Category Archives: Human Rights

የመሐል ዳኛው ሸለመ በቀለ ራሳቸውን ከተሰየሙበት ችሎት አገለሉ፤ ፤የጋዜጠኞቹ እና ብሎገሮቹ ጉዳይ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቀርቧል

z9

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ለተከታታይ ሶስት ቀናት ፍርድ ቤት ሲመላለሱ የነበሩት 9 ተጠርጣሪዎች ዛሬ ለ19ኛ ጊዜ ፍርድ ቤት ቀርበዋል፡፡ እንደትላንትናው ሁሉ ዘግይቶ ተጀመረው ቸሎት የመሃል ዳኛው አንዲነሱ የቀረበውን አቤቱታ ምርምሮ ብይን ለመስጠት ነበር ፡፡ በዚህም መሰረት ያለመሃል ዳኛ የመጡት ሁለት የግራ እና የቀኝ ዳኞች ተሰይመው አቤቱታውን ካነበቡ በኋላ ማለትም
1.ዳኛው ለአቃቤ ህግ ተደጋጋሚ የማሻሻል እድል በመስጠት አፋጣኝ ፍትህ የማግኘት መብታችንን ነፍገውናል
2. ፍርድ ቤቱ ራሱ የሰጠውን ትእዛዝ ራሱ ሽሮ ያለምንም የፍሬ ሃሳብ ለውጥ ያለተሻሻለ ክስ ተቀብሏል
3. ሃሳባችንን ስንገልጽ ክልከላዎች ይደረጉብናል በመሆኑም ለዚህ የፍትህ መጓደል መሃል ዳኛው ሚና ዋሳኝ ነው ብለን ስለምናምን አንዲቀየሩልን እንጠይቃለን የሚል ሲሆን ዳኞቹ አቤቱታው አግባብነት የሌለው ነው ውሳኜው በመሃል ዳኞች ብቻ ሳይሆነ በጋራ የሚወሰን ስለሆነም ጭምር አቤቱታውን ውድቅ አድርገነዋል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም እንዲህ አይነት አቤቱታ ውድቅ ሲሆን ለእያንዳንዳቸው ተከሳሾች 500 ብር የሚያስቀጣ ቢሆንም በስሜታውነት ነው ያቀረቡት በማለት ፍርድ ቤቱ አልፎታል ብለዋል ፡፡

በመቀጠል መሃል ዳኛውን ይዘው በመምጣት ችሎቱን አሟልተው አንደሚመለሱ ገልጸው መሃል ዳኛውን ይዘው መጥተው ደግመው ተሰይመዋል፡፡ መሃል ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ እነደተሰየሙ የምናገረው ነገር አለኝ በማለት ” ምንም አንኳን ሌሎቹ ዳኞች በዳኝነት አንድቀጥል ቢፈቅዱልኝም እኔ ግን በዚህ ክስ መቀጠል አልፈልግም ከዚህ በኋላ የምሰጠውም ዳኝነትም ቢሆን አመኔታ ስለማያገኝ አንድቀየር ማመልከቻ አስገብቻለሁ በማለት ራሳቸውን ከችሎቱ እንዲያገሉ መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህንን ተከትሎ አዲስ ዳኛ ተተክቶ የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል አንደሚቀበል እና ሌላ ቀጠሮ እነደሚሰጥ ተገልጿል፡፡ የተከሳሾች ጠበቆች በበኩላቸው ይህ ጉዳይ ተጠናቆ መቅረብ ሲገባው እነደገና ሌላ ቀጠሮ መሰጠቱ አግባብ ስላልሆነ አጭር ቀጠሮ ይሰጥልን በማለታቸው የእምነት ክህደት ቃል ለመስጠት ለየካቲት 11 ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ጦማሪ አቤል ዋበላ ላይ እየደረሰ ያለ ማሰቃየት

ጦማሪ አቤክ ዋበላ በበኩሉ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታ ለማቅረብ አንደሚፈልግ ተናግሮ ሲፈቀድለት ትላንትና ከፍርድ ቤት መልስ ጀምሮ በውሻ ሰንሰለት ታስሮ እንዳደረና ሲሰደብና ሲያዋርዱት አንደነበር ተናግሯል፡፡ ትላንትና ከፍርድ ቤት ወደ ማረሚያ ቤት በሚመለሱበት ወቅት ጠባቂዎቹ በካቴና ሳያስሩት አንደረሱት እና በራሳቸው ጥፋት የተነሳ ለምን አልታሰርክም ሲሉኝ ራሳችሁ ስላላሰራችሁኝ ብዬ በመመለሴ እናሳይሃለን በሚል ዛቻና ማስፈራሪያ ወደ ቅሊንጦ መመለሱን አና እዚያ ከደረሰ ጀምሮ በውሻ ሰንሰለት ታስሮ ማደሩን ማእከላዊ በደረሰበት ድብደባ የተነሳ የጆሮ ማዳመጫ መሳሪያ ለማድረግ ተገዶ የነበረ በመሆኑ የጆሮ ማዳመጫ መሳሪያውንም አንደተቀማ ገልጾ ከዚህ ስወጣ ምን አንደሚጠብቀኝም አላውቅም ህይወቴ አደጋ ላይ ነው ሲል በከፍተኛ ምሬት እንባ እየተናነቀው ተናግሯል ፡፡ አቤት የደረሰበትን ሰቆቃ ሲናገር ችሎቱን ሲታደሙ የነበሩት ወላጅ አባቱ እህቱና ሌሎች ጓደኞች ሲያለቅሱ ታይተዋል፡፡

በቦታው የነበሩት የማረሚያ ቤቱ ተጠሪ ምክትል ሳጅን ዘውዱ በፍርድ ቤቱ ተጠርተው የተጠየቁ ሲሆን የማውቀው ነገር የለኝም በማለት መልሰዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ የአቤልን አቤቱታ በጽሁፍ አንዲያስገባ የተናገረ ሲሆነ ማረሚያ ቤቱ በሚቀጥለው ቀጠሮ ምላሹን ይዞ እነዲመጣ በማዘዝ ችሎቱ ተጠናቋል፡፡

UN

በተያያ ዜና  በእስር ላይ በሚገኙት የዞን 9 ብሎገሮችና  ጋዜጠኞች  የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ጉዳይ ለተባበሩት መንግሰታት ድርጅት አለአግባብ እስር የተፈጸመባቸው ዜጎችን ጉዳይ lሚያይ ቡደን ቀርቧል ፡፡ በቡድኑ አሰራር መሰረት የኢትዬጲያ መንግሰት የቀረበበትን አቤቱታ አስመልክቶ መልስ ለመስጠት ጊዜ ይሰጠዋል፡፡ አቤቱታው

የታሰሩትን ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ያጋጠማቸውን የመብት ጥሰት ዝርዝር
2. የመታሰራቸው ምክንያት አግባብ አለመሆን የክሱን አለም አቀፍ መብቶችንም ሆነ የወንጀል ህግ መሰረቶች የጣሰ እና ሃሳባቸውን በመግለጻቸው ብቻ መሆኑን የሚያስረዳ ሲሆን መንግሰት ላይ የቀረበውን ክስ ያዘጋጁት Ethiopian Human Rights Project እና Freedom Now በተባሉ ድርጅቶች ናቸው፡፡

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ደብዳቤ

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ደብዳቤ

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው

ቀን 02/06/2007 ዓ.ም
ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን

አዲስ አበባ

ጉዳዩ፡- የልጄ ተመስገን ደሳለኝን ጉብኝት ይመለከታል

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ከአብራኬ የወጣ ሁለተኛ ልጄ ነው፡፡ ገና ከህፃንነቱ ጀምሮ ለሰው አሣቢ፣ ሀገር ወዳድና ታታሪ ስለመሆኑ ከእኔ በላይ የሚያውቁት ይመሰክራሉ፡፡ ልጄ ተመስገን ለወገኔ አሰብኩ ባለ በእስር ቤት ያለጎብኚ እየተሰቃየብኝ ይገኛል፡፡ መቼም፣ የእናት ሆድ አያስችልምና እባካችሁ ልጄን ታደጉት፡፡ እባካችሁ ቢያንስ ካለበት እየሄድኩ የልጄን አይን እንዳይ እንዲፈቀድልኝ ተባበሩኝ፡፡ የልጄን ድምጽ ከሠማሁ ይኸዉ አንድ ወር ሞላኝ፡፡ ታናሽ ወንድሙ ታሪኩ ደሳለኝ ለወንድሙ ብሎ የቋጠረዉን ምሣ ይዞ ዝዋይ ማረሚያ ቤት ቢሄድም በማረሚያ ቤቱ ጠባቂዎች ተደብድቦ የያዘውን ምግብ እንኳ ሣያደርስ ሜዳ ላይ ተደፍቶ ተመልሷል፡፡ መቼም እናንተም ልጆች ይኖራችኋል፤ ደግሞም የልጅን ነገር ታውቁታላችሁ፡፡ እኔ አሁን በእርጅና ዕድሜዬ ላይ እገኛለሁ፡፡ ከአሁን በኋላ ብቆይም ለትንሽ ጊዜያት ነው፡፡ በዚህች ጊዜ ውስጥ ልጄን እየተመላለስኩ እየጠየኩ፣ ድምፁን እያሰማሁ፣ አይዞህ እያልኩ ብኖር ለእኔ መታደል ነበር፡፡ እባካችሁ እርዱኝ የልጄ ድምጽ ናፈቀኝ፡፡ እሱን መጎብኘት የተከለከለበት ምክንያት ምን እንደሆነ እንኳን እስካሁን አላወቅሁም፡፡ ከወንድሙ ድብደባ በኋላም ጥር 10 ወደ ጠዋት አካባቢ የሄዱት ጓደኞቹ እና ወንድሞቹ ሳያዩት ተመልሰዋል፡፡

ተምዬ ስታመም የሚያስታምመኝ፣ “አይዞሽ እማዬ” የሚለኝ ረዳቴ ነው፡፡ ሌላ ዘመድ የለኝም፡፡ የምተዳደረውም ልጆቼ ለፍተውና ደክመው በሚያመጧት ትንሽ ብር ነው፡፡ ዛሬ ግን ይኸዉ ልጆቼም ወንድማቸውን ለማየት እየተንከራተቱ ነው፡፡

በእናታችሁ ይዣችኋለሁ፤ ከቻላችሁ ልጄ እንዲፈታልኝ እና እኔም ያለችኝን ቀሪ የእድሜ ዘመን አይን አይኑን እያየሁ እንድኖር እንድታደርጉልኝ፤ ይህን ማድረግ ከአቅም በላይ ከሆነ ደግሞ ካለበት ድረስ እየተመላለስኩ እኔና ሌሎች ልጆቼ እንዲሁም ወገኖቹ እንዲጠይቁት ቢደረግልኝ ስል በአክብሮት እጠይቃችኋለሁ፡፡ ልጄን አውቀዋለሁ፡፡ አንድ ነገር ሲገጥመዉ ሆድ ይብሰዋል፡፡ ቢያንስ እንኳን ቤተሰቦቹን ሲያይ ስለሚፅናና ይኸዉ እንዲፈቀድልኝ እማፀናለሁ፡፡ እኔ ምንም አቅም የሌለኝ አሮጊት ነኝ፡፡ ሁሉንም ለናንተ ሠጥቻችኋለሁ፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር እንደምታስተካክሉልኝ እና እንደገና የልጄን ፊት እንዳይ እንደምታደርጉኝ ሙሉ ተስፋ አለኝ፡፡

እንግዲህ የየካዉ ቅዱስ ሚካኤል ይከተላችሁ፡፡ መቼም የእናትን ሆድ ታውቁታላችሁ፤ የልጅ ነገር አያስችልም፡፡ ሆድም ቶሎ ይሸበራል፡፡ ስለዚህ እባካችሁ እኔንም ልጆቼንም እርዱን እንላለን፡፡

ግልባጭ
_ ለጠ/ሚኒስተር ፅ/ቤት
_ የህግና፣ ፍትህና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ
_ ለአፈ-ጉባኤ ፅ/ቤት
_ የሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ሰመጉ)
_ ለእምባ ጠባቂ
_ ለአሜሪካ ኢምባሲ
_ ለእንግሊዝ ኢምባሲ

ከሰላምታ ጋር
ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው

የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች የክስ መቃወሚያ ውድቅ ተደረገ

prisoners

በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት እየታየ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችና ሌሎች በተመሳሳይ መዝገብ የተከሰሱት ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ ላይ ያቀረቡት መቃወሚያ ውድቅ ተደረገባቸው፡፡ አመራሮቹ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም ችሎት ቀርበዋል፡፡

በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የተከሰሱት የአንድነት፣ የሰማያዊና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች የሆኑት አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዳንኤል ሺበሽ እና ሌሎች ስድስት ተከሳሾች መቃወሚያቸው በፍርድ ቤቱ ውድቅ ተደርጓል፡፡

ተከሳሾች በጠበቆቻቸው አማካኝነት የቀረቡባቸው የተለያዩ የክስ ይዘቶች ላይ መቃወሚያቸውን አቅርበው የነበር ቢሆንም ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ የተከሳሽ መቃወሚያ ውድቅ እንዲደረግለት የጠየቀውን በመቀበል ‹‹በመቃወሚያው ላይ የተነሱት ነጥቦች በአብዛኛው ማስረጃ በማሰማት ሂደት ወቅት ሊረጋገጡ የሚችሉ ስለሆኑ›› በሚል መቃወሚያቸው ውድቅ ተደርጓል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤት በቀረበው ክስ አግባብ የክስ ሂደቱ እንዲቀጥል ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

በሌላ በኩል ተከሳሾች በእስር ላይ በሚገኙበት ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ላይ ‹‹የመብት ጥሰት እየተፈጸመብን ነው›› በሚል አቤቱታ አቅርበው የነበር ሲሆን በአቤቱታው ላይ እስካሁን ከማረሚያ ቤቱ መልስ አለመሰጠቱ ታውቋል፡፡ አቤቱታው በጽሑፍ ተገልብጦ ለማረሚያ ቤቱ መላኩን የገለጸው ፍርድ ቤቱ፣ ለአቤቱታው መልስ ከማረሚያ ቤቱ እየተጠበቀ እንደሆነ ተገልጹዋል፡፡

በመሆኑም ይህንኑ የማረሚያ ቤቱን መልስ ለመስማትና የክሱን ሂደት ለመቀጠል ፍርድ ቤቱ ለየካቲት 11 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ምንጭ፡-ነገረ-ኢትዮጵያ

ብሎገሮቹና ጋዜጠኞቹ ሰብሳቢ ዳኛው ከችሎት እንዲነሱ ጠየቁ

ከቀኝ ወደ ግራ የዞን 9 ብሎገር ማህሌት ፋንታሁን እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ ከችሎት ሲወጡ

ከቀኝ ወደ ግራ የዞን 9 ብሎገር ማህሌት ፋንታሁን እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ ከችሎት ሲወጡ

በእነ ሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው የዞን ዘጠኝ ብሎገሮችና ጋዜጠኞች፤ ሰብሳቢ ዳኛው ከችሎት እንዲነሱ ጠየቁ፡፡
ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም ለ17ኛ ጊዜ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 1ልደታ ምድብ 9ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት ብሎገሮቹና ጋዜጠኞቹ የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ የሆኑት አቶ ሸለመ በቀለ “የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብታችንን አላስከበሩልንም” በሚል ከችሎት እንዲነሱ በጽሑፍ አቤቱታ አቅርበዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የተሰየመው ተሻሽሎ ቀርቧል በተባለው የአቃቤ ህግ ክስ ላይ የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል ለመስማት እንደነበር ዳኞቹ ቢናገሩም፣ ተከሳሾች አቤቱታ እንዳላቸው በመግለጽ የእምነት ክህደት ቃል ለመስጠት ዝግጁዎች አለመሆናቸውን ለችሎቱ ማስረዳት ችለዋል፡፡
ተከሳሾች ‹‹እኛ በሰብሳቢ ዳኛው ላይ አቤቱታ አለን፤ ፍርድ ቤቱ የራሱን ውሳኔ እንኳ አላከበረም፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሆነን የእምነት ክህደት ቃላችንን ለመስጠት ዝግጁዎች አይደለንም›› በሚል ፍርድ ቤቱ አቤቱታቸውን እንዲቀበል ጠይቀዋል፡፡

ዳኛ ሸለመ በቀለ “ፍርድ ቤቱ ቃሉን አላከበረም›› በሚለው ጉዳይ ላይ መልስ ሲሰጡ ‹‹የእኛን ውሳኔ የማትቀበሉ ከሆነ ጉዳዩን በይግባኝ እንዲታይ ማድረግ ይቻላል” ብለዋል፡፡
“ላለፉት ስድስት ወራት በነበረው የክርክሩ ሂደት የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ ሂደቱን በአግባቡ በመምራት የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብታችንን አላስጠበቁልንም፡፡ በተለያየ ጊዜም ሐሳባችን ለመግለጽ ስንሞክር ክልከላ አድርገውብናል፡፡ አሁን ደግሞ ችሎቱ ራሱ የሰጠውን ትዕዛዝ ራሱ ሽሮ ፈጽሞ ልንረዳው በማንችለውና የመከላከል መብታችንን በሚያጣብብ የክስ ሁኔታ ክርክሩን እንድንቀጥል ሲበየንብን የችሎቱ ሰብሳቢ ወሳኝ ሚና ነበራቸው” ሲሉ ተከሳሾች በሰብሳቢ ዳኛው ላይ ቅሬታቸውን በአቤቱታቸው ገልፀዋል፡፡
ፍርድ ቤቱም የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ ከችሎት እንዲነሱ የሚጠይቀውን አቤቱታ አይቶ ነገ ብይን ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል ሲል ነገረ-ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡

ፍርድ ቤቱ በብሎገሮቹና በጋዜጠኞች ላይ ተሻሻለ የተባለውን የአቃቤ ህግ ክስ ተቀበለ

z9

ባለፉት 9 ወራት በፖሊስ ቁትጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ሲታይ የነበሩት 6 የዞን 9 ጦማርያንና 3 ጋዜጠኞች ላይ አቃቤ ህግ በዛሬው ዕለት ጥር 20 ቀን 2007 ዓ.ም. አሻሽዬ አቅርቤዋለሁ ያለውን የክስ ቻርጅ የልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ የወንጀል ችሎት ተቀባይ አድርጎታል፡፡

በዚህም መሰረት ተከሳሾቹ በአሸባሪነት ወንጀል እንደሚጠየቁና ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ የእምነት ክህደት ቃላቸውን እንዲሰጡ ዛሬ ጠዋት በነበረው የክስ ሂደት ወቅት ጠይቋቸው ጉዳዩን ለከሰዓት አስተላልፎት ነበር፡፡ ነገር ግን ከጥቂት ሰዓታት በፊት በነበረው የክስ ሂደት ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን ለ17ኛ ጊዜ ለሚቀጥለው ማክሰኞ ጥር 26 ቀን ቀጠሮ በመስጠት ተበትኗል፡፡

ስድስቱ የዞን 9 ጦማርያንና ሦስቱ ጋዜጠኞች ከባለፈው ዓመት ሚያዚያ 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ሲታይ የከረመ ቢሆንም የክስ ሂደቱ ላይ ግን በርከት ያሉ የህግ ሂደትን ያልተከተሉ ሁኔታዎች ሲስተዋሉ መቆየቱን አዲስ ስታንዳርድ ዘግቧል፡፡