴግ የፈራውን ህዝባዊ አብዮት እየጠራ ነው

ብስራት ወልደሚካኤል

ከዚህ በፊት ኢህአዴግ ጠንካራ የሰላማዊ የፖለቲካ ታጋይ አመራሮችንና አባላቱን አሰረ፡፡ በመቀጠልም ጋዜጠኞችና የዞን 9 ብሎገሮችን አሰረ፡፡ ይህም አልበቃ ሲለው አሁን ደግሞ በራሱ ምርጫ ቦርድ ተወዳድረን እናሸንፍሃለን ብለው የቆረጡ ተፎካካሪዎችን ከምርጫ ለማስወጣት ባትሏል፡፡ ለዚህም ማሳያ አንድነት ፓርቲን አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባዔ ጥሩ ምናም…መኢአድን ደግሞ እናንተም ችግር የውስጥ ችግራችሁን ፍቱ፣…ሰማያዊ ፓርቲን ደግሞ ምርቻ ቦረድ በጠራው ስብሰባ ላይ ረግጣችሁ ጥታችኋልና ይቅርታ ካልጠየቃችሁኝ፣…ኃይማኖታዊ በዓል በሆነውና ከጥር 10-12 በሚከበረው የጥምቀት በዓል ዋዜማና ስነስርኣት ሰማያዊ ልብስ እንዳይለበስ የሚል ትዕዛዝ መስጠት፣…ዛሬ ደግሞ ለነገ ጠቅላላ ጉባኤ የጠራውን አንድነት ፓርቲ ላይ ለመሳተፍ የተንቀሳቀሰውን የአንድነት ፓርቲ የምስራቅ ቀጠና አደራጅ አዳማ/ናዝሬት ላይ ማገት፣…እያለ ጠንካራ የተባሉ የተፎካካሪ ፖለቲካ አባላትንና አመራሮችን ማገትና ማሰሩን ቀጥሏል፡፡ ከዚህ በፊት ከ200 ያላነሱ ጠንካራ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣አባላት፣ጋዜጠኞች፣ብሎገሮችንና አክቲቪስቶችን በግፍ ማሰሩ አይዘነጋም፡፡

eprdf

በርግጥ ኢህአዴግ ድሮም ፈሪ ነው፡፡ የሚፈራው የኢትዮጵያን ህዝብ ብቻ ሳይሆን፤ ሐሳብን በራሱ ይፈራል፡፡ ለዚህም ነው ከእስክሪብቶና ወረቀት ውጭ በእጃቸው ምንም የሌላቸውን ንፁሃንን አሸባሪ እያለ ሚያስረው፡፡ አምባገነንቱና ጨካጭነጹ ከፍርሃትና ከድንቁርና የመኘጨ እንጂ የፖለቲካ ስትራቴጂ ሆኖ አይደለም፡፡ ይህ ግን በስልጣን ለመቆየት ዋስትና ሊሆን አይችልም፤ሆኖም አያውቅም፡፡ ይልቅ ጭቂና እና ጭካኔ በገዥዎች በተበራከተ ቁጥር ገና ወደፊት ይመጣል ተብሎ የተፈራውን ህዝባዊ አብዮት ራሱ ኢህአዴግ እያቀረበ ያለ ይመስለኛል፡፡ ምንም እንኳ የምርጫ እንቅስቃሴ መኖሩና ተፊካካሪዎች ወደ ውድድሩ ቢገቡ እንደ አንድ መልካም ነገር ቢታይም፤ ምርጫው ላይ ከበፊቱ የተለየ ውጤት ይኖራል ተብሎ ላይጠበቅ ይችላል፡፡ የምርቻ ሂደቱ በራሱ ግን ህዝቡን የፖለቲካ መብቱን እንዲጠይቅና እንዲጠቀም ከማድረግ አኳይ አዎንታዊ ሚና መኖሩ እሙን ነው፡፡

