ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ “ስለ ኦሮሞና አማራ ትክክለኛ የዘር ምንጭ” ያብራራሉ!!
ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ “ስለ ኦሮሞና አማራ ትክክለኛ የዘር ምንጭ” ያብራራሉ!!
• ሁሉም የኢትዮጵያ ብሔር፣ የአንድ አባትና እናት ልጆች ነው
• አዳም የተፈጠረው ጎጃም፤ ኖህ መርከቡን ያሳረፈው አራራት ተራራ ላይ ነው
• ስለ ኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ አጥንቼ አለሁ ይላሉ …

ኑሮአቸውን በአሜሪካ ያደረጉት ታዋቂው የሥነፅሁፍ ምሁር ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሣ፤ የፃፉት‹‹የኦሮሞና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ›› የተሰኘ አዲስ አነጋጋሪ የታሪክ መፅሐፍ ዛሬ ለገበያ ይቀርባል፡፡ የኦሮሞና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ ማን እንደሆነ በጥናት ደርሼበታለሁ የሚሉት ፕሮፌሰሩ፤ እስከ ዛሬ የተለያዩ የታሪክ ምሁራን ከተናገሩት ፍፁም የተለየና አዲስ የጥናት ውጤት ማግኘታቸውን ይናገራሉ፡፡ የሁለቱ ቋንቋዎች አመጣጥም በጥናቱ ተካቷል ብለዋል፡፡ በሊንከን ዩኒቨርሲቲ በሂዩማኒቲስ የትምህርት ዘርፍ የሚያስተምሩት ፍቅሬ ቶሎሳ ፤ከዚህ ቀደም ‹‹Heaven to Eden›› እና ‹‹The Hidden and untold History of the Jewish People and Ethiopians›› የሚሉ መጽሐፍትን በእንግሊዝኛ ቋንቋ ያሳተሙ ሲሆን ሁለቱም በኢንተርኔት
“አማዞን” በተባለ የመፅሃፍ ሽያጭ ድረገፅ ላይ ከተፈላጊ መፃህፍት ተርታ ተሰልፈዋል፡፡ በሙያቸው
ፀሃፌ-ተውኔትና የሥነ ፅሁፍ ምሁር ሲሆኑ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ጥልቅ ጥናትና ምርምሮችን
በማድረግም ይታወቃሉ፡፡
አንጋፋው ምሁር ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም በቅርቡ ለንባብ ባበቁት
“አዳፍኔ” የተሰኘ መፅሃፋቸው ላይ፤“የኦሮሞን ታሪክ ሙሉ አደርጎ ሊፅፍ የሚችለው ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ ብቻ ነው” ሲሉ ለብቃታቸው ምስክርነትና ዕውቅና መስጠታቸው አይዘነጋም፡፡ ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሣ በርካታ ቲያትሮችን ለደረክ ያበቁ ሲሆን ከእነዚህም መካከል “ጓደኛሞቹ”፣ “ፍቅር በአሜሪካ” እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡ በቅርቡም ‹‹ላሟ›› የተሰኘ ባለ ሁለት ገቢር ቲያትር ፅፈው ማጠናቀቃቸውንም ተናግረዋል፡፡ ፕሮፌሠሩ ለአጭር ጊዜ ዕረፍት ወደ ኢትዮጵያ መጥተው የነበረ ሲሆን ወደ አሜሪካ ከመመለሳቸው በፊት ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር በታሪክ ጥናቶቻቸው ዙሪያ ቃለ ምልልስ አድርገዋል፡
በእንግሊዝኛ ቋንቋ ያሳተሟቸው “Heaven to Eden” እና “The Hidden and untold History of the Jewish People and Ethiopians›› የሚሉት መፃህፍት በአለማቀፍ ደረጃ ሰፊ ተቀባይነት ያገኙበት ሚስጥር ምንድነው? በምን ርዕሰ ጉዳይ ላይ ነው የሚያተኩሩት?
የመፅሐፍቱ ይዘት ነው ወሳኙ፡፡ ተቀባይነት ያገኙት በቋንቋ አጠቃቀም ለአንባቢያን ምቹ ስለሆኑ ይመስለኛል፡፡
በአይሁዶች ታሪክ ላይ የሚያተኩረው መፅሐፍ፤በጉዳዩ ላይ ከተጻፉ ሌሎች መጻህፍትና በተለምዶ ስለ አይሁዶች ከሚታወቀው ምን የተለየ ነገር ይዟል?
ብዙ ጊዜ ስለ አይሁዳውያን ሲወራ፣ቀዳማዊ ሚኒልክ የዛሬ 3ሺህ ዓመት፣ 40ሺህ አይሁዳውያንን ይዞ መጣ የሚለውን ነው የምናውቀው፡፡ ከመጡት መካከል 12ሺህ ያህሉ ንፁህ እስራኤላውያን ናቸው። 28ሺህ ያህሉ እነሱን በሥራ ያገለግሉ የነበሩ ኢያቡሳውያን የሚባሉ ነገዶች ናቸው፡፡ ቀዳማዊ ሚኒልክ ለ12 ሺህዎቹ ልዩ ቦታ ሰጥቷቸው፣ በሀገሪቷ ላይ ካህናት አድርጎ ታቦት እያስቀረፀ፣ ኢትዮጵያ ላይ በዚህ መልክ ሾሟቸው ነበር፡፡ ኢያቡሳውያን ደግሞ ንጉሱን በእጅ ስራና በውትድርና ያገለግሉት ነበር፡፡ ይሄ እንግዲህ አይሁዳውያን ወደ ኢትዮጵያ ያደረጉት ሁለተኛው ፍልሰት ነው፡፡
የመጀመሪያውና ብዙም የማይነገረው የአይሁዳውያን ፍልሰት፣ የእስራኤላውያኑ መሪ ሙሴ በህይወት እያለ አባ ብሄር የሚባል ልኡል ነበር። የሙሴ አማች ነው፡፡ አባ ብሄር የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ሊሆን ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ፣አይሁዳውያን ተከትለውት መጥተው ነበር፡፡ ምክንያቱም አባ ብሄር ያገባት ልጅ የሙሴ እህት ነበረች፡፡ ሙሴ በወቅቱ ለአባ ብሄር ፅላት ቀርፆ እንዲሁም ቀይ ባህርን የከፈለባትን በትር ሰጥቶት፣ወደ ሳባ ከተማ መጥቶ ነግሷል፡፡ በወቅቱ ብዙ አይሁዳውያንም ተከትለውት መጥተው ነበር፡፡
ሶስተኛው ፍልሰት የምንለው፣የኢራቁ ናቡከደነፆር አሸንፏቸው በሚያሳድዳቸው ጊዜ፤ “ኢትዮጵያ ውስጥ አይሁዳውያን ወገኖች አሉን” ብለው ወደ ኢትዮጵያ መጥተዋል፡፡ አይሁዳውያን በነዚህ መንገዶች ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጡት፡፡
ትክክለኛዎቹ አይሁዳውያን በኢትዮጵያ ያሉት ናቸው የሚሉ ወገኖች አሉ…?
የሃይማኖታቸውን ስርአት፣ መፅሃፍትና ህግጋት ከመጠበቃቸው አንፃር ከሌላ ህዝብ ጋር ስላልተደባለቁ ትክክለኛው ያለው እነሱ ጋ ነው፡፡ ሌሎቹ ወደ አውሮፓ፣ እስያ፣ አሜሪካ የተሰደዱት እነዚህን ነገሮች በተለያዩ ጫናዎች የተነሳ ሙሉ ለሙሉ ጠብቀው አላቆዩትም፡፡ ወደዚህ የመጡት ግን በግድ ባህላችሁን ሃይማኖታችሁን ለውጡ ተብለው በኢትዮጵያውያን አልተረበሹም፤ነፃነት ነበራቸው፡፡ መሬትና ሁሉ ነገር የተመቻቸላቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ነበር፡፡ ሌላ አገር ላይ ቦታ እንዳይኖራቸው ተደርገው በየጊዜው ይሰደዱ ነበር፡፡ እንደውም በሩሲያ ውስጥ በድንገት አይሁዳውያንን የመግደል ድርጊት ይፈፀም ነበር። ሩሲያውያኑ ተሰባስበው፤“ዛሬ አይሁዳውያንን ገድለን እንምጣ” እያሉ ይዘምቱባቸው ነበር፡፡ ወደ መንደራቸው ሄደው አውድመዋቸው ይመለሳሉ፡፡ ማንም ስለማይበቀልላቸው ደማቸው ደመ ከልብ ሆኖ ነበር የሚቀረው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን ከተሰጣቸው ክብር የተነሳ በትንንሽ ንጉስነት ጭምር ይሾሙ ነበር፡፡ በርካቶቹም ካህናትና ሊቀ-ካህናት ተደርገው ለአይሁድ እምነት ተሹመል፡፡ ቀጥሎ ደግሞ የሰለሞን ዘር ነን በሚሉት ውስጥም ገብተው፣ ስርወ መንግስት እስከ መመስረት የደረሱ ነበሩ፡፡ በዓለም ላይ አይሁዳውያን ደልቷቸው የኖሩት ኢትዮጵያ ላይ ብቻ ነው፡፡ በጠቅላላው በኢትዮጵያ ሀገራት ማለትም፡- በግብፅ፣ የመን፣ ኑቢያ—ኢትዮጵያ ባስተዳደረቻቸው አካባቢዎች በሙሉ በክብር ተይዘው ነው የኖሩት፡፡ ትልቁ ማስረጃ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ፣ እናቱ ማርያምና ቅዱስ ዮሴፍ በስደቱ ዘመኑ እኛ ጋ ብቻ ነው ጥገኝነት ያገኙት። በወቅቱ ግብፅ ለሁለት ተከፍሎ ነበር፡፡ አንዱ ክፍል በሮማውያን ቁጥጥር ስር ነበር፡፡ ሁለተኛው የኢትዮጵያ ክፍል ነው፡፡ ኢየሱስ ከመወለዱ ከ880 ዓመት በፊት አማራዎች፤ አማሩላ ደልታ ወደሚባል ቦታ ሄደው፣ አክሱማይት የተባለውን ህፃን ልጅ ዙፋን በመጠበቅ ያገለግሉ ነበር፡፡ በኋላ በ800 ዓመታት ውስጥ አማሩላ ደልታ የሚባል መንደር መስርተው ነበር፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ጋርና ከቅዱስ ዮሴፍ ጋር ሲሸሹ፣ እዚያ ነው ማረፊያ ያገኙት፡፡ ይሄ መፅሃፍ ቅዱስ ውስጥ የለም፤እኛ ግን ከተለያዩ መዛግብት እናገኘዋለን፡፡ በወቅቱ የአካባቢው ንጉስ አማናቱ ተትናይ ይባላሉ፡፡ ከጎጃም ከጣና አካባቢ ነው ወደዚያ የሄደው፡፡ ሌላው አይሁዳውያኑ መፅሐፍ ቅዱሳቸው ሲጠፋባቸው ከኛ ነው የወሰዱት፡፡ አፄ ደንቀዝ የተባለው ንጉሰ ነገስት ነው ከግዕዝ ወደ እብራይስጥ አስተርጉሞ የሰጣቸው፡፡
ትክክለኛውን የአይሁድ ባህልና እምነት በመጠበቅ በኢትዮጵያ ያሉት አይሁዳውያን ብቸኞቹ ናቸው ማለት ይቻላል?
አዎ! ኦሪትን ይዘዋል፡፡ ግን በደማቸው ከኛ ተደባልቀዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ነው ሃበሻ የተባሉት። ሃበሻ ማለት የተደባለቀ ነው፡፡ “አበሳ” ያለበት ወይም እንከን ያለበት ማለት ነው፤ ሃበሻ ማለት፡፡ በቀዳማዊ ሚኒልክ ጊዜ የመጡት ከኛ ጋር ተደባልቀው 560 ዓመት ከቆዩ በኋላ በባቢሎን ስደት ጊዜ ሶስተኛዎቹ ሲመጡ፣ነባሮችን ሲያዩአቸው በመልካቸው አይሁዳውያንን አልመስል አሏቸው። ስለዚህ፤“እናንተማ ክልስ ናችሁ፤አበሳ አለባችሁ” ብለው ይሰድቧቸዋል፡፡ ነባሮቹ አይሁዶች ደግሞ፤ “እናንተ ፈላሾች፤እኛ ሀገር አለን” እያሉ ይሰድቧቸው ነበር፡፡ በዚህም “አበሻ” እና “ፈላሻ” የሚለው መጠሪያቸው ሆነ፡፡ “ሀበሻ” የሚለው ቃል እኛን አይወክለንም የምለው ለዚህ ነው፤ሀበሻ አይሁዳውያኑን ነው የሚወክለው፡፡ እኛ የኢትዮጰያ ልጆች ነን፤ ኢትዮጵያውያን ነን፡፡
“በሃበሻነቴ እኮራለሁ” ስንል የከረምነውስ—–ቀለጠ ማለት ነው?
አዎ! እኔ ኢትዮጵያዊ እንጂ ሀበሻ አይደለሁም። ሀበሻ የሚለው ቃል የስድብ ቃል ነው፡፡ እኛን አይወክለንም፡፡ አይሁዳዊ ካልሆነ በስተቀር አንድ ሰው ራሱን “ሀበሻ ነኝ” ብሎ ሊጠራ አይገባውም። ስድብ አያኮራም፡፡ ብዙ ሰው ስለማያውቅ ነው በሀበሻነቴ እኮራለሁ የሚለው፡፡ በአረብኛም ብናየው “የተደባለቀ”፤ “ንፁህ ያልሆነ” ማለት ነው። ይሄ መልካም ቃል አይደለም፡፡ ግን ሀበሻ የሚለው “አበሳ” ከሚለው እንጂ ከአረብኛ የመጣ አይደለም። ሁለቱ አይሁዳውያን መሃል ያለ የመሰዳደቢያ ቃል ነው እንጂ እኛ ኢትዮጵያውያንን አይመለከተንም፡፡
‹‹ኢትዮጵያ›› የሚለውስ ከየት የመጣ ነው?
ኢትዮጵያ የሚለው ‹‹ኢትዮጵ›› ከተባለው ሰው የመጣ ነው፡፡ ኢትዮጵ ማን ነው ካልን፣ በመፅሐፍ ቅዱስ ላይ የተጠቀሰው መልከፀዴቅ የሚባል የሳሌም ንጉሰ ነገስትና ሊቀካህን ነበር፡፡ ይህ ሰው ሃገር ያስተዳድራልም፤ሃይማኖትም ይመራል፡፡ እሱም የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነበር፡፡ ይሄ እንዴት ይሆናል ከተባለ፣ኢየሱስ በምፅአት ቀን ሲመጣ፣ የንጉስ ንጉስ፣ የካህን ካህን ሆኖ ነው፤መልከፀዴቅም የዚህ ምሳሌ ነው፡፡ ኢትዮጵያን ከዚሁ ጋር ምን ያገናኛታል ሊባል ይችላል፡፡ በጣም የሚያኮራ ግንኙነት አለው፡፡ የመልከፀድቅ ልጅ ኢትኤል ይባል ነበር፡፡ እግዚአብሔር ኢትኤልን ካለህበት የሳሌም ምድር ለቀህ ጣና ላይ ስፈር አለው፡፡ ‹‹ከዚያም ያንተ የልጅ ልጆች፣ እኔ ከ2000 አመታት በኋላ በምወለድበት ጊዜ በኢትዮጵያ ግዛት ላይ ስለ መወለዴ ኮከብ አሳይሃለሁ” ይለዋል (እንደኔ ምርምር፤ይሄ ኮከብ የተባለው መልአኩ ገብርኤል ነው) በዚህ ሁኔታ ኢትኤል አሁን ወዳለችው ኢትዮጵያ ሲደርስ እግዚአብሔር፤‹‹ኢትዮጵ›› ተብለህ ተጠራ አለው፡፡ ‹‹ኢት›› – ስጦታ ማለት ነው፡፡ ‹‹ዮጵ” – ማለት ደግሞ ቢጫ ወርቅ ነው፡፡ ስለዚህ “ቢጫ ወርቅ ስጦታ” ተባለ፡፡ በኋላ ሃገሪቷን ኢትዮጵያ አሠኛት፡፡
በመፅሐፍ ቅዱስ በተደጋጋሚ ኢትዮጵያ ተብሎ የሚጠቀሰው ስም የትኛዋን ኢትዮጵያ ነው የሚወክለው?
እሱ አሁን ያለችውን ኢትዮጵያን ነው የሚወክለው፡፡ ግን ኢትዮጵያ የሚለው መጠሪያ እስከ 13ኛው ክ/ዘመን ድረስ ለመላዋ አፍሪካ መጠሪያ ሆኖ ሲያገለግል ቆይቷል፡፡ በኋላም የመጣው አፍሪካ የሚለው ስም ከዚሁ ከኢትዮጵያ የተገኘ ነው፡፡ ከአፋሮች ነው አፍሪካ መጠሪያዋን ያገኘችው፡፡ በመፅሃፈ እዝራ ምዕራፍ ስድስት ላይ፤‹‹አፍሪካንሳውያን›› ይላል፡፡ ይሄ አፋሮችን ነው የሚወክለው፡፡ በመርከብ ስራ በቀይ ባህር ላይ የተራቀቁ ሰዎች ነበሩ፡፡ የዛሬ 3ሺህ አመት ንጉስ ሰለሞን ቤተመቅደሱን ሲሰራ፤ልዩ እንጨት፣ እጣን፣ ወርቅ (ኦፊር የተባለ ታዋቂ ወርቅ- በነሱ የተሰየመ) ጭምር ይነግዱና ለንጉሡ ያቀርቡ ስለነበር፣ስማቸው የገነነ ሆኖ አፍሪካንሳውያን የተባሉት፡፡ በሳይንሱም አፋር የሰው ዘር መገኛ እያልን ነው፡፡ ኢስያውያንም ስያሜያቸውን ያገኙት ከሣባ ቀድሞ ከነገሰው ‹‹ኢስአኤል›› ከተባለው ንጉስ ነው፡፡ ምድሪቱን ያስተዳድር ስለነበር ኢስያ ተባለች፡፡ ‹‹አፄ” የሚለውም ከዚህ የመጣ ነው፡፡
ኢትዮጵያ የሚለው ከግሪክ ቃል የመጣ ነው የሚለውስ —?
ኢትዮጵያ የሚለው ከግሪክ ቃል የመጣ ነው የሚለው ውሸት ነው፡፡ ይሄን አጣርቻለሁ፡፡ በነሱ መዝገበ ቃላት ውስጥ ይሄ ቃል የለም፡፡ ‹‹ፊቱ የተቃጠለ›› የሚለው ቃል በግሪክ ቋንቋ ኢትዮጵያ የሚለውን ሳይሆን ሌላ ትርጉም ነው የሚኖረው፡፡ ግሪኮቹ ከኛው ሰምተው ነው መልሠው ኢትዮጵያ ያሉን፡፡ እኛ ከነሱ በፊት ነበርን እንጂ እነሱ ከኛ በፊት አልነበሩም፤ ስማችንን ሊያወጡልን አይችሉም፡፡
በምርምርዎ አዳምና ሄዋን የተፈጠሩበት ቦታ የት ሆኖ አገኙት?
ኢትዮጵያ ውስጥ ነው፡፡ ጎጃም፤ ዳሞትና ጣና አካባቢ ያለ ቦታ ነው፡፡
ለዚህ ድምዳሜ ማስረጃዎ ምንድን ነው?
አንደኛ ኤደንን ከሚያጠጡ አራት ወንዞች ውስጥ አባይ የምንለው ነው ኤፌሶን የሚባለው። በኦፌር ወርቅ ዙሪያ የሚዞር መሆኑ ተፅፏል፡፡ በኔ ድምዳሜ፣የኤፌሶን ወንዝ የአሁኑ ዋቢ ሸበሌ ነው። ጤግሮስና ኤፈራጥስ ደግሞ ጊዮን ራሱ ጥንት ሜዲትራኒያን ባህር ይገባ ነበር፡፡ ድሮ ሜድትራኒያን “ኪቲ” ይባል ነበር፡፡ ጥንት ጊዮን ወንዝ ሜድትራኒያን ሲደርስ ተራራ ስለነበር ተጋጭቶ ይመለስ ነበር፡፡ ከዚያ ነው መሬት ተነቃንቆ፣ቦታው ተቆራርጦ አሁን ወዳለበት ኢራቅ የሄደው እንጂ አካባቢው እዚሁ ነበር፡፡
አዳም የት ተፈጠረ ለሚለው በመፅሃፈ ሄኖክ ላይ “ኤልዳ” በሚባል ቦታ ተፈጠረ ይላል፡፡ ኤልዳ ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ ነው ያለው፡፡ ምክንያቱም አስሌዳውያን ወይም ኤልዳውያን የሚባሉ አሁንም ድረስ ጎጃም ውስጥ አሉ፡፡ ሄኖክ በመፅሃፉ ኤልዳ ነው የተፈጠረው ይላል፡፡ ከዚያ ወስዶ ነው እግዚአብሄር በ40 ቀኑ ወደ ኤደን ገነት የከተተው ይላል፡፡ ሄዋንን ደግሞ ከአዳም ጎን አውጥቷት ነው በ80 ቀኗ ወደ ኤደን ገነት የከተታት፡፡ ከዚህ ተነስቶ ነው ወንድ በ40፣ ሴት በ80 ቀን ክርስትና የሚነሱት። ይሄ አይነቱ ስርአት በዓለም ላይ የትም የለም፤እና ይሄ በሄኖክ መፅሃፍ የተፃፈውና አሁን ያለው እውነታ ይገኛል፡፡
ሌላው ኮሬብ የሚባል ዋሻ ውስጥ አዳም ተቀበረ ይላል፡፡ በእርግጥ በሲናይ በረሃ አካባቢ ኮሬብ የሚባል ቦታ አለ፤ ግን በተመሳሳይ ይህ ቦታ ኢትዮጵያ ውስጥም አለ፡፡ ሌላው ኖህ መርከቡን ያሳረፈው አራራት ተራራ ላይ ነው ይላል፡፡ አራራት ተራራን ለመፈለግ ወደ ቦታው ሄጄ ነበር፤ በታንኳ ጣናን አቋርጬ፡፡ አራራት ተራራ የሚባለውን ሳገኘውና አቀማመጡን ሳጠናው፣ ለመርከብ ማሳረፊያነት በአናቱ ላይ ምቹ ሜዳ አለው፡፡ ኖህ ወይን ጠጅ ጠጥቶ ሰክሮ ነበር ይላል፤መፅሃፍ ቅዱስ፡፡ በእርግጥም ቦታው የወይን ጠጅ ፍሬ ለማብቀል ተስማሚ ነው፡፡ አሁንም አትክልቶችና ጌሾ ይበቅልበታል፡፡ ከዚሁ ማስረጃ ሳልወጣ፣አዲስ አመትን አበቦች አብበው አከበረ፤የእንጨት መስዋዕትም አደረገ ይላል፡፡ ይሄ እንግዲህ ዛሬ በመላ ኢትዮጵያ ያለው የአዲስ ዓመት መቀበያ ስርአት፣ ከየት መጣነትን ሊያስረዳ ይችላል። በኋላ ወደ ክርስትናው የመስቀል በዓል ደመራነት ተለወጠ እንጂ በፊት ደመራ የሚነደው በአዲስ ዓመት መጀመሪያ ላይ ነው፡፡ ለዚህ ማስረጃው አሁንም ድረስ ክርስቲያን ያልሆኑ የሀገራችን ሰዎች የደመራ ስርአት አላቸው። ይሄ የአባታቸው የኖህ ትዝታ (ማስታወሻ) ነው ሲወረስ ሲዋረስ የመጣው፡፡ በዚህና በኖህ ጉዳይ ሰፊ ጥናት እያደረግሁ ነው፤ወደፊት ይፋ ይሆናል፡፡ አንድ እዚህ ላይ ልጠቅሰው የምፈልገው፣ሌላ አራራት የሚባል ተራራ አርመን ውስጥ አለ፡፡ ተራራው ግን በረዶ ያለበት፣ ገደላገደል፣ እንኳን መርከብ ሊያሳርፍ ለሰው ልጅ የማይመችና የማያብብ ቦታ ነው፤ ስለዚህ ያ ሊሆን አይችልም፡፡
በሰንደቅ አላማው ላይም የተለየ መከራከሪያ ያቀርባሉ፡፡ ለኢትዮጵያ የተሰጠ ስጦታ ነው ሲሉ ምን ማለትዎ ነው?
ሰንደቅ አላማው ለኖህ ከተሰጠው ምልክት የመጣ ነው፡፡ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ የጎሉበት ቀለማት ሰማይ ላይ ታይተዋል፡፡ እነዚያ ቀለማት ናቸው ዛሬ ያሉት፡፡ ከንግስት ሳባ በፊት የነገሰው አፄ ኢሲአኤል ነው ሰንደቅ አላማ እንዲውለበለብ ያደረገው፡፡ ሰንደቅ አላማ የሚለው የመጣው የኢስአኤል መንግስት “ሰንደቅ አለማ” ከሚለው ነው፡፡ ከዚያ የመጣ ነው። እሱ በወቅቱ የመረጠው፡- አረንጓዴ ቢጫ፣ቀይና ሰማያዊ ቀለማት ነበር፡፡ ለሰንደቅ አላማው ያልተገዛና ያላውለበለበ ይቀጣል ብሎ ለመጀመሪያ ጊዜ አስገዳጅ ህግ ያወጣውም እሱ ነበር፡፡ በሰንደቋ አናት ላይ ኮከብ ነበር የሚቀመጠው፡፡ ኢየሱስ ሲወለድ የሚጠቁመውን ኮከብ ለማስታወስ ይጠቀም ነበር፡፡ በዓለም ላይ ሰንደቅ አላማን የፈለሰፈ የመጀመሪያው ሰውም ሊሆን ይችላል፡፡
የኢትዮጵ የልጅ ልጅ የሆነው ኢስአኤል ከፈለሰፈው ሰንደቅ አላማ ነው፣ዛሬ ያሉት የሰንደቅ አላማ ቀለማት የመጡት፡፡ ስለዚህ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በሰንደቅ አላማው ላይ ከዚህ ተነስቶ አንድ አይነት አቋም ቢይዝ መልካም ነው፡፡ ኢስአኤል ለኦሮሞውም፣ ለአማራውም፣ ለትግሬውም፣ለአፋሩም ለሌላውም ብሄረሰብ ሁሉ አባት ነው፡፡ ከአባቶቻችን የወረደ ሰንደቅ አላማ እንጂ ከባዕድ የመጣ አይደለም፡፡
ሰውየው እጅግ ጠቢብ ነበር፤ልእለ ሰብዕ (superman) ነበር፡፡ 150 አንበሳ መግደሉን ለማስታወስ ጭምር አፄ ኢስአኤል የሰብዕ እና የአውሬዎች ንጉሰ ነገስት ብሎ ነበር ራሱን የሚጠራው፡፡ ሰውየው እጅግ ጠቢብ ከመሆኑ የተነሳ የጀነቲክ ኢንጅነሪንግን የፈለሰፈውም እሱ ነው፡፡ እንስሳን ከእንስሳ፣ ዘርን ከዘር እየቀላቀለ የፈለሰፈ የመጀመሪያው የጀነቲክ ኢንጅነር ነበር። በቅሎን የፈጠረውም እሱ ነው፡፡ አህያንና ፈረስን አዳቅሎ፡፡ ይህ ሰው የሁሉም ኢትዮጵያውን አባት ነው፡፡ የኢትዮጵ ልጅ ነው፡፡ የኢትዮጵ 10 ወንዶች ልጆች ናቸው፤ አሁን የምናያቸውን የኢትዮጵያውያን ጎሳዎች ሁሉ የፈጠሩት፡፡
ሰሞኑን ለአንባቢያን የሚቀርብ መፅሃፍ እንዳዘጋጁም ሰምቼአለሁ፡፡ የመፅሐፉን ይዘት በአጭሩ ሊነግሩኝ ይችላሉ?
መፅሐፉ፤“የኦሮሞና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ” የሚል ነው፡፡ አሁን ያሉት ኢትዮጵያውያን በሞላ የኢትዮጵ ልጆች መሆናቸውን ከላይ አስረድቻለሁ፡፡
አሁን እንደምናው በሁላችንም ላይ የማንነት ቀውስ አለ፡፡ የማንነት ቀውሱ የመጣውም እኛ ማን እንደሆንን በትክክል ባለማወቃችን ነው፡፡ ስለዚህ ይህ መፅሐፍ እኛ ማን እንደሆንን፣በርካታ ታሪካዊ ማስረጃዎችና ሰነዶችን አስደግፎ፣ግልጥልጥ አድርጎ ያስረዳናል፡፡ ይህ የማንነት ቀውሳችን ከተስተካከለና ራሳችንን ካወቅን፣ በመካከላችን ግጭቶች ሊኖሩ አይችሉም፡፡ መፅሐፉ፤ፍቅር፣ ሰላምና ህብር ሊፈጥር ይችላል የሚል እምነት አለኝ፡፡ እኛ የትልቅ ሰው ዘር ነን የሚለውን በማስረጃ የሚያሳየን ነው፡፡ የሰው ዘር ምንጭ ናሙናዎች መሆናችን ይተነትናል፡፡ ማንነታችንን በትክክል ተረድተን፣ አንድ ላይ ለመጓዝ ያስችለናል ብዬ አስባለሁ – ይህ ብዙ የተደከመበት የምርምር ውጤት፡፡
የኦሮሞና የአማራ የዘር ሀረግ አንድ ነው የሚለውን ነው መፅሃፉ የሚያስረዳው?
አማራና ኦሮሞ ብቻ ሳይሆን ሁሉም በኢትዮጵያ ግዛት ያለው ብሄር፣ ጎሳ ከ10ሩ የኢትዮጵ ልጆች ነው የመጣው፡፡ ዝቅ ሲል ደግሞ የኢትዮጵ የልጅ ልጅ የሆነ፣ ጎጃም ላይ አዳምና ሄዋን ተፈጥረዋል ብዬ ባልኩት አካባቢ አንድ ጠቢብ ሰው ነበር፡፡ “ደሴት” ወይም “ደሸት” ይባላል፡፡ እሱ ነው የኦሮሞና የአማራ አባት፡፡ የዛሬ 3600 ዓመት 4 ወንዶች ልጆች ወለደ፡- መንዲ፣ መደባይ፣ ማጂ፣ ጅማ የሚባሉ፡፡ እነዚህ 4ቱም አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ የሀገር መጠሪያ ሆነዋል። ማጂ ደግሞ ማራ እና ጀማን ይወልዳል። ዛሬ አማራ የምንለው ማራ ነው፡፡ “ማራ” ማለት “እውነተኛ ብርሃን” ማለት ነው፡፡ አማራ ያሉት አጋዚያን ወይም የግዕዝ ቋንቋ ተናጋሪዎች ናቸው፡፡ ማጂ ማራን ወለደ ካልን፤ ጀማ እና ማራ ወንድማማቾ ናቸው፡፡ ሁለቱ ወንድማማቾች በአካባቢው ካሉት ጋፋቶች ጋር መዋጋት ሰልችቷቸው፣ ሃገር ለቀው ወደ ሸዋ ሲመጡ አንድ ወንዝ ያገኛሉ፡፡ ወንዙን ጀማ አሉት። አሁን የጀማ ወይም የ“ዠማ” ወንዝ ማለት ነው። ከአካባቢው እየራቁ ሲሄዱ የጥንት አባቶቻቸውን ቋንቋ “ሱባ”ን ትተዉ አማርኛን መፈልሰፍ ጀመሩ፡፡ መደባይ፣ ጅማና መንዲ ደግሞ ግማሾቹ ጎጃም ላይ ቀሩ፤ ግማሾቹ ወለጋ ሄዱ፤ሌሎቹም እየራቁ በምስራቅ አፍሪካ ተሰራጩ፡፡ ኦሮሚኛ ቋንቋ የሚባለውንም ፈጠሩ፡፡ በዚህ ሁኔታ ነው ዛሬ ያሉት ኦሮሞና አማራ የመጡት፡፡ ዘረ ደሸት ይባላሉ፡፡ የደሸት ልጆች ናቸው። የዘር ሀረጋቸው አንድ ነው፡፡ ቋንቋቸው የተለያየ የሆነው በሂደት ነው፡፡
ኦሮሞው የኩሽቲክ፣ አማራው የሰሜቲክ ዘር ናቸው፤ የመጡትም ከውጭ ነው የሚለው ለዘመናት የዘለቀ ታሪክስ …?
