Category Archives: News

እነ ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ ጥፋተኝነት ሲበየንባቸው፣ አቶ በቀለ ገርባ እና ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጣቸው

በእነ ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ ከ600 ቀናት በላይ ፍርድ ቤት ሲመላሱ የቆዩት ተከሳሾች ላይ ዛሬ ብይን ተሰጥቷል፡፡ በዚህም መሰረት አንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ፣ ሰለሞን ግርማ ፣ መምህር ተስፋዬ ተፈሪ ጥፋተኛ ተብለዋል፡፡ በተመሳሳይ መዝገብ የተከሰሱት ባህሩ ደጉ እና ዬናታን ወልዴ በነጻ ተሰናብተዋል፡፡

Zelalem Workagegnehu

በተመሳሳይ የክስ ፋይል አብረው የተከሰሱት የፓቲካ ፓርቲ አመራሮች ( አብርሃ ደስታ ፣ ሃብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሺ፣ የሸዋስ አሰፋ) እና መምህር አብርሃም ሰለሞን መከላከል ሳያስፈልጋቸው ነጻ መባላቸው ይታወሳል፡፡

Bekele Gerba

ለአራት ወር ለሚጠጋ ጊዜ ማእከላዊ ምርመራ የከረሙት የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ፣ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው እና አብረው የታሰሩ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስና የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ተጨማሪ አንድ ሳምንት ጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ እስካሁን ድረስ በሽብር ከመጠርጠር ውጪ ክሳቸው በውል ያልታወቀው ፣ አቶ በቀለ ገርባ ፣ አቶ ደጀኔ ጣፋ፣ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራውን ጨምሮ ኦሮሚያ ላይ የተነሳው ህዝባዊ አመጽ ተከትሎ ለእስር መዳረጋቸው ይታወሳል፡፡

Getachew Shiferaw

ባለፈው ሳምንት ፍርድ ቤት ቀርበው ለዛሬ ክሳቸው እዲነበብ የተቀጠሩት 33 በአዲስ አበባ ከተማ ቦሌ ቡልቡላ አካባ ኦነግ ተዋጊነት የተጠረጠሩት እነ ሃብታሙ ሚልኬሳ ዛሬም ክሳቸው ሳይሰማ ለሚያዝያ 20 ሌላ ቀጠሮ እንዲቀርቡ ተላልፏል፡፡

ምንጭ፡- EHRP

እነ ኦኬሎ ኦኳይ ጥፋተኛ ተባሉ

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ መጋቢት 28ቀን 2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት የቀድሞው የጋምቤላ ርዕሰ መስተዳድር ኦኬሎ ኦኳይ እና አብረዋቸው የተከሰሱት ስድስት ተከሳሾች ጥፋተኛ ናቸው ብሎ ውሳኔ አስተላለፈ።ፍርድ ቤቱ የቅጣት አስተያየት ለመስማት ሚያዚያ 17 ቀጠሮ ስጥቷል፡፡

Okello Akuay

በሰኔ ወር 2006ዓ.ም የሽብር ክስ ተመሰርቶባቸው ክሳቸው እየታየላቸው የሚገኙት እነ ኦኬሎ ኦኳይ በየካቲት 28 ቀን 2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውሳኔ ለማስተላለፍ ለዛሬ ለሶስተኛ ጊዜ ተቀጥረው ነበር፡፡ በዚህም መሰረት ዛሬ በችሎት ከተሰየሙት ሶስት ዳኞች መካካል የቀኝ ዳኛ የሆኑት አቶ ሳሙኤል ታደሰ የፍርድቤቱን ውሳኔ በንባብ አሰምተዋል፡፡

ዳኛ ሣሙኤል ታደሰ ወደ አንድ ስዓት በቆየው የፍርድ ውሳኔ ንባባቸው እንዳመለከቱት አቶ ኦኬሎና ስድስቱ ተከሳሾች የጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል በመሆን እና የጋምቤላ ክልልን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ተንቀሳቅሰዋል፡፡ ከአሜሪካ ገንዘብ በማሰባሰብ እና የሽብር ቡድን ማስተባበራቸውን በንባባቸው ጠቅሰዋል፡፡

አቃቤ ህግ በነኦኬሎ ላይ ከዘረዘራቸው ክሶች መካከል ከኤርትራ መንግስት ጋር የሽብር ድርድር በማድረግ እና ከኦነግ እና ግንቦት 7 አመራሮች ጋር በተለይ ከሞት ፍርደኛው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ጋር መገናኘት እንደሚገኙበት ዳኛ ሳሙኤል አስታውሰዋል፡፡ከዚህም በተጨማሪ ወጣቶችን ለሽብር ተግባር መመልመል፣ ወታደራዊ ስልጠና መስጠት በክሳቸው ላይ መጠቀሱን ዳኛው ተናግረዋል፡፡

ከክስ ንባብ መስማት በኃላ ወደ ሁለት አመት ያህል ፍርድቤት የተመላለሱት እነ ኦኬሎ አኳይ የክስ መቃወሚያ ካቀረቡበት ጊዜ አንስቶ ለውሳኔ እስከተቀጠሩበት ጊዜ ያለው ሂደት በዳኛው ተብራርቶ ቀርቧል፡፡
የእነ ኦኬሎ የክስ መቃወሚያ በፍርድ ቤቱ ሙሉ ለሙሉ ውድቅ መደረጉን እና የተከሰሱበትን ክስ ክደው መከራከራቸውን ያስታወሱት ዳኛ ሳሙኤል በመቀጠል አቃቤህግ ምስክሮቹን አቅርቦ ማሰማቱን አስረደተዋል፡፡
ለወራት ከዘለቀው የምስክሮች መሰማት ሂደት በኃላ ፍርድቤቱ ተከሳሾቹን እንዲከላከሉ መወሰኑን ዳኛው ጠቅሰዋል፡፡ ተከሳሾቹ በምርመራ ወቅት በከፍተኛ ጫና እና ድብደባ ውስጥ እንዳለፉ ማስመዝገባቸውን ዳኛው ጠቁመዋል፡፡

የግራና የቀኙን ክርክር ያዳመጠው እና የቀረቡለትን ማስረጃዎች የመረመረው ፍርድ ቤት በሁሉም ተከሳሾች ላይ የጥፋተኛ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

አንደኛ ተከሳሽ ኦኬሎ አኳይ በሰው እና መማስረጃ የጋምቤላን ክልል ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር በመሆን የአመራር ሰጪ ውሳኔዎችን ሲመራ በመቆየቱ አቃቤህግ በሰው እና በማስረጃ ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዳ ዳኛው በውሳኔው አመልክተዋል፡፡ተከሳሹ በበኩሉ የተከሳሽነት ቃል ከማሰማት በስተቀር መከላከያ ምስክሮችም ይሁን ሰነዶችን አቅርቦ በበቂ ሁኔታ እንዳልተከላከለ ዳኛው ገልፀዋል፡፡
ቀሪዎቹም ተከሳሾች በምርመራ ወቅት ለፖሊስ ቃላቸውን ተገደው ስለመስጠታቸው ያሰረዱ እንጂ የቀረበባቸውን ክስ የሰው ምስክር እና የሰነድ ማስረጃ አቅርበው እንዳልተከላከሉ በዳኛው ተገልጿል፡፡
“[ተከሳሾቹ] ምስክሮቻቸው ማዕከላዊ አብረዋቸው የነበሩ፣ በሌላ ወንጀል ተጠርጥረው ያሉ እና ተዓማኒነታቸው ጥርጣሬ ውስጥ የሚገባ ከመሆኑ በተጨማሪ ከዋናው ክስ እና የክስ ማስረጃ ጋር የማይገናኙ በመሆናቸው ክሳቸውን በደንብ አልተከላከሉም” ሲሉ ዳኛው ገልፀዋል፡፡

ክሱ መታየት ያለበት በፀረ ሽብር አዋጁ ነው ወይስ አይደለም የሚለውን ፍርድቤቱ መርምሮ በአንደኛ ተከሳሽ የተመሰረተው ጋህነን፣ የጋምቤላ ህዝብን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ከተለያዩ የሽብር ቡድኖች ጋር የስልጠና ትብብር መጠየቃቸው በአቃቤ ህግ የተረጋገጠ ነው ብለዋል ዳኛው፡፡ ሆኖም ድርጊቱ የአገሪቷን አንድነት የማፈራረስ ሙከራን የሚያቋቁም እንደሆነ የገለፁት ዳኛው በዚህም መሰረት ተከሳሾቹ በፀረ ሽብር አዋጁ ሳይሆን የወንጀል ህጉን 241 በመተላለፋቸው በወንጀለኛ መቅጫ ስነስርአት ህግ 149(1) የጥፋተኝነት ውሳኔ ማስተላለፉን ተናግረዋል፡፡

መጋቢት 28/2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት የጥፋተኝነት የፍርድ ውሳኔ የተላለፈባቸው ሰባት ሰዎች ሲሆኑ፣ እነዚህም ኦኬሎ አኩዋይ፣ ዴቪድ ኦጅሉ፣ ኡቻል አፒዮ፣ ኡማን ኒኮዮ፣ ኡጅሉ ቻም፣ ኡታካ ኡዋር እና ኡባንግ ኡቡንግ ናቸው፡፡

ምንጭ፡- EHRP

በኦሮሚያ ለግጭት ምክንያት የነበረው የከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች ተሰረዙ

በውድነህ ዘነበ

Fekadu Tesema,Oromia PR

በኦሮሚያ ክልል ሕዝባዊ ጥያቄ የተነሳበት የከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች ተሰረዙ፡፡ እነዚህ አወዛጋቢ የተባሉ አንቀጾች ከተሰረዙ በኋላ ባለፈው ሳምንት የተሰበሰበው ጨፌ ኦሮሚያ አዋጁን አፅድቋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ተነስቶ ለነበረው ረብሻ የአዲስ አበባና ዙሪያዋ ኦሮሚያ ልዩ ዞን የጋራ ማስተር ፕላንና የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ ምክንያት እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የማስተር ፕላኑን ተግባራዊነት ማቆሙን በወቅቱ በይፋ የገለጸ ሲሆን፣ ለውዝግቡ መባባስ ምክንያት የነበሩ የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች እንዲሰረዙ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

የተሰረዙት ሦስት አንቀጾች ከተሞችን መቀላቀል፣ የተቀላቀሉ ከተሞች ስያሜና ራዲዮ ፖሊ (የክልሉን ትልልቅ ከተሞች በተመለከተ) የሚያትቱ ናቸው፡፡ የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ አንድ የክልሉ ከተማ በዙሪያው ካሉት አነስተኛ ከተሞችን (ሳተላይት) በመያዝ እንደ አዲስ ይደራጃል ይላል፡፡
ለፀጥታ መደፍረስ ምክንያት የሆነው የኦሮሚያ ልዩ ዞን ውስጥ ያሉ ከተሞችን ከአዲስ አበባ (ፊንፊኔ) ጋር ለመቀላቀል ነው የሚሉ ግምቶችን ከተለያዩ ወገኖች በመስጠቱ ነው ተብሏል፡፡

በሌላ በኩል የክልሉ ከተሞች ሲቀላቀሉ አንድ ስም የግድ ይመርጣሉ፡፡ ይህ ሁኔታ የክልሉን ታሪክና ባህል ያጠፋል፣ ልዩ ዞኑን ከአዲስ አበባ ጋር ለመቀላቀል ያለመ ነው የሚል ትንታኔ አሁንም በመስጠቱ ለችግሩ መንስዔ ነው ተብሏል፡፡

በሦስተኛ ደረጃ የተቀመጠው የራዲዮ ፖሊ ትንታኔ ነው፡፡ የአገሪቱ መዲና አዲስ አበባ የፌዴራል መንግሥት ከተማ ነች፡፡ የክልል ከተሞች ባህር ዳር፣ መቐለ፣ ሐዋሳ፣ ጅማ፣ አዳማና የመሳሰሉት ከተሞች በራዲዮ ፖሊ ምድብ ይገኛሉ፡፡
የፌዴራል መንግሥት ባወጣው የከተሞች ፖሊሲ ራዲዮ ፖሊ ከተሞች ከፌዴራል መንግሥት ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ታቅዷል፡፡

የኦሮሚያ ክልል በከተሞች አዋጅ ላይ ስለ ከተሞቹ የገለጸ ሲሆን፣ ለዚህ ጉዳይ ከተለያዩ ወገኖች የተሰጠው ምላሽ ግን የኦሮሚያ ከተሞች በፌዴራል ሥር ሊገቡ ነው የሚል ነው፡፡ እነዚህ ሦስት ጉዳዮች በኦሮሚያ ተከስቶ ለነበረው ደም አፋሳሽ ግጭት መንስዔ እንደነበሩ ተገልጿል፡፡

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊና የካቢኔ አባል አቶ ፈቃዱ ተሰማ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በእነዚህ ጉዳዮች ላይ ሕዝብ ጥያቄ በማንሳቱና የኦሮሚያ መንግሥት ሕዝብ የማይስማማበትን አንቀጾቹን ከአዋጁ ውስጥ ፍቆታል፡፡

አቶ ፈቃዱ ‹‹እነዚህ አንቀጾች ጉዳት ኖሯቸው ሳይሆን ፅንፈኞች በአሉታዊ መንገድ ጉዳዩን እጅግ ያስተጋቡት በመሆኑና እኛ ደግሞ በተገቢው መንገድ ግልጽነት ስላልፈጠርን የተፈጠረው ብዥታ ከፍተኛ ነበር፤›› ብለዋል፡፡

‹‹እነዚህ ጉዳዮች የሕዝቡን ጥቅም የሚጎዱ ሆነው አይደለም፤›› በማለት ክልሉ ሐሳቡ የሕዝብ እስከሆነ ድረስ የሕዝብን ጥያቄ እንደሚቀበለው አቶ ፈቃዱ ገልጸዋል፡፡

እነዚህ አንቀጾች ከመሰረዛቸው በተጨማሪ በሌሎች ሁለት ጉዳዮች ላይ ማሻሻያ መደረጉን አቶ ፈቃዱ ገልጸዋል፡፡ ፀድቆ በነበረው የከተሞች አዋጅ የክልሉ ከተሞች የሚሰበስቡትን ፋይናንስ ለራሳቸው ይጠቀማሉ የሚል አንቀጽ ነበር፡፡ ነገር ግን ገቢ የማመንጨት አቅም የሌላቸውን ከተሞች ስለሚጎዳ፣ በማዕከል ደረጃ በጀት ቢከፋፈል የተሻለ መሆኑ ስለታመነበት ማሻሻያ ተደርጓል፡፡

ቀደም ሲል በክልሉ ከተሞች በላይኛው የአስተዳደር እርከንና በቀበሌ መካከል ራሱን የቻለ የመንግሥት መዋቅር አልነበረም፡፡ ቀደም ብሎ ፀድቆ በነበረው አዋጅ የወረዳ መዋቅር እንዲከፈት ተደንግጎ ነበር፡፡ ነገር ግን ከወረዳ ይልቅ ክፍለ ከተማ የተሻለ መዋቅር ነው ተብሎ ማሻሻያ መደረጉን አቶ ፈቃዱ ገልጸው፣ ትልልቅ ከተሞች የክፍለ ከተማ መዋቅር እንዲመሠርቱ በአዲሱ አዋጅ ማሻሻያ ተደርጓል፡፡

ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ

በኮንሶ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ሁለት ሰዎቸ ተገደሉ

በደቡብ ክልል ከዚህ ቀደም በልዩ ወረዳ አስተዳደር የነበረና በአሁን ወቅት የሰገን አካባቢ ዞን ስር ወደ ወረዳ አስተዳደርነት እንዲወረድ የተደረገው የኮንሶ ማኀበረሰብ አባላት የዞን አስተዳደር መዋቅር እንዲፈቀድላቸው መጠየካቸውን ተክትሎ በመንግሥት ተጣቂዎች በተወሰደ እርምጃ በግብርና የሚተዳደሩ ሁለት ሰዎች ተገድለዋል፡፡

እሁድ መጋቢት 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀትር ላይ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉት አቶ ሞሌ አዛዥ እና አቶ ፋንታዬ ጊዮርጊስ በግብርና ሙያ የሚተዳደሩ ጎልማሶች እንደሆኑ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ከተገደሉት በተጨማሪ 3 ሰዎች በፀኑ የቆሰሉ ሲሆን፤ ማኀበረሰቡም የተገደሉ 2 አስከሬኖች ይዞ ወደ ካራት አደባባይ በመውጣት ከፍተኛ ተቃውሞ ማሰማቱ ታውቋል፡፡

Konso Protest Ethiopia

የአዲስ ሚዲያ መረጃዎች እንዳረጋገጡት፤ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ አሁንም በኮንሶ በርካታ የደቡብ ልዩ ፖሊስ ኃይል የደንብ ልብስ የለበሱ ፖሊሶች በኮንሶ ዋና ከተማ ካራት እና በተለያዩ የገጠር ቀበሌዎች ጭምር እንደሰፈሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የህዝባዊ ተቃውሞ ዋነኛ ምክንያት 55ሺህ የኮንሶ ማኀበረሰብ ስምና ፊርማ ያለበት ስምምነት ወደ ዞን አስተዳደር እንደግ የሚል ጥያቄ ከደቡብ ክልል እስከ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ማስገባታቸውና መንግሥትም በሐረገ-መንግሥቱ መሰረት ተገቢውን መልስ ሳይሰጥ ከልዩ ወረዳነት ወደወረዳነት በማውረድ ጥያቄያቸው ምላሽ ባለማግኘቱ በተፈጠረ አለመግባባት እንደሆነ ታውቋል፡፡ ተቃውሞንም ተከትሎ የኮንሶ ባህላዊ ንጉስ ካላ ገዛኸኝ ወልደ ዳዊትን ጨምሮ ከ200 ያላነሱ የአካባቢው ዜጎች መታሰራቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ መንግሥት የሰጠው ይፋዊ ምላሽ ባይኖርም በአካባው ከፍተና ውጥረት መኖሩን ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡

በኦሮሚያ ክልል የደረሰውን የሰብዓዊ ጉዳት አስመልክቶ በ33 ወረዳዎች ብቻ 103 ዜጎች መገደላቸውን የሚገልፅ ገለልተኛ የምርመራ ሪፖርት ይፋ ሆነ

HRCO-logo-150x150

ከህዳር አጋማሽ 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ተጀምሮ በነበረው እና መላው ኦሮሚያ ክልልን ያዳረሰው ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ የደረሰው ሰብዓዊ ጉዳት ልዩ የምርመራ ሪፖርት መግለጫ ይፋ ሆነ፡፡ ልዩ መግለጫው ይፋ የሆነው መጋቢት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. አዲስ አበባ በሚገኘው የሰመጉ ዋና ጽህፈት ቤት ሲሆን፤ መግለጫውም የ103 ዜጎች ህይወት መጥፋቱን አስታውቋል፡፡

ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) ይባል የነበረውና በኋላም የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ(ሰመጉ) እየተባለ የሚጠራው ብቸኛው ሀገር በቀል መነግሥታዊ ያልሆነ ገለልተኛ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅት ሲሆን፤ ባለፉት አራት ወራት በተጀመረውና እስካሁንም በቀጠለው የኦሮሚያ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ የሰብዓዊ ጉዳት ቀዳሚውን ልዩ መግለጫ ይፋ አድርጓል፡፡ ሰመጉ በ140ኛው የተቋሙ ሪፖርት “የኦሮሚያ ክልል በ18 ዞኖች እና በ342 ወረዳዎች የተከፋፈለ ሲሆን ሰመጉ ከ9 ዞኖች ውስጥ በ33 ወረዳዎች ብቻ ባደረገው የመስክ ምርመራ ባገኘው ውጤት መሰረት 103 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን 57 ሰዎች በጥይት የመቁሰል እና ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡” ብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተገደሉትና ከቆሰሉት በተጨማሪ በ22 ሰዎች ላይ ማሰቃየት እና ድብደባ መፈፀሙን፣ 84 ሰዎች መታሰራቸውን እንዲሁም 12 ሰዎች የደረሱበት ወይም ያሉበት አለመታወቁንም ጠቁሟል፡፡

TPLF victims in Oromia region

ሰመጉ 34 ገፅ ባለው ልዩ መግለጫው እንዳስታወቀው ከሆነ፤ የደረሰው የሰብዓዊ ጉዳት ምርመራ የሚያካትተው ከህዳር 2 ቀን እስከ የካቲት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. የደረሱ የሰብዓዊ ጉዳቶች ብቻ መሆኑን አስታውቋል፡፡ በተለይ በምርመራ ወቅት ድርጅቱ የጋጠሙትን ችግሮችም የጠቀሰ ሲሆን በተለይም የገንዘብ ፣ የሰው ኃይልና የምርመራ መሳሪያ እጥረት፣ በሀገሪቱ ያለው የፖለቲካ ሁኔታ ውጥረት የተሞላበት በመሆኑ በኦሮሚያ ክልል በተከሰተው ቀውስ እንደልብ ተዘዋውሮ ለመስራት አለመቻል፣የመንግሥት የደህንነት እና የፀጥታ ኃይሎች ከፍተኛ ጫና እና ክትትል ማድረጋቸው፣ ሕዝቡ ከፍተኛ ፍርሃት ውስጥ በመግባት ማንንም ሰው አለማመን እና መረጃ ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆን ዋነኞቹ መሆናቸው ጠቅሷል፡፡

በክልሉ አሁንም በተለያዩ ቦታዎች ተቃውሞች መቀጠላቸውንም በመጥቀስ፣ ማንኛውም የሰብዓዊ መብት የሚመለከተው አካል የኢትዮጵያ መንግሥት የዜጎችን ሰብዓዊ መብት እንዲያከብር፣ እንዲያስከብርና እንዲያስጠበቅ ጫና እንዲያደርጉ ጠይቋል፡፡

ሙሉ መግለጫውን ከዚህ ቀጥሎ ያለውን መስፈንጠሪያ (ሊንክ) በመጠቀም ያገኙታል፡- http://ehrco.org/wp-content/uploads/2016/03/The-Human-Rights-Council-HRCO-140th-Special-Report-Amharic-Scanned-March-14-2016.pdf