ህዝባዊ አብዮት ምንጊዜም የሚፈጠረው በገዥዎች ምክንያት ድንገት እንጂ በህዝቡ ታቅዶና ተፈልጎ አይደለም፡፡ ህዝቡ የአብዮቱ ምክንያት በሆኑ ገዥዎች ህዝባዊ እምቢተኝነት አንዱ አፀፋ ምላሽ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ ኢህአዴግ በርካታ የጦር መሳሪያ አለኝ ብሎ በአፈሙዝ አስቦና ተመክቶ ህዝባዊ አብዮትን ቢፈራም በራሱ ጊዜ እያፈጠነውና እየጠራው ያለ ይመስለኛል፡፡

አሁን ግን ኢህአዴግ ምርጫ ቦርድን፣ ፍርድ ቤትን፣ ደህንነትን፣ ፖሊስን፣ መከላከያን፣ሚዲያውን እና ኢኮኖሚውንም ይዞ ሊረጋጋ አልቻለም፡፡ የሚገርመው ህዝባዊ ደጀን ከጀርባቸው እንዳለ በማመን እስክሪብቶ፣ወረቀትና ሐሳብ የያዙትን ከጦር በላይ መፍራቱ እርግጥ ነው፡፡ ግን በመፍራት፣ ጭካኔና ኃላፊነት በጎደለው ስሜት የሚወሰዱ እርምጃዎችን ከፈሩት ነገር ለማምለጥ ዋስትና ከመሆን ይልቅ የፈሩትን ነገር የማምጣት ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡

ኢህአዴግ አሁን እያደረገ ያለው የእውር ድንብር ተግባሩ በራሱ ጊዜ የፈራውን ህዝባዊ አብዮት ከምን ጊዜውም በላቀ ሁኔታ እየጠራው ነው፡፡ ይሄም በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች፣አባላትና አመራሮች፣ በአክቲቪስቶችና ጋዜጠኞች ሳይሆን በራሱ በኢህአዴግ የከበረ ጥሪ እየተደረገለት ነው፡፡ በርግጥ ህዝባዊ አብዮት ድንገት የሚፈጠር ህዝባዊ አመፅ/እምቢተኝነት በመሆኑ አምባገነኖችን ድንገት ሳያስቡ ከስልጣን በማውረድ በበጎ ጎኑ ቢታይም የጦርነት ውጊያን ያህል ባይሆንም የሰው ህይወትና ንብረት ላይ ጉዳት ማድረሱ አይቀርም፡፡ ነገር ግን ራሳቸው አምባገነኖች በሚፈጥሩት ቅጥ ያጣ ጭቆና የሚመጣ በመሆኑ በፀጋ ከመቀበል ውጭ ሌላ አማራጭ ያለ አይመስለኝም፡፡ እነደ ሌሎቹ ስልጡናን የመንግስት ስርዓት ከጦርነት ክህዝባዊ አብዮት ይልቅ በሰለጠነው ነፃና ፍትሃዊ በሆነ የህዝብ ምርጫ ቢሆን መልካም ነበር፡፡ ነገር ግን የዚህ ሁሉ ዕድል ከተዘጋ የታፈነ ህዝብ ነገ ባልታሰበ ጊዜ ህዝባዊ እምቢተኝነት ወይም አመፅ ውስጥ መግባት አይቀሬ ነው፡፡ ለዚህ ተጠያቂ ደግሞ ራሱ ኢህአዴግና የበኩር ልጁ ምርጫ ቦርድ መሆናቸውን ማወቅ አለባቸው፡፡

nebe

አሁን አብዮቱን እየጠራ ያለው ኢህአዴግ ብቻ ሳይሆን ልጁ ታማኝ ልጁ ምርጫ ቦርድ በመሆናቸው በሀገሪቱና በህዝቡ ላይ ለሚፈጠሩ ጥፋቶች ተጠያቂዎቹ ተቋማቱ ብቻ ሳይሆኑ የኢህአዴግ አመራሮችና የምርጫ ቦርድ ዋና አመራሮችና እንደ የደረጃቸው ሌሎች የቦርዱና የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚዎች እንደየስራቸው ከተጠያቂነት ማምለጥ እንደማይችሉ ከወዲሁ ራሳቸውን መመርመርና የዓለማችንና የህዝባንን ነባራዊ ሁኔታ መገንዘብ ያለባቸው ይመስለኛል፡፡ አለበለዚያ እንደ ከዚህ ቀደሙ በንፁሃን ደም ነግዶ መኖርና ማላገጥ፣ ሀገርና ትውልድ አጥፍቶ አመልጣለሁ ማለት የማይቻልበት ጊዜ ላይ መድረሳችንንም ሊረሳ አይገባም፡፡ ስለዚህ በሀገሪቱ ላይ እስካሁን ከፈፀሙት በደል በተጨማሪ አሁንም ለመፈፀም ለተዘጋጁ ጥፋቶች ምርጫ ቦርና ኢህአዴግ ከነተባባሪዎቻቸው መቼም ቢሆን ከተጠያቂነት እንደማያመልጡ መረዳት አለባቸው፡፡ ምንክንያቱም እንደከዚህ ከቀደሙ በዝምታም ሆነ በፍራቻ የሚታለፍበት ጊዜ አልፏልና፡፡ ምናልባት ለመተንበይ አስቸጋሪ ቢሆንም በኢትዮጵያ የፖለቲካ ስርዓት ለውጡ የማይቀር እውነት ነው፡፡

መቼም በአሁን ጊዜ እንደቀድሞ በተጭበረረበር ምርጫና በካድሬ ውዳሴ ከንቱ ዳንኪራ ምርጫ አድርጌ አሸንፊያለሁ ማለት ለምርጫው የወጣውን ወጪ ከየትኛውም የኢኮኖሚ ኪሳራ በላቀ አጉልቶ ከማሳየት በስተቀር በስልጣን ለመቆየት ዋስትና ሊሆን አይችልም፡፡ ምርጫ አንዱ የዴሞክራሲያዊ የመነግስት ስርዓት ሽግግር መገለጫ እንጂ ብቸኛው ህዝብን የስልጣን ባለቤት ማድረጊያና አምባገነኖችን ከሚንደላቀቁበት ስልጣን ማስወገጃ መንገድ አይደለም፡፡ ይሄ ደግሞ ከማንም የሚሰወር አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም የተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ባይኖሩ እንኳ በርካታ የሰላማዊ ትግል ስልቶች እንደየወቅቱ፣እንደየሀገሩና ህዝቡ የሚተገበሩ አሉና፡፡ ስለሆነም መጪውን ጊዜ ስለሀገራችን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ በተለይም የፊታችን ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ለሚደረገው ምርጫ ሂደትና ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም ይፋ ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ውጤት ከወዲሁ በጉጉት እንድንጠብቀው ግድ ብሎናል፡፡

ኦኬሎ አኳይ እጅና እግራቸውን ታስረው ጨለማ ክፍል መታሰራቸው ተገለፀ

-ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ከቤተሰብ ውጭ ጠያቂ ተከልክሏል

የቀድሞ የጋምቤላ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ ኦኬሎ አኳይ

የቀድሞ የጋምቤላ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ ኦኬሎ አኳይ

የቀድሞው የጋንቤላ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ኦኬሎ አኳይ እጅና እግራቸው ታስሮ ጨለማ ክፍል መታሰራቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ገለጹ፡፡

አቶ ኦኬሎ ቂሊንጦ በእስር ላይ እንደሚገኙ የሚታወስ ሲሆን፣ ሰውዬው ከሰሞኑ የርሃብ አድማ ማድረጋቸውን ተከትሎ በእስር በሚገኙበት እስር ቤት እጅና እግራቸውን ታስረው ብቻቸውን ጨለማ ክፍል እንዲገቡ እንደተደረጉ ምንጮች ተናግረዋል፡፡

ዛሬ ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም ወደ ቂሊጦ ማረሚያ ቤት እስረኞችን ሊጠይቁ ሄደው እንደነበር የገለጹት ምንጮች፣ እዚያው በእስር ላይ ካሉ ሰዎች አቶ ኦኬሎ ያሉበትን ሁኔታ መረዳታቸውን አክለው ገልፀዋል፡፡

በሌላ በኩል የ18 አመት እስር ፍርደኛው ታዋቂው ጋዜጠኛና የፖለቲካ ተንታኝ እስክንድር ነጋ ከቤተሰብ ውጭ ሌላ ሰው መጠየቅ እንደተከለከለ የነገረ-ኢትዮጵ ዘገባ አመልክቷል፡፡

አንድነት ፓርቲ በአንድ ወር ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ አስቸኳይ ልዩ ጠቅላላ ጉባዔ ጠራ