እሱ ፈፅሞ ውሸት ነው፡፡ ሁለቱም ከውጭ አልመጡም፡፡ እንዳስረዳሁት እዚሁ የበቀሉ ናቸው። የአማራም የኦሮሞም አባት ደሸትም ሆነ ታላቁ አባት ኢትዮጵ ኩሽ ነው፡፡ መልከፀዴቅም ኩሽ ነው። ኦሮሞና አማራ ሁለቱም ኩሽ ናቸው፡፡ አማራ ሴም አይደለም፤ ኩሽ ነው፡፡
እስከ ዛሬ ሲነገር የነበረው ውሸት ነው። ምናልባት የአማርኛ ቋንቋ ከሌሎች ጋር ሲደበላለቅ ሴሜቲክ ቤተሰብ ውስጥ ተገኝቶ ሊሆን ይችላል። ሁሉም ኢትዮጵያውያን የኩሽ ዘሮች ናቸው። በዚሁ መፅሐፌ ላይ ስለ ቋንቋም አስረድቻለሁ፡፡ በእብራይስጥም ሆነ በአረቢክ የሌሉ እንደ ጨ፣ቀ፣ፀ ያሉ ድምጾች በአማርኛና በኦሮሚኛ ቋንቋ ውስጥ አሉ። ይሄን በዝርዝር በመፅሐፉ አስቀምጫለሁ፡፡
ኦሮሞና አማራ አንድ ነው የሚለው አመለካከት በተለይ በኦሮሞ ምሁራን ዘንድ እምብዛም ተቀባይነት ያገኘ አይመስልም፡፡ በግድ ኦሮሞን አማራ ለማድረግ ነው በሚል ወቀሳ የሚሰነዝሩ አሉ …
እንዲህ የሚሉት ሁሉም ከኢትዮጵ ዘር የመጣው የደሸት ልጆች መሆናቸውን ባለማወቃቸው ነው። ይሄ መረጃ ስለሌላቸው ራሳቸውን እንደ ባዕድ አግልለው ስለሚያዩ ነው እንጂ አሁን ይሄ እኔ ያቀረብኩትን ማስረጃ በቅን ልቦና አገናዝበው ለመረዳት ከሞከሩ፣ የትልቁ ሰው የኢትዮጵ፣ የጠቢቡና የሊቀካህናቱ የደሸት ልጅ እንደሆኑ በሚያውቁ ጊዜ፣ እነሱ እንደተሳሳቱ ተገንዝበው ወደ ማንነታቸው ላይ አተኩረው ይኮሩበታል ብዬ አስባለሁ፡፡ የመጣነው ከትልቅ ዘር ነው፡፡ ኦሮሞውም አማራውም የመጣው ከዚህ ትልቅ ሰው ነው፡፡ በዚህ ሁላችንም ልንኮራ ይገባናል፡፡
የአሁኗ እና የቀድሞዋ ኢትዮጵያ ልዩነታቸውና አንድነታቸው ምንድን ነው?
በግዛት ከሄድን ጥንት መላው አፍሪካ ኢትዮጵያ ነው የሚባለው፡፡ ከየመን አልፎ ሁሉ ይሄዳል፡፡ ግብፅ ውስጥ ፈርኦኖች የሚባሉት ኢትዮጵያውያን ነበሩ፡፡ ኢትዮጵያውያን ከአባይ ላይ ከመርከብ ወርደው ሜዳ አግኝተው የሰፈሩበት ቦታ ነው፤ ግብፅ፡፡ የአፍሪካ ሁሉ ነገር ከኛ አይወጣም፡፡
የኢትዮጵያ ታሪክ የ3ሺህ ዘመን ነው ይባላል፡፡ እርሶ የደረሱበት የጥናት ውጤት ምን ይላል?-
አዎ፤ በተለምዶ 3ሺህ አመት ይባላል እንጂ ከ7ሺ በላይ ነው፤ የኢትዮጵያ ታሪክ፡፡ ኖህ ኢትዮጵያ ላይ ነግሷል፤ ከዚያ ጀምሮ 7ሺህ አመት ነው፡፡
እስካሁን በነገሩን ታሪክ ውስጥ መፅሐፍ ቅዱስ ብቻ ነው በማስረጃነት የሚጠቅሱት፡፡ መፅሐፍ ቅዱስን ብቻ የታሪክ ምንጭ ማድረግ ይቻላል?
መፅሐፍ ቅዱስ ብቻ አይደለም፡፡ 42 ሰነዶችን አሁን በሚወጣው መፅሐፌ ላይ በግልፅ አስቀምጫለሁ። እነዚህ ሰነዶች በተለያዩ ሰዎች በጥንት ጊዜ የተፃፉ ናቸው፡፡ ኑቢያ ውስጥ ጀበል ኑባ በተባለ ቦታ ተቀብረው የቀሩ፣በጥንት ፍርስራሽ የኢትዮጵያ ቤተ-ክርስቲያን (ከእስልምና በፊት የነበረ) ድንጋይ ሳጥን ውስጥ ተቀብረው የነበሩ የብራና ሰነዶች አግኝቻለሁ፡፡ በዚያ ላይም የተመሰረተ ነው። ከመፅሐፍ ቅዱስ ውጪ 42 ተጨማሪ የታሪክ ሰነዶችን ተጠቅሜያለሁ፤ይሄን መፅሐፍ ሳዘጋጅ፡፡
ቀጣይዋ ኢትዮጵያ ምን መምሰል አለባት ይላሉ?
አሁን ማንነታችንን አውቀን፣ የማንነት ቀውሳችንን ፈትተን፣ሁላችንም የኢትዮጵያ ዘር፣ የአንድ አባትና እናት ልጆች—–መሆናችንን ተገንዝበን፤ በፍቅር፣ በሰላም፣ በመከባበር፣ በእኩልነት መኖር አለብን ብዬ አስባለሁ፡፡ ሁላችንንም ኢትዮጵ ያገናኘናል፡፡
ምንጭ፡- አዲስ አድማስ
የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እንቅስቃሴን የተመለከተ መረጃ ለኤርትራ መንግስት ያቀበሉ ዘጠኝ ግለሰቦች በእስራት ተቀጡ
በታሪክ አዱኛ
በኢትዮጵያ ድንበር ስለሚገኙ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እና ኤርትራውያን ስደተኞች እንቅስቃሴ ለኤርትራ መንግስት መረጃ ያቀበሉ ዘጠኝ ግለሰቦች በፅኑ እስራት ተቀጡ።

ተከሳሾቹ 1ኛ ካሃሳ መስፍን፣ 2ኛ አብደላ ኢብራሂም፣ 3ኛ ልኡል መሃሪ፣ 4ኛ ፍስሃይ ተክለገብረስላሴ፣ 5ኛ ጎይቶም ይደጎ ተስፋይ፣ 6ኛ ጎበዘይ ገብረስላሴ፣ 7ኛ ገብረሚካኤል ገብረማርያም፣ 8ኛ ብርሃኔ ምረጽ ይልማ እና 9ኛ ትኩህ ንጉሴ ገብረ መድን ይባላሉ።
ከ1ኛ እስከ 5ኛ ያሉ ተከሳሾች የኤርትራ ዜግነት ያላቸው ሲሆኑ ከ6ኛ እስከ 9ኛ ያሉ ተከሳሾች ደግሞ ኢትዮጵያውያን ናቸው።
ተከሳሾቹ ከጥቅምት ወር 2004 ዓ.ም እስከ 2006 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት ከኤርትራ መንግስት የመረጃ ሰራተኞች ጋር ሚስጥራዊ ግንኙነት በመፍጠር በኢትዮጵያ ድንበር የሚገኙ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እና የኤርትራ ስደተኞች እንቅስቃሴ በአጠቃላይ ስለ ኢትዮጵያ ሚስጥራዊ መረጃዎችን ለኤርትራ መንግስት አቀብለዋል ይላል የአቃቤ ህግ ክስ።
በተጨማሪም 2ኛ ተከሳሽ በግንቦት ወር 2006 ዓ.ም አራት ኤፍዋን ቦምቦችን በአካባቢው ለሚገኙ ግለሰቦች ለመሸጥ ሲዘጋጅ በቁጥጥር ስር ውሏል።
በተመሳሳይ 8ኛ ተከሳሽም የመሳሪያ ጥይቶችን እና አምስት ቦምቦችን ሸሽጎ መያዙንም ክሱ ያስረዳል።
በዚህም መሰረት አቃቤ ህግ የሃገሪቱን ሚስጥራዊ መረጃ በማቀበል እና ስለላ ወንጀል ክስ መስረቶባቸዋል።
ተከሳሾቹ ድርጊቱን ክደው የተከራከሩ ቢሆንም አቃቤ ህግ የብሄራዊ የመረጃና ደህንነት አገልግሎት ኤጀንሲ የሰነድ ማስረጃና የሰው ምስክር አቅርቦ አሰምቷል።
የግራ ቀኙን ክርክር የተከታተለው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎትም ተከሳሾቹን ጥፋተኛ ብሏቸዋል።
ችሎቱ ከ7ኛ እና ከ8ኛ ተከሳሾች ውጪ ያሉትን ተከሳሾች በ3 አመት ከ4 ወር እስራት እንዲቀጡ ወስኗል።
7ኛ ተከሳሽ የደም ግፊት ህመምተኛ መሆኑን በማስረጃ በማቅረቡ አንድ ማቅለያ ተይዞለት በሶስት አመት ጽኑ እስራት ሲቀጣ፥ 8ኛ ተከሳሸ ደግሞ በአራት አመት ከስድስት ወር እስራትና በ500 ብር እንዲቀጣ ተወስኖበታል።
በተከሳሾቹ እጅ ላይ የተያዙ ቦምቦች ለመንግስት ገቢ እንዲሆኑ ፍርድ ቤቱ አዟል።
በአጠቃላይ ሁሉም ተከሳሾች ለአምስት አመት ከማንኛውም ህዝባዊ መብታችው እንዲታገዱ ችሎቱ ወስኗል።
ምንጭ፡- ፋናቢሲ (የሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ዘገባ), http://www.fanabc.com/index.php/news/item/17450
በርካታ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በተለያየ የአፍሪካ ሀገራት እየታሰሩ መሆኑ ቢታወቅም፤ በርካታ ወጣቶች አሁንም በመሰደድ ላይ መሆናቸውን ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት አስታወቀ
በተለያዩ የምዕራብና ደቡባዊ አፍሪካ ሀገራት ቁጥራችዉ በትክክል ሊታወቅ ያልቻለ ስደተኛ ኢትዮጵያውያን በእስር ላይ መሆናቸውንና በርካታ ወጣቶች ከሀገሪቱ በመሰደድ ላይ እንደሚገኙ የአለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት (IOM) ሐሙስ አስታወቀ ። ባለፉት ስድስት ወራቶች ብቻ በተለያዩ 10 የአፍሪካ ሀገራት ለዚሁ ችግር ተጋለጠዉ የነበሩ 1ሺ 657 ኢትዮጵያዉያንን ወደ ሀገር ቤት መመለስ እንደቻለም ድርጅቱ ገልጿል።
የዓለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት ስደተኞቹን ወደ ሀገር ለማመላለስ ጥረትን ቢያደርግም አሁንም ድረስ በርካታ ወጣቶች ከሀገሪቱ በመሰደድ ላይ መሆናቸው ስጋትን እየፈጠረ መምጣቱን አክሎ አመልክቷል።

በተያዘዉ ሳምንት በዛሚቢያ በህገ-ወጥ መንገድ ገብታችኋል ተብለዉ የተላለፋባቸዉን የእስር ቅጣት የጨረሱና ወደ ሀገር መመለስ ያልቻሉ 14 ታዳጊ ህፃናት ወደ ኢትዮጵያ መመለሱን የስደተኞች ተቋም ገልጿል። በማላዊ ፣ ዛሚቢያ ፣ ታንዛኒያ እና ሌሎች ሀገራት ቁጥራቸዉ በትክክል ሊታወቅ ያልቻለ ስደተኞች በእስር ላይ የሚገኙ ሲሆን የእስር ጊዜያቸውን ያጠናቀቁ ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸዉ የሚመልሳቸዉ ባለመኖሩ ለችግር ተጋልጠዋል ። የማላዊ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾ ድርጅቶችና ግለሰቦች ከ120 የሚበልጡ ኢትዮጵያዉያን በእስር ቤት እየደረሰባቸዉ ያለን ስቃይ በመቃወም ስደተኞቹ ወደ ሀገራቸዉ እንዲመለሱ በመጠየቅ ዘመቻን መክፈታቸዉ ይታወሳል።
የምዕራብና ደቡባዊ አፍሪካ ሀገራትን በመጠቀም ስደተኛ ኢትዮጵያውያኑ ወደ ደቡብ አፍሪካ የመግባት እቅድ እንዳላቸዉ የተለያዩ አካላት ይገልፃሉ። ሰሞኑን የአለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት (IOM) ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት ታዳጊ ህፃናት በርካታ ኢትዮጵያዉያን በተለያዩ ሀገራት በሚገኙ እስር ቤቶች በስቃይ ላይ መሆናቸዉን እንዳስታውቁ ድርጅቱ በችግሩ ዙሪያ ባወጣዉ ሪፖርት አመልክቷል።
የስደተኛ ድርጅቱ ለችግር ተጋልጠዉ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገር ለመመለስ እያደረገ ባለዉ ጥረት ባለፉት 6 ወራቶች ብቻ 1 ሺ 657 ስደተኞች ከ10 የፍሪካ ሀገራት ሊጓጓዙ ችለዋል። መንግስት በተለያዩ ሀገራት ለችግር ተጋልጠዉ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን በተመለከተ እስካሁን ድረስ የሰጠው ምላሽ የለም ።
ምንጭ፡- ኢሳት
በጎንደር በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 ያላነሱ ሰዎች ሲገደሉ፤ በአካባቢው ውጥረቱ እንደቀጠለ ነው
በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን በሚገኘው ጎንደር ከተማ፤ በያዝነው ሳምንት ማክሰኞ ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት ጀምሮ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ20 ያላነሱ ዜጎች መገደላቸው ተጠቆመ፡፡ መረጃዎች እንደሚመለክቱት ከሆኑ፤ 10 ያህል ንፁሃን ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ርምጃ መገደላቸውን ተከትሎ፤ ህዝቡ በወሰደው የአፀፋ እርምጃ 9 የፌደራል ፖሊስ እና 1 የመከላከያ ሰራዊት አባል ተገድለዋል፡፡
በስፍረው የሚገኙ የዓይን እማኞች በበኩላቸው የተገደሉ ሶወች ቁጥር ከተጠቀሰው እንደሚልቅ ይናገራሉ፡፡ ይሁን እንጂ በግጭቱ የተገደሉ ሰዎችን ቁጥር በተመለከተ እስካሁን ከገለልተኛ አካልም ሆነ ከመንግሥት የተሰጠ ማረጋገጫ የለም፡፡

ባለፈው ማክሰኞ ሐምሌ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረ ግጭት በጎንደር ለሁለት ተከታተይ ቀናት የነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ ወደሌሎች አጎራባች ከተሞች መዛመቱ ተሰምቷል፡፡ ህዝባዊ ተቃውሞውም ሐሙስ ወደ ዳባርቅ ከተማ የተዛመተ ሲሆን፤ አሁን ደግሞ ወደ ሳንጃ ወረዳ እና ወደ ሌሎች አጎራባች ከተሞችና ወረዳዎች መዛመቱ እየተነገረ ነው፡፡

በተፈጠረው ግጭትም የሰው ህይወትን ጨምሮ የህወሃት እና የደጋፊው ናቸው የተባሉ ንብረቶች መውደምንም አስከትሏል፡፡
የግጭቱ መንስኤ የወልቃይት ጠገዴ ህዝብ የአማራ ማንነትና ተያያዥ መብታቶቻችን ይከበሩልን የሚል ጥያቄን ለትግራይ ክልላዊ መስተዳደርና ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ሲያቀርቡ የነበሩ ተወካይ ኮሚቴዎችን ከሚኖሩበት ጎንደር ከተማ የትግራይ ክልልና የፌደራሉ መንግሥት የፀጥታ ኃይሎችና የደህንነት አባላት ለማፈን እና ለማሰር በወሰዱት የኃይል እርምጃ በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑ ይታወቃል፡፡
በተለይ ከወልቃይት የአማራ ማንነት ተወካይ ኮሚቴዎች መካከል ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ፤ ሊያግቷቸው የመጡ የፀጥታ ኃይሎችን “ህጋዊ ከሆናችሁ በቀን መምጣት ትችላላችሁ፤ ካልሆነ በሌሊት እኔ እጄን ለማንም አልሰጥም” ማለታቸውን ተከትሎ በተፈጠረው አለመግባባት፤ ህዝቡ የመንግሥት ኃይሎችን የሌሊት እገታና ሌሎች 4 የኮሚቴ አባላትን እስርና እገታ በመቃወም ከመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ጋር ግጭት እንደተፈጠረ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡
በጎንደር በተፈጠረው አለመረጋጋት የተባበሩት መንግሥታትን ጨምሮ የአሜሪካና የእንግሊዝ መንግሥታት ዜጎቻቸው ወደጎንደርና አቅራቢያው ከመሄድ እንዲቆጠቡ አስጠንቅቀዋል፡፡ እስራኤል በበኩሏ በጎንደር የሚገኙ 6 ሺህ ቤተ እስራኤላውያንን እና በስፍራው የሚገኙ በኢትዮጵያ የእስራኤል ኤምባሲ ተወካዮችን ደህንነት በተመለከተ ከፍተኛ ቁጥጥር ወደሚደረግበት ስፍራ ጥበቃ እያደረገችላቸው መሆኑን የኢየሩሳሌም ፖስት ዘገባ አመልክቷል፡፡
በጎንደር ግጭቱ ለጊዜው የተረጋጋ ቢመስልም፤ አሁንም በአካባቢው በመንግሥትና በህዝቡ መካከል ከፍተኛ ውጥረት መኖሩ እየተገለፀ ነው፡፡
በጎንደር ህዝባዊ ተቃውሞ እና ውጥረቱ ቀጥሏል
(አዲስ ሚዲያ) በጎንደር ከተማ የወልቃይት የማንነት ጥያቄን የሚመሩ የኮሜቴ አባላትን ለማሰር በተወስደ እርምጃ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ከፍተኛ ግጭት አስከተለ። ግጭቱ የተከሰተው ትናንት ሰኞ ሐምሌ 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ሌሊት ጀምሮ እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
የመንግሥት ደህነት እና የፀጥታ ኃይሎች የወልቃይት ማንነት ጥያቄ የሚመሩ ኮሜቴ አባላት መካከል አቶ አታላይ ዘርፌ፣ አቶ ጌታቸው አደመ፣ አቶ መብራቱ ጌታሁንና አቶ አለነ ሻማ በቁጥጥር ስር ያደረገ ሲሆን፣ ኮሎኔል ደመቀ ