Daily Archives: December 25th, 2015

በእስር ላይ የሚገኙት የኢትዮጵያ ሙስሊሙ ማኀበረሰብ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሜቴ አባላት መግለጫ ሰጡ

በእስር ላይ የሚገኙት የኢትዮጵያ ሙስሊሙ ማኀበረሰብ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሜቴ አባላት በአዲስ አበባ መርካቶ በሚገኘው አንዋር መስኪድ ባለፈው አርብ ታህሳሥ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. የደረሰውን ድንገተኛ የቦንብ ፍናዳታ አደጋን አስመልክቶ ዛሬ አርብ ታህሣሥ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ በእስር ላይ የሚገኙት የኮሚቴ አባላት ባለፈው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በነበረው ችሎት ከ7 ዓመት እስከ 22 ዓመት የሚደርስ ፅኑ እስራት እንደተፈረደባቸው አይዘነጋም፡፡ ሙሉ መግለጫው የሚከተለው ነው፡-

Dimetsachin Yisemaየአንዋር መስጊዱን የቦምብ ጥቃት አስመልክቶ በእስር ቤት ከሚገኙ የኮሚቴው አባላት የተሰጠ መግለጫ አርብ ታህሳስ 15/2008

ህዝበ ሙስሊሙ ለተንኮለኞች ሴራ ሳይበገር አንድነቱን አጠንክሮ፣ አመለካከቱን አቻችሎ ሰላማዊ የመብት ትግሉን መቀጠል ይኖርበታል!

በአንዋር መስጊድ ቅጥር ግቢ ታህሳስ 01/2008 የደረሰው የቦንብ ጥቃት የዓለም አቀፉ ሕብረተሰብ ትኩረት እንዲሰጠው፣ ድርጊቱም በገለልተኛ አካላት በአስቸኳይ ተጣርቶ ለህዝብ ይፋ ይደረግ ዘንድ እንጠይቃለን!
አርብ ታህሳስ 15/2008 /አዲስ አበባ/ኢትዮጵያ

ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ሕገመንግስታዊ የመብት ጥያቄያችንን ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ማቅረባችን ይታወቃል። ለጥያቄዎቻችን ተገቢውን እና ፍትሃዊ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ ጥያቄውን በሀሰት በመፈረጅ ሰላማዊ ሂደቱን ለመቀልበስ ተደጋጋሚ ጥረት ተደርጓል። የህዝበ ሙስሊሙን የፍትህ ጥያቄን ለማጠልሸት እና በመካከሉ ልዩነትን ለመፍጠር የተለያዩ የፕሮፓጋንዳ ስራዎች ሲከናወኑ ቆይተዋል። ለህዝበ ሙስሊሙ ጥያቄዎች መፍትሄ ለማፈላለግ ሕዝብ በወከለን መሰረት በመንቀሳቀሳችን ወንጀለኛነት እና የረጅም እስር ፍርድ እንዲወሰን ተደርጓል። ይህም ሁሉ ሆኖም የሙስሊሙን አንድነት መስበርም ሳይቻል ቀርቶ ለመብቱ መከበር የሚያደርገውን ትግል በተጠናከረ መልኩ እየቀጠለ ባለበት ወቅት እጅግ ጸያፍ የሆነ የቦምብ ጥቃት በእምነት ቤታችን ቅጥር ግቢ ውስጥ መሰንዘሩ እጅግ ያሳዘነን ክስተት ነው።

የህዝበ ሙስሊሙን ጥያቄ ለመቀልበስ የሚደረጉ ሙከራዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ እና የህዝበ ሙስሊሙን ሰላማዊ የትግል ሂደት መንገድ ሊያስቱ እንደሚሞክሩ ደጋግመን ስናስጠነቅቅ ቆይተናል። የሸፍጥ ጥቃቶችን በስውር በመፈጸም ፓለቲካዊ ጥቅም የሚያስገኙ እርምጃዎችን ለመውሰድ የማመቻቸት ተግባር በተለያዩ ሀገሮች የምናየው ክስተት ነው። በሰላማዊ የትግል ሂደታችንም በተለያየ ጊዜ የተረዳነውና ያጋጠመንም ነው። ሆኖም ግን ሙስሊሙ ህብረተሰብ የመከላከል ስራዎች ላይ በልዩ ትኩረት በመስራቱ ሰላማዊ ሂደታችን ለፓለቲካ ግብዓት እንዳይውል እድሉን ነፍጓቸው ቆይቷል። እንግዲህ በአንዋር መስጊድ ቅጥር ግቢ ውስጥ ታህሳስ 01/2008 የደረሰው የቦንብ ጥቃት ቀደም ብለን እንደ ህዝብ ገምተን ስንከላከለው፣ መንግስትም የሀይማኖት ተቋማትን በተለይም የመስጂዶችን ደህንነት ለመጠበቅ በኩል ያለበትን ሀላፊነት በትክክል እንዲወጣ ስናስጠነቅቅበት የቆየነው እንጂ ሌላ አይደለም።

ሙስሊሙ ህብረተሰብ ፍትሃዊና ሰላማዊ ትግሉን አጠናክሮ ለመቀጠል ዳግም ቃል እየተጋባ ባለበት በአሁኑ ወቅት እና አማኞች የፈጣሪያቸውን ግደታ ለመወጣት በተሰባሰቡበት ቦታና ሰዓት የቦንብ ጥቃት ማድረስ በእርግጥም የሙስሊሙን ሰላማዊ ሂደት ለማጠልሸት፣ የትግል ወኔውን ለመስበር፣ አንድነቱን ለመረበሽ ዛሬም የማይፈነቀል ድንጋይ እንደማይኖር የሚያረጋግጥ ነው። ከዚህ በመነሳት በቀጣይም በመስጊዶች ብቻ ሳይወሰን በክርስትና እና በሌሎች የአምልኮ ቦታዎችም ላይ ተመሳሳይ ጥቃቶችን በማድረስ በተለያዩ እምነት ተከታይ ኢትዮጵያዊያን መካከል ቅራኔን ለመፍጠር ሙከራዎች እንደሚደረጉ መገመት ከእውነታ የራቀ አይሆንም። በዚህ አይነት የተንኮለኞች ሴራ አገራችን እና ህዝባችን አደገኛ ወደ ሆነ አቅጣጫ እንዲመሩ አንፈቅድም። በመሆኑም ጉዳዩ የዓለም አቀፋዊ ማህበረሰብ ትኩረት እንዲቸረው እና ይህ እኩይ ተግባር በገለልተኛ አካል ይጣራ ዘንድ ሀገር እና ወገን ወዳድ የሆኑ ሁሉ ጥረት እንዲያደርጉ አጥብቀን እንጠይቃለን። በደረሰው ጥቃት ለተጎዱት ወገኖቻችን፣ እንዲሁም ለመላው ሙስሊም ህብረተሰብ እና ኢትዮጵያዊያን ሁሉ በሁኔታው የተሰማንን ሀዘን እንገልጻለን። ህዝበ ሙስሊሙም በፍንዳታው ጉዳት ለደረሰባቸው ወንድሞቹ እና ለቤተሰቦቻቸው አስፈላጊውን እገዛ በማድረግ እና ከጎናቸው በመቆም አጋርነቱን፣ አንድነቱን እና ከምንም በላይ የትኛውም አይነት ሴራ የማይበግረውን ከፈጣሪው በተዘረጋ የእምነት ገመድ ላይ ያለውን የአንድነት ትስስር በተግባር ሊያሳይ ይገባል።

የህዝበ ሙስሊሙ ጥያቄያች ፍትሀዊ ናቸው፡፡ ሂደቱም ሰላማዊ ነው። በህዝበ ሙስሊሙ መካከል ጥርጣሬን ለማስፈን፣ ክፍፍልን በማምጣት እርስ በርሱ ለማጋጨት የሚፈጸም የትኛውም ደባ የከሸፈ ከንቱ ጥረት ነው። ህዝባችን በዚህ እና መሰል ሴራዎች ሳይበገር አንድነቱን ጠብቆ፣ አመለካከቱን አቻችሎ ሰላማዊ የመብት ትግሉን ከመቼውም ጊዜ በላይ አጠናክሮ እንዲቀጥል እናሳስባለን።

አገራችን ያለችበትን ተጫባጭ የታሪክ ፈታኝ ምእራፍ በመረዳት ህብረተሰባችን ያለአንዳች የብሄር፣ የዘር፣ የሃይማኖትና የጾታ ልዩነት ለፍትህ እና ለሕግ የበላይነት በመቆም ዜጎቿ በሰላም ተሳስበን የምንኖርባት ሀገር ትሆንልን ዘንድ ጠንክረን መታገል ይኖርብናል። ለዚህ ስኬት ከጥረታችን ባሻገር ሁላችንም ፈጣሪያችንን በጽኑ እንለምን። በመተናነስ፣ በጸሎት፣ በሰደቃ እና በመልካም ተግባር ወደፈጣሪያችን አላህ (ሱ.ወ) መቃረብ እንደሚኖርብን ህዝባችንንም ራሳችንንም ሳናስታውስ አናልፍም!
ድል የሚከጀለው ከአላህ እንጂ ከሌላ አይደለም!
ትግላችን እስከድል ደጃፎች በአላህ ፈቃድ ይቀጥላል!
ድምጻችን ይሰማል!
አላሁ አክበር!

ምንጭ፡-ቃልኪዳን ቲዩብ

እነ ሀብታሙ አያሌው በጠቅላይ ፍርድ ቤት የቃል ክርክር አደረጉ

ኢዩኤል ፍስሃ ዳምጤ

“እኔ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል እንደመሆኔ መጠን የኢህአዴግን ጭቆና ማጋለጥ ግዴታዬም መብቴም ጭምር ነው! ይህን ካላደረጉ ምኑን ተቃዋሚ ሆንኩ?” አብርሃ ደስታ
“እኔ አሸባሪ አይደለሁም! የታሰርኩት በኢህአዴግ የፖለቲካ ሴራ ነው! እኔ የፖለቲካ እስረኛ ነኝ!” ዳንኤል ሺበሺ

Political prisoners

 

በሽብርተኝነት ወንጀል ተጠርጥረው በሥር ፍርድ ቤት ውሳኔ በነፃ የተሰናበቱት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች የሆኑት አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ አቶ አብርሃ ደስታ፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ አቶ የሺዋስ አሰፋና በተመሳሳይ የክስ መዝገብ ውስጥ ከአመራሮቹ ጋር የተከሰሰው አቶ አብርሃም ሰለሞን በፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ዛሬ ታህሳስ 15 ቀን 2008 ዓ.ም በመቅረብ የቃል ክርክር አድርገዋል፡፡
በችሎቱ የተሰየሙት ግራ ዳኛ መዝገቡ ለዛሬ የተቀጠረው ታህሳስ 8 ቀን 2008 ዓ.ም ተከሳሾቹ የፍርድ ቤቱ ሰብሳቢ ዳኛ የሆኑት አቶ ዳኜ መላኩ ከሰብሳቢነታቸው እንዲነሱ ባቀረቡት የፅሁፍ አቤቱታ ላይ መልስ ለመስጠት፤ የተከሳሾቹንና የአቃቤ ሕግን የቃል ክርክር ለማድመጥ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ተከሳሾቹ “ሰብሳቢው ዳኛ ይነሱልን!” ብለው ያቀረቡት ጥያቄ ፍ/ቤቱ ስላላመነበት ውድቅ መደረጉን ገልፀዋል፡፡

አቃቤ ሕግ በችሎቱ ባቀረበው የይግባኝ አቤቱታው ተከሳሾቹ ከግንቦት ሰባት አመራር አባላት ጋር በተለያየ ጊዜ መገናኘታቸውን፤ ይህንንም የሚያስረዳ ማስረጃ ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ ማቅረባቸውን ነገር ግን የስር ፍርድ ቤቱ እነዚህን ማስረጃዎች ሳይመዝን “በደፈናው ውሳኔ ስለሰጠ” ይግባኝ መጠየቃቸውንና የስር ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ሲሰጥ ከጭብጥ መውጣቱን ገልጿል፡፡ “ፍርድ ቤቱ ከፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ አንቀፅ 23 መሰረት የቀረበውን የሰነድ ማስረጃዎች በመመልከት የስር ፍርድ ቤት ውሳኔን በመሻር ተከሳሾቹ የቀረበባቸውን ክስ እንዲከላከሉ ፍርድ ቤቱ ይወስንልን ዘንድ እንጠይቃለን” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡

1ኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ አያሌውና 5ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃም ሰለሞን በጠበቃቸው አምሃ መኮንን በኩል የመከራከሪያ ሃሳባቸውን አቅርበዋል፡፡ አቶ አምሃ መኮንን የስር ፍርድ ቤቱ ደምበኞቻቸውን በነፃ ሲያሰናብታቸው የቀረቡትን ማስረጃዎች መዝኖ መሆኑን ለችሎቱ አስረድተዋል፡፡ አቃቤ ሕግ በክሱ ላይ ያቀረባቸው ነገሮች እንደመረጃ እንጂ እንደማስረጃ ሊያዙ እንደማይገባ የተከሳሾቹ የቀድሞ ጠበቃ በስር ፍርድ ቤት ክርክር አድርገው የስር ፍርድ ቤቱ ሐምሌ 2 ቀን 2007 ዓ.ም “በማስረጃ ሊያዙ ይገባል!›› ብሎ ብይን ማስተላለፉን አቶ አምሃ አውስተዋል፡፡

ጠበቃው ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ በኩል የሚቀርቡ ማስረጃዎችም ፍርድ ቤት ሊመረምራቸው እንደሚገባ ሲያስረዱ፡- “የብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ በኩል የሚቀርቡ መረጃዎችን ፍርድ ቤቱ ሙሉ ለሙሉ የሚቀበል ከሆነ የፍርድ ቤቱ ሚና ምን ሊሆን ነው? ፍርድ ቤቱ ከተቋሙ በኩል የሚቀርቡለትን መረጃዎች ሙሉ ለሙሉ የሚቀበል ከሆነም ፈራጁ ፍርድ ቤት ሳይሆን ብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ ነው” በማለት አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡

ደምበኛቸው አቶ ሀብታሙ አያሌውም በክሱ ላይ ‹‹ዘመነ ካሴ›› ከተባለው የግንቦት ሰባት አባል ጋር በመነጋገር አብረው ለመስራት ተስማሙ ተብሎ ቢገለፅም ይህን የሚያስረዳ ማስረጃ አለመቅረቡን ገልፀዋል፡፡ ደምበኛቸው ከግለሰቡ ጋር ባደረጉት የስልክ ልውውጥ አንድም ቦታ ላይ አብረው ለመስራት መስማማታቸውን እንዳልገለፁ ጠበቃው ጠቁመዋል፡፡ በክሱ ላይ የአንድነት ፓርቲ ሕዝብ ግንኙነት ክፍል ኃላፊ የሆነው አቶ ሀብታሙ አያሌው ከዘመነ ካሴ ጋር ግንኙነት አደረጉ ተብሎ የተገለፀው ከእውነታ የራቀ መሆኑን ጠበቃው ገልፀዋል፡፡ በተጠቀሰው ጊዜ አቶ ሀብታሙ አይደለም የአንድነት ፓርቲ ሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሊሆኑ ቀርተው፤ የፓርቲው አባል እንዳልነበሩም አቶ አምሃ አስረድተዋል፡፡ አቶ ሀብታሙ በበኩላቸው በክሱ ላይ ተከሳሽ በዚህ የሞባይል ቁጥር ግንኙነት አድርጓል ተብሎ አለመገለፁን የስልክ ልውውጡም ምን እንደሆነ የሚያስረዳ አንዳች ነገር አለመቅረቡን ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡

Abreham Solomon

አቶ አምሃ ደምበኛቸው በሆነው 5ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃም ሰለሞን ላይ ምንም አይነት የሰነድ ማስረጃ አለመቅረቡን የግንቦት ሰባት አባል ነው ሲባልም፤ በግንቦት ሰባት መዋቅር ውስጥ እንዳለ የሚያሳይ ማስረጃ አለመቅረቡን ደምበኛው በምንም አይነት የሽብርተኝነት ተግባር ላይ እንደተሰማራ የሚገልፅ ምንም አይነት ማስረጃ አለመቅረቡን ገልፀዋል፡፡ አቶ አብርሃም ሰለሞን በበኩሉ ያለአንዳች ማስረጃ መታሰሩን ሲያስረዳ፡- “ከታሰርኩ በኋላ ነው ማስረጃ ሲፈለገብኝ የነበረው፤ ከታሰርኩ በኋላም ቤቴ እንኳ አልተፈተሸም፡፡ መንግስት አሰረኝ ብዬ አላምንም ያሰረኝ አንድ ግለሰብ ነው” ሲል ተደምጧል፡፡

2ኛ ተከሳሽ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ 3ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃ ደስታና 4ኛ ተከሳሽ የሺዋስ አሰፋ ያለጠበቃ በመቆም በግል ክርክራቸውን ያካሄዱ ሲሆን፤ ሶስቱም ተከሳሾች የአቃቤ ሕግ የይግባኝ ማመልከቻ ላይ እነሱን የሚመለከት ቅሬታ አለመቅረቡን ለፍርድ ቤቱ ገልፀዋል፡፡ አቶ ዳንኤል ሺበሺ “እኔ አሸባሪ አይደለሁም! የታሰርኩት በኢህአዴግ የፖለቲካ ሴራ ነው! እኔ የፖለቲካ እስረኛ ነኝ!” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ የቃል ክርክር ለማድረግ ያዘጋጁት ወረቀትም በማረሚያ ቤቱ እንደተቀደደባቸው ለፍርድ ቤቱ አሳይተዋል፡፡ ወረቀቱ ማህተም የተደረገበት ቦታ ተቀዶ መውጣቱን በችሎቱ ለነበሩ ታዳሚያን በግልፅ ታይቷል፡፡

3ኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃ ደስታም ከታሰሩ በኋላ ማስረጃ ሲፈልግባቸው እንደነበርና በብሔራዊ መረጃና ደህንነት ኤጀንሲ የሚቀርብ መረጃ በፍርድ ቤት ሳይመዘን ሙሉ ለመሉ ተቀባይነት የሚያገኝ ከሆነ ተቋሙ ከሳሽም፣ መስካሪም፣ ዳኛም ሆነ ማለት ነው፡፡ ይህ ከሆነ ዘንድ ደግሞ ፍርድ ቤት መምጣትም አያስፈልግም ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ በክሱ ላይ ለኢሳት ቴሌቪዥን ቃለምልልሰ ሰጠ ተብሎ የቀረበው ክስ ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ሲያስረዱ፡- “እኔ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል እንደመሆኔ መጠን የኢህአዴግን ጭቆና ማጋለጥ ግዴታዬም መብቴም ጭምር ነው! ይህን ካላደረጉ ምኑን ተቃዋሚ ሆንኩ?” በማለት ለፍ/ቤቱ የገለፁ ሲሆን፤ በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ በመቅረብ ሃሳባቸውን ሲገልፁ የነበሩትም የኢህአዴግን ጭቆናን ማጋለጥ መብታቸው በመሆኑ እንደሆነ ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡

4ኛ ተከሳሽ አቶ የሺዋስ አሰፋ በእሳቸው ላይ የቀረበ አንድም የሰው ምስክር እንደሌለ ገልፀው፤ ማዕከላዊ በነበሩበት ወቅትም በምርመራ ላይ አንድም ቀን ስለግንቦት ሰባት ተጠይቀው እንደማያውቁ ምርመራ ላይ ሲጠየቁ የነበሩትም ስለ ሰማያዊ ፓርቲ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ አቶ የሺዋስ የሰማያዊ ፓርቲ አባል በመሆናቸው ብቻ አያሌ መከራዎችን እየተጋፈጡ እንደሚገኙ ለፍ/ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ያለፉትን 6 ወራት በማንም አለመጎብኘታቸውን ለፍ/ቤቱ ገልፀዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የቃል ክርክሩ በፅሁፍ ተገልብጦ ከቀጣይ ቀጠሮ በፊት ከመዝገቡ ጋር ተያይዞ እንዲቀርብ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ 1ኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ አያሌው የሚገኙበት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ተከሳሹ ባቀረቡት አቤቱታ ላይ ታህሳስ 19 ቀን 2008 ዓ.ም መልስ እንዲሰጥ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ የማረሚያ ቤት ተወካዩ በተጠቀሰው ቀን አቶ ሀብታሙን ይዞ እንዲቀርብ ፍርድ ቤቱ አዟል፡፡

የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የግራ ቀኙን ክርክር መዝኖ ውሳኔ ለመስጠት ለታህሣሥ 29 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ እነ ሀብታሙ አያሌው ነሐሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ከተመሰረተባቸው የሽብርተኝነት ክስ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ውሳኔ ማስተላለፉ አይዘነጋም፡፡

አምስቱ የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ይግባኝ ተጠየቀባቸው

ባለፈው ሚያዝያ 2006 ዓ.ም. አጋማሽ ላይ በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ታስረው ፣ጉዳያቸው ለአንድ ዓመት ከ5 ወር በላይ ሲታይ ቆይቶ ከበፈቃዱ ኃይሉ በስተቀር ቀሪዎቹ “መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ” ተብሎ ከሁለት ወራት በፊት የተወሰነላቸው አምስቱ የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ይግባኝ ተጠየቀባቸው፡፡

የፌደራል ዐቃቤ ሕግ በአምስት የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች ላይ ባቀረበው ይግባኝ መሠረት ለቃል ክርክር ተዘጋጅተው እንዲቀርቡ የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የወንጀል ችሎት ማዘዙ ተሰምቷል፡፡

Federal court charge

ፍርድ ቤቱ በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ለሚከራከሩት አምስት የዞን ዘጠኝ አባላት መጥሪያውን ያወጣው ታህሣሥ 4 ቀን 2008 ዓ.ም ሲሆን፤ ለቃል ክርክር ቀነ-ቀጠሮ የሰጠው ለፊታችን ታህሣሥ 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ከጠዋቱ 2፡30 መሆኑን መጥሪያው ያስረዳል፡፡ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ መጥሪያው የደረሰው ለበፍቃዱ ኃይሉ ብቻ ሲሆን፤ በተሰጠው የቃል ክርክር ቀነ-ቀጠሮ እንዲቀርቡ መጥሪያ የወጣላቸው በፈቃዱ ኃይሉ፣ አጥናፍ ብርሃኔ፣ አቤል ዋበላ፣ ናትናኤል ፈለቀ እና በሌለችበት ክስ የተመሰረተባት ሶሊያና ሽመልስ መሆናቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

ከዚህ ቀደም፤ በፍቃዱ ኃይሉ የተቀየረለትን “አመፅ የማነሳሳት” የወንጀል አንቀፅ ለመከላከል ለጥር 30 ቀን 2008 ዓ.ም. መቀጠሩ አይዘነጋም።

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ታሰረ

የነገረ ኢትዮጵያ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ዛሬ ታህሣሥ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት ለስራ ከቤቱ ሲወጣ በፌደራል ፖሊሶችና በደህንነት ሰዎች ተይዞ ታስሯል። የፀጥታ ኃይሉ መኖሪያ ቤቱን ከፈተሹ በኋላ ፣ጋዜጠኛውን ወደ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ማዕከል ማዕከላዊ መስደው ማሰራቸው ቢገለፅም፤ መንግሥት ጋዜጠኛውን ለምን እንዳሰረ የገለፀው ነገር የለም፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው የነገረ ኢትዮጵያ ዋና አዘጋጅ ከመሆኑ በተጨማሪ የእንቁ መፅሔትም ፀሐፊ እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን፤ ከዚህ በፊት በመንግሥት ኃይሎች ከፍተኛ ማስፈራሪያና ዛቻ ይፈፀምበት እንደነበርም ታውቋል፡፡ጌታቸው ነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣን እና ደረ- ገፅን ጨምሮ በተለያዩ ድረ-ገፆችና የራሱ ማኀበራዊ ገፅ ላይ የተለያዩ ሐሳቦችን ይፅፍ እንደነበርም ይታወቃል፡፡

ከጋዜጠኛ ጌታቸው በተጨማሪ በተደጋጋሚ ሲታሰሩና ሲፈቱ የነበሩት ሶስቱ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት መካከል ዳንኤል ተስፋዬ፣ ኤርምያስ ፀጋዬ እና ቴዎድሮስ አስፋው ዛሬ መታሰራቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡

Getachew Shiferaw

በተመሳሳይ ዜና ባለፈው ቅዳሜ ታህሣሥ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት አዲስ አበባ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቱ በፀጥታ ኃይሎች ተይዞ የታሰረውና የኦሮሚያ ሬዲዮናቴሊቪዥን ዜና አንባቢ ጋዜጠኛ ፈቃዱ ምረከና አለመፈታቱ ታውቋል፡፡ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ ጋዜጠኛ ፈቃዱ ምርከናም ሆነ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በምን ምክንያት እንደታሰሩ ከመንግሥት በኩል የተገለፀ ነገር የለም፡፡

Fekadu Mirkena

ከጋዜጠኛ ፈቃዱ እና ጌታቸው በተጨማሪ በርካታ ጋዜጠኞች በእስር ላይ እንደሚገኙና በዓለም አቀፍ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋቾች ድርጅቶች፤ ኢትዮጵያም ጋዜጠኞችን በማሰር ከአፍሪካ የሁለተኛ ደረጃን ተቀዳጅታ እንደነበር አይዘነጋም፡፡

%d bloggers like this: