- “ለአንድ አላማ እንታገላለን” አቶ ግርማ በቀለ
- “መሰባሰባችን ትግሉን ያጠናክረዋል” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት
የኦሞ ሕዝቦች ዲሞክራሲያዊ ህብረት (ኦሕዲኅ) አባላት በሰማያዊ ፓርቲ ምልክት ለመወዳደር መወሰናቸውን የኦሕዲኅ ሊቀመንበር አቶ ግርማ በቀለ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጹ፡፡ ‹‹ጥቅምት 26/2006 ዓ.ም ፓርቲው ባደረገው ጠቅላላ ጉባኤ አባላቱና አመራሩ ከአገር አቀፍ ፓርቲዎች ጋር በውህደት መስራት እንዳለባቸውና በኦሕዲኅ ስም የሚደረገው የመጨረሻ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲሆን ወስነው ነበር›› ያሉት ሊቀመንበሩ የፓርቲው እጩዎች በሰማያዊ ፓርቲ ስምና ምልክት መመዝገባቸው አባላቱና አመራሩ ‹‹አገራዊ ፓርቲ ጋር በውህደት አሊያም በሌላ መንገድ አብረን መስራት አለብን፡፡›› በሚል በጠቅላላ ጉባኤው ያስተላለፉት ውሳኔ አካል ነው ብለዋል፡፡
አቶ ግርማ ፓርቲያቸው ከሰማያዊ ጋር ሆኖ ለመታገል የተነሳበትን ምክንያትም ‹‹አሉ ከሚባሉት 70 ያህል ፓርቲዎች አብዛኛዎቹ የክልል ፓርቲዎች ናቸው፡፡ የክልል ፓርቲዎች በአገራችን ፖለቲካ ፋይዳ ያለው ለውጥ እያመጡ አይደለም፡፡ የክልል ፓርቲዎች ሲጠናከሩም ቢሆን ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው እንደሚያመዝን ተረድተናል፡፡ በተቃራኒው አገር አቀፍ ፓርቲዎች ሲጠናከሩ የተሻለ ለውጥ ማምጣት ይችላሉ›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡ አቶ ግርማ አክለውም ‹‹እስካሁን የክልልና አገራዊ ፓርቲ ተባብለን ተበታትነን ቆይተናል፡፡ አሁን ግን የተሻለ ለውጥ ለማምጣት አንድ አይነት ጥያቄ አንስተን፣ በአንድ አላማ ለመታገል ወስነናል፡፡ አንድነት ኃይል በመሆኑ በኢትዮጵያ ፖለቲካ የተሻለ ለውጥ እንደምናመጣ የሚል ትልቅ ተስፋ አለን›› ብለዋል፡፡
ፓርቲው ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ስምምነት በመፈረሙ አባላቱ በሰማያዊ ፓርቲ ስር ሆነው እንዲወዳደሩ ለምርጫ ቦርድ ባስገባው ደብዳቤም ‹‹የዚህ ስምምነት አላማ ፈራሚዎች ለ2007 ዓ.ም አጠቀላይ አገራዊ ምርጫ አባላትን በጋራ በአንድ የመወዳደሪያ ምልክት ማቅረብ፣ ማለትም የአንዱ ፓርቲ አባልና አመራር በሌላው ፓርቲ ሥምና ምልክት የሚወዳደሩበትን ሁኔታ ማመቻቸት፣ ስምምነት ሲደረስም ተግባራዊ ማድረግ ነው›› ብለዋል፡፡
በተመሳሳይ የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት የቀድሞ የአንድነት አባላት ወደ ሰማያዊ ፓርቲ መምጣታቸውን አስታውሰው አሁንም የኦሕዲኅ አባላት በሰማያዊ ፓርቲ ስር ለመወዳደር በፓርቲው ጥላ ስር መሰባሰባቸው ሰላማዊ ትግሉን እንደሚያጠናክረው ገልጸዋል፡፡ ‹‹በአንድነት መቆማችንና መሰባሰባችን ትግሉን ያጠናክረዋል፡፡ ኢህአዴግ የአንድነት አመራሮችና አባላት ወደ ሰማያዊ በመምጣታቸው፣ ሰማያዊም እጁን ዘርግቶ በመቀበሉ ከፍተኛ ፍርሃት ተፈጥሮበታል፡፡›› ብለዋል፡፡ ኢ/ር ይልቃል አክለውም ‹‹አሁንም ሌሎች ፓርቲዎች መቀላቀላቸው ለኢህአዴግ ትልቅ ስጋት ነው፡፡ ይህም በመሆኑ በቴሎቪዥንና በራዲዮ እጩ ያቀረቡ ፓርቲዎችን ሲያስተዋውቅ የሰማያዊን ስም ሳይጠቅስ ቀርቷል፡፡ በተቃራኒው በሬዲዮና በቴሊቪዥን ሰማያዊ ተቋማትን አይቀበልም እያለ በሀሰት እየወነጀለ ያለው የተቃውሞ ጎራው በአንድነት በመቆም እየተጠናከረ በመምጣቱ ነው፡፡›› ሲሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት በሰማያዊ ስር መሰባሰባቸው ያለውን ፋይዳ መግለፃቸውን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