Tag Archives: TPLF/EPRDF Ethiopia

ለመከላከያ ምስክርነት የተጠሩት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ “ሊቀርቡ ባለመቻላቸው” ምስክርነታቸው ውድቅ ተደረገ

*አብርሃ ደስታ 4 ወራት፣ የሺዋስና ዳንኤል 2 ወራት እስር ይቀራቸዋል

በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ አንደኛ ተከሳሽ አቶ ዘላለም ወርቃገኘሁ በቀረበበት የሽብር ክስ ላይ ከግንቦት ሰባት ዋና ጸሐፊ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ጋር ተጻጽፈሃል የሚል ማስረጃ በአቃቤ ህግ እንደቀረበበት በመግለጽ ይህን እንዲከላከሉለት አቶ አንዳርጋቸውን ለምስክርነት ቢጠራቸውም በተደጋጋሚ ቀጠሮ ሊቀርቡ ባለመቻላቸው ከፍተኛው ፍርድ ቤት ምስክሩ በተከሳሽ በኩል እንደተተው ይቆጠራል በሚል በይኗል፡፡

Zelalem Workagegnehu

ፍርድ ቤቱ ዛሬ የካቲት 25 ቀን 2008 ዓ.ም ብይኑን ሲያሰማ እንደገለጸው ተከሳሽ አቶ ዘላለም ወርቃገኘሁ ምስክሩን በተመለከተ በተደጋጋሚ እንዲቀርቡለት ጠይቆ እንዳልቀረቡለት በመግለጽ ‹‹ምስክሩ የማይቀርቡልኝ ከሆነ ከምስክሩ ጋር በተያያዘ የቀረበብኝ ክስ ፍሬ ነገር ከክሱ ወጥቶ ብይን ይሰጠኝ›› የሚል አቤቱታ አቅርቧል፡፡

አቃቤ ህግ በበኩሉ ተከሳሹ ምስክሩን አቅርቦ የማሰማት ግዴታ እንዳለበት በመጥቀስ ተከሳሹ የጠየቀው የፍሬ ነገር ይውጣልኝ አቤቱታ የህግ አግባብን የተከተለ ስላልሆነ ምስክሩን እንደተዋቸው ተቆጥሮ ብይን እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡

ችሎቱ በበኩሉ ለምስክሩ የተጻፈው የመጥሪያ ትዕዛዝ ደርሷቸው እንደቀሩ ማረጋገጫ ስለሌለ በተከሳሽ የቀረበው አቤቱታ ተቀባይነት እንደሌለው በማስረዳት ምስክሩ እንደተተው ቆጥሮ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ በመዝገቡ ላይ በተካተቱት አምስት ተከሳሾች ላይ የፍርድ ብይን ለመስጠት ለመጋቢት 29 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ከዚህ ቀጠሮ በፊት የክርክር ማቆሚያ ካላቸው ግራቀኙም በጽህፈት ቤት በኩል በጽሁፍ ማቅረብ እንደሚችሉ ፍርድ ቤቱ ገልጹዋል፡፡

Andaregachew Tsigie
በሌላ በኩል ነሐሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም በዚሁ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ከተከሰሱበት የሽብር ወንጀል ነጻ ናቸው በሚል የተበየነላቸው እነ አብርሃ ደስታ በዚሁ ችሎት፣ ‹‹ችሎት ደፍራችኋል›› በሚል የተላለፈባቸው ቅጣት ከመቼ ጀምሮ እንደሚታሰብ ግልጽ አድርጓል፡፡

በዚህም አመት ከአራት ወር የተፈረደበት አቶ አብርሃ ደስታ እና እያንዳንዳቸው አንድ አመት ከሁለት ወር የተፈረደባቸው አቶ የሺዋስ አሰፋ እና አቶ ዳንኤል ሺበሺ ከመጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ በሚታሰብ እስር መቀጣታቸውን ገልጹዋል፡፡ በመሆኑም አብርሃ አራት ወራት፣ እና እነ የሺዋስ ሁለት ወራት እስር ይቀራቸዋል ማለት ነው፡፡

Abereha, Yeshiwas, Daniel
እነ አብርሃ ደስታ አቃቤ ህግ በጠየቀባቸው ይግባኝ ላይ ብይን ለማግኘት ለመጋቢት 30 ቀን 2008 ዓ.ም ጠቅላይ ፍርድ ቤት ቀጠሮ እንዳላቸው ይታወሳል፡፡
ምንጭ፡ ነገረ ኢትዮጵያ

የዛሬው የአዲስ አበባ የታክሲ አድማ፤ ታሪክ ራሱን ሊደግም ይሆን?

ብስራት ወልደሚካኤል

የዛሬ 42 ዓመት በየካቲት 11 ቀን 1966 ዓ.ም. በቀዳማዊ አጼ ኃይለስላሴ ዘመን በሊትር የ10 ሳንቲም የነዳጅ ጭማሪን (50 በመቶ ጭማሪን)ተከትሎ የታክሲ ባለንብረቶች እና ሾፌሮች የታሪፍ ማሻሻያ ጭማሪ ቢጠይቁ ተቀባይነት በማጣታቸው የታክሲ አድማ ተደርጎ ነበር፡፡ በተመሳሳይ ዕለት የኢትዮጵያ መምህራን ማኀበር በጠራው አድማ የሀገሪቱ መምህራን በሙሉ ስራ አቁመው ነበር፡፡ ይህም እየተቀጣጠለ ከአዲስ አበባ ወደ ሌሎች ከተሞች ሳይዳረስ በሚል የወቅቱ መንግሥት የነዳጅ ጭማሪውን መሰረዙን ይፋ አደረገ፡፡

Addis taxi strike

ይሁን እንጂ ተቃውሞው እንደሰደድ እሳት ተቀጣጠለ፤ከዛም መፍትሄ ይሆናል በሚል የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት ፀሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ኃብተወለድ ልክ የዛሬ 42 ዓመት የካቲት 21 ቀን 1966 ዓ.ም. ከስልጣናቸው እንዲሰናበቱ ተደረ፡፡ ይሄም መፍትሄ አልሆነም፤ይልቅ የመምህራን ማኀበርና የታክሲ የተቃውሞ አድማ ወደ ወታደሩ ዞረ፤ከዛም ንጉሱንም ዘውዳዊ ስርዓቱን ላይመለስ እስከነ አካቴው አሰናበተው፡፡ ልብ በሉ ይህ ሁሉ ልክ የዛሬ 42 ዓመት የነበረ የአዲስ አበባ ታክሲ አድማ ምን እንዳስከተለ፡፡ ይሄ ሁሉ 4ኛ ወሩን ያስቆጠረውና እስካሁንም የቀጠለውን የኦሮሚያ ክልል ተቃውሞ በተጨማሪ መሆኑ ነው፡፡ አሁን ደግሞ በጎንደርም ተቃውሞዎች እያገረሹ መንገድ እስከመዝጋት እንደደረሱ እየተሰማ ነው፡፡

ዛሬ ከ42 ዓመት በኋላ በዘመነ ኢህአዴግ የካቲት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የመንግሥትን አዲስ መመሪያ በመቃወም የተደረገው የታክሲ አድማ በጠዋቱ ጀምሯል፡፡ ይህ እስከተፃፈበት ድረስም የአዲስ አበባው የታክሲ አድማ እንደቀጠለ ነው፡፡ አድማውም ለ ሁለት ተከታታይ ቀናት እንደሚደረገ የታቀደ ቢሆንም፤ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከሆነ ግን አድማው ሊቀጥል እንደሚችል ነው፡፡ የዚህ ምክንያት ደግሞ የአዲስ መመሪያ ዋና ሰለባዎች የታክሲ ሾፌሮች በመሆናቸው ነው፡፡

Flyers

New Addis Ababa Transport regulation

እስካሁን ባለው አድማም በከተማው የመንግሥት የመስሪያ ቤት የትራንስፖርት አገልግሎት አውቶቡስ፣ የግለሰቦች የጭነት ተሸከርካሪዎች (በግድ ተሳፋሪ እንዲጭኑ እየጠደረጉ) ከሚሰጡት አገልግሎት በስተቀር የተለመዱት የሚኒባስ ታክሲዎች አድማ መትተዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ህዝብ ብዛትና ከተጠቃሚው ብዛት እንዲሁም ቀድሞም ከነበረው የትራንስፖርት እጥረት አንፃር የታክሲዎች አድማ የሚያስከትለው ተፅዕኖ በቀላሉ የሚገመት አይደለም፡፡መንግሥት በስሩ ባሉ መገናኛ ብዙኃን በጠዋት ዜና እወጃው የአዲሱን የአዲስ አበባ ትራንሰፖርት ደንብ መመሪያ ትግበራ ለ3 ወራት ማራዘሙን ቢገልፅም፤የታክሲዎች አድማ ግን ቀኑን ሙሉ ቀጥሎ ውሏል፡፡

ምንም እንኳ ሀገር አቀፍ ምርጫ ከተደረገ 100 ቀናት ቢያልፉትም፤ የዛ “ምርጫ” ኢህአዴግ 100% የህዝብ ድምፅ “በምርጫ” አሸንፊያለው የሚለው መዝሙር ሳያባራ በየአቅጣጫው ጠንከር ያለ ተቃውሞ መምጣቱ ምናልባትም አማራጭ ሐሳብ ያለመኖርና እንዲኖር ያለመፈለጉ ያመጣው መዘዝም ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ በርግጥ የዛ ተዓምረኛው “ የ100% ምርጫ” ውጤት መዘዝ ገና ብዙ ክስተቶችን በመላው ሀገሪቱ ሊያስተናግድ እንደሚችልም ይጠበቃል፡፡

የዛሬው የአዲስ አበባ የታክሲ ተቃውሞ አድማ ወደ ሌሎች የግልና መንግሥታዊ ተቋማት አድማሱን አስፍቶ የዛሬ 42 ዓመቱን ታሪክ ይደግመው ይሆን?

Public service Bus as a taxi in Addis

በተለይ ከዓለም ገበያና ሀገሪቱ ነዳጅ ከገዛችበት 365 % (ነዳጁ ከተገዛበት ወደ 4 እጥፍ) ክፍያ የተጫነበት ተጠቃሚው ህዝብ ትክክለኛ መረጃ ቢኖረው ከታክሲ አድማው ይልቅ የተሳፋሪው አለመቅደሙ አስገራሚ ቢሆንም፤የዛሬው የታክሲዎች አድማ ሌላም ቁጣ ይቀሰቅስ ይሆን ወይስ እንደተለመደው በማስፈራሪያ አሊያም ደንብ ቁጥር 208/2003 ተከትሎ ወጥቷል የተባለው አዲሱ መመሪያ ተሰርዟል በሚል ወደስራቸው ይመለሱ ይሆን?

ሁሉንም ጊዜ ያሳየናል፡፡

በኢትዮጵያ ለተከታታይ አራት ወራት የቀጠለው ተቃውሞ ላይ የሚፈፀመው ግድያና እስር መቀጠሉ አስመልክቶ ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አስታወቀ

ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች አራተኛ ወሩን ይዞ የቀጠለውን የኦሮሚያ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ ላይ መንግሥት በፀጥታ ኃይሉ በወሰደው የኃይል እርምጃ ሰዎች መደላቸውን፣ በርካታ ሰዎች መቁሰላቸውን እና መታሰራቸውን እንዲሁም ታግተው የደረሱበት ያልታወቁ ሰዎች መኖራቸውን በመግለፅ መግለጫ አወጣ፡፡

Oromia region protest 1

ሂውማን ራይትስ ዎች በመግለጫው “አጠቃላይ የተገደሉ ሰዎችን ቁጥር ለማረጋገጥ አልቻለም ምክንያቱም በኢትዮጵያ ያለው እንቅስቃሴ እና በነጻነት የመዘገብ ሁናቴ የተገደበ በመሆኑ ነው፡፡ ተሟጋቾች በተለይ ከማህበራዊ ድረ-ገፆችን መሰረት በማድረግ ባገኟቸው የቪዲዮ፣ የፎቶ እና የድረ-ገጽ ላይ ጽሁፎች መረጃዎች መሰረት ከኖቬምበር 12 ቀን ጀምሮ ከ200 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ጠቁመዋል፡፡ ያለው መረጃ እንሚጠቁመው በበርካታ ሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ታስረዋል፤ በርካቶቹ የት እንሚገኙም አይታወቀም፤ የሚገመተው በሃይል እንዲሰወሩ መደረጉን አስታውቋል፡፡

Oromia region protest 2

እ.አ.አ.ከህዳር ወር 2015 ዓ.ም. ጀምሮ በኦሮሚያ ክልል በስፋት እየተካሄደ ያለውን ሰላማዊ ተቃውሞ የኢትዮጵያ የጸጥታ ሃይል በጉልበት እያፈነው እንደሚገኝ ሂውማን ራይትስ ዎች አስታወቀ፡፡ ከ2016 ዓ.ም. መነሻ ጀምሮ በእየለቱ ሰዎች እንደሚገደሉ እና በዘፈቀደ እንደሚታሰሩ በመግፅ፤ የወታደራዊ ሰራዊትን ያካተተው የጸጥታ ሃይል ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ ላይ የሚገኙ በርካታ ሰዎችን ቀጥታ በመተኮስ ገድሏል፡፡ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ታስረው ያለምንም ክስ እንደታገቱ ይገኛሉ፡፡ ባለፉት ሳምንታት የተቃውሞው ድግግሞሽ የቀነሰ መስሎ ቢታይም አፈናው ግን ቀጥሏል፡፡” ይላል ፤በመግለጫው፡፡
የተቋሙን ሙሉ መግለጫ (በአማርኛ እና በእንግሊዘኛ) ለማግኘት የሚከተለውን ሊንክ ይጠቀሙ፤

ምንጭ፡ https://www.hrw.org/am/news/2016/02/21/287126
https://www.hrw.org/news/2016/02/22/ethiopia-no-let-crackdown-protests

ገራፊዬን አየኹት

 

Abel Wabella

አቤል ዋበላ

ቀልድ ያለፈበት ጨዋታ ሆኗል፡፡ አሁን ዘውጉ ተቀይሯል፡፡ ፍጥጥ ግጥጥ ያለ ዕውናዊ ድርሰትን መመልከት ይዘናል፡፡አይን አያየው የለም፡፡ አሁን ደግሞ ገራፊዬን አሳየኝ፡፡ በኮምፒዩተር የኤሌክትሪክ ገመድ ጀርባዬ እስኪቀደድ የገረፈኝን፣ በመጥረጊያ እንጨት ውስጥ እግሬን ያነደደኝን፣ እጄ በካቴና ታስሮ ወለል ላይ ያንከባለለኝን፣ ጨለማ ቤት ውስጥ አስገብቶ ከየት እንደመጣ በማላውቀው ጅራፍ አሳሬን ያበላኝን፣ እናቴን ከመቃብር ጠርቼ “አንቺ እናቴ ለምን ጥሩ ሁን ብለሽ አሳደግሽኝ? ብዙ ክፉ ሰዎች እንዳሉ ለምን አልመከርሽኝም?” ብዬ እንድወቅሳት ያደረገኝን፣ ወንድ፣ የወንዶች ቁና በካቴና የታሰረን ሰው በዕኩለ ሌሊት ጠርቶ አፉ ውስጥ ጨርቅ ወትፎ የሚደበድብ በአይኔ በብረቱ አየኹት፡፡

ዮናታን ተስፋዬ ለጊዜያዊ ቀነ ቀጠሮ አራዳ ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ ሰምቼ ነው ወደዚያ የሄድኩት፡፡ ይህችን የተለመደች ሰርከስ ሁሉም የፖለቲካ እስረኛ ይወዛወዛታል፡፡በማዕከላዊ ይጀመራል ከዚያ አራዳ ፍርድ ቤት ይቀጥላል፡፡ የማዕከላዊ ደብዳቢዎች በጨለማ የሚያሰቃዩትን እስረኛ በቀን ሰው መስለው (ወገኞች ናቸው አንዳንዴማ ዩኒፎርምም ያጠልቃሉ) ፍርድ ቤት ያቀርቡታል፡፡ ውሸት ውሸቱን ይቀባጥራሉ፡፡ “ግበረ አበሮቹን በኢንተርፖል እያሳደድን ነው፣ ክቡር ዳኛ በዋስ ከተለለቀቁ ልማታችንን ያደናቅፋሉ፡፡ ወህኒ ሰብረው እስረኛ ያስፈታሉ” የመሳሰሉትን በጠራራ ጸሐይ ይቀባጥራሉ፡፡ እየቀለድኩኝ አይደልም የምሬን ነው እንዲህ አይነት በሬ ወለደ ምክንያት በጆሮዬ ሰምቻለው፡፡ ዳኛውም አብሮ ይተውናል፡፡ የፈለጉትን ቀን ያህል ያራዝማል፡፡

ገራፊዬንም ያየሁት እኔንና ጓደኞቼን እንደነዳው እንዲሁ ተረኛውን ገፈት ቀማሽ ሲያመጣ ነው፡፡ ላንዳፍታ አይኖቻችን ተጋጩ፡፡ አስተውሎኝ ይሁን አይሁን አላውቅም በፍርድ ቤቱ ቢሮዎች መሐል ገብቶ ተሰወረ፡፡ እኔ ግን በእርግጠኝነት ለይቸዋለው፡፡ ውስጤ ዳግም ተቆጣ፡፡ እስር ቤት ብቻዬን ደጋግሜ ባሰብኩት ቁጥር እንደአዲስ የልቤ ቁስል ያመረቅዝ ነበር፡፡ ቂም ስቋጥር እና ስፈታ ከአመት በላይ ቆይቻለው፡፡ ቂም ይዣለው በውድም ሆነ በግድ ኢትዮጵያዊ በሆነ ሁሉ ላይ ቂም ይዣለው፡፡ እንዴት ሰው በሀገሩ ይህንን ጉድ ተሸክሞ ይኖራል? እንዴት እንደዚህ አይነት ተቋም በመዲናይቱ እምብርት ላይ አስቀምጦ ዝም ይላል? ይህን ባርቤሪዝም ጌጡ ካደረገ ማኀበረሰብ ጋር በቀላሉ የማይበርድ ግጭት ውስጥ ነኝ፡፡ ስለዚህ በመንገድ ስታገኙኝ ፊቴ ጥቁር ብሎ ብታገኙኝ “ምን ሆነህ ነው?” አትበሉኝ፡፡ ቂም ይዤ ነው፡፡ ተራ ማኩረፍ አድርጋችኹ አትውሰዱት ስር የሰደደ ከነፍስ የሚቀዳ ጸብ ነው፡፡

በግርፋት የተሰነጠቀውን ጀርባዬ በቅባት ላሹኝ ዕድሜ ለእነ ኤባ ቁስሉ እዛው ማዕከላዊ ነው የዳነው፡፡ የልቤ ስንጥቅ ግን አልዳነም ፡፡ ያ ዘላለም ክብረት “ምድር ብዙ ክፋት የሚፈጸምባት ቦታ ናት በእኛ ላይ የደረሰውም አዲስ ነገር አይደለም” እያለ ብዙ እንዳላዝን ቢመክረኝም ያቄመው ልቤን ሊያሸንፈው አልቻለም ነበር፡፡ የተገኘሁበት፣ ያሳደገኝ ማኀበረሰብ ላይ እንዳቄምኩኝ ከእስር ወጣኹኝ፡፡ ባለፉት አራት ወራት በአንጻራዊ ነጻነት ማሳለፌ ግን ትንሽ እንዳዘናጋኝ የገባኝ ግን በቀደም ገራፊዬን ያየኹት ቀን ነው፡፡ወይ ጊዜ ስንቱን ያስረሳል አልኩኝ፡፡ አሁን ከእስር መፈታት ብርቅ የሆነበት ጊዜ አልፏል፡፡ ቁስሌ ዳግም አመርቅዟል፡፡ ገራፊዬን እና አለቆቹን የያዘው ህንጻ ካልፈረሰ አልያም ሙዚየም ካልሆነ ዕርቅ የማይታሰብ ነው፡፡ ድሮ እስር ቤት ሳለኹኝ በእስረኛ ማጓጓዣ መኪና ወደ ፍርድ ቤት ስንመላለስ በመስኮት ስመለከተው የዕለት ጉርሱን ለማብሰል የሚራኮተው አዳሜ አሁንም ውስጡ ሁኜ ስመለከተው ከሆዱ በቀር የኔ ቁስል ግድ የሰጠው አይመስልም፡፡ ስለዚህ ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ ብዬ ይቅር እላለው? ውስጤ የበለጠ ስለሻከረ እምቢኝ ብያለው፡፡ ይህ የአንዲት ነጠላ ነፍስ መብት ነው፡፡ በገዛ ነፍሴ ጥላቻን ማርገዝ መብቴ ነው፡፡ ከፈለጋችኹ ለዐቃቤ ሕግ ንገሩትና በፊት ‘የማኀበረሰቡን ጤና እና ደህንነት ለአደጋ በማጋለጥ’ እንደ ከሰሰኝ አሁን ደግም ‘በማኀበረሰቡ ላይ ስር የሰደደ ጥላቻና ቂም በመቋጠር’ ይክሰሰኝ፡፡

እነ ኤቢሳ አካላዊ ቁስሌን እንደሳምራዊው ሰው በቅባት እንዳሹልኝ አሁን ደግሞ ዘመዶቻቸው የተሰበረ መንፈሴን የቆሰለ እኔነቴን ሊጥገኑ ተነስተዋል፡፡ የእነኤቢሳ፣ የእነቶፊቅ እና የእነ ቶላ ዘመዶች እኔን ከህመሜ ሊያድኑኝ ደማቸውን እየከፈሉ መሆናቸውን ድፍን ፌስቡክ እየተመለከተው ነው፡፡ አዲስ አበቤ “አገር ሊያፈርሱ ነው ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር አትኖርም” ቅብርጥሴ ቅብርጥሴ ቢልም እኔ ግን ከሚፈርሰው አገር ከፒያሳ ከፍ ብሎ ያለው ማዕከላዊ ጎልቶ ይታየኛል፡፡ ስለዚህ በመሬት ላይ ዋጋ እየከፈሉ ያሉትን ወገኖቼን ይቅር ብያለው፡፡ ከነዚህ በቀር ሌላው ማኀበረሰብ “እርሱ” አይደለም “እኔ” ራሱ ይቅርታን አያገኛትም፡፡ አራዳ ፍርድ ቤት መሄዴ አይቀርም፡፡ በማዕከላዊ በርም አልፋለው፡፡ በየጊዜው እየሄደኩኝ ከገራፊዎቼ አንዱን እያየው ጥላቻዬን እያደስኩኝ እመጣለው፡፡ ቁስሉ ይበልጥ እንዲቆጠቁጠኝ ወደገራፊዬ ተጠግቼ አይኖቹን በአይኖቼ አድናለው፡፡ አይገርምም ግን ………….…ገራፊዬ እስካሁን እዚያው ነው፡፡

በኦሮሚያ ክልል ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ አሁንም ቀጥሏል፤ እየተገደሉ እና እየቆሰሉ ያሉ ዜጎችም መጠንም ጨምሯል

በህዳር አጋማሽ በምዕራብ ሸዋ የጀመረው ተቃውሞ በአብዛኛው የኦሮሚያ ክልል ከተሞች ዛሬም ድረስ ቀጥሏል፡፡ ባለፈው ሳምንት በነበሩ ተቃውሞች ህፃናት እና ኣዛውንቶችን ጨምሮ ከ130 ያላነሱ ሰዎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸው ተጠቁሟል፡፡ በተለይ በምዕራብ አርሲ አጄ አካባቢ በነበረው ተቃውሞውም የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ህዝቡ ላይ የወሰዱትን የኃይል እርምጃ ተከትሎ 11 ያህል የመንግሥት ወታደሮች መገደላቸው ታውቋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በሀገሪቱ የፖለቲካ እስረኞች ከሚበዙበት ወህኒ ቤቶች መካከል አንዱ እንደሆነ የሚነገርለት የአምቦ ወህኒ ቤት በእሳት የመቃል አደጋ ደርሶበታል፡፡ የቃጠሎው መንስኤ እና ቃጠሎውን ተከትሎ ስለደረሰው ጉዳት ከመንግስትም ሆነ ከገለልተኛ አካል የተገለፀ ነገር የለም፡፡

Dembi dolo

በዛሬው የካቲት 14 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ሐረርጌ መቻራ ከተማ በነበረው ተቃውሞ የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት የኃይል እርምጃ እስካሁን ቁጥራቸው በውል ያልተለዩ በርካታ ሰልፈኞች መገደላቸውና ከ15 በላይ ዜጎች ደግሞ በፅኑ ቆስለው ገለምሶ ሆስፒታል የህክምና እርዳታ እየተደረገላቸው መሆኑን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ህዝባዊ ተቃውሞን ተክተሎ በክልሉ እየታሰሩ ያሉ ወጣቶች ቁጥርም በከፍተኛ ደረጃ የቸመረ ሲሆን፤ በትናንትናው ዕለትም ዋና ፅህፈት ቤቱ 6 ኪሎ አዲስ አበባ አፍንጮ በር የሚገኘው የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ/መድረክ ዋና ፅሕፈት ቤት በመንግሥት የፀጥታና የደህንነት ኃይሎች ቁጥጥር ስረ ወድቆ በቢሮው የነበሩት ተደብድበው መታሰራቸውንም የፓርቲው የመረጃ ማኀበራዊ ገፅ አመልክቷል፡፡ በወቅቱ የፓርቲው ሊቀመንበር ዶ/ር መረራ ጉዲናም ወደ ቢሯቸው እንዳይገቡ ተከልክለው እንደነበር የፓርቲው ገፅ አስታውቋል፡፡

Oromo protest 2

በተለይ በምዕራብ አርሲ በነበረው ተቃውሞ የአካባቢው ሽማግሌዎች ለተቃውሞ የወጡና የተቃውሞ ሰልፎች ላይ ንቁ ተሳታፊ ናቸው የተባሉ በርካታ ወጣቶችን በመሰብሰብ በሚደረገው ተቃውሞ በሌሎች ብሔሮች አካልም ሆነ ንብረት ላይ ምንም ዓይነት ጉዳትና ጥቃት እንዳትፈፅሙ፣ ተቃውሞ በምንግሥትና በስርዓቱ ላይ እንጂ በየትኛውም የህዝብ አካላ ላይ አይደለም፡፡ ይህን ተላልፎ የተገኘም የእና አካል አይደለም፤ሊሆንም አይችልም ሲሉ ቃል ማስገባታቸው ታውቋል፡፡ በክልሉ ያለው ተቃውሞ በአርሲ፣ በወለጋ፣ በነጌሌ፣ በሱሉልታ፣ በምዕራብና ምስራቅ ሐረርጌ ተጠናክሮ መጠሉ ታውቋል፡፡ይሁን እንጂ መንግሥት ምዕራብ ወለጋን ጨምሮ በተለያዩ ከተሞች የመከላከያ ከባድ የጦር መሳሪያዎችን እና ሰራዊት የጫኑ ተሸከርካሪዎች በሰፊው ሲንቀሳቀሱ ታይተዋል፡፡