Category Archives: Social and Culture

የኦሮሞ ቻርተር ጉዳይ ወዴት ያደርሰናል?

semahegn-gashu

ሰማሀኝ ጋሹ (ዶ/ር)

የኦሮሞ ቻርተርና ወታደራዊ ክንፍ መቋቋምን በተመለከተ የሚመክር በአትላንታ የሚካሄድ ስብሰባ ዜና እና ሰነድ ይፋ ከተደረገ በሗላ በተለያዩ ወገኖች ዘንድ ጥርጣሬና ጥያቄ አስነስቷል። ጋዜጠኛ ሳዲቅ አህመድ አቶ ጃዋርንና ፕ/ር ህዝቄልን የኦሮሞ ቻርተርን በተመለከተ ውይይትም አካሂዷል። በውይይቱ ወቅት የመገንጠል ጥያቄዉን በተመለከተ ጥሩ ማብራርያ የተሰጠ ቢሆንም አሁንም በርካታ መልስ የሚሹ ጉዳዮች አሉ። በተለይ አትላንታ ይካሄዳል ተብሎ የታሰበዉን ስብሰባ በተመለከተ የወጣዉ መግለጫ በብዙዎች ዘንድ ያልተጠበቀ ነገር ነዉ። በጎንደር በተካሄዳዉ የተቃዉሞ ሰልፍ ወቅት ህዝቡ ‘ የኦሮሞ ደም የኛ ደም ነዉ’ ፥ ‘ በቀለ ገርባ መሪያችን ነዉ’ በማለት ለኦሮሞ ህዝብ የተቃዉሞ እንቅስቃሴ ያለዉን አጋርነት ከገለፀ በሗላ በህዝቦች መካከል የነበረዉንና በህወሓት ለዘመናት የሚዘወረዉን የከፈፍልህ ግዛ (divide and conquer) ፖለቲካ በማዳከም ከፍተኛ የትግል አንድነት ያመጣ መሆኑ ይታወቃል። ህዝቡ ይህንን የተፈጠረዉን አንድነት የሚያጠናክር የፖለቲካ ሀይሎች የጋራ መድርክ ሲጠብቅ የተናጥል ስብሰባ መጠራቱ በብዙዎች ዘንድ ጥርጣሬ መጫሩ የሚጠበቅ ነዉ። ከዚህ አኳያ የተፈጠረዉን የህዝብ አንድነት ሊያጠናክር የሚችል ስራ ላይ ማተኮር ሲገባ የተናጠል የስብሰባ ጥሪ መጠራቱ በጋራ ትግሉ ላይ የራሱን ተፅእኖ ማሳደሩ የማይቀር ነዉ።

ከዚህ የከፋዉ ደግሞ የቀረበዉ ሰነድ ስለ ህዝቡ የጋራ ትግልና የደረሰበትን ደረጃ ጨርሶ አያነሳም። ሰነዱ ወደፊት የኦሮሞ ህዝብ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ስርአት ዉስጥ የሚኖረዉን ሚና በተመለከተም ምንም አይነት ፍንጭ ያልሰጠ ሲሆን የኦሮሞን ህዝብ በደሴትነት ተነጥሎ የተቀመጠ ያስመስለዋል። እንደዉም ሰነዱ የኦሮሞ ህዝብ ከኢትዮጵያ ጋር ያለዉን ግንኙነት የቅኝ ግዛት አድርጎ ያቀርበዋል። የቅኝ ግዛት ትንታኔዉን (colonial thesis) በርካታ የኦሮሞ ምሁራንና ፖለቲከኞች እንደማይደግፉት እየታወቀ ሁሉንም የኦሮሞ መሪዎች ላማሰባሰብ ያለመ ሰነድ ለምን ያአንድ ወገን አቋም ብቻ ለማንፀባርቅ እንደፈለገ ግልፅ አይደለም። የኦሮሞ ህዝብ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ያለዉን ግንኙነት የቅኝ ግዛት ጥያቅ እንዳልሆነ የሚያምኑትን የኦሮሞ ፖለትከኞችና ምሁራን የሚያገል ያሰመስለዋል። የኦሮሞን ህዝብ ቅኝ እንደተገዛ አድርጎ ማቅረቡ የኦሮሞ ህዝብ ከሌላዉ ህዝብ ጋር ያለዉን የባህልና የታሪክ ትስስርና የኦሮሞ ህዝብ ለኢትዮጵያ አንድነትና ህልዉና ያበረከተዉን አስተዋፅኦ የሚያሳንስ ነዉ። ከዚህም በተጨማሪ ይህን አይነቱ ትንታኔ አንዱን ማህበረሰብ ጨቋኝ ሌላዉን ተጨቋኝ በማድረግ የሚቀርበዉን የታሪክ ትንታኔ ህያዉ ሆኖ እንዲቆይ የሚፈልግ ያስመስለዋል። ይህም እስካሁን የሄድንበትን የጋራ አለመተማመን (mutual suspicion) በማስቀጠል ልንፈጥረዉ ለምናስበዉ ዴሞክራሲያዊ ስርአት እንቅፋት ይሆናል።

በተለይ በኢትዮጵያን አንድነትና በግለሰብ መብት ላይ የተመሰረተ የፖለቲካ ስርአት እንዲቋቋም የሚፈልጉ ዜጎችን የቀድሞዉ ስርአት ናፋቅዎችና ምኒልካዉያን እየተባለ መስደብ የተለመደ ነዉ። ያሁኑን ተዉልድ የፖለቲካ አስተሳሰብ መተቸት ካስፈለገ በራሱ በትዉልዱ አስተሳሰብ ላይ ተመስርቶ መተቸት ሲገባ ከቀደሙት ስርአቶች ጋር በማያያዝ አንገት ለማስደፋት የሚደረገዉ እንቅስቃሴ ያደባባይ ሚስጥር ነዉ። የዚህ ፅሁፍ አቅራቢ ከወራት በፊት ያደረገዉን የሬድዮ ዉይይት አስመልክቶ የቀድሞዉ ስርአት ናፋቂ የሚል ስድብና ዛቻ የኦሮሞ አክቲቪስቶች ነን ከሚሉ ወገኖች አስተናግዷል። ለዚህም ነዉ የአማራ ወጣቶች ሁሉም የብሄር ድርጅቶች አማራን በጠላትነት የሚፈርጁ በመሆኑ ተደራጅተን እራሳችንን እንከላከል እያሉ ያሉት። ምንም እንኳን ያለፈዉን ታሪካችንን በተመለከተ ብሄራዊ መግባባት ላይ መድረስ አስቸጋሪ ሊሆን ቢችልም እንዲህ አይነት የታሪክ ትንታኔዎችን ለፖለቲካ ፍጆታ ባለመጠቀም የተሻለ የፖለቲካ ድባብ ለመፍጠር ጥረት እንዳልተደረገ ግን ከቀረበዉ ሰነድ መረዳት ይቻላል።

ከዚህም በጠጨማሪ የቀረበዉ ሰነድ ባለፉት አስርተ አመታት የብሄረሰቦችን እኩልነት ለማምጣት የተሄደበትን መንገድ፥ ዉጤቱንና ችግሮቹን ሳያነሳ የኦሮሞ ህዝብ ከዛሬ አርባ አመት በፊት በነበረበት ሁኔታ እንዳለ አድርጎ ያቀርበዋል። ከሁሉም ብሄረሰቦች የተወጣጡ ወጣቶች በተማሪዎች እንቅስቅሴ ወቅት ያነሱት የመሬት ላራሹና የራስን እድል በራስ የመወሰን ጥያቄ በደቡብ ኢትዮጵያ የነበረዉን የጭሰኝነት ስርአት ያስወገደ ሲሆን ይህም ለኦሮሞ ህዝብ ታላቅ ለዉጥ አምጥቷል። ደርግም ሆነ ወያኔ ስታሊናዊ በሆነ መንገድ ችግሮቹን ለመፍታት የሄዱበት መንገድ ዉጤቱ አመርቂ ባይሆንም ሙከራዎች ግን ተደርገዋል። ይህ ሁሉ የፖለቲካ ለዉጦች በተካሄዱበት ሀገር አሁንም ቅኝ እንደተገዛን ነን የሚል እድምታ ያለዉ አቀራረብ በጣም ጨለምተኛና ካላፈዉ ስህተቶች ተምሮ የቀረዉን የእኩልነት ጥያቅ ለማሳካት በሚያስችል መልኩ አለመቀረፁ በኢትዮጵያ ያለዉን አስቸጋሪ የፖለቲካ ሁኔታ ለመፍታት ያለዉን ቁርጠኝነት ዉሱን ያስመስለዋል።

የኦሮሞ መሪዎች ስብሰባ ያስፈለገበትን ምክንያት አቶ ጃዋር ሲያስረዳ ወደፊት ለሚደረገዉ የሽግግር ወቅት እያንዳንዱ ማህበረሰብ የራሱን ቻርተር አዘጋጅቶ መምጣት ስላለበት የኦሮሞን ቻርተር ለማዘጋጀት በማስፈለጉ ነዉ ይላል። ለዚህም የደቡብ አፍሪካዉን ብሄራዊ ኮንግረስና የህንዱ ጃዋራላል ኔህሩ በትግል ወቅት እንዲህ አይነት ቻርተር አዘጋጀተዉ ነበር ሲል ያስረዳል አቶ ጃዋር። እያናንዳንዱ ማህብረስብ የራሱን ቻርተር አዘጋጅቶ ይምጣ ከተባለ ሁሉም ብሄረሰቦች አንዳንድ ቻርተር በማዘጋጀት ሲመጡ ቢያንስ ከ 80 ያላነሱ ቻርተሮች ተዝጋጅተዉ ሊቀርቡ ነዉ ማለት ነዉ( ያዉም እያንዳንዱ ማህበረሰብ በአንድ ድርጅት ይወከላል ብለን ካሰብን ነዉ።) እንዲህ ያለ ሁኔታን እንዲኖር መፈለግ አላማዉ ዴሞክራሲያዊ ስርአት ወይስ የባቢሎንን ግንብ ለመገንባት ነዉ? ሁሉም ብሄር የራሱን መብት እንዲከበር በሚል በሚያደርገዉ ፍላጎት ሁሉንም የሚያረካ መፍትሄ ማግኘት የሚክብድ ከመሆኑም በተጨማሪ የፈለገዉን ያላገኘዉ ወገን ‘የራሴን እድል በራሴ’ እወስናለሁ ወደሚል ሌላ ዙር ግጭት ይገባል። በተለይ ወታደራዊ ክንፍ ያለዉ የብሄር ድርጅት የሚበረታታ ከሆነ በጉልበት የፈለገዉን ለማድረግ ማንገራገሩ የማይቀር ነዉ። ወያኔም በ1983 ዓም ባደረገዉ የሽግግር መንግስት ምስረታ ወቅት በብሄር የተደራጁትን ብቻ ተቀብሎ ህብረ ብሄር የሆኑትን ግን አልቀበልም ነበር ያለዉ። ለዚህም የተማመነዉ የነበረዉን ጉልበት ነዉ። ኦነግንም ከሽግግሩ መንግስት እንዲወጣ ያደረገዉ ይሄዉ የወያኔ እብሪተኝነት ነዉ። አሁንም በብሄር ተደራጅታችሁ የራሳችሁን ቻርተር አዘጋጅታችሁ ኑ ማለት ተመሳሳይ አካሄድ ያለዉ ነዉ። በርካታ ማህበረሰቦችም በተለያየ ምክንያት ተደራጅተዉ ቻርተር አዘጋጅተዉ ላይቀርቡ ይችላሉ። በዚህ ጊዜ የነዚህ ማህበረሰቦች እድል ቻርተር አዘጋጅተዉ በመጡት ሊወሰን ነዉ ማለት ነዉ? ይህስ አካሄድ ወያኔ በ1983 ካደረገዉ በምን ይለያል? ወታደራዊ ክንፍ ያላቸዉ የፖለቲካ ሃይሎች እኛ ባልነዉ ካለተስማማችሁ ዞር በሉ ቢሉ ዋስትናዉ ምንድን ነዉ? አልሸሽም ዞር አሉ እንደሚባለዉ ተመልሶ ወደ ግጭት አያስገባንም ወይ?

አቶ ጃዋር ያቀረባቸዉ የደቡብ አፍሪካ፤ ህንድና ቱኒዝያ ምሳሌዎች አሁን ከተጠራዉ የኦሮሞ የነፃነት (freedom) ቻርተር ጉዳይ በጣም የተለዩ ናቸዉ። በነዚህ ሃገሮች የቀረቡት የነፃነት (freedom) ቻርተሮች ሆነ ድርድሮች ሃገራዊና የሁሉንም ማህበረሰብ ፍላጎት የሚያንፅባርቁ እንጂ የአንድ ብሄርን ብቻ የሚመለከቱ አልነበሩም። እንዲሁም በህንድ የተካሄደዉ የፀረ ቅኝ ግዛት ትግልና በደቡብ አፍሪካ የተካሄደዉ የፀረ አፓርታይድ ትግል አሁን ኢትዮጵያ ዉስጥ ካለዉ የፖለቲካ ሁኔታ ጋር ያላቸው ዝምድናና እና ልዩነት በግልፅ አልቀረበም ። የምናቀርባቸዉ ምሳሌዎች ተገቢ ትርጉማቸዉን የያዙ ቢሆኑ የምናቀርበዉን ሃሳብ ተአማኒነት ያጠናክረዋል። አቶ ጃዋር ስለ ቱኒዝያ የተናገረዉም እኛ እየሄድንበት ካለው ጋር የሚገናኝ አይደለም። ከሌሎች አብዮት ከተካሄደባቸዉ የአረብ ሃገራት በተለየ የተሻለ የፖለቲካ ሽግግር በቱንዝያ የተፈጠረዉ እንደ ሊቢያና ሶርያ በሃይማኖትና በጎሳ ለመከፋፈል ባለመፍቀዳቸዉ ነዉ። ወታደራዊ ክንፍ ያላቸዉ የብሄር ድርጅቶችን የምናበረታታ ከሆነ ግን ለጊዜዉ በአንድ ጠላት ላይ ሲያተኩሩ ልዩነት የሌላቸዉ የሚመስሉ የፖለቲካ ህይሎች ያ ጠላት ከስፈራዉ ሲነሳ እርስ በርሳቸዉ መበላላታቸዉ የማይቀር ነዉ። ሊብያ ዉስጥ በተካሄደዉ አብዮት ወቅት ሁሉም ጎሳዎች ጋዳፊን ለመጣል ሰምና ወርቅ ሆነዉ ከሰሩ በሗላ አሁን ሁሉም በየፊናዉ ወታደራዊ ቀጠና አቋቁሞ እየተጋጨ ሲሆን ማዕከላዊ መንግስት በስምምነት ለመመስረት አልቻሉም።

በእዉነት የኢትዮጵያን የፖለቲካ ችግሮች ለመፍታት ቅንነቱና ቁርጠኝነቱ ካለ እንደ ኑክልየር ሳይንስ ዉስብስብ ስላልሆነ 80 ቻርተር ማዘጋጀት አያስፈልገዉም። የኢትዮጵያ የፖለቲካ መሰረታዊ ችግሮች እንዴት ብሄራዊ አንድነትንና የብሄር መብትን፥ የግለሰብና የቡድን መብትን አጣጥመን እንቀጥል፥ እንዴት ብሄራዊ መግባባትን እንፍጠር፥ ዴሞክራሴያዊ ባህልና ተቋማት እንዴት እንገንባና ማህበራዊና ኤኮኖምያዊ ፍትህ እንዴት እናረጋግጥ የሚሉት ናቸዉ። እነዚህን የፖለቲካ ጥያቄዎች ለመመለስ ዋናዉ መነሻ የተናጥል አካሄድን በተቻለ መጠን በማስቀረት ሁሉም የፖለቲካ ሃይሎች በጋራ የሚመክሩበትን ሁኔታ ማመቻቸት ነዉ። ነገር ግን አሁንም የሽግግር ሂደቱን በበላይነት ለመቆጣጠር የሚካሄደዉ ፉክክር ስር የሰደደዉን የፖለቲካ ሃይሎች አለመተማመን እንዲቀጥል የሚያደርገዉ ከመሆኑም በተጨማሪ የግጭትንና የእኔ አውቅልሃለሁን የቆየ የፖለቲካ ባህል ለመለወጥ የሚኖረዉን እድል ያደበዝዘዋል።

የአምቦ ዩኒቨርስቲ መምህር እና ብሎገር ስዩም ተሾመ ታሰረ

ስዩም ተሾመ

seyoum-teshome

በአምቦ ዩኒቨርስቲ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ ወሊሶ ግቢ መምህር እና ብሎገር ስዩም ተሾመ ታሰረ፡፡ መምህር እና ብሎገር ስዩም ተሾመ ከሚኖርበትና ከሚሰራበት ወሊሶ ከተማ ዛሬ ቅዳሜ መስከረም 21 ቀን 2009 ዓ.ም. በፀጥታ ኃይሎች ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ መታሰሩ ተጠቁሟል፡፡ ስዩም ተሾመ በአምቦ ዩኒቨርስቲ ወሊሶ ግቢ የማናጅመንት ትምህርት ክፍል ኃላፊ እና መምህር ሲሆን፤ ከማኀበራዊ ሚዲያ በተጨማሪ በ ”ኢትዮቲንክታንክ” እና የገዥው ስርዓት ደጋፊ እንደሆነ በሚታወቀው ”ሆርንአፌይርስ” ድረ-ገፅ ጭምር በመፃፍ ይታወቃል፡፡

በተለይ ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በመንግሥት እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረው አለመግባባት ችግሮች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ እና ሌሎች ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የተለያዩ መፍትሄ ሊሆኑ ይችላሉ ያላቸውን ምክረ ሐሳቦችን በመሰንዘርም ይታወቃል፡፡

10ኛ ወሩን ባስቆጠረው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ በአማራ እና በደቡብ ኮንሶ ተከታታይ ህዝባዊ ተቃውሞች መቀጠላቸውን ተከትሎ ከ820 ያላነሱ ሰላማዊ ዜጎች በፀጥታ ኃይሉ ወታደራዊ ርምጃ ሲገደሉ፤ በሺህዎች የሚቆጠሩ ቆስለው፣ በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ታፍነው ታስረዋል፡፡ ከተገደሉ፣ ከቆሰሉና ከታሰሩት መካከል ህፃናት እና አዛውንት፣ መምህራን፣ ጋዜጠኞችና ብሎገሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች እና ተማሪዎች ይገኙበታል፡፡ በተለይ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ፤ በተለያዩ ኦሮሚያ እና አማራ ክልል ከተሞችና ወረዳዎች የመንግሥት ግድያና እስር እንደቀጠለ ነው፡፡

የኮንሶ ብሔረሰብ የዞን ምሥረታ ጥያቄ ከሕግ አንጻር ሲፈተሸ

woubeshet-mulat

ውብሸት ሙላት

ኮንሶ፣ በደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልል በሰገን ሕዝቦች ዞን ውስጥ የምትገኝ ወረዳ ናት፡፡ ቀደም ሲል ግን ልዩ ወረዳ ነበረች፡፡ ኮንሶ አስተዳደር እርከን ብቻ ብቻ አይደለችም፤ብሔረሰብም ጭምር እንጂ! የሰገን ሕዝቦች ዞን ደግሞ በፊት የኮንሶ፣ የደራሼ፣ የአማሮ እና የቡርጂ ልዮ ወረዳዎች የነበሩትን በማጠቃለል የተመሠረተ ነው፡፡

በደቡብ ክልል ሕገ-መንግሥት መሠረት ልዩ ወረዳ ከዞን ጋር አቻ ሥልጣን አለው፡፡ ተጠሪነቱም ቀጥታ ለክልሉ ነው፡፡ ልዩ ወረዳ፣ ብዙ ጊዜ በአንድ ብሔር ብቻ ስለሚመሠረት የአንድ ብሔር ብቻ አባላት ያሉበት የወረዳ ምክር ቤት ይኖረዋል፡፡ የራሱ የልዩ ወረዳው የሥራ ቋንቋ እንዲኖረው መወሰን ይችላል፡፡ በዞን ደረጃ የሚኖሩትን መንግሥታዊ መዋቅሮችን በወረዳው በማቋቋም በርካታ የብሔረሰቡ ተወላጆች የሥራ ዕድል እንዲኖራቸው ያስችላል፡፡

መደበኛ ዞኖች ሕግ አውጪ የላቸውም፡፡ የዞን ሥራ አስፈጻሚዎችም የሚሾሙት በቀጥታ በክልሉ ሥራ አስፈጻሚ በመሆኑ የክልል ውክልና እንጂ በምርጫ የተገኘ ሥልጣን አይደለም፡፡ ወረዳዎችም ቢሆኑ ለአስተዳደር ቅልጥፍና፣ ድጋፍና ክትትል ሲባል በተጨማሪነት ለዞን ተጠሪነት ያለባቸው ቢሆንም ይህ ሁኔታ የመነጨው የክልሉ አስፈጻሚ አካላት በሚሰጠው ውክልና ላይ ተመሥርቶ እንጂ ሕገ-መንግሥታዊ መነሻ የለውም፡፡ ለዚያም ነው የወረዳ አስተዳዳሪዎችና ከንቲባዎች በዞን አስተዳዳሪዎች የማይሾሙትም ሆነ የማይወርዱት፡፡

በልዩ ዞኖች ግን የብሔረሰብ ምክር ቤት ስላላቸው፣ የዳኝነት መዋቅርና ሹመት በክልል ደረጃ ቢከናወንም እንኳን ከዞኑ የሚጠቆሙትና የሚሾሙት ዳኞች ላይ አስተያየት የመስጠት መብት አላቸው፡፡

የኮንሶ ብሔረሰብ፣ የዞንነት ጥያቄ በማንሳት ተቃውሞ ከጀመረ አንድ ዓመት አለፈው፡፡ ከተቃውሞው ጋር በተያያዘ ቀላል የማይባል የሰው ሕይወት ጠፍቷል፡፡ የክልሉ የኮሚኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ሓላፊ ለአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ በቅርቡ በተናገሩት መረጃ እንኳን ከ1500 ቤቶች በላይ ተቃጥለዋል፡፡ ከአንዳንድ መገናኛ ብዙኃን እንደሚሰማው የዞንነት ጥያቄው ካልተሳካ ወደ ኦሮሚያ ክልል የመካለል ጥያቄንም በአማራጭነት ሕዝቡ እያነሳ ነው፡፡

ይህ ጽሑፍ ዞን የሚመሠረትበትን ሕጋዊ አሠራር ይፈትሻል፡፡ የራስን ዕድል በራስ ከመወሰን መብት ጋር የሚኖረውን ግንኙት በማየት የኮንሶ ብሔረሰብ ጥያቄ ከክልሉ እና ከፌደራሉ ሕገ-መንግሥት እንዲሁም ከሌሎች አግባብነት ካላቸው ሕጎች አንጻር ዳሰሳ ያደርጋል፡፡ እግረ-መንገዱንም አንድ ወረዳ ወይንም ሌላ አስተዳደረዊ መዋቅር ከአንድ ክልል ወደ ሌላ ክልል መጠቃለል የሚችልበትን ሕገ መንግሥታዊ ሁኔታም ካለ ምጥን ፍተሻ ያደርጋል፡፡

ኮንሶ ከሌሎች ዞኖች ጋር በሕዝብ ብዛት ስትነጻጸር፤

የኮንሶን የዞን ምሥረታ ጥያቄን በአግባቡ ለመረዳት በኢትዮጵያ ውስጥ ካሉት ዞኖች ጋር፣ በ1999 ዓ.ም. የተደረገውን የሕዝብና ቤት ቆጠራን መሠረት በማድረግ እናነጻጽራለን፡፡ በዚህ የሕዝብና ቤት ቆጠራ ውጤት መሠረት የኮንሶ ልዩ ወረዳ ወደ 235 ሺህ የሚጠጋ ሕዝብ ነበረው፡፡ የዛሬ አስር ዓመት የነበረው የወረዳው ሕዝብ ብዛት ማለት ነው፡፡ ከወረዳው ውጭም የሚኖሩትን ጨምሮ፣ የኮንሶ ብሔረሰብ ብዛት ከ250 ሺህ በላይ ነው፡፡ ዞን ለመመሥረት በአንድ አካባቢ መኖርን ስለሚጠይቅ፣ ለዞን ምሥረታ ጥያቄው ተገቢው ቁጥር መኖር ቅድመ-ሁኔታ ነው ማለት ይቻላል፡፡

የኮንሶ ወረዳ ሕዝብ፣ ከሀረሪ ክልል ሕዝብ ይበልጣል፡፡ የዛሬ አስር ዓመት የክልሉ ሕዝብ ብዛት፣ ገና 200 ሺህ እንኳን አልሞላም ነበር፡፡ የኮንሶ ወረዳ በሕዝብ ብዛት፣ ከትግራይ ክልል የመቀሌ ልዩ ዞንን፣ ከአፋር ክልል የዞን ሦስት እና አምስትን፣ ከአማራ እና ከኦሮሚያ ክልሎች ከዞኖች ጋር አቻ ከሆኑት የባሕር ዳር፣ የደሴ፣ የጎንደር፣ የአዳማ እና የጅማ ከተሞችን፣ ከቤኒሻንጉል-ጉሙዝ፣ የካማሼ ዞንን፣ የጋምቤላ የሁሉንም ዞኖችን፣ እንዲሁም ከራሱ ከደቡብ ክልል ደግሞ የሸካ ዞንን በሕዝብ ብዛት ይበልጣል፡፡ የጋምቤላ ክልል ከኮንሶ ሕዝብ ወደ 80 ሺህ በሚጠጋ ቁጥር ብቻ ነው የሚበልጠው፡፡

konso-karat-town

ራስን በራስ የማስተዳደር መብት፤

የኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 89(1)፣ መንግሥት በዴሞክራሲያዊ መርሆች ላይ በመመሥረት ሕዝቡ በሁሉም ደረጃዎች ራሱን በራሱ የሚያስተዳደርበትን ሁኔታ ማመቻቸት ያለበትን ስለመሆኑ የፖለቲካዊ ፖሊሲው በጥቅሉ አስቀምጦታል ፡፡ ማንኛውም የብሔርነት፣ የብሔረሰብነት ወይንም ደግሞ የሕዝብነት ዕውቅና ያገኘ ማኅበረሰብ ራሱን በራሱ የማስተዳደር መብቱን ተግባራዊ የሚያደርግበትን አስተዳደራዊ መዋቅር የመመሥረት ገደብ የሌለው ሕገ-መንግሥታዊ መብት እንዳለው የፌደራሉም የክልሎችም ሕገ መንግሥት አንቀጽ 39 (3) ላይ ተደንግጓል፡፡

ራስን የማስተዳደር ሙሉ መብት በክልል ላይ ብቻ የተንጠለጠለ አይደለም፡፡ ይህ መብት ውጤታማ እንዲሆን ያልተማከለ አስተዳደር ተግባራዊ መሆን አለበት፡፡ ያልተማከለ አስተዳደርን እንደ አንድ ፕሮግራም ብናየው ብዙ የሚያካትታቸው ነጥቦች አሉት፡፡ ከሚያካትታቸው ነጥቦች ውስጥ በባሕርያቸው የአካባቢው መንግሥት ሥልጣንና ሥራ የሆኑትን ለአካባቢው መተው፣ እንዲሁም ባሕርያቸው አካባቢያዊ ባይሆኑም እንኳን እነሱ ቢፈጽሟቸው የሚሻል ከሆነም ለአካባቢው መንግሥት መተው አለባቸው፡፡

እንዲህ መሆኑ ከታመነበት ግጭትን ለመቀነስም ሆነ በልበ-ሙሉነት ለመሥራት ሲባል ሥልጣንና ተግባራቸው በግልጽ ተለይቶ መቀመጥን ይፈልጋል፡፡
የአካባቢ መንግሥታት (Local Government) የራሳቸውን ጉዳይ በራሳቸው የመጨረስ፣ ፖሊሲ የመንደፍ፣ ለፖሊሲያቸው የሕግ ማዕቀፍ የመስጠት የመጨረሻ የሥልጣን ባልተቤት መሆን ያሻቸዋል፡፡

አካባቢያዊ መንግሥታት፣ አስተዳደራዊ ተቋሞችን የማቋቋምና ለሥራ ምቹ በሚሆን መንገድ በነጻነት የማዋቀርና የሰው ሃይል የመቅጠርም የማባረርም ሥልጣንን ይይዛል፡፡ ስለሆነም አካባቢያዊ መንግሥታት ፖለቲካዊ፣ የገቢና ወጭ፣ እንዲሁም አስተዳደራዊ ሥልጣንን ያካትታል ማለት ነው፡፡ ይህ አሠራር የማእከላዊ መንግሥት ድጋፍና ቁጥጥር እንዲሁም በይነመንግሥታዊ ትብብርንም አያስቀርም፡፡

ፖለቲካዊ ራስ ገዝነት ባልተማከለ አስተዳደርም ይሁን ራስን በራስ በሚያስተዳድሩ ብሔሮች ዘንድ ቁልፍ የሆነ ጉዳይ ነው፡፡ ማእከላዊም ይሁን የክልል መንግሥታት ባሰኛቸው ጊዜ የሚያፈርሷቸው ሲመቻቸው ደግሞ የሚያቋቁሟቸው ልዩ ዞኖች፣ ወረዳዎች፣ ቀበሌዎች ሊኖሩ አይገባም፡፡ ቀጣይ መሆን አለባቸው፡፡ በመኖርና በመፍረስ በስጋት እየወላወሉ የሚኖሩ ተቋማት ሊሆኑ አይገባቸውም፡፡ ወይንም ደግሞ እንዴት እንደሚቋቋሙም ይሁን እንደሚፈርሱ ግልጽ ሕግ፣ሁሉም የተስማሙበት ኖሮ በዚያው መሠረት መፈጸም አለበት፡፡ የኮንሶ ነገርም፣ በአንድ ወቅት ልዩ ዞን የነበረች ሲሆን አሁን ግን መደበኛ ወረዳ ብቻ በመሆን በሰገን ሕዝቦች ሥር ትገኛለች፡፡

በሕገ-መንግሥቱ በአንቀጽ 50(4) ከተገለጸው አንጻር ቋሚነት አላቸው ማለት ቢቻልም በተግባር እንደታየው ግን፣ ከ1994 ዓ.ም. በፊት ይህ ዓይነት ሥልጣን የሌላቸው ሲሆን፣ በኋላ ደግሞ መለወጡ ብሎም በአንዳንድ ክልሎች ሥልጣናቸው በሕገ-መንግሥት ሳይሆን በአዋጅ መገለጹ ወይንም በግልጽ አለመቀመጡ አጠራጣሪ አስመስሎታል፡፡

በተጨማሪም እንዴት ወረዳዎች እንደሚመሠረቱና እንደሚታጠፉ፣ ድንበራቸው እንደሚካለልና እንደሚደካ አለመገለጹ፤ መሥፈርቶቹን አንዳንድ ክልሎች በአዋጅ (ለምሳሌ ደቡብና ኦሮሚያ) ሌሎቹ ደግሞ ለአስፈጻሚው አካል መተው (ለምሳሌ ቤኒሻንጉል ጉሙዝና አማራ) ጉራማይሌ አድርገውታል፡፡ በመሆኑም ለልዩ ዞኖችም ይሁን ወረዳዎች የተሻለ ዋስትና መስጠት ያስፈልጋል፡፡ የዚህ ዋስትና አለመኖር ነው ኮንሶን በአንድ ወቅት ልዩ ወረዳ፣ በሌላ ጊዜ መደበኛ ወረዳ በመሆን ምንአልባትም ለተለያዩ ተቃውሞዎች መነሻ የሆነው፡፡

የልዩ ዞንና ወረዳ ምሥረታ ሂደት፤

በሽግግሩ ዘመን ሥራ ላይ በነበረው አዋጅ ቁጥር 7/1984 መሠረት ወረዳን ጨምሮ ወደ ላይ ያሉ መስተዳድሮችን ማቋቋም የማይችሉት በግልጽ ተዘርዝረው ነበር፡፡ በሕገ-መንግሥቱ ይህ ገደብ ተነስቷል፡፡ በተጨማሪም ክልል መመሥረት እንደመገንጠል ሁሉ ገደብ የለውም፡፡ ለነገሩ ክልል መመሥረትም ጉዳዩ ከክልል መሆኑ ነው እንጂ ያው መገንጠል ነው፡፡ ገደብ አለመኖሩን ለማመልከት “በማናቸውም ጊዜ” የሚል ቃል ተጠቅሟል፡፡

በሕገ-መንግሥቱ እንዲህ ዓይነቱ “መድልኦ” ተወግዷል ብንልም እንኳን በጋምቤላ አኙዋ፣ ኑዌርና መዠንግር ልዩ ዞን ሊያቋቁሙ እንደሚችሉ ሲገለጽ ኡፖና ኮሞ አይችሉም በማለት የክልሉ ሕገ-መንግሥት ገልጿል፡፡ በዚህም ከብሔረሰቦች መርጦ ለዞንና ለወረዳ አለ ማለት ነው፡፡ ቁጥራቸው አናሳ (በ1999ኙ ዓ.ም. በተደረገው ቆጠራ በክልሉ ውስጥ የሚኖሩት ማኦ 64፣ ኡፖ ደግሞ 990) መሆናቸው አንድ ነገር ሆኖ በሕገ-መንግሥት መከልከል ደግሞ ሌላ ነገር ነው፡፡

የአሁኑ ደቡብ ክልል ከመመሥረቱ በፊት አራት ክልሎች ነበሩ፡፡ አንድ ክልል ከሆኑ በኋላ ዞኖችና ወረዳዎች በተለያዩ ጊዜያት እንደገና ተዋቅረዋል፡፡ ለምሳሌ ሰሜን ኦሞ (ወላይታ፣ ጋሞ-ጎፋ፣ዳውሮ) ወደ ሦስት ብሔረሰብ ዞኖች ተከፋፈለ (ወላይታ፣ ጋሞ-ጎፋ እና ዳውሮ ) ተብለው፡፡ እንዲሁም ሁለት ልዩ ወረዳዎች ተጨመሩ ባስኬቶና ኮንታ፡፡ ሌላ ካፋ-ሸካ የሚል እንደ አንድ ልዩ ዞን ቢቋቋሙም ውሎ አድሮ ካፋ እና ሸካ ልዮ ዞኖች ተብለው ራሳቸውን ቻሉ፡፡ ቤንችና ማጂ ይባሉ የነበሩት ሁለት ዞኖች፣ ኋላ ላይ ቤንች-ማጂ ተብለው አንድ ዞን ሆኑ፡፡ ስልጤ ዞንም ከጉራጌ ተነጥሎ ራሱን ቻለ፡፡ ቀደም ሲል ስምንት ልዩ ወረዳዎች የነበሩ ሲሆን አሁን አራቱ (ኮንሶ፣ደራሼ፣ ቡርጂ እና አማሮ) በአንድነት ሰገን ዞንን መሥርተዋል፡፡

ቋንቋ፣ማንነት፣ የአሰፋፈር ሁኔታና ፍቃደኝነት ላይ መሠረት በማድረግ የሚቋቋሙ አካባቢያዊ መስተዳድሮች (local territorial autonomy) ጉዳትም እንዳላቸው የሚገልጹ አሉ፡፡ ከእነዚህም ጉዳቶች መካከል ክፍፍልን ያባብሳል፣ ክልሎች በአብዝኃኛው ወጥ የሆነ አንድ ብሔር ስለማይኖርባቸው አሁንም ቢሆን በኢትዮጵያ የአናሳና የብዙኃንን ግንኙነት ማስቆም አያስችልም፤ በተጨማሪም አሁን ባለው ሁኔታ ዞኖችና ወረዳዎች ሲዋቀሩም ይሁን ሲዋሃዱ ወጥ የሆነ የታወቀ ሕገ-መንግሥታዊ መርሕ የለውም፤ እንደገዥው ፓርቲ የፖለቲካ ግምገማና ድምዳሜ የሚወሰን ነው፤ ዘፈቀዳዊም ነው የሚሉ ክሶች ይቀርባሉ፡፡

የዞንና ምሥረታ በደቡብ፤

ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ማንነታቸው ከታወቀ እንደቡድን ማንኛውንም አስተዳደራዊ እርከን የመመሥረት መብት አላቸው ብለናል፡፡ ከደቡብ ውጭ ያሉት ክልሎች፣ በውስጣቸው የሚገኙት ነባር ብሔረሰቦች ቁጥራቸው ዝቅተኛ ስለሆነ፣ ወይ መሥርተዋል፤ አሊያም ትተዋቸዋል፡፡ መመሥረት ቢፈልጉ ደግሞ እንዴት ጥያቄያቸውን እንደሚያቀርቡ፣ ለማን እንደሚያቀርቡ፣ ምን ምን ሁኔታዎችን ማሟልት እንዳለባቸው ወዘተ የሚያሳይ ሕግ የላቸውም፡፡ ደቡብ ግን አለው፡፡

የደቡብ ክልል የብሔረሰቦች ምክር ቤት ስላለው፣ የዞንም ይሁን የወረዳ አመሠራረት ጥያቄ እንዴት መስተናገድ እንዳለበት፣ ይህንን ምክር ቤት ለማጠናከርና ሥልጣንና ተግባሩን ለመወሰን በወጣው አዋጅ ላይ ተገልጿል፡፡ ሥነ-ሥርዓቱ ከክልል ምስረታ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ልዩነቱ ጥያቄውን ያቀረበው በአስተዳደራዊ መዋቅር ተደግፎ ከሆነ (ለምሳሌ ልዩ ወረዳ የነበረው ልዩ ዞን መሆን ቢፈልግና ጥያቄው የቀረበው የወረዳው መስተዳደር ቢሆን) የመስተዳድሩ ምክር ቤት በሁለት ሦስተኛ ድምፅ ከደገፈው ወይንም ጥያቄውን ያቀረበው፤ ሕዝቡ ከሆነ (5% የሚሆነው ስምና ፊርማ አስፍሮ) ሕዝቡ በአብላጫ ድምፅ ሲደግፈው እና የክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት ሲወስን ተፈጻሚ ይሆናል፡፡

በዚህ ሕግ መሠረት ሕዝቡ በአብላጫ ድምፅ ወስኖ እንኳን ምክር ቤቱ ተጨማሪ ማስረጃ የማሰባሰብ ሥልጣን ስላለው አሰባስቦ ከመረመረ በኋላ ነው ውሳኔውን የሚያሳውቀው፡፡ ውሳኔውን ያሳውቃል ማለት ሕዝቡ በአብላጫ ድምፅ የወሰነውንም ሊሽረው ይችላል ማለት ነው፡፡ ይህ ዓይነቱ አሠራር ወለፈንድ ይመስላል፡፡ ድምፅ ሳይሰጡ ቢሆን እንኳን ይሻላል፤ ድምፅ ሰጥተው ከጨረሱ በኋላ የሌሎች ብሔረሰቦች ተወካዮች የሕዝብን ውሳኔ ካላከበሩ የት ላይ ነው ታዲያ የራስን ዕድል በራስ መወሰኑ? ይሔው ሕግ ይሔንኑ ጉዳይ በሚደነግግበት ክፍሉ ስለየራስን ዕድል በራስ መወሰን ነው የሚያወራው፡፡ በራሳቸው የወሰኑት ከተሻረ የትኛው ዕድላቸው ላይ ወሰኑ?

ሌላው ይህ ሕግ በዝርዝር ባያብራራውም በውሳኔው መሠረት ለብቻቸው ተለይተው ራሳቸውን ማስተዳደር የሚጀምሩት ብሔረሰቦች ቀድሞ ከነበሩበት ዞን ወይንም ወረዳ ፍትሐዊ የሆነ የሀብት ክፍፍል ሊያደርጉ እንደሚችሉ አስቀምጧል፡፡ ክልል ሲመሠርቱ ያልተቀመጠውን፣ በደቡብ ክልል ውስጥ ዞንና ወረዳ (ልዩም ይሁን አይሁን) ሲመሠርቱ የንብረት ክፍፍል እንዲደረግ ያስቀምጥና ስለተግባራዊነቱም የብሔረሰቦች ምክር ቤት እንደሚከታተል ገልጿል፡፡ ፌደሬሽን ምክር ቤት አዋጅ ወይንም የፌደራሉ ሕገ-መንግሥት ስለ ክልል ምሥረታ ያላስቀመጠውን በሥሩ ለሚገኙ መስተዳድሮች ማስቀመጡ ለፌደራሉም መንግሥት ትምህርት ነው፡፡

የክልሉ ብሔረሰቦች እና የፌደሬሽን ምክር ቤቶች ሚና ሲገመገም፤

ከላይ በጥቅሉ ባስቀመጥነው መሠረት የኮንሶን ጉዳይ እንመልከተው፡፡ የኮንሶ ሕዝብ ከጠቅላላው አምስት ፐርሰንት ድጋፍ ካገኘ በክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት አማካይነት ሕዝበ-ውሳኔ ይካሄዳል፡፡ የልዩ ዞንነቱን ጥያቄ አብዝኃኛው ድምጽ ሰጪ ከደገፈው ውጤቱ ለክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ቀርቦ ከጸደቀ በኋላ የዞን ምሥረታው ተግባራዊ ይሆናል፡፡ ምክር ቤቱ፣ ስለ ድምጽ አሰጣጡ እና በአጠቃላይ ስለ ነበረው ሁኔታ እና ሂደት ካጣራ በኋላ ሊያጸድቅም ሊሽረውም ይችላል፡፡

ጥያቄው አዲስ ክልል የመመሥረት ቢሆን ኖሮ ግን፣ ጥያቄውን ያቀረበው ብሔረሰብ ምክር ቤት፣ለምሳሌ ሲዳማ ቢሆን የሲዳማ ምክር ቤት፣ በሁለት ሦስተኛ ድምጽ ድጋፍ ካገኘ ይሄንኑ ውሳኔ በጽሑፍ ለክልል ምክር ቤት ያቀርባል፡፡ ጥያቄው የቀረበለት የክልል ምክር ቤት ሕዝበ-ውሳኔ ከማዘጋጀት የዘለለ በሕግ የተቀመጠ የመከልከል ወይንም ሌላ ሥልጣን የለውም፡፡ ጥያቄውን ለማብረድ ፖለቲካዊ ሥራ ሊሰራ ይችል ይሆናል፡፡ ጥያቄው በደረሰው በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ድምፀ-ውሳኔ ማዘጋጀት አለበት፡፡

የኮንሶን በተመለከተ፣ የደቡብ ክልል የብሔረሰቦች ምክር ቤት አንድም ሙሉ በሙሉ ጥያቄውን ካልተቀበለ አሊያም ተቀብሎ ሕዝበ-ውሳኔ ካላዘጋጀ ወይንም ደግሞ የሕዝበ-ውሳኔውን ውጤት ከሻረው ጉዳዩን በይግባኝ ወደ ፌደሬሽን ምክር ቤት ማምጣት ይቻላል፡፡ምክር ቤቱ ጥያቄውን በአወንታ ተቀብሎ ሕዝበ-ውሳኔ ሊያዘጋጅ መሆኑን የሚያሳዩ መረጃዎች መኖራቸውን ስለማይታወቅ ወደ ፌደሬሽን ምክር ቤት ሊመጣ ይችላል ማለት ነው፡፡

የክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት አወቃቀሩ ልክ እንደ ፌደሬሽን ምክር ቤት በክልሉ ውስጥ የሚገኙ ከእያንዳንዱ ብሔር አንድ አባል ያለበት፣ ነገር ግን ከአንድ ሚሊዮን በላይ ቁጥር ካለው ለእያንዳንዱ አንድ ሚሊዮን ሌላ ተጨማሪ አንድ አባል ለምክር ቤቱ ይጨመርለታል፡፡

አባላቱ የሚመረጡት የብሔረሰቡ ዞኖች ወይንም ወረዳዎች ምክር ቤት መካከል ሆኖ መሥተዳድር ከሌላቸው ግን በቀጥታ ከብሔረሰቡ ተመርጠው ይወከሉበታል፡፡ የፌደሬሽን ምክር ቤት ደግሞ ለክልል ምክር ቤት ከተመረጡ ተወካዮች ውስጥ በክልሉ አሸናፊ የሆነው የፖለቲካ ፓርቲ የፈለገውን ሰው ከምክር ቤቱ አባላት መርጦ ይልካል፡፡ ስለሆነም፣ የደቡብ ክልል ብሔረሰቦች ምክር ቤት የሚኖረው የአባላት ብዛት እና ክልሉ በፌደሬሽን ምክር ቤት የሚኖረው ውክልና እኩል ነው፡፡

የኮንሶ ብሔረሰብ፣ ቢያንስ 65 አባላት በሚኖሩት የብሔረሰቦች ምክር ቤት አንድ ወኪል ይኖረዋል፡፡ በፌደሬሽን ምክር ቤትም እንዲሁ፡፡ ከሕገ መንግሥታዊነት እና ሕጋዊነት ይልቅ፣ ከሕገ መንግሥቱ ጋር አብሮ በማይሄደው ፓርቲያዊ የሆነው ዴሞክራሴያዊ ማእከላዊነት ላይ በመመርኮዝ ውሳኔዎች እንደሚሰጡ ስለሚታወቅ፣የብሔረሰቦቹ ምክር ቤት አባላትም ለተመረጡበት ፓርቲ መታመን ስለሚጠበቅባቸው በክልል እና በፌደሬሽን ምክር ቤቶች መካከል የተለያዩ ውሳኔዎችን መጠበቅ አይቻልም፡፡

የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች በክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት ላይ የሚኖራቸው ተጽእኖ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ የበለጠ የሚከፋው ደግሞ እነዚህ የክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ የክልሎቹን ርዕሰ መስተዳደር ጨምሮ፣የፌደሬሽን ምክር ቤት አባል መሆናቸው ነው፡፡ ክልል ላይ ላደረሱት በደል አቤቱታ ሲቀርብባቸው፣ በፌደሬሽን ምክር ቤት በዳኝነት ይሰየማሉ፡፡

የፌደሬሽን ምክር ቤት ካሉት 153 አባላት ውስጥ፣ ከ65 የማያንሱ ከደቡብ ክልል የተወከሉ ናቸው፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች የክልሉ አቋም ለኮንሶ የዞን ጥያቄን አለመቀበል ከሆነ፣ የፓርቲውን ጫና እና የተማከለ ውሳኔውን እንኳን ብንተወው፣ የፌደሬሽን ምክር ቤት ላይ አብላጫ ድምጽ ለማግኘት በጣት የሚቆጠሩ ደጋፊዎችን ማፍራት ብቻ ነው የሚጠበቅበት፡፡

የኮንሶ ብሔረሰብ ወደ ኦሮሚያ ክልል ለመጠቃለል …..

የፌደራሉ ሕገ መንግሥት እንዴት መገንጠል እንደሚቻል እንጂ ሌሎች አገራት ከኢትዮጵያ ጋር መዋሃድ ቢፈልጉ እንዴት ሊቀላቀሉ እንደሚችሉ የሚገልጽ ሥነ-ሥርዓት አላስቀመጠም፡፡ አንድ ክልል ከሌላ ክልል ጋር መዋሐድ ቢፈልግ ወይንም አንድ ብሔር ከአንድ ክልል ወጥቶ ወደ ሌላ ክልል መካለል ቢፈልግ፣ ይሄንን ማስተናገድ የሚችል ግልጽ የሆነ ሕግ የለንም፡፡ እንደ አዲስ ክልል መመሥረት ለሚፈልግ ሥርዓት አለው፡፡ ግንኙነቱም በተገንጣዩ እና በቀሪው ክልል መካከል ይሆናል፡፡ ወደሌላ ክልል መጠቃለል ከሆነ ግን የሌላ ክልል ተሳትፎን ይጠይቃል፡፡

የኮንሶ ሕዝብ በኦሮሚያ ክልል ከቦረና፣ሊበን ከሚባለው አካባቢ መጣን ብለው ስለሚያምኑ፣ የቋንቋው ቤተሰብም ኩሽቲክ በመሆኑ፣ ከኦሮሞ ሕዝብ ባህል ጋር የሚመሳሰሉ ልምዶች ስላላቸው ይመስላል ይህ ዓይነት አማራጭ ሊነሳ የቻለው፡፡ የሁለቱ ክልሎች ቅንነት እስካለ ድረስ የድንበር ግጭት ሊፈታ በሚችልበት መንገድ በስምምነት መጨረስ ይቻላል፡፡ በተጨማሪም፣ የድንበር ማካለል ጥያቄ በማንሳት በሕዝበ ውሳኔ መፍታት ይቻላል፡፡

ይህን ለማድረግ ግን፣በኮንሶ ጉዳይ፣የኦሮሚያ ክልል የድንበር ጥያቄ ማንሳት ወይንም የሕዝቡን ጥያቄ መቀበል አለበት፡፡ ከወልቃይት ጉዳይ የሚለየው የኮንሶ ሕዝብ የኦሮሞነት ጥያቄ አለማንሳቱ ነው፡፡ ሁለቱም ቢሆኑ የድንበር ማካለል ብቻ አይደሉም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ጥያቄዎችም ሕጋዊ አሠራር የሚያስፈልጋቸው ይመስላል፡፡

ሲጠቃለል፣ ሁሉም ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በማናቸውም ጊዜ ክልል የመመሥረት ሕገ-መንግሥታዊ የሆነ መብት አላቸው፡፡ ነገር ግን ከሰማኒያ በላይ ክልል የማቋቋም አቅም አለን ወይ? እንኳን ክልልና ወረዳና ዞን መቋቋምም ከወጭ አንጻር ከባድ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ ከ50 በላይ የሚሆኑት ብሔረሰቦች ቁጥራቸው ከ100,000 በታች ሲሆኑ ሃያ አንዱ ደግሞ ከ10,000 በታች ናቸው፡፡ ለቀበሌና ለወረዳ የመሳሰሉት አስፈላጊ የሆኑ ተቋማትንስ መቋቋም ይቻላልን? የበጀት፣ የሰው ኃይል እና የመሳሰሉትን ፍላጎቶች መሸፈን መቻሉ አጠራጣሪ ነው፡፡ይሁን እንጂ፣ መተግበር የማይቻል መብት ውሎ አድሮ ቅያሜ ማምጣቱ አይቀርም፡፡ የኮንሶም ጉዳይ ይሄው ነው፡፡ እናም የአሰፋ አባተን ግጥም ልዋስና ልደምደም፡፡

“የማትበላ ወፍ ተይዛ በጭራ፣
ልቤን አደማችው ሞጭራ ሞጫጭራ፤”

እንዳለው የማይተገበር መብት አስቀምጦ የሰው ሕይወት እና ንብረት እንዲጠፋ ምክንያት ከመሆን እንደ አዋጅ ቁጥር 7/1984 በግልጽ የትኞቹ ብሔረሰቦች ምን ዓይነት መስተዳደር ማቋቋም እንደሚችሉ አስቀድሞ ሕገ መንግሥቱን በማሻሻል ማስቀመጥ፣ ወይንም ደግሞ መብቶቹን ተግባራዊ ማድረግ ነው፡፡ አንድ ጊዜ ልዩ ወረዳ፣ ሌላ ጊዜ እንደ ኮንሶ፣ ከሌሎች ጋር በመቀላቀል ዞን ማድረግ ግጭትን መጥራት ነው፡፡ ተመጣጣኝ የሕዝብ ቁጥር እያላቸው፣ አንዱን መርጦ ዞን እንዲኖረው ማድረግ ፍትሐዊ አይደለም፡፡

አልወድቅም ያለው ደመራ

 

Abel-Wabella

አቤል ዋበላ

ሁለት ተከታታይ ደመራዎችን ያበራኹት ቂሊንጦ ዞን አንድ ነበር፡፡ በእስር ቤት ሀይማኖታዊ እና ብሔራዊ በዓላት እንደሁኔታው እንደአቅሚቲ ይከበራሉ፡፡ ዛሬ በዚህች አጭር ማስታወሻ ላጫውታችኹ የወደድኩት በዚያ ካሳለፍኳቸው በዓላት አንዱ የሆነውን የ2007 ዓ.ም. የደመራ በዓል ነው፡፡

ቂሊንጦ ያለው እስረኛ በሙሉ ያልተፈረደበት የቀጠሮ እስረኛ ነው፡፡ ያው ሁሉም እንደሚያውቀው ፍርድ ቤቱ ማስረጃዎችን መርምሮ ውሳኔ እስኪሰጥ አመታት መፍጀቱ የተለመደ ነው፡፡ ስለዚህ በእስር ቤቱ አመታትን ያሳለፉ ሲኒየር የቀጠሮ እስረኞችን ማግኘት የተለመደ ነው፡፡ አምና ለበዓል የተደረገው ዘንዶሮ እንዳይቀርባቸው እስረኞቹ ኮሚቴ አቋቁመው ተፍ ተፍ ይላሉ፡፡ በመዋጮም በጨረታም ብር ይሰበስባሉ፡፡ ከውጭ ተገዝተው የሚመጡ ዕቃዎችን እንዲያስገቡ የማረሚያ ቤቱን ኃላፊዎች እንዲማልዱ ትልልቅ ሰዎች ተመልምለው ይላካሉ፡፡ ብዙውን ጊዜ በሙስና የተከሰሱ ሰዎች በማረሚያ ቤቱ ኃላፊዎች ዘንድ ተሰሚነት ስለሚኖራቸው የሚላኩት እነርሱ ናችው፡፡ እነርሱም ተስማምተው ደጅ ከጠኑ፣ ከቦጨቁትም በጥቂቱ ዘግነው ስለሚሰጡ በስኬት ይመለሳሉ፡፡

በዚያ አመት ማረሚያ ቤቱ ለደመራ ታስበው የተገዙ ችቦዎችን አላስገባም በማለቱ እስረኛው ሲያጉረመርም ትዝ ይለኛል፡፡ አንዳንዱ እስረኛ እስር ቤት መሆኑን ይዘነጋዋል፡፡ እስኪ አላስገባም ይበሉና እንተያያለን በማለት ሲዝቱ ሳይ ግርም አለኝ፡፡ ጸብ ቢነሳ ወዴት መሮጥ እንዳለብኝ ማሰቤ አልቀረም፡፡ በዚያን ወቅት ከማዕከላዊ ከመጣኹ ገና ሁለት ወሬ ስለነበር የእስረኛውን ስነ ልቦና ስላልተረዳው አንድ ግርግር እንዳይፈጠር መስጋቴ አልቀረም፡፡ እየቆየው ስሄድ ባዶ ጉራ እንደሆነች ገባኝ፡፡

በኋላ ምልጃው ከውጭ የመጣውን ባያሰገባም የማረሚያ ቤቱ ውጨኛው ግቢው ውስጥ ከሚገኙ ዛፎች የሚነድ ነገር ተሰብስቦ ደመራው እንዲዘጋጅ የሚፈቅድ ይሁንታን አስገኘ፡፡ የተወሰኑ ልጆች ተመርጠው ከኛ ዞን ወጥተው የሚነድ ነገር ለመልቀም ከአጃቢ ፖሊስ ጋር ወደዋናው ጊቢ ወጡ፡፡

መስከረም ከክረምቱ ብዙም ያልተለየ ስለሆነ ብዙም ያልደረቀውን ማገዶ ይዘው መጡ፡፡ ከዚያ ወፈር ያለውን ስር የሌለው ልጅ-እግር ዛፍ መኸል አቁመው ደመራ የሚስል ነገር ሠሩልን፡፡ ቆፍረው ቢቀብሩትም አመሻሽ ደርሶ ሳንሎክሰው እንዳይወድቅ ስጋት ውስጥ ገባን፡፡

በአይነ ቁራኛ ሲጠበቅ ሰዓቱ ደረሰ፡፡ ከእስረኛው መካከል ካህናት እና ዲያቆናት አልታጡም፡፡ ለስርዓተ ጸሎቱም ደመራውንም ለመሎከስ ተዘጋጁ፡፡ ጸሎቱ አብቅቶ ደመራው ጋዝ ተርክፍክፎበት መንደድ ጀመረ፡፡ ወፍራሙም ዲያቆን ከበሮውን አንስቶ ይደቃው ጀመር፡፡

በደመራ ትውፊት ደመራው መሀል ከላይ የአደይ አበባ በመስቀል ቅርጽ የሚታሰርበት ያለው አውራ ነዶ ወዴት እንደሚወድቅ በጉጉት ይጠበቃል፡፡ ታዳሚው ወዴት እንደሚወድቅ ሳይመለከት አይበተንም፡፡ ከልጅነት ጀምሮ እንዳስተዋልኩት ደመራው ወዴትም ይውደቅ ወዴት አመቱ የደስታ ነው፤ አመቱ የሰላም እና የብልጽግና ነው፤ የሚል በጎ በጎ ምኞት ይሰነዘራል እንጂ ወደሰሜን ከወደቀ ሀዘን ወደደቡብ ከወደቀ ደስታ የሚል የተደነገገ አሉታዊ ትርጓሜውም፡፡ የኛም ደመራ ለዚህ ወግ በቅታ ወዴት እንደምትወድቅ መጠበቅ ጀመርን፡፡ እስረኛውም ወደመውጫው በር ወድቆለት አመቱ የፍቺ ዓመት ነው እያለ ለማሳለፍ ተዘጋጅቷል፡፡ የማረሚያ ቤቱ ፖሊሶችም ወዴት ይወደቅ ብቻ ቶሎ ይውደቅና ቆጥረውና ቆልፈውብን ለመሄድ ጓግተዋል፡፡

ቢጠበቅ ቢጠበቅ ወደታች በጥልቀት ይቅበሩት አልያም እንጨቱ እርጥብ ስለሆነ ብቻ ባልታወቀ ምክንያት ሳይወድቅ ቆየ፡፡ በዙሪያው ያለው ርብራብ ተቃጥሎ ወደአመድነት ተለውጧል፡፡ ከመሬት ትንሽ ከፍያለው ወደባቱ አከባቢ እሳት እንደበላው ያስታውቃል፡፡ ዲያቆኑም ደክሞት መዝሙር መምራቱን አቁሟል፤ ፖሊሶቹ እየተቁነጠነጡ ነው፤ ደመራው አልወደቀም፡፡ ሁሉም ሰው ግራ ገብቶት ትውፊቱን ላለመተው በግርምት ይተያያል፡፡

አንድ መላኩ የሚባል በነፍስ ማጥፋት ወንጀል ተጠርጥሮ የገባ እስረኛ አለ፡፡ ፍርድ ቤቱ መታመሙን እርግጠኛ ባይሆንም የአእምሮ ህመምተኛ ሆኗል፡፡ ቢያንስ ቢያንስ ኦብሰሲቭ ኮምፐልሲቭ ዲሶርደር እንዳለበት በግልጽ ያስታውቃል፡፡ ዝርዝሩን ለባለሙያዎች እንተወው፡፡ ቆሻሻ ሲያነሳ እና ሲጥል ነው የሚውለው፡፡ ሰው ሰለማይተናኮል እስረኛው ሁሉ ወዳጁ ነው፡፡ የተደራጀ ነገር ባያወራም ከመታሰሩ በፊት ኮሚክ ነገር እንደነበር ያስታውቃል፡፡ አንዳንዴ ሲለው እንግሊዘኛ ይሞካክራል ይሄን ጊዜ እስረኛው “ፓ! መሌ እኮ የተማረ ነው” ብሎ ያደንቀዋል:: ብቻ ምን አለፋቹኽ መሌ ራሱ ተረኩ ብዙ ነው፡፡

የመሌን ታሪክ መጥቀሴ አለነገር አይደለም፡፡ በዚያ ቀን እስረኛው እና ፖሊሱ ተፋጥጦ ትውፊት ላለማፍረስ የደመራውን በራሱ መውደቅ ሲጠባበቅ የመሌን ትኩረት ይስባል፡፡ መዝሙር የለ፤ እንቅስቃሴ የለ ፡፡ የሚስቅ የሚጫወት ሰውም አይታይም፡፡ ሰው ሁሉ ያን በእሳት የተበላ እንጨት በጉጉት ይመለከታል፡፡ መሌ ምን ቢያደርግ ጥሩ ነው? ቀጥ ብሎ ሄደና ደመራውን አንዴ በእርግጫ ሲለው በአፍጢሙ ድፍት አለ፡፡ መጻኢውን ጊዜ ለመተንበይ የፈለጉ ጥቂት የማይባሉ ሰዎች ቢናደዱም አብዛኛው እስረኛ ፖሊሶቹን ጨምሮ በሳቅ እያውካካ የበዐሉ ፍጻሜ ሆነ፡፡

ዛሬ እቤቴ ቁጭ ብዬ ሳስብ ያ በእሳት ተበልቶ ሳይወድቅ ለተወሰኑ ደቂቃዎች የቆየ እንጨት የወያኔ መንግስት ይመስለኛል፡፡ (At least metaphorically) እንደመሌ ያለ በካልቾ ብሎ እስኪያደባያው ድረስ የሚጠብቅ ይመስለኛል፡፡ የመሌን ድርሻ የሚወስድ ማን ይሆን?

የሪዮ ኦሎምፒክ እና የኢትዮጵያ መንግሥት ገመና

ብስራት ወልደሚካኤል

ኢትዮጵያ ከሐምሌ 29 እስከ ነሐሴ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በተካሄደው የ2016ቱ የብራዚሉ የበጋ ሪዮ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያ 35 ስፖርተኞችን በ3 ዘርፍ በማሳተፍ 8 ሜዳሊያ በማግኘት ከዓለም ተወዳዳሪዎች 44ኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች፡፡ በበርካታ ዓለም አቀፍና የኦሎምፒክ ውድድሮች ኢትዮጵያ በምታገኛቸው ድሎች ትበልጣት የነበረችውና በአፍሪካ የቅርብ ተቀናቃኟ ኬንያ በበኩሏ 13 ሜዳሊያ በማግኘት 15ኛ ደረጃ ይዛ አጠናቃለች፡፡

ኢትዮጵያ ለ13ኛ ጊዜ የበጋ በሪዮ ኦሎምፒክ ውድድር የተሳተፈችው በሶስት የውድድር ዘርፍ በተለይም በአትሌቲክስ ሩጫ፣ ዋና እና ብስክሌት ውድድር ሲሆን፤ ሜዳሊያ ያገኘችው በሩጫው የአትሌትክስ ዘርፍ ብቻ ነው፡፡ በዚህም 1 ወርቅ፣ 2 ብር እና 5 ነሐስ ያገኘች ሲሆን በአጠቃላይ 8 ሜዳሊያ አግኝታ ተመልሳለች፡፡ ባለፈው የለንደኑ 2012ቱ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያ በ2 ስፖርት ዘርፍ 35 ተወዳዳሪዎችን በማሰለፍ 3 ወርቅ፣ 2 ብር እና 2 ነሐስ በአጠቃላይ 7 ሜዳሊያ በማግኘት በዓለም 23ኛ ደረጃን በመያዝ ያጠናቀቀች ሲሆን፤ በቤጂንጉ የ2008 ኦሎምፒክ በ1 ስፖርት ዘርፍ 27 ተወዳዳሪዎችን በማሰለፍ 4 ወርቅ፣ 1 ብር እና 2 ነሐስ አጠቃላይ 7 ሜዳሊያ በማግኘት 18ኛ ደረጃን ይዛ ነበር ያጠናቀቀችው፡፡ ይህም የኢትዮጵያ የኦሎምፒክ ውድድር፣ ተሳትፎ፣ ብቃት እና ውጤት ከጊዜ ወደ ጊዜ እጅግ እየቀነስ መሄዱን ቢያሳይም፤ በተለይ በአትሌቲክስና በሌሎች ፌዴሬሽኞች እንዲሁም በኦሎምፒክ ኮሚቴና በስፖርት ፌዴሬሽን በኩል ከመገናኛ ብዙኃኝ ፍጆታ ባለፈ ለስፖርቱ መሻሻል ትኩረት እንዳልተሰጠው ያሳያል፡፡

ኬንያ በ2012 የለንደኑ ኦሎምፒክ በ4 ስፖርት ዘርፍ 47 ተወዳዳሪዎችን አሳትፋ 2 ወርቅ፣ 4 ብር እና 6 ነሐስ በአጠቃላይ 12 ሜዳሊያ በማግኘት ከዓለም 28ኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀች ሲሆን፤ በ2008ቱ የቤጂንግ ኦሎምፒክ በ5 ስፖርት ዘርፍ 48 ተወዳዳሪዎችን በማሳተፍ 6 ወርቅ፣ 4 ብር እና 4 ነሐስ በአጠቃላይ 14 ሜዳሊያ 13ኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቋይታወሳል፡፡ በርግጥ አብዛኞች የኢትዮጵያ ድሎች በአትሌቶች የግል ጥረት እንጂ በፌዴሬሽነች ስራ ጥረት እንዳልሆነ በተደጋጋሚ ቅሬታን መፍጠሩ የሚታወቅ ሲሆን፤ በሪዮ ኦሎምፒክም በተለይ በስመ ጥር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ሳይቀር ባልተለመደ መልኩ ከፍተኛ ተቃውሞና ቅሬታ መሰማቱ ይታወሳል፡፡

ኢትዮጵያ በ3 የውድድር መስክ በአጠቃላይ 38 ተወዳዳሪዎችን ለኦሎምፒክ ውድድሩ ብታስመዘግብም፤ እስካሁን ለምን እንደሆነ በይፋ የታወቀ ነገር ባይኖርም ውድድሩ ላይ ለመሳተፍ የጠጓዙት ግን 35 ተወዳዳሪዎች ብቻ ነበሩ፡፡ ተወዳዳሪዎችን አስቀርቶ በምትካቸው ከስፖርቱ ጋር ምንም ግንኙነት የሌላቸውን ልዑካን ይዞ መሄድ እና ስፖርቱን በፖለቲካዊ ዝምድና እና ማዕቀፍ ውስጥ መውደቁ አዲስ ባይሆንም፤ የሪዮ ኦሎምፒክ በሀገር ቤት የተገደበውን ፖለቲካዊ ፈር የለቀቀ ሙስና ለአደባባይ የበቃበት ክስተት አሳዛኝ ትዝታን አስፍሮ አልፏል፡፡ ይህ ክስተት ምንም እንኳ በሪዮ ኦሎምፒክ አዲስ ባይሆንም ከምን ጊዜውም ይበልጥ በተለይ ገዥውን ስርዓት በዓለም አደባባይ ያጋለጠ ነበር፡፡

የሪዮ ኦሎምፒክ ውድድር ውጤት ለኢትዮጵያ አስደሳች ባይሆንም፤ በዓለም የኦሎምፒክ መድረክ አሳዛኝ፣ አስደሳችና አሳፋሪ አዳዲስ ክስተቶች በኢትዮጵያውያን ተወዳዳሪዎች ለዓለም አደባባይ በቅቷል፡፡ በተለይ ስፖርታዊ ቅርፅም ሆነ ብቃት የሌለው ሮቤል ኪሮስ፣ አባቱ የውሃ ዋና ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት በመሆናቸው፣ የኦሎምፒክ ኮሚቴው ፕሬዘዳንት አቶ ብርሃነ ኪዳነማርያምና የኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ዋና ፀሐፊ ወ/ሮ ዳግማዊት ግርማይ አማካኝነት ብቃት ያላቸውን ተወዳዳሪዎችና የዋና አሰልጣኑ አበበ ቢቂላን ሀገር ቤት ጥለው ባላቸው የስጋና ፖለቲካዊ ዝምድና ብቻ በዓለም መድረክ ሀገርን ወክሎ እንዲወዳደር በማድረግ ሀገሪቱንም ልጁንም የዓለም መሳቂያ ማድረግ ችለዋል፡፡ በአትሌቲክ ፌሬሽንም ተመሳሳይ ቅሬታ ያለ ሲሆን፤ በተለይ የማራቶን አሰልጣኙ ሐጂ አዲሎ በጀት የለንም በሚል ከሪዮ ኦሎምፒክ እንዲቀሩ ተደርጉ፤ ከስፖርቱ ጋ ምንም ግንኙነት የሌላቸው እንደነ ሚሚ ስብሃቱ ያሉ የስርዓቱ ደጋፊ ሰዎች በኦሎምፒክ ኮሚቴ ወጪ እንዲጓዙ መደረጉም ታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ አሰልጣኙ ሐጂ አዲሎ አትሌቶቹ በውድድሩ ውጤታማ ይሆኑ ዘንድ ለማገዝ በራሱ ሙሉ ወጪ ብራዚል ሪዮ ኦሎምፒክ እንደሄደ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በተለይ ሮቤል ኪሮስን የተለያዩ የስፖርት ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃንም ስፖርታዊ ብቃትና ቅርፅ አልባ መሆኑን በመታዘብ ሮቤል ዓሳ ነባሪው የሚል ስም በመስጠት ግርምታቸውን ለዓለም ህዝብ አሰራጭተው ነበር፡፡ በተለይ በሀገር ቤት በዋና ውድድር ለኦሎምፒክ ማጣሪያ በጥሩ ብቃትና ተክለ ቁመና አንደኛ ሆኖ ያለፈው የአዲስ አበባው አብዱልመሊክ በዋና ፌዴሬሽኑ እና በኦሎምፒክ ኮሚቴው አማካኝነት ያለምንም ምክንያት በሪዮ ኦሎምፒክ እንዳይሳተፍ ሲደረግ፤ በምትኩ ብቃትና ቅርፅ አልባው ሮቤል ኪሮስ፤ በአባቱና በኦሎምፒክ ኮሜቴው አማካኝነት እንዲሄድ መደረጉ እጅግ አሳዛኝና አሳፋሪ ክስተት ሆኖ ተመዝግቧል፡፡

ወደ ኦሎምፒኩ ውድድር መሄድ ያለበት ተወዳዳሪ እንዲቀር ከመደረጉ በተጨማሪ የውሃ ዋና አሰልጣኙ ዋናተኞች እንዲያሰለጥኑ በሪዮ ኦሎምፒክም ዋናተኞች ይዘው በዛውም ልምድ ቀስመው ለቀጣይ ዓለም አቀፍ በቃት ያላቸው ተወዳዳሪዎችን ማፍራት እንዲችሉ በሚል አሰልጣን አበበ ቢቂላ በማስታወቂያ በተደረገ ውድድ አልፈው ከሚሰሩበት ጋምቤላ ተጠርተው፣ የሪዮ ኦሎምፒክ ግብዣ ቢመጣላቸውም፤ የውሃ ዋና ፌሬሽን ፕሬዘዳንት በሆኑት የሮቤል አባት አቶ ኪሮስ ሃብቴ እና በኦሎምፒክ ኮሚቴው ፕሬዘዳንት አቶ ብርሃነ ኪዳነ ማርያም አማካኝነት አዲስ አበባ እንዲቀሩ ተደርገዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ያለ ብቃት ኦሎምፒክ ላይ እንዲሳተፍ የተደረገው ሮቤል ኪሮስ አሰልጣን አበበ ቢቂላ የኦሎምፒክ ጉዞውን እንዲሰርዝና አዲስ አበባ እንዲቀር የ10 ሺህ ብር ቼክ ጉቦ መስጠቱን፣ አሰልጣኙም ጉዳዩን ለዋና ፌሬሽን፣ ለኦሎምፒክ ኮሜቴ፣ ለስፖርት ኮሚሽን እና ለወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ጋር ድረስ ቢያሳውቁም ምላሽ ሳያገኙ መቅረታቸው ሌላ ጥያቄን የሚያስነሳ ጉዳይ ነው፡፡

በውድድሩ በሮቤ፣ በአባቱ አቶ ኪሮስና በኦሎምፒክ ፖለቲካው ና ስጋዊ ዝምድና ምክንያት ሀፍረት ውስጥ የወደቀችው ሀገር፤ በአልማዝ አያና የሴቶች 10 ሺህ ሜትር ውድድር በአዲስ ክብረወሰን አንደኛ ሆና የወርቅ ሜዳሊያ ማምጣቷ ብዙዎችን አስደስቷል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን አትሌቷ በ5 ሺህ ሜትርም ተወዳድሯ ለሀገሯ የነሐስ ሜዳሊያንም በማምጣት ከማስደሰቷ በተጨማሪ ሁለት ወርቅ ባለማምጣቴ ህዝቡን ይቅርታ እጠይቃለሁ ያለችው ንግግር ይበልጥ የብዙዎችን ልብ ሰብሯል፡፡

አትሌት አልማዝ አያና ብቃት ብቻ ሳይሆን ትህትና እና ብሔራዊ ፍቅርን አንድ ላይ አንግባ በግሏ በአንድ የኦሎምፒክ ውድድር ብቻዋን ሁለት ሜዳሊያ ማምጣቷ ከኢትዮጵያውያን አልፎ ከዓለም አቀፉ ማኀበረሰብም ከፍተኛ አድናቆትና ክብርንም አጎናፅፏታል፡፡ በርግጥ በአንድ ኦሎምፒክ ሁለት ሜዳሊያ ስታመጣ ለኢትዮጵያ የመጀመሪያዋ ባትሆንም፤የሪዮ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያውያን በብዙ የሀዘን እና የመከፋት እንዲሁም በውጤት ላይ ስጋት ውስጥ በነበሩበት ወቅት መሆኑ ልዩ ያደርገዋል፡፡

ሌላው በኢትዮጵያዊው አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ አማካኝነት ከስፖርቱ በተጨማሪ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃንን ትኩረት የሳበነ፣ የተከፉና የተገፉ ኢትዮጵያውያንን በሁለት ነገሮች ያስደሰተ፤ ግን ደግሞ ለኢትዮጵያ እንዲሁም ለአፍሪካ ታሪክ አዲስ የሆነ፤ በኦሎምፒክ ታሪክ ደግሞ ሁለተኛ የሆነ አሳዛኝ ክስተት በሪዮ ኦሎምፒክ አደባባይ ታይቷል፡፡ አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ የኦሎምፒኩ መዝጊያ በሆነው በወንዶች ማራቶን ውድድር ሁለተኛ ሆኖ በማሸነፍ ለሀገሩ የብር ሜዳሊያ ቢያስገኝም፤ በሀገር ቤት መንግሥት በዜጎች ላይ እያደረሰ ያለውን ግድያ፣ እስር፣ ስቃይና እንግልት በመቃወም ለዓለም አደባባይ አሳይቷል፡፡ ተበድለናል የሚለውን ገላጭ ምልክቱን በፕሬስ መግለጫ እና በሽልማት ስነ ስርዓቱም ላይ ደግሞታል፡፡

የአትሌት ፈይሳ ያልተጠበቀው የተቃውሞ ክስተት ገዥውን ስርዓት ሀፍረት ውስጥ ቢከተውም፣ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ያሉ ኢትዮጵያውንን በተለይም በገዥው ስርዓት ግፍና በደል የተፈፀመባቸውን እንዲሁም ለዴሞክራሲና ሰብዓዊ መብት የቆሙትን በሙሉ አስደስቷል፡፡ በመጨረሻም አትሌቱ ውድድሩን ሁለተኛ ሆኖ በሚያጠናቅቅበት ወቅት እጁን በመስቀለኛ አጣምሮ በተለይም ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ተቃውሞ በኋላም የኦሮሞ ተቃውሞ አሁን ደግሞ በአማራ ተቃውሞም ታስረናል፣ ተጨቁነናል፣ ተበድለናል፣ ነፃነት እንፈልጋለን የሚል መልዕክት ያለውን ምልክት እያሳየ ውድድሩ ሲያሸንፍ ታይቷል፡፡ ድርጊቱ ባለስልጣናቱን እና የስርዓቱን ደጋፊዎች እጅግ አስደንግጧል፡፡

አትሌት ፈይሳም በኦሎምፒኩ መድረክ የተገኙ የተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ለምን ያንን ምልክት እንደተጠቀመ ሲጠየቅ፤ ሀገር ቤት በተለይ መንግሥት በኦሮሚያ በርካቶችን እየገደለ፣ እያሰረ ያለውን ድርጊት መቃወሙን ለመግለፅ እንደሆነ፣ ያቀረበውን ተቃውሞ ተከትሎ ሀገር ቤት ቢመለስ መንግሥት እንደሚገድለው፣ ምናልባት ባይገድለው እንኳ እንደሚያስረው አሊያም ከሀገር እንዳይወጣ ሊያደርገው እንደሚችል ስለሚሰጋ ወደ ሀገር ቤት እንደማይመለስ በማስታወቅ ለጊዜው ብራዚል ቀርቷል፡፡ ሌሎች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች እና የልዑካን ቡድን አባላቱ ወደ ሀገር ቤት መመለሳቸው ታውቋል፡፡

በውጭ የሚገኙ የተለያዩ የኢትዮጵያውያን መገናኛ ብዙኃንም ቃለመጠይቅ ያደረጉለት ሲሆን፤ አትሌቱም የቅርብ ጓደኞቹና አብረውት የተማሩ ሳይቀሩ በባሌ፣ በአርሲ፣ እንዲሁም በተለያየ የኦሮሚያና አማራ ክልል ሰዎች እየተገደሉ እና እየታሰሩ መሆኑን በመግለፅ፤ ድርጊቱንም በመቃወም ምልክቱን እንዳሳየና ህዝቡም በአንድነት ተባብሮ ስርዓቱን ማስወገድ እንዳለበት እምነቱን ሲገልፅ ተሰምቷል፡፡ በተለይም ህዝቡ በዘር ከመከፋፈል ይልቅ ሁሉም ተባብሮ ስርዓቱን ማስወገድ እንዳለበት በአፅንዖት ሲናገር ተሰምቷል፡፡

በተለይ የመንግሥት ባለስልጣናት እና ደጋፊዎች የአትሌት ፈይሳ የኦሎምፒክ ማራቶን ድል የብር ሜዳሊያ እንዲሰረዝ የዓለም አቀፉ ኦሎምፒክ ኮሚቴ ላይ ጫና ለማድረግ ቢሞክሩም፤ ዓለም አቀፉ የኦሎምፒክ በበኩሉ የአትሌቱን ሜዳሊያ ሊነጥቅም ሆነ ምንም ዓይነት ርምጃ እንደማይወስድ ይፋ አድርጓል፡፡ በመጨረሻም የኢትዮጵያ መንግሥት አትሌቱ ወደ ሀገሩ መመለስ እንደሚችል እና ላሳየው ተቃውሞ ምምልክት በማሳየቱ ምንም እንደማይደርስበት ቢያሳውቅም፤ አትሌቱ ግን ወደ ሀገር ቤት መመለስ ለደህንነቱ አደጋ እንዳለው በመግለፅ ለጊዜ ብራዚል ሪዮ ዲ ጄኔሪዮ መቅረቱ ተረጋግጧል፡፡

በ2016ቱ የሪዮ ኦሎምፒክ የኢትዮጵያ ውጤት:

ውጤት የተወዳዳሪ ስም        የውድድር ዓይነት እና ርቀት      የተገኘው ሜዳሊያ
1ኛ. አልማዝ አያና                 በሴቶች 10,000 ሜትር           ወርቅ
2ኛ. ገንዘቤ ዲባባ                  በሴቶች 1,500 ሜትር               ብር
2ኛ. ፈይሳ ሌሊሳ                    በወንዶች ማራቶን                     ብር
3ኛ. ጥሩነሽ ዲባባ                   በሴቶች 10,000 ሜትር           ነሐስ
3ኛ. ታምራት ቶላ                   በወንዶች 10,000 ሜትር          ነሐስ
3ኛ. ማሬ ዲባባ                      በሴቶች ማራቶን                       ነሐስ
3ኛ. አልማዝ አያና                  በሴቶች 5,000 ሜትር               ነሐስ
3ኛ. ሐጎስ ገብረህይወት            በወንዶች 5,000 ሜትር            ነሐስ
አጠቃላይ ድምር                     8    ሜዳሊያ

በተለይ በኦሎምፒክ ውድድር ዘርፍ ኢትዮጵያ ካሏት በርካታ የወድድር መስክ ዕድሎች ውስጥ አብዛኛውን ለምን መጠቀም እንደማትፈልግ እስካሁን ግልፅ ባይሆንም፤ በውጤትም ሆነ በውድድር ዘርፍ እንዲሁም ውጤት ማነስ ብዙ ጥያቄ የሚያስነሱ ጉዳዮች አሉ፡፡ ይሁን እንጂ ስፖርቱ አጠቃላይ በፖለቲካ መዋቅር የተሳሰረ በመሆኑ እና በብቃት ሳይሆን በፖለቲካ ሹመት ከየክልሉ በሚመጡ ሹመኞች እና ለፖለቲካ ስርዓቱ ታማኝ የተባሉ ብቻ ከፌዴሬሽን፣ ኦሎምፒክ ኮሜቴ እና ስፖርት ኮሚሽን ስለሚሞሉ ስርዓቱ እስካለ ስፖርቱ ላይ የተለየ አዎንታዊ ለውጥ ሊመጣ እንደማይችል እሙን ነው፡፡ ምክንያቱም ከወረዳ እስከ ፌደራል ድረስ ባሉ የስፖርት ፌዴሬሽን እና ስፖርት ኮሚሽን የሚመለከታቸው ሰዎች ባላቸው የትምህርት ዝግጅት፣ ዕውቀት፣ ብቃት፣ ልምድና ተነሳሽነት ኃላፊነት የሚቀመጡ ሳይሆን ባላቸው የፖለቲካ ወገንተኝነት ብቻ የሚሾሙ አንዳንዶቹ ስለ ስፖርት ስራና አስፈላጊነት ምን እንደሆነ እንኳ የማያውቁ የፖለቲካ ሹመኞች የኃላፊነት ቦታውን ይዘው እንዳሉ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡

ብቃቱ ያላቸው የስፖርት አመራር ባለሙያዎች ብቻ ሳይሆን ተወዳዳሪዎችም ነፃ የወድድር ተሳትፎ ሊያገኙ የሚችሉባቸው ዕድሎችም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየመነመኑ መጥተዋል፡፡ ስለዚህ ሀገሪቱ ኦሎምፒክን ጨምሮ በሁሉም የስፖርት ዘርፎች ውጤታማ እንድትሆን በአጠቃላይ የስርዓት ለውጥ ካልመጣ አሁን ባለው አሰራር የሚሾሙ ሰዎች ቢቀያየሩ እንኳ የተለየ ውጤት መጠበቅ አስቸጋሪ ነው፡፡

በ2016ቱ የሪዮ ኦሎምፒክ አጠቃላይ ውጤት አሜሪካ 121 ሚዳሊያ (46 ወርቅ፣ 37 ብር እና 38 ነሐስ)፣ እንግሊዝ 67 ሜዳሊያ (27 ወርቅ፣ 23 ብር እና 17 ነሐስ)፣ ቻይና 70 ሜዳሊያ (26 ወርቅ፣ 18 ብር፣ 26 ነሐስ)፣ ራሽያ 56 ሜዳሊያ (19 ወርቅ፣ 18 ብር እና 19 ነሐስ) እንዲሁም ጀርመን 42 ሜዳሊያ (17 ወርቅ፣ 10 ብር እና 15 ነሐስ) በማግኘት እንደ ቅደም ተከተላቸው ከ1ኛ እስከ 5ኛ ያለውን ደረጃ በመያዝ አጠናቀዋል፡፡

የበጋው የሪዮ ኦሎምፒክ 207 የዓለም ሀገሮች የተውጣጡ 11,303 ተወዳዳሪዎች የተሳተፉበት ዓለም አቀፍ ዝግጅት ባለፈው እሁድ ነሐሴ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በመዝጊያው የማራቶን ውድድር በሰላም ተጠናቋል፡፡ በቀጣይም በ2018 የክረምት ኦሎምፒክ በደቡብ ኮሪያዋ ፓዮንቻን የሚካሄድ ሲሆን፤ የ2020ው የበጋው ኦሎምፒክ ውድድር ደግሞ በጃፓኗ መዲና ቶክዮ እንደሚዘጋጅ ይጠበቃል፡፡