አቶ በቀለ ገርባ በድጋሚ ታሰሩ
የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ/መድረክ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበር እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር አቶ በቀለ ገርባ ዛሬ በድጋሚ መታሰራቸው ተገለፀ፡፡ አቶ በቀለ ዛሬ የታሰሩት አዳማ/ናዝሬት ከሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው በ14 የደህንነት አባላት ለሰባት ሰዓታት ያህል ፍተሻ ከተደረገ በኋላ ተይዘው ወደ አዲስ አበባ መምጣታቸውን የኢሳት ዘገባ አመልክቷል፡፡
ባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. ከተቀጣጠለው የኦሮሚያ ክልል ህዝብ ተቃውሞን ተከትሎ የፌደራል ፖሊስ፣ የአጋዚ ልዩ ኃይል እና መከላከያ ሰራዊት በክልል በተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ ከ86 በላይ ሰዎች መገደላችን፣ በርካታ ሰዎች መቁሰላቸውን እና መታሰራቸውን ተከትሎ አቶ በቀለ በፓርቲያቸው ኦፌኮ/መድረክ አማካኝነት ከፍተኛ ተቃውሞ ሲያሰሙ ከነበሩ አመራሮች አንዱ መሆናቸው ይታወቃል፡፡
አቶ በቀለ ከዚህ በፊት በሰኔ 2003 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል በመንግሥት ስለሚፈፀሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በተመለከተ ለአምንስቲ ኢንተርናሽናል ጋር ያደረጉትን አጭር ቆይታ ተከትሎ መንግሥት በሽብር ወንጀል ፈርዶ ለ3 ዓመት ከ7 ወር በኋላ የእስር ፍርድ ጊዜያቸውን ጨርሰው ባለፈው መጋቢት 2007 ዓ.ም. መፈታታቸው አይዘነጋም፡፡ አቶ በቀለ ዛሬ ከመኖሪያ ቤታቸው ተይዘው የታሰሩበት ምክንያት እስካሁን እንዳልተገለፀላቸው ታውቋል፡፡
በተያያዘ ዜና ከአቶ በቀለ ገርባ በተጨማሪ ቀደም ሲል ከኦፌኮ/መድረክ ከፍተኛ አመራሮች አቶ ደጀኔ ጣፋ እና የተለየዩ የፓርቲው አባላትና የዞን አመራሮችም መታሰራቸው ታውቋል፡፡
ለለአንድ ወር የዘለቀው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞ አዲሱን የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላንን በመቃወም መነሻ ቢሆንም በተጨማሪ የተለያዩ የመብት ጥያቄዎችን ያካተተ እንደነበር አይዘነጋም፡፡