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ ጠራ፡፡ ፓርቲው ነገ እሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤ በድጋሚ እንዲጠራ የተገደደው ገለልተኛ እንዳልሆነ ተደጋጋሚ ቅሬታዎች የቀረቡበትና እየቀረቡበት ያለው ምርጫ ቦርድ ባደረገበት ጫና መሆኑን በመግለጫው አስታውቋል፡፡

በተለይ በአሁን ወቅት በርካታ አመራሮቹና አባሎች የታሰሩበት አንድነት ፓርቲ፤ የፊታችን ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በሚደረገው ምርጫ ላይ ለመሳተፍ መወሰኑን እና በመላ ሀገሪቱም ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚወዳደሩ 450 ዕጩዎቹን ማዘጋጀቱንና ምርጫውንም በአሸናፊነት ለመወጣት ህዝቡን “2007 ለለውጥ ተደራጅ” በሚል መርህ ሰፊ ሀገራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡ ይህንንም ተከትሎ አንድነት ፓርቲ፣ ከኢህአዴግና ከምርጫ ቦርድ ጋር ባለው የፖለቲካ እንቅስቃሴ ከቀድሞ በበለጠ እየተካረረ መሄዱን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡ ይህንንም በተመለከተ ፓርቲው መግለጫ አውጥቷል፡፡ የፓርቲውን ሙሉ መግለጫ ከታች ይመልከቱ፡-

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዓርማ

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዓርማ

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)

በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ፖለቲካዊ ደባ አንድነት ከመስመር አይወጣም!
*******************************************************************************

ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ መግለጫ
በየትኛውም የአለም ክፍል በተለያየ አጣራርና ስያሜ ቢሰጣቸውም ምርጫን ለማስፈፀም በሕግ የሚቋቋሙ ተቋማት ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ተቋማት በአንድ ሀገር ዘላቂ ለሆነ ሠላምና መረጋጋት ብሎም ለዴሞክራሲዊ ስርዓት ግንባታ ከፍተኛ ሚና ይጫወታሉ፡፡ እንደ ኢትዮጵያ በአንባገነን ስርዓት ውስጥ ላሉ ሀገሮች ደግሞ ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ያላቸው ሚና ከምንም በላይ ከፍተኛ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራው ምርጫ ቦርድ ይህን የመሰለ ግዙፍ ተግባር እንዲያከናውን፣ የሕዝብ እና የሀገር አደራ እንዲወጣ ኃላፊነት የተሰጠው ተቋም ነው፡፡ የዚህ ተቋም አሰራር በተቋቋመለት ዓላማ፣ ሕግ እና አለም አቀፍ መስፈርት መሠረት ነፃ፣ ገለልተኛ፣ ዴሞክራሲያዊ እና በህዝብ ዘንድ ተአማኒነት ያለው መሆን ይጠበቅበታል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቀደሙት አሠራሮችና ውሳኔ አሰጣጦች በበርካታ ኢትዮጵያውያን እና አለም አቀፍ ታዛቢዎች በአሉታዊ ጎኑ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የ2ዐዐ7 ሀገር አቀፍ ምርጫን ‹‹የኢህአዴግ መጨረሻ›› እናደርገዋልን ብሎ ፖለቲካዊ አቋም ወስዶ እንቅስቃሴ ሲጀምር የምርጫ ቦርድን ቀደምት አሉታዊ ተግባሩን ዘንግቶ አይደለም፡፡ ይህ ተቋም መልካም ስም እንዲገነባ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር በመሆን እድል ለመስጠት ነበር፡፡ በዚህ ስትራቴጂ መሠረት ቦርዱን በተግባር ፈተና ላይ ጥለነዋል፣ ማንነቱንም ለኢትዮጵያ ሕዝብ እና ለዓለም ማህበረሰብ በማጋለጥ ላይ እንገኛለን፣ ዛሬ ለሁለም የሚዲያ አካላት ያካሄድናቸውን የደብዳቤ ልውውጦች በይፋ አንሰጣለን፣ ሁሉም ዜጋ እንዲደርሰውም እናደርጋለን፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አንድነት ፓርቲን ከ2ዐዐ7 አጠቃላይ ምርጫ ገፍቶ ለማስወጣት ካልተሳካለትም በተዳከመ የአባላትና ደጋፊ ስሜት ውስጥ ገብተን እንድንጫወት የፈለገ ይመስላል፡፡ ይህ ደግሞ ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ የአንድነት ፓርቲ በ2ዐዐ7 ዓም ሀገራዊ ምርጫ ከጅምሩ በሁሉም ሂደቶች በንቁ ለመሳተፍ የያዘው አቋም እንዳስደነገጠው፤ ከዚያም አልፎ ከምንም በላይ ቅድሚያ የሚሰጠውን ስልጣን አጣለሁ በሚል መሸበሩን የሚያጋልጥ ነው፡፡ ይህን ፍርሃቱን በህዝብ ፊት በሚደረግ ትግል ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ የመረጠው ሜዳ በብሔራዊ ምርጫ ቦርደ በኩል እንዲሆን ነው፡፡ የቦርዱ ኃላፊዎች ተቋማዊ በሆነ መልክ ደብዳቤ ሲሰጣቸው፣ በደብዳቤ መልስ ከመስጠት ይልቅ በመገናኛ ብዙሃን ምላሻቸውን ቀድመው መናገር ጀምረዋል፡፡ ለዚህም ማሳያው ታህሣሥ 27 ቀን 2ዐዐ7 ዓም የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ የሆኑት ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዝአብሔር ከቦርዱ ስብሰባ በፊት በሚዲያ ወጥተው ውሳኔ በመገናኛ ብዙሃን ተናግረዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው ቦርዱ እንደተቋም ሳይሆን በግለሰብ ውሳኔ የሚመራ መሆኑን ነው፡፡ ለዚህም መገለጫው በታህሳስ 30/2007 የደረሰን ደብዳቤ የቦርዱን ምክትል ስብሳቢ ከሚዲያ መግለጫ ጋር ተመሳሳይ መሆኑ ነው፡፡ ከምርጫ ቦርድ ባልተናነሰ ሁኔታ በኢትዮጵያ በህግ የተቋቋሙት እና በህዝብ ሀብት የሚንቀሳቀሱት የመገናኛ ብዙሃንም በፍጥነት ተቀብለው ማስተጋባታቸው በውዥንብር ፈጠራ ላይ ተሳታፊነታቸውን ያሳያል፡፡ ዓላማው በአባላት፣ በደጋፊና በህዝቡ ውስጥ ውዥንብር ለመፍጠር ታሰቦ የሚካሄድ ፖለቲካዊ ደባ ነው፡፡

በሀገራችን አስተማማኝ ሠላም እና ዘላቂነት ያለው ደህንነት የሚያረጋግጠው እንደ ምርጫ ቦርድ ያሉ ተቋሞች ነፃ፣ ገለልተኛ እና በህዝብ ዘንድ አመኔታ ሲጣልባቸው ነው፡፡ ይህ ተቋም አሁን በያዘው ሁኔታ ከቀጠለ ከታሪክ ተጠያቂነት አይድንም፡፡ ገዢው ፓርቲም ጧት ማታ የሚያባንነው ሕዝባዊ እምቢተኝነት መምጣቱ አይቀሬ ነው፡፡ በመሆኑም አሁን ፓርቲያችንን ለመታደግ እና የቦርዱን የመጨረሻ ካርድ ለማስጣል አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለ2ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርተናል፡፡ ይህ ማለት የትግሉ መጨረሻ አይደለም፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያደረሰብንን የሕግ ጥሰት ይዘን በፍርድ ቤት ክስ እንመሰርታለን፡፡ እስከ አሁን ያለውን ሂደት ስናየው የቦርዱ ፖለቲካዊ ደባ ቀጣይ እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡ ስለሆነም መላው አባሎቻችን፣ ደጋፊዎቻችን እና የኢትዮጵያ ሕዝብ ለምንወስዳቸው ተከታታይ ፖለቲካው ውሳኔዎች እና እርምጃዎች ከጎናችን እንዲቆም ጥሪያችንን በአክብሮት እናስተላልፋለን፡፡

ድል የሕዝብ ነው
ጥር 1 ቀን 2ዐዐ7 ዓም
አዲስ አበባ