Monthly Archives: July, 2017

ፖሊስ በወልቃይት ኮሚቴዎች ላይ አንድ ምስክር ለማቅረብ የበጀት እጥረት ገጥሞኛል አለ

በጌታቸው ሺፈራው
• ‹‹ደንበኞቻችን እየተንገላቱ ነው›› ጠበቆች

Wolkayet Committee

በእስር ላይ የሚገኙ የወልቃይት ኮሚቴ አባላት በከፊል

የፌደራል ፖሊስ በሽብር ተከሰው ጉዳያቸውን በፍርድ ቤት እየተከታተሉ የሚገኙት የወልቃይት ኮሚቴ አባላት ላይ በተደጋጋሚ ያልቀረበውን አንድ ምስክር አስሮ እንዲያቀርብ በፍርድ ቤት ታዞ የነበር ቢሆንም ምስክሩ የሚኖረው ትግራይ ክልል በመሆኑ እና በጀት ስላልተለቀቀልኝ ምስክሩን አስሮ የሚያመጣ አባል መላክ አልቻልኩም ሲል ዛሬ ሐምሌ 18 ቀን 2009 ዓ.ም ለከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አራተኛ ወንጀል ችሎት መልሱን በደብዳቤ ገልፆአል።

አቃቤ ህግም ፍርድ ቤቱ ፖሊስ አጋጠመኝ የሚለውን ችግር ከግምት ውስጥ በማስገባት ምስክሩን ይዞ እንዲያቀር ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቆአል። በሌላ በኩል የተከሳሽ ጠበቆች ደንበኞቻቸው እስር ቤት ከመሆናቸውም ባሻገር ፖሊስ ያቀረበው ምክንያት ተቀባይነት የሌለው በመሆኑ ምስክሩ ታልፎ ለብይን እንዲቀጠርላቸው ጠይቀዋል። አቃቤ ህግ ለመመስከር የሚመጡትን ምስክሮች አልፈልጋቸውም ብሎ እያሰናበተ፣ የማይገኝና የሌለ ምስክር አመጣለሁ በማለት ደንበኞቻቸውን እያንገላታ መሆኑን ለፍርድ ቤቱ አስረድተውታል።

‹‹ትግራይ ኢትዮጵያ ውስጥ ነው። በአከባቢው የክልሉ ፖሊስ አለ። ፖሊስ ምስክሩን ማቅረብ ቢፈልገግ በቀላሉ ማቅረብ ይችላል ነበር።›› ሲሉ ፖሊስ ሆን ብሎ በደንበኞቻቸው ላይ በደል እየፈፀመ እንደሆነ ገልፀዋል። አቃቤ ህግና ፖሊስ ቀጠሮ በማራዘም ደንበኞቻቸው ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት እየፈፀሙ ነው ያሉት ጠበቆቹ ‹‹የታሰረው ሰው ነው። ሰውን እስር ቤት አስቀምጠው ምስክሩን ለማቅረብ በጀት የለንም ማለት የተከሳሾችን ሰብአዊ መብት መጣስ ነው። የቀረበው ምክንያትም አሳማኝ ባለመሆኑ ምስክሩ ይታለፍ›› የሚል አቤቱታ አቅርበዋል።

ይሁንና ፍርድ ቤቱ ፖሊስ የሰጠውን ምክንያት ታሳቢ አድርጌያለሁ በሚል የመጨረሻ ቀጠሮ ሰጥቶአል። እነ መብራቱ ለአራተኛ ጊዜ ለምስክር ተቀጥረው ምስክሩ ከመቅረቱም በተጨማሪ የዛሬው ቀጠሮ ለመጨረሻ እንዲሆን እና ፖሊስ ምስክሩን አስሮ ማምጣት ካልቻለ ምስክሩ ታልፎ መዝገቡ ተመርምሮ ብይን ለመስጠት ሊቀጠር ይገባ እንደነበር ገልፀዋል። ፖሊስ በበጀት ምክንያት ማቅረብ አልቻልኩም ያለውን ቀሪ አንድ ምስክር ለመስማት ለነሐሴ 11 ቀን 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

በሽብር የተከሰሰው ወጣት ህክምና ተከልክሎ እንደሞተ ተገለፀ

በጌታቸው ሺፈራው

• ‹‹አውቀው ነው የገደሉት፡፡ እኛንም ይገድሉናል!›› 1ኛ ተከሳሽ መልካሙ ክንፈ
• ‹‹ይህን የሚያደርገው መንግስት ከሆነ ቁርጡን አውቀነው እንሞታለን!›› 4ተኛ ተከሳሽ ይማም መሃመድ

Ayele Beyene

አቶ አየለ በየነ

በእነ መልካሙ ክንፈ የክስ መዝገብ በሽብር ተከሶ ቂሊንጦ እስር ቤት ታስሮ የነበረው ወጣት አየለ በየነ ነገሰ ህክምና እንዳያገኝ ተከልክሎ እንደሞተ ተገለፀ፡፡ ወጣት አየለ በየነ ህክምና ተከልክሎ ለሞት እንደተዳረገ በአባሪነት የተከሱት ዛሬ ሀምሌ 18/2009 ዓ.ም ለከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4 ወንጀል ችሎት ገልፀዋል፡፡
ተከሳሾቹ የፀረ ሽብር አዋጁ ከሚፈቅደው አራት ወር በተጨማሪ 5 ወር በአጠቃላይ 9 ወራትን ማዕከላዊ ታስረው እንደቆዩ የተገለፀ ሲሆን ሟች ለረዥም ጊዜ ታሞ ህክምና ቢጠይቅም ህክምና ሳይገኝ ቀርቷል ተብሏል፡፡ ህመሙ ከጠናበት በኋላም ከ10 ቀን በላይ ምግብ መብላት ባለመቻሉ ለእስር ቤቱ አስተዳደሮች በቀን ከሶስት ጊዜ ባላይ ህክምና እንዲያገኝ ጥያቄ ቢያቀርቡም መልስ ሳያገኙ መቅረታቸውንና በመጨረሻ ከእስር ቤቱ ውጭ እንዲታከም ቢታዘዝለትም በተቋሙ ቶሎ ህክምና ማግኘት ባለመቻሉ ህይወቱ ማለፉን ተከሳሾቹ ለፍርድ ቤቱ ገልፀዋል፡፡
ቀሪዎቹ ተከሳሾችም ህክምና ሊያገኙ ባለመቻላቸው ለህይወታቸው እንደሚሰጉ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታቸው አሰምተዋል፡፡ 1ኛ ተከሳሽ መልካሙ ክንፈ ታሞ በየወሩ ህክምና እየወሰደ የነበር ቢሆንም መርማሪዎች የፈለጉትን መረጃ ስላልስጠ ህክምና መከልከሉንና የሟች እጣፈንታ ሊደርስበት እንደሚችል ስጋቱን ለፍርድ ቤት ገልፆአል፡፡ ‹‹አውቀው ነው የገደሉት፡፡ እኛንም ይገድሉናል፡፡›› ያለው 1ኛ ተከሳሽ ንፁህ በመሆናቸውና መረጃ ስላልተገኘባቸው ህጉ ከሚፈቅደው ውጭ ለ9 ወራት ማዕከላዊ መቆየታቸው ይህም ለንፁህነታቸው ማስረጃ እንደሆነ ገልፆአል፡፡ ማች ንፁህ በመሆኑም ክሱ እንዳይቋረጥ፣ ምስክሮችም ተሰምተው የፍርዱን ሂደት ማወቅ እንደሚፈልጉ ገልጾአል፡፡
ሌሎች ተከሳሾም ተመሳሳይ ችግር እንደገጠማቸው የተገለፀ ሲሆን 4ኛ ተከሳሽ ይማም መሃመድ ‹‹ይህን የሚያደርገው መንግስት ከሆነ ቁርጡን አውቀነው እንሞታለን›› ሲል ገልፆአል፡፡ ‹‹አየለን ሞተ ማለት አልችልም፡፡ ተቀጠፈ ነው የምለው፡፡ የሞተው ዘመድ አጥቶ አይደለም፡፡ ጓደኛና ቤተሰብ አጥቶ አይደለም፡፡ የሞተው ህክምና የሚሰጠው አጥቶ ነው›› ሲልም አክሏል፡፡
ባለፉት ቀጠሮዎች ሟችን ፍርድ ቤት ሳያቀርብ የቀረውን ቂሊንጦ እስር ቤት ፍርድ ቤቱ ተከሳሹን የማያቀርብበትን ምክንያት እንዲገልፅ ወይንም ተከሳሹን እንዲያቀርብ በጻፈለት ትዕዛዝ መሰረት ሀምሌ 17/2009 ዓ.ም ተከሳሽ መሞቱን ቢገልጽም በምን ምክንያት እንደሞተ እንዳልገለፀ ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ቂሊንጦ ሟች በምን እንደሞተና ለሞቱ ማረጋገጫ ባልላከበት ሁኔታ ግለሰቡ መሞቱን እርግጠኛ መሆን ስለማይቻል እስር ቤቱ ለሀምሌ 26/2009 ዓ.ም ተከሳሹ ስለመሞቱ የሚያሳይ ማረጋገጫና የሞተበትን ምክንያት እንዲያመጣ ሲል ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
አየለ በየነ በመዝገቡ ስር 2ኛ ተከሳሽ የነበር ሲሆን ከኦነግ መሪ ዳውድ ኢብሳ ጋር ግንኙነት በመፍጠር እና ሀገር ውስጥ ያሉ መረጃዎችን ሪፖርት አድርጓል የሚል ክስ ቀርቦበት ነበር፡፡ የሟች ታናሽ ወንድም ቦንሳ በየነም በዚሁ ክስ መዝገብ ስር ክስ ተመስርቶበታል፡፡ በመዝገቡ ስር፡-
1.መልካሙ ክንፉ ተፈሪ
2. አየለ በየነ ነገሰ
3. ቦንሳ በየነ ነገሰ
4. ይማም መሃመድ ኬሮ
5. ለሜሳ ግዛቸው አባተ
6. ኩመራ ጥላሁን ዴሬሳ
7. መያድ አያና አቶምሳ
8. ሙሉና ዳርጌ ሩዳ የተከሰሱ ሲሆን ተመሳሳይ ችግር እየደረሰባቸው እንደሆነ ተገልፆአል፡፡

በኢትዮጵያ ወቅታዊ የሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ

1. የመሬት መብት ተሟጋቹ ኦሞት አግዋ ቀሪ መከላከያ ምስክራቸውን ያሰሙት ባሳለፍነው ሰኔ ወር ነበር፡፡

የመሬትና አካባቢ ጥበቃ አክቲቪስት ኦሞት አግዋ ሰኔ 05 ቀን 2009 ዓ.ም ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ቀርበው ቀሪ ሁለት የመከላከያ ምስክሮችን አስደምጠዋል፡፡ ምስክሮቹ በእስር ላይ የሚገኙት የቀድሞው የጋመቤላ ክልል ፕሬዝዳንት ኦኬሎ አኳይ እና አቶ ሳምሶን አባተ የተባሉ ምስክር ናቸው፡፡

ምስክሮቹ በዋናነት ኦሞት አግዋን የሚያቋቸው በ1996 ዓ.ም ጋምቤላ ክልል በተነሳ ግጭት በክልሉ መንግስት በተቋቋመ የሰላም ኮሚቴ ውስጥ አባል ሆነው ግጭቱን ለማብረድና ግጭቱን በመሸሽ የተሰደዱ ዜጎችን ለማስመለስ መልካም ስራ መስራታቸውንና ተከሳሹ “የጋምቤላ ሰለምና ልማት ጉባኤ” የሚባል ምግባረ ሰናይ ድርጅትም መስርተው ሲሰሩ እንደሚያውቁ አስረድተዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ቀሪ ሦስት የተከሳሽ መከላከያ ምስክሮችን ከዝዋይ እና ሸዋ ሮቢት የፌደራል እስር ቤቶች ሲቀርቡ ለመስማት በሚል ለሐምሌ 20 ቀን 2009 ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።

2. የኦፌኮ አባላትና አመራሮች እነ ጉርሜሳ አያና ላይ ይሰጣል የተባለው ብይን አሁንም በቀጠሮ መጓተቱ ቀጥሏል

የሽብር ክስ በቀረበባቸው የኦፌኮ አመራሮችና አባላት እነ ጉርሜሳ አያኖ (በቀለ ገርባ) መዝገብ ላይ ሰኔ 9 ቀን 2009 ዓ.ም ብይን ለማሰማት የመጨረሻ ቀጠሮ ተሰጥቶ የነበር ቢሆንም ብይኑ ‹‹ተሰርቶ አላለቀም›› በሚል ሌላ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

ለብይን በሚል ቀጠሮ እየተሰጠባቸው አራት ወራት ያህል ያስቆጠሩት እነ ጉርሜሳ አያኖ (22 ሰዎች)፣ ብይኑን ትሰማላችሁ ተብለው ለሰኔ 15 ቀን 2009 ቀጠሮ ቢሰጣቸውም በዕለቱ ቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር ተከሳሾቹን ፍርድ ቤት ሳያቀርባቸው ቀርቷል፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ እንደገና ተከሳሾች ባልቀረቡበት ሁኔታ ለሐምሌ 06 ቀን 2009 ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

3. በእነ ንግስት ይርጋ መዝገብ የአቃቤ ህግ ምስክሮች ባለመቅረባቸው ተከሳሾች በቀጠሮ እየተጉላሉ ነው

በአክቲቪስት ንግስት ይርጋ የክስ መዝገብ በሽብር የተከሰሱት ተከሳች ላይ አቃቤ ህግ አሉኝ የሚላቸውን ምስክሮች ባለማቅረቡ በተደጋጋሚ ቀጠሮ ተከሳሾች መጉላላት ላይ ይገኛሉ፡፡ ሰኔ 20 ቀን 2009 ዓ.ም ቀሪ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ችሎት ቀርበው የነበሩት ተከሳሾች ምስክር ሳይሰማባቸው እንደገና ምስክር ለመጠባበቅ ለሐምሌ 11 ቀን 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

ተከሳሾች በተደጋጋሚ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ቀጠሮ መሰጠቱን በመቃወም አቤቱታ አሰምተዋል፡፡ በዚህም 5ኛ ተከሳሽ የሆነው በላይነህ አለምነህ “እኛ የታሰርነው እና ድርጊቱ ተፈፀመ የተባልነው ባህርዳርና ጎንደር ቢሆንም ምስክር እየተጠበቀ ያለው ግን ከአዲስ አበባ ነው፡፡ ይህ እንዴት ይሆናል? በባለፈው ቀጠሮ ምስክር ረጅም ቀጠሮ እየተሰጠን ያለው አቃቤ ህግ ምስክሮችን እስኪያሰለጥን ድረስ ነው ወይ ብለን አስተያየት ሰጥተን ነበር፡፡ ፍርድ ቤት አቃቤህ ግን ማዘዝ ከቻለ ለምንድነው ሃይ የማይለው?” ሲል ተናግሯል፡፡

4. ዶ/ር መረራ ጉዲና ያቀረቡት የመጀመሪያ ደረጃ የክስ መቃወሚያ ውድቅ ተደርጓል

*የምስክሮች ማንነት ይገለጽ በሚለው መቃወሚያ ላይ ብቻ ብይኑ አልተሰራም፤ ጉዳዩ ለህገ-መንገስታዊ ትርጉም ለፌደሬሽን ምክር ቤት ተልኳል ተብሏል፡፡

በፌደራል አቃቤ ህግ ሦስት የተለያዩ ክሶች የቀረቡባቸው የኦፌኮ ፕሬዚደንት ዶ/ር መረራ ጉዲና በቀረቡባቸው ክሶች ላይ ያቀረቡት የመጀመሪያ ደረጃ የክስ መቃወሚያዎች አብዛኞቹ ውድቅ ሲደረጉ አንዱ ብቻ ለህገ-መንግስታዊ ትርጉም ለፌደሬሽን ምክር ቤት መላኩን ሰኔ 30 ቀን 2009 ዓ.ም ጉዳዩን ለማየት የተሰየመው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት አስታውቋል፡፡

ዶ/ር መረራ መቃወሚያቸው ውድቅ መደረጉን ከችሎቱ ከሰሙ በኋል፣ ‹‹የተከሰስሁት ፖለቲካዊ ክስ ነው፡፡ እኔ የተከሰስሁት ለኦሮሞ ህዝብ፣ ለኢትዮጵያ ህዝቦች በመከራከሬ ነው፡፡ ይህንን እናንተ ዳኞችም፣ የኢትዮጵያ ህዝብም ያውቃል፡፡ እኔ የተከሰስሁት በሀገራችን ሀቀኛ ፌደራላዊ ስርዓትና ፍትህ እንዲሰፍን በመከራከሬ ነው›› ሲሉ አስተያየታቸውን አሰምተዋል፡፡

ችሎቱ የፌደሬሽን ምክር ቤት የተላከለትን የትርጉም ስራ ሰርቶ መላኩን ለመጠባበቅ በሚል ለሐምሌ 25 ቀን 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

5. ጋዜጠኞችና አርቲስቶች ሙዚቃና ግጥሞችን ዩ ቲ ዩብ ላይ ጭነዋል በሚል የሽብር ክስ ቀርቦባቸዋል

ሁከትና አመጽ የሚያስነሱ ዜና፣ ግጥምና ሙዚቃ በማዘጋጀት ዩ ቲ ዩብ ላይ እንዲጫን አድርገዋል በሚል ሰባት ሰዎች የሽብር ክስ የቀረበባቸው ባሳለፍነው ሰኔ ወር ነበር፡፡

በፌደራል አቃቤ ህግ ክሱ የተመሰረተባቸው ተከሳሾች ኦሊያድ በቀለ፣ ኢፋ ገመቹ፣ ሞይቡሊ ምስጋኑ፣ ቀነኒ ታምሩ፣ ሃይሉ ነጮ፣ ሴና ሰለሞን እና ኤልያስ ክፍሉ ናቸው፡፡ አቃቤ ህግ ተከሳሾችን የጸረ-ሽብር አዋጁን አንቀጽ 4 መተላለፍ ክስ ያቀረበባቸው ሲሆን፣ ተከሳሾቹ ሰኔ 23 ቀን 2009 በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19 ወንጀል ችሎት ቀርበው ክሱ ተነቦላቸዋል፡፡

6. ሁለት ጋዜጠኞች የእስር ጊዜያቸውን ጨርሰው ባሳለፍነው ሰኔ ወር ከእስር ተፈተዋል

የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው እና የኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ አዘጋጅና ባለቤት ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ የተበየነባቸውን የእስር ቅጣት አጠናቀው ከእስር ተፈተዋል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው አመጽ በማነሳሳት ጥፋተኛ ተብሎ የተበየነበትን የአንድ አመት ከስድስት ወር እስሩን ጨርሶ ከቃሊቲ እስር ቤት የተፈታው ሰኔ 16 ቀን 2009 ዓ.ም ሲሆን፣ በስም ማጥፋት ክስ የአንድ አመት እስር ተበይኖበት የነበረው ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ ደግሞ በአመክሮ ከሸዋሮቢት እስር ቤት የተፈታው ባሳለፍነው ሳምንት ነው፡፡

ምንጭ፦ ኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት

የዶ/ር መረራ ጉዳይ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ትርጉም እንዲሰጥበት ትእዛዝ ተሰጠ

የእነ ዶ/ር መረራ ጉዲና መዝገብ ለዛሬ የተቀጠረው ከዚህ ቀደም በቀረበው መቃወሚያ ላይ ብይን ለመስጠት ነበር። በመሆኑም ዛሬ – ሰኔ 30/2009 – ዶ/ር መረራ ጉዲና በተመሰረተባቸው 3ት ክሶች ላይ ያቀረቧቸው መቃወሚያዎች ላይ 19ኛው ወንጀል ችሎት ከፊል ብይን ሰጥቶበታል። ችሎቱ፣ ዶ/ሩ ያቀረቡትን ክሱ እንዳይንጓተት ከሌሎቹ በሌሉበት ከተከሰሱት ሶስት ተከሳሾች ይነጠልልኝ የሚለውን መቃወሚያ ጨምሮ ሌሎቹን መቃወሚያዎች በሙሉ ውድቅ ሲያደርግ አንዱን ግን ለትርጉም ወደ ፌደሬሽን ምክር ቤት ለትርጉም መላኩን ተናግሯል።

dr-merera-gudina-aau

ዶ/ር መረራ ጉዲና

በእነዶ/ር መረራ መዝገብ የተከፈተው ክስ ላይ አቃቤ ህግ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጁን በመጥቀስ፣ የምስክሮች ሥም ሳይጠቀስ የቀረ ሲሆን፣ ይህ በሥራ ላይ ያለው የሥነ ስርዓት ሕግ ተከሳሾች የሚቀርብባቸውን ማስረጃ እና ምስክር የማወቅ መብት አላቸው ከሚለው ጋር የሚጋጭ በመሆኑ እንዲተረጎም ወደፌዴሬሽን ምክር ቤት ተልኳል። የተከሳሹ ጠበቃ አቶ ወንድሙ ኢብሳ በበኩላቸው “እኛ የጠየቅነው፣ ደንበኛችን ባልተከሰሱበት የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ የምስክር ጥበቃው አንቀፅ ሊጠቀስባቸው አይገባም ብለን እንጂ ትርጉም ያስፈልጋል ብለን አይደለም” ብለው ቅሬታቸውን አቅርበዋል።

ዶ/ር መረራም መልእክት አለኝ በማለት የሚከተለውን ለዳኞች ተናግረዋል፣ “የተመሰረተብኝ ፖለቲካዊ ክስ ነው። መንግስት ይዞ የተነሳው ተቃዋሚዎችን በራሱ የተበላሸ አስተዳደር ጥፋት ጉዳይ መወንጀል ስለሆነ እንጂ መንግሥት የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ በጠየቀበት ጉዳይ ነው የተከሰስኩት። የተከሰስኩት፣ ለኦሮሞ ሕዝብ መብት በመታገሌ ነው። የተከሰስኩት ለኢትዮጵያ ሕዝብ መብት በመታገሌ ነው። የተከሰስኩት ለእኩልነት እና ሁላችንንም እኩል ለሚመለከት ስርዓት በመታገሌ ነው። የተከሰስኩት ሀቀኛ የፍትህ ስርዓትና የፌዴራል ስርዓት እንዲኖር በመታገሌ ነው። ዳኞች እስካሁን ካላነበባችሁ፣ የአቤ ጉበኛን አልወለድም እና የበአሉ ግርማን ኦሮማይ አንብቡ። ሊወድቅ እየደረሰ መንግስት የሚሰራውን ሥራ የሚያስረዱ መፅሃፍት ናቸው።”

ዳኞች መዝገቡን ለሐምሌ 25/ 2009 የተቀጠሩ ሲሆን፤ በሚቀጥለው ቀጠሮ ችሎቱ የምስክሮች ዝርዝር መገለፅ አለበት በሚል ክሱ እንዲሻሻል ወይም የለበትም በሚል የቃቤ ሕግ ምስክሮችን ለማድመጥ ቀጠሮ ይይዛል ተብሎ ይጠበቃል።

EHRP

የኦሮሚያ ክልልን ልዩ ጥቅም ለመወሰን የወጣው ረቂቅ አዋጅ ከሕገ መንግሥቱ አንጻር ሲቃኝ

Wuobishet Mulat

ውብሸት ሙላት

በዚህ ዓመት የሚጸድቁት ዋና ዋና አዋጆችን የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ክቡር ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ የሕዝብ ተወካዮች እና የፌደሬሽን ምክር ቤቶች የ2009 ዓ.ም. የሥራ ዘመናቸውን ሲጀምሩ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር ላይ አሳውቀዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የምርጫ ሕጉና የኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ላይ የሚኖረውን ልዩ ጥቅም የሚመለከቱት ከሚወጡት ውስጥ እንደሚሆኑ ገልጸዋል፡፡

የምርጫ ሕጉን በተመለከተ እስካሁን ለሕዝብ የደረሰ ነገር የለም፡፡ የኦሮሚያ ልዩ ጥቅምን በተመለከተ ግን የበርካታ ሰውን ትኩረት የሳበ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ከዚህ አንጻር የመንግሥት አይደሉም የተባሉ ረቂቅ አዋጅና የጥናት ሰነዶች በማኅበራዊ ሚዲያ መሠራጨታቸውም ይታወሳል፡፡ በያዝነው ሳምንት ደግሞ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የተዘጋጀና የጸደቀ ረቂቅ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም ለሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴዎች የመራው መሆኑን ተዘግቧል፡፡ ለወትሮው ከሚወጡት ሕጎች ለየት ባለ መልኩ ረቂቁን የሚመለከት ዘለግ ያለ የሚኒስትሮች ምክር ቤት መግለጫ ተሰጥቷል፡፡

ሕገ መንግሥቱ ጸድቆ ሥራ ላይ ከዋለ ሃያ ሁለት ዓመታት ሊሆነው ሁለት ወራት የማይሞሉ ጊዜያት ቢጎድሉትም፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 49 ንዑስ አንቀስ 5 ላይ የሰፈረውና ዝርዝሩ በሌላ ሕግ እንደሚወሰን ተስፋ የተጣለበት፣ ክልሉ በአዲስ አበባ ላይ የሚኖረው የኦሮሚያ ልዩ ጥቅም ‘ጃሮ ዳባ ልበስ’ ተብሎ ኖሮ ገና በዚህ ዓመት ሕግ ሊወጣለት ነው፡፡ ለረቂቅ አዋጁ መነሻ የሆነው የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ የሚከተለው ነው፡፡

“የኦሮሚያ ክልል የአገልግሎት አቅርቦት ወይም የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምና የመሳሰሉትን ጉዳዮች በተመለከተ እንዲሁም አዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል መሐል የምትገኝ በመሆኗ የሚነሱ ሁለቱን የሚያስተሳስሩ አስተዳደራዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ያለው ልዩ ጥቅም ይጠበቅለታል፡፡ ዝርዝሩ በሕግ ይወሰናል” ይላል፡፡
ይኽ ጽሑፍ ከላይ የተገለጸውን ሕገ መንግሥታዊ አንቀጽ ተመርኩዞ የወጣው ረቂቅ አዋጅ ላይ ምጥን ቅኝት ያደርጋል፡፡ ዋና ትኩረቱም የኦሮሚያ ክልል ልዩ ጥቅሞች ተብለው በሕገ መንግሥቱ ላይ የተቀመጡት ሐረጋትን በአጠቃላይ ከሕገ መንግሥቱ መንፈስ ላይ በመመርኮዝ ረቂቅ አዋጁን መፈተሽ ነው፡፡ በመሆኑም፣በረቂቁ ላይ የተቀመጡ ግልጽነት የጎደላቸውን፣ዘርዘር ማለት የሚያስፈልጋቸውን፣መካተት ሲገባቸው ያልተካተቱ ጉዳዮችን እና በልዩ ጥቅም ሥር ሊወድቁ የማይችሉ ነጥቦችን ይመለከታል፡፡ ስለሆነም፣የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ያላቸውን መብት የዚህ ጽሑፍ አካል አይደለም፡፡

ረቂቁ በአጭሩ ፤
ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው ረቂቅ አዋጅ በ25 አንቀጾች እና በአራት ክፍሎች ተቀነብቦ በአጭሩ የቀረበ ነው፡፡ በረቂቅ አዋጁ መሠረት የኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ከተማ ላይ በሦስት ክፍል የተቀመጡ ልዩ ጥቅሞች ይኖሩታል።

የመጀመሪያው ከአገልግሎት አቅርቦት ጋር የተያያዘ ልዩ ጥቅም ነው፡፡ በመሆኑም፣ ልጆቻቸውን በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው ማስተማር ለሚፈልጉ የኦሮሞ ብሔር ተወላጆች የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በአፋን ኦሮሞ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት የማደራጀት ግዴታ አለበት።

አዲስ አበባ ወይም ፊንፊኔ የኦሮሚያ ክልል ዋና ከተማ በመሆኗ በከተማዋ የሚሰጠው የጤና አገልግሎት በከተማዋ ዙሪያ ያሉ የክልሉ ተወላጆችን ታሳቢ ያደረገ ይሆናል፤ ከዚህ ባለፈም ከአማርኛ በተጓዳኝ አፋን ኦሮሞ በከተማ አስተዳደሩ የሥራ ቋንቋ ሆኖ እንደሚያገለግል ተገልጿል።

የኦሮሞ ሕዝብን ማንነት የሚያንጸባርቁ አሻራዎች በከተማዋ በቋሚነት እንዲኖሩ በከተማዋ፥ አደባባዮች፣ ጎዳናዎች፣ ሠፈሮች እና የመሳሰሉት ቦታዎች እንደ አስፈላጊነቱ በቀድሞ የኦሮሞ ስማቸው ሊጠሩ እንደሚችሉ በረቂቁ ላይ ተቀምጧል።

የከተማው አስተዳደርም የኦሮም ሕዝብን ባህልና ታሪክ የሚያንፀባርቁ የባህልና ታሪክ ማዕከላት፣ ቲያትር፣ ኪነ ጥበባትና የመዝናኛ ማዕከላት የሚገነቡበትና የሚተዋወቁበትን ሁኔታ የማመቻቸት ግዴታ ተጥሎበታል። እንዲሁም፣ የከተማዋ መጠሪያዎች “ፊንፊኔ” እና “አዲስ አበባ” በሕግ ፊት እኩል ተቀባይነት እንዳላቸው በረቂቁ ላይ ሰፍሯል።

ከተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም አንጻር ደግሞ በረቂቁ ላይ የተካተቱት ሦስት ፈርጆች አሏቸው፡፡ የመጀመሪያው የኦሮሚያ ክልል እና የኦሮሞ ብሔር ተወላጆች ከአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር የሚያገኛቸው የሚመለከቱ ናቸው፡፡

በዚህም መሠረት፣ የኦሮሚያ ክልል መንግሥት የተለያዩ መንግሥታዊ ሥራዎች እና ሕዝባዊ አገልግሎቶች መስጫ የሚውሉ ሕንጻዎች የሚሠሩበትን መሬት የከተማው መስተዳድር ከሊዝ ነጻ እንዲያገኙ ይደረጋል። በአዲስ አበባ ጋር በተያያዘ በዙሪያ ያሉ ወጣቶች በተቀናጀ ሁኔታ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ ሁኔታዎችን የማመቻቸት ሌሎች በአዲስ አበባ ዙሪያ ባሉት አካባቢዎች አዲስ አበባ የሚሠራቸው ሥራዎች ለዙሪያ ወጣቶች የሥራ ዕድል የማመቻቸት ግዴታ ተጥሎበታል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም፣ በግብርና ሥራ የሚተዳደሩ አርሶ አደሮች በተደራጀ መለክ ምርቶቻቸውን የሚሸጡባቸውን የገበያ ማዕከላት አቋቁሞ ለአርሶ አደሮች እና ማኅበሮቻቸው ያቀርባል።

ከዚህ በተጨማሪም በከተማው የሚኖሩ የኦሮሚያ ክልል ሠራተኞች በመንግሥት ወጪ ከሚገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የማገኘት አርሶ አደሩ ለልማት ተነሺ ሲሆን፥ በቂ ካሳ የማግኘትና በዘላቂነት የማቋቋም ግዴታ ይኖርበታል፡፡ የካሳና የማቋቋሙ ጉዳይ ከአሁን በፊት የተነሱትም ሊጨምር ሊጨምር ይችላል፡፡
በሁለተኛው ፈርጅ የሚካተቱት ደግሞ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር ከኦሮሚያ ክልል (በተለይም በዙሪያው ከሚገኘው ዞን) የሚያገኛቸውን የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም የሚመለከት ነው፡፡ ከዚህ አኳያ፣ ለአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች የመጠጥ ውሃ፣ ለከተማው ልማት የግንባታ ማእድናት ማግኛ ሥፍራዎች ሊኖሩ ስለሚችሉ የአየር ብክለት እንዳያስከትሉ እና ለደን ልማት ወይም ለሌሎች ልማቶች መዋል እንዲችሉ እንዲያገግሙ የማድረግ ኃላፊነት አለበት፡፡ ለአዲስ አበባ ከተማ የደረቅና ፍሳሽ ቆሻሻ ማከሚያና ማስወገጃ ቦታዎች እንዲሁም መልሶ መጠቀሚያ ስፈራዎች አስተዳደሩና ክልሉ በጋራ ባጠኗቸወ ቦታዎችና ሳይንሳዊ መስፈርቶችን ባሟሉ ሁኔታዎች እንዲተዳደሩ እንደሚደረግ ረቂቁ ስለሚያመለክት የማዕድናት ማውጫ ቦታ እና የቆሻሻ ማስወገጃ እና ማከሚያ ቦታ ክልሉ ያቀርባል ማለት ነው፡፡

በሦስተኝነት የምናገኛቸው የከተማ መስተዳድሩ በራሱ ድንበር ውስጥ በሚያከናውናቸው ተግባራት ምክንያት በዙሪያው ባሉ ነዋሪዎች የሚደርሰውን የጎንዮች ጉዳት በተመለከተ እና በተለይም የውሃ አቅርቦት ከሚያገኝበት አካባቢ ለሚኖረው ሕዝብ የሚኖረበትን ግዴታ የሚመለከት ነው፡፡ በአጭሩ ከአካባቢ ጥበቃ እና ውሃ ለወጣበት ወይንም ለሚያልፍበት አካባቢ ንጹህ የመጠጥ ውሃ ከማዳረስ ግዴታን የሚመለከት ነው፡፡
በዚህም መሠረት በመስተዳድሩ ዙሪያ ባሉ ከተሞችና ቀበሌዎች ደህንነቱ ሳይጠበቅና ቁጥጥር ሳይደረግበት በሕግ ከተቀመጠው ደረጃ በላይ ወደ ክልሉ በተጣሉ ወይም በፈሰሱ ቆሻሻዎች ምክንያት በሰው፣ በእንስሳትና በተፈጥሮ አካባቢ ላይ ለደረሰው ጉዳት በሕግ አግባብ ከአስተዳደሩ ካሳ የማግኘት መብት እንዳለቸው ረቂቁ ይገልጻል፡፡ የመጠጥ ውሃን በተሚመለከት ደግሞ የከተማ መስተዳድሩ በአብዛኛው ውሃ የሚያገኘው ከኦሮሚያ ክልል በመሆኑ ጉድጓዱ የሚቆፈርበት፣ ግድብ የሚለማበት ወይም የውሃ መስመሩ አቋርጠው የሚያልፍባቸው የክልሉ ከተሞችኛ አና ቀበሌዎች ለሚኖሩ ነዋሪዎች በአስተዳደሩ ወጪ የመጠጥ ዉሃ የማቅረብ ግዴታ አለበት፡፡

አዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል የተከበበች በመሆኑ፣የተቀናጀ የትራንስፖርት አገልግሎትም መሥጠት ይጠበቅባታል፡፡ ከላይ የተገለጹትን ልዩ ጥቅሞች ለማስፈጸም የሚገለግል አንድ ተቋም ከከተማው መስተዳድር እና ከክልሉ ምክር ቤት በእኩል ቁጥር የተወከሉ ሰዎች የሚገኙበት ተጠሪነቱ ለፌደራል መንግሥት የሆነ ምክር ቤት እንደሚቋቋም ረቂቁ ላይ ተገልጿል፡፡ ረቂቅ አዋጁ በአጭሩ ከላይ የቀረበውን ይመስላል፡፡
በመቀጠል ሕገ መንግሥቱ “ልዩ ጥቅም” በማለት ቀድሞ የተቀመጠው ምን እንደሆነ እንመለከታለን፡፡
ሕገ መንግሥቱ ቀድሞ ያሰበው፤

ቀድመው በፌደራል ሥርዓት የማይተዳደሩ አገራት በተለይም ገና እንደ አዲስ ሲመሠረቱ ከሚያሳስቧቸው ጉዳዮች መካከል አንደኛው የዋና ከተማ ነገር ነው፡፡ በተለይም፣ ዋና ከተማው አንድን ክልል አላግባብ እንዳይጠቅም ወይንም እንዳይጎዳ ጥንቃቄ ማድረግን ይጠይቃል፡፡

በዚህም መሠረት፣ ከተማው ለሚገነባበት ወይንም በዋና ከተማነት የተመረጠው ቦታ ቅርብ የሚሆነው ክልል ወይንም ሌላ ከተማ፣ የበለጠ ተጠቃሚ መሆኑ እርግጥ ነው፡፡ ከዚህ አንጻር በምሳሌነት የአውስትራሊያን ብንወስድ ዋና ከተማዋ ሲዲኒ (የኒውሳውዝ ዌልዝ ክልል ዋና ከተማ) ወይንም ሜልቦርን (የቪክቶሪያ ክልል ዋና ከተማ) እንዳይሆን ያደረገችው እና ከሲዲኒ ከተማ ከመቶ ማይልስ ባላነሰ እርቀት ላይ እንዲቆረቆር የተወሰነው በዚሁ ምክንያት ነው፡፡

ዋና ከተማ የሚሆንበት ክልል ወይንም ቅርብ የሆነ ከተማ ውስጥ የሚገኙ ኗሪዎች በርካታ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ዕድሎች ይኖሯቸዋል፡፡ በሌላ ክልል ሊፈጠር የማይችል ዕድል እና ተጠቃሚነት ማለት ነው፡፡ አዲስ አበባ ዋና ከተማ በመሆኗ በአቅራቢያዋ ለሚገኙ ከተሞች ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳደረገችው ማለት ነው፡፡

ይሁን እንጂ፣ አዲስ አበባ ቀድማ የተቆረቆረች እና ዋና ከተማም የነበረች በመሆኗ በሽግግር ወቅቱ (ከ1983-1987 ዓ.ም.) ክልል 14 ተብላ ከሌሎች ክልሎች ጋር እኩል ሥልጣን የነበራት ብትሆንም፣ ሕገ መንግሥቱ የቀድሞውን አወቃቀር አልመረጠም፡፡ ይልቁንም፣ ተጠሪነቷ ለፌደራል መንግሥት እንዲሆን መርጧል፡፡ ሕገ መንግሥቱ ረቂቅ በነበረበት ወቅት ከተዘጋጀው ማብራሪያ መረዳት የሚቻለውም፣ አዲስ አበባ የበርካታ ዓለም ኣቀፍ ተቋማት መቀመጫ ስለሆነችና የፌደራሉም መንግሥት በራሱም ስለ ዓለም አቀፍ ተቋማቱም በአግባቡ ኃላፊነቱን መወጣት በሚያስችለው መንገድ መዋቀር የቀድሞው አወቃቀር የተቀየረ መሆኑን ነው፡፡

በተለምዶ፣ዋና ከተማ የሚሆነው ቀድሞ የነበረ እና የሕዝብ ቁጥሩም ከፍተኛ ከሆነ ሌላው ከተማው ቀድሞ የነበረና ትልቅ ሆኖ የኗሪውም ብዛት ከፍተኛ ከሆነ የኗሪውን መብቶች በሚገድብ መልኩ ርዕሰ ከተማ መቆርቆር ብዙም አልተለመደም፡፡ ለዚህ ጥሩ ምሳሌ የሚሆኑት ሞስኮ እና በርሊን ናቸው፡፡ በሩሲያ ከቀድሞው ዋና ከተማ ከሴንት ፒተርስበርግ ወደ ሞስኮ ሲዛወር፣ በጀርመን ደግሞ ከቦን ወደ በርሊን ሲቀየር ቀድመው የነበሩና በርካታ ሕዝብ ስለነበራቸው ከክልል ጋር እኩል ሥልጣን እንዲኖራቸው ተደርጓል፡፡ በመሆኑም ትልቅ ከተማ ሲሆኑ የክልልነት ደረጃ መስጠት የተለመደ ነው፡፡ የሕዝብ ቁጥሩ አናሳ ሲሆን ደግሞ ለማእከላዊው ተጠሪ ማድርግ የተለመደ ነው፡:

ይሁን እንጂ፣የኢፌዲሪ ሕገ መንግሥት የርእሰ ከተማዋን አስተዳደር በተመለከተ ተጠሪነቷ ለፌደራል መንግሥት ከመሆን በዘለለ በሌሎች አገራት ያልተለመደ ወይንም የተለየ መንገድ ተከትሏል፡፡ ይኼውም አዲስ አበባ የምትገኝበት ክልል ከከተማው የተለየ ጥቅም እንዲኖረው መደንገጉ ነው፡፡ ይህ ልዩ ጥቅም ምን እንደሆነ በግልጽ ባይቀመጥም ሕገ መንግሥቱ ሲጸድቅ ከነበረው ውይይት እና በቃለጉባኤ ከተያዘው የተወሰኑ ነጥቦችን መረዳት ይቻላል፡፡

በውይይቱ ወቅት በግልጽ ከተነሱት ጉዳዮች አንዱ በከተማ መስተዳድሩ ውስጥ ካሉ ፋብሪካዎች ወደ ኦሮሚያ ክልል ፍሳሽ በመልቀቅ ክልሉና ነዋሪዎች ላይ ሊደርስ የሚችለው ጉዳት ነው፡፡
ሁለተኛው ደግሞ፣ከተማዋ መስፋቷ ስለማይቀር በዙሪያው የሚኖሩ አርሶ አደሮች ላይ የሚደርሰው መፈናቀልን ጋር የተገናኘ እንደሆነ ተመልክቷል፡፡ እንዲሁም የከተማውን ዙሪያና ከተማውን በተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም እንደሚገናኝም ተወስቷል፡፡ ከአጽዳቂ ጉባኤያተኞች አንዱ የነበሩት፣ አቶ ተሰማ ጋዲሳ የተባሉ ግለሰብ ስለጉዳዩ ሲያስረዱ ከተማዋ የኦሮሚያ ክልልም ዋና ከተማ በመሆኗ መስተዳድሩ ለክልሉ ከተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም ባሻገር፣ የጽሕፈት ቤት አቅርቦትንና የመሳሰሉትን የሚመለከት እንደሆነ ገልጻዋል፡፡ ሌላው አስተዳደራዊ ጉዳዮችንም የሚመለከት ተነስቷል፤ምንም እንኳን ዝርዝር ነገር ባይኖረውም፡፡ የረቂቅ ሕገ መንግሥቱ ማብራሪያም ከቃለጉባኤው ጋር በይዘቱ ተመሳሳይ ነው፡፡

ስለሆነም፣የክልሉ ልዩ ጥቅም እንዲከበር መነሻ የሆነው፣ አዲስ አበባ ኦሮሚያ ውስጥ መገኘቷ፣ ከተማዋ ወደ ፊት የመስፋቷ ጉዳይ አይቀሬ መሆኑ፣ ከተማዋ ከክልሉ የተለያዩ የተፈጥሮ ሃብቶችን ማገኘቷ፣የክልሉ ዋና ከተማ መሆኗ እና በከተማ መስተዳድሩ ውስጥ የሚፈጸሙ የተለያዩ ድርጊቶች በክልሉ ነዋሪዎች ላይ ሊያደርሱት የሚችሉት ጉዳት መሆናቸውን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከእዚህ ሌላ፣ሕገመንግሥቱ ላይ “ማኅበራዊ አቅርቦትን” የሚል ሃረግ ስላለው ይህንን ትርጉም መሥጠት ያስፈልጋል፡፡
ከረቂቅ አዋጁ የምንረዳው የትምህርት፣የቋንቋ አጠቃቀም፣የሕክምና አገልግሎትን በሚያካትት መንገድ ተዘርዝሯል፡፡

በረቂቅ አዋጁ ላይ ከተካተቱት ውስጥ በተወሰነ መለክ ግለጽነት የሚጎድላቸው፣በጣም በጥቅሉ በመቀመጣቸው ዝርዝር መሆንን የሚጠይቁ፣በሌላ መልኩ ደግሞ በልዩ ጥቅም ውስጥ ያልታሰቡ ነገር ግን የተካተቱ እንዲሁም የአዋጁ አካል እንዲሆኑ የሚጠበቁ ነገር ሳይካተቱ የታለፉ ጉዳዮች ስላሉ በቅድም ተከተላቸው የተወሰኑትን እንመልከት፡፡

ግልጽነት የሚጎደላቸው ፤

በረቂቁ ላይ ከተቀመጡት እና የከተማ መስተዳድሩ በዙሪያው በሚገኘው ዞን ውስጥ ማከናወን ካለበት ተግባራት አንዱ “የተፋሰስ ልማት” ነው፡፡ የከተማ መስተዳድሩ የውሃ ጉድጓድ በሚቆፍርበት፣በሚያመነጭበት፣መስመሮቹ በሚያልፉበት አካባቢ የተፋሰስ ልማት በራሱ ወጭ የሚያከናውንበት ሁኔታ እንደሚያመቻች ተገልጿል፡፡ ይሁን እንጂ፣ የተፋሰስ ልማት ማለት የአካባቢው ቅርጽ እዳይቀየር ለማድረግ መልሶ መገንባት ነው? ወንዞችን ማጎልበት ነው? ደን መትከል ነው? ይዘቱ አይታወቅም፡፡
በተጨማሪም መስተዳድሩ “ያመቻቻል” ማለት ግዴታ አይደለም፡፡ እንዲህ ዓይነት አገላለጽ ኋላ ላይ ለማስፈጸም ያዳግታል፡፡

ከዚሁ ጋር መነሳት ያለበት ውሃ የሚወጣበት ወይንም የሚያልፍበት ከተማ፣ቀበሌ፣በአስተዳደሩ ወጪ ውሃ የማቅረብ ግዴታ የሚመለከተው ነው፡፡ ከገፈርሳ ለሚመጣው ውሃ፣ለቡራዩ ከተማ በሙሉ ማቅረብን ወይንስ ለሚገኝበት ቀበሌ ወይንስ መስመሩ የሚያልፍበትን አካባቢ የቱን እንደሚመለከት ግልጽነት ይጎድለዋል፡፡ ከገፈርሳ የሚነሳው ውሃ ጀሞ ወደ ሚባለው ሠፈር ቢሄድና በመካከል በሰበታ ከተማ የሚተዳደርን መንደር ቢያቋርጥ የከተማ መስተዳድሩ ውሃ የማዳረስ ግዴታው ለመንደሩ ወይንስ ለቀበሌው ወይንስ ለሰበታ ከተማ በሙሉ ነው?

ሌላው ግልጽ መሆን ያለበት ነገር በአዲስ አበባ ዙሪያ የሚገኙ ወጣቶች በከተማው ከሚፈጠረው የሥራ ዕድል መጠቀም እንዳለባቸው ቢገለጽም እንደማንኛውም ሠራተኛ እኩል ተወዳድረው ነው? ወይንስ በድጋፍ እርምጃ መልክ (Affirmative Action) መልክ ነው፡፡ በጥቃቅን እና አነስተኛ ማደራጀትን ይጨምራል ወይስ በቅጥር ብቻ ነው?

በረቂቁ ላይ ከተካተቱት በጎ ነጥቦች አንዱ አፋን ኦሮሞ በመስተዳድሩ ተጨማሪ የሥራ ቋንቋ እንዲሆን መወሰኑ ነው፡፡ ይሁን እንጂ፣ ሁለትና ከእዚያ በላይ ቋንቋዎች በአንድነት ሥራ ላይ ሲውሉ የሚፈጠር ችግር አለ፡፡ ይኸውም፣ መስተዳድሩ አገልግሎት ሲሰጥ አፋን ኦሮሞ አስተርጓሚዎችን በየመሥሪያ ቤቱ በመመደብ አልበለዚያም በአማርኛ አገልግሎት የሚሰጡ ሠራተኞች እንዳሉ ሁሉ በትይዩ እኩል በአፋን ኦሮሞ አገልግሎት የሚሰጡ ተጨማሪ የሠው ኃይል መቅጠር ይጠበቅበታል፡፡ ካልሆነም ደግሞ ሁለቱንም ቋንቋ ብቻ የሚችሉ መሆን አለባቸው ማለት ነው፡፡
እያንዳንዳቸው አማራጮች የራሳቸው ጥቅምና ጉዳት፣ መስተዳድሩንና ክልሉን ለግጭት ስለሚዳርጉ፣እንዲሁም የሕገመንግሥት ጥያቄም ስለሚያስነሱ በአዋጁ ላይ በምን ዓይነት ሁኔታ ሥራ ላይ መዋል እንዳለበት መቀመጥ ይገባዋል፡፡

ረቂቁ ላይ ከተቀመጡ የመስተዳድሩ ግዴታዎች አንዱ ለክልሉ አርሶ አደሮች የገበያ ማእከላት ማመቻቸትን የሚመለከት ነው፡፡ ይህ ድንጋጌ በርካታ ክፍተቶች አሉበት፡፡ የመጀመሪያው መስተዳድሩ ማዘጋጀት ያለበት ባዶ ቦታ ላይ (Open Market) ወይንስ ሕንጻ ነው የሚለው ሲሆን ቀጥሎ የሚመጣው ደግሞ ለክልሉ አርሶ አደሮች በሙሉ የመሆኑ ነገር ነው፡፡ በኦሮሚያ ክልል ለሚገኝ ብሔሩ ምንም ይሁን ምን፣ለሁሉም ገበሬ በፈለጉት መንገድ ቢደረጁ ከቦታ እና ከሌሎች ግብኣት አንጻር ማሳካት የሚቻል አይመስልም፡፡ ከአርሶ አደሮቹ ብዛት፣ከምርታቸው መለያየት አንጻር የከተማ መስተዳድሩ በምን መልኩ ይተገብረዋል በዙሪያው ላሉት አርሶ አደሮች ቢሆን ተጠየቃዊ ይሆናል፡፡

በረቂቅ አዋጁ ላይ ከተቀመጡት ጉዳዮች አንዱ የአዋጁን አተገባበር የሚከታተልና የሚስፈጽም ምክር ቤት መቋቋሙ ነው፡፡ የምክር ቤቱ ተጠሪነት ለፌደራል መንግሥቱ እንደሚሆን ተገልጿል፡፡ በተለምዶ መንግሥት በመባል የሚታወቀው አስፈጻሚው አካል ነው፡፡ ይሁን እንጂ፣ የከተማ መስተዳድሩ ተጠሪነቱ ለፌደራል መንግሥቱ (በብዙ መልኩ ለአስፈጻሚው) ሆኖ ሳለ፣ የከተማውን እና የክልሉን ጉዳይ የሚመለከተውን ምክር ቤት ተጠሪነት ለፌደራል መንግሥት ማድረግ ተገቢነት አይኖረውም፡፡ የፌደራልና የክልል ጉዳዮችን የሚያስተባብር ወይንም የሚያሳልጥ ተቋም ቢኖር ለዚያ፤ አልበለዚያም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቢሆን ይመረጣል፡፡

ልዩ ጥቅም ሳይሆኑ የተካተቱ፤

በረቂቁ ውስጥ መካተት የሌለባቸው ነገር ግን የተካተቱ ሁለት ጉዳዮች አሉ፡፡ የመጀመሪው የመስተዳድሩ የራሱ የውስጥ ጉዳይ ሲሆን ሁለተኛው ግን የሕገ መንግሥት ማሻሻያ የሚጠይቅና በልዩ ጥቅምነትም መካተቱ አጠራጣሪ የሆነ ነው፡፡

ቀዳሚው፣ በከተማው ክልል ውስጥ የሚኖሩ ብሔራቸው ምንም ይሁን ፣በተለያዩ ምክንያት በልማት ሲነሱ ካሳ መክፈልና ማቋቋምን በተመለከተ ኦሮሚያ ክልልን የሚመለከት ባለመሆኑ በልዩ ጥቅም ውስጥ መካተት የለበትም፡፡ ከተማ መስተዳድሩ በልማት ምክንያት ስለሚፈናቀሉ ሰዎች በራሱ የማቋቋምና ራሳቸውን እንዲችሉ የማድረግ ግዴታ አለበት፡፡ ወደ ሌላ ክልልም ማስፈርም የለበትም፡፡ ሌሎች መፍትሔዎችን መከተል ይገባዋል፡፡ በመሆኑም በረቂቅ አዋጁ ላይ እንደ ኦሮሚያ ልዩ ጥቅም መወሰድ የሚገባው አይደለም፡፡
ሁለተኛው ጉዳይ የአፋን አሮሞ የሥራ ቋንቋነትን የሚመለከት ነው፡፡ በቅድሚያ፣ የኦሮሚያ ክልል በከተማ መስተዳድሩ ላይ ሊኖሩት ከሚችሉት ልዩ ጥቅሞች ውስጥ ሊካተት መቻሉ አጠራጣሪ ነው፡፡ ነገር ግን፣ ውሳኔው ተገቢ መሆኑ ባያጠራጥር እንኳን የሕገመንግሥት ጥያቄ ማስነሳቱ ግን አይቀርም፡፡ መነሻው ደግሞ፣ የፌደራል መንግሥቱ በተቋማቱ በሥሩ ለሚገኙ መስተዳድሮች የሥራ ቋንቋው አማርኛ እንደሆነ በሕገ መንግሥቱ ላይ መደንገጉ ነው፡፡ በመሆኑም፣አዋጁ ከመጽደቁ በፊት ሕገመንግሥቱን ማሻሻል ይገባል፡፡
መካተት ሲኖርባቸው ያልተካተቱ፤ ረቂቁ ላይ መካተት የነበረባቸው ነገር ግን ያልተካተቱ በርካታ ጉዳዮች አሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ሦስቱን ብቻ እንመለከት፡፡ በመጀመሪያ፣ አዋጁ መተግበር ሲጀምር በመስተዳድሩ እና በክልሉ መካከል ሊፈጠሩ የሚችሉ ግጭቶችን ለመፍታት የታሰበ ተቋም አለመኖሩ ነው፡፡

የአካባቢ ብክለትን ለሚመለከት አለመግባባት ፍርድ ቤትን መጠቀም እንደሚቻል ተቀምጧል፡፡ ከዚያ ውጭ ባሉት ጉዳዮች ሊነሱ የሚችሉ አለመግባባቶችን፣ከፖለቲካዊ ውሳኔ ባለፈ፣ በየትኛው ተቋም ይፈታሉ? በሚቋቋመው ምክር ቤት እንዳይባል እኩል አባላት ከክልሉም ከመስተዳድሩም ስለሚወከሉበት በስምምነት ከመጨረስ ባለፈ ዳኝነት መሥጠት አይቻላቸውም፡፡ በፌደሬሽን ምክር ቤት እንዳሆን አንድም ጉዳዩ የሕገመንግሥት ላይሆን ይችላል፡፡ አንድም፣ከአዲስ አበባ መስተዳድር ወኪል በሌለበት ተቋም የሚሠጠው ውሳኔ ተገቢ አይሆንም፡፡

ሌላው፣ ከተማዋ ከፌደራሉ በተጨማሪ የክልሉም በርእሰ ከተማ መሆኗ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ በከተማዋ ላይ ምን ዓይነት መብቶች እንዳሉት የተገለጸ ነገር የለም፡፡ ከመስተዳድሩ የሚያገኛቸውን ጥቅሞች እንጂ በራሱ ማከናወን ስለሚችላቸው ሁኔታዎች አልተቀመጠም፡፡ የከተማው መሥተዳድር ተጠሪነቱ ለፌደራሉ ስለሆነ የፌደራሉ መንግሥት መብቶቹን በራሱ ሊወስን ይችላል፡፡ የክልሉ ግን ሁልጊዜም በመስተዳድሩ ላይ የተንጠለጠለ ነው፡፡ የፌደራሉ፣የመስተዳድሩ እና የክልሉ መንግሥት ከተማዋን በተመለከተ በተለይም ግንባታን በሚመለከት የሚኖራቸው ግንኙነት በአዋጁ መቀመጥ አለበት፡፡ በሌሎች የፌደራል ከተሞች ላይ ይህንን የሚያሳልጥ፣’ስታንዳርድ’ የሚያስቀምጥ ‘ብሔራዊ የዋና ከተማ የፕላን ኮሚሽን’ አላቸው፡፡
በሦስተኛነት መቀመጥ ያለበት የከተማው የጸጥታ አጠባበቅ እና የክልሉን ግንኙት የሚመለከት ነው፡፡ የፌደራሉ እና የከተማ መስተዳድሩ የፖሊስ ግንኙነት በአዋጅ ተለይቷል፡፡ የፌደራል እና የዓለም አቀፍ ተቋማት ጥበቃ የሚከናወነው በፌደራል ፖሊስ ሲሆን የመስተዳድሩን ደግሞ በአዲስ አበባ ፖሊስ ነው፡፡ በከተማው ውስጥ የሚገኙ የክልሉ ተቋማትን ጥበቃ የሚያደርገው ማን እንደሆነ እንዲሁም የሦስቱም መንግሥታት የፖሊስ ግንኙነት መታወቅ አለበት፡፡ እዚሁ ጋር ተያይዞ መነሳት ያለበት ኦሮሚያ ክልልን የሚመለከቱ ነገር ግን በዋና ከተማው ላይ ሰላማዊ ሰልፎች ሲኖሩ ጥበቃ የሚደረግበትን፣ማወቅ ያለበት ተቋም ማን እንደሆነ ወዘተ መገለጽ ይኖርበታል፡፡

በጥቅሉ፣አዋጁ ከመጽደቁ በፊት በአግባቡ መፈተሽን ይፈልጋል፡፡ የርዕሰ ከተማ አስተዳደር ውጥረት እንደሚኖርበት ይታወቃል፡፡ በአንድ በኩል የፌደራል መንግሥቱ እንደ ብሔራዊ ከተማ፣መገለጫ መውሰድ፣ ብሔራዊ ውክልናና እና የባህል መለያ እንዲሆን ስለሚፈለግ፤ በሌላ ጎኑ ደግሞ የአካባቢው ሕዝብ ደግሞ ቅድሚያ ለራሱ በማሰብ በራስ መንገድ ማስተዳደር እና የራሱ መገልጫ እንድትሆን የመፈለጉ ጉዳይ ሁልጌዜም የማይጠፋው ውጥረት ነው፡፡ ኢትዮጵያ ላይ ሲሆን ደግሞ፣የክልልም ይጨመርበታል፡፡
የፌደራል ሥርዓት የሚከተሉ አገራት ዋና ከተሞቻቸውን ከሦስቱ በአንዱ መንገድ ማዋቀራቸው የተለመደ ነው፡፡ አንደኛው፣ ዋና ከተማው ከክልል ጋር በእኩልነት እንዲቋቋም በማድረግ እኩል ሥልጣን እንዲኖረው በማድረግ ነው፡፡ ሞስኮ፣በርሊን፣ቪየና እና ብራሰልስ በዚህ መልኩ የተቋቋሙ በመሆናቸው ለፌደራሉ መንግሥት ተጠሪነት የለባቸውም፡፡ በሽግግር ወቅቱ ጊዜ፣አዲስ አበባም፣ክልል ዐስራ አራት ተብላ የክልልነት ደረጃ ነበራት፡፡

ሁለተኛው መንገድ ደግሞ፣ የፌደራሉ መንግሥት መቀመጫ በአንድ ወይንም ከዚያ በላይ በሆኑ ክልሎች ውስጥ ሆኖ የሚቋቋምበት ሥርዓት ነው፡፡ የፌደራሉ መንግሥት የሚያስተዳድረው መሬት ወይንም ግዛት የለም፡፡ ደቡብ አፍሪካ፣ሲውዘርላንድ፣እና ካናዳ ይሄንን ዓይነት አካሄድ መርጠዋል፡፡
ሦስተኛው በፌደራሉ መንግሥት ሥር የሚገኝ ከተማ እና ለዚህም የሚሆን የተለየ ግዛት በመከለል የሚቋቋሙ ከተሞች ናቸው፡፡ የከተሞቹም ተጠሪነት ለፌደራሉ መንግሥት ይሆናል፡፡ በርካታ አገራት ዋና ከተሞቻቸውን በዚህ መንገድ ነው ያቋቋሙት፡፡ አዲስ አበባም ከ1987 ዓ.ም. ጀምሮ ክልልነቷ ቀርቶ የፌደራል ከተማ መሆኗ ይታወቃል፡፡

የፌደራል ከተሞች ከሌሎች ክልሎች (የፌደሬሽኑ አባላት) የሚለዩባቸው የአስተዳደር ጠባይ አሏቸው፡፡ የአዲስ አበባ ደግሞ ከክልልም ብቻ ሳይሆን በዓለም ላይ ካሉ የፌደራል ዋና ከተሞችም የሚለያት ባሕርይ ስላላት ይህንኑ የሚመጥን ብሎም አንድ የፖለቲካ ማኅበረሰብ ለመገንባት በሚመች መልኩ ከኦሮሚያ ክልልም ጋር ሆነ ከፌደራሉ ጋር የምትተዳደርበት እና የምትመራበት ሕግ ነው የሚያስፈልጋት፡፡

%d bloggers like this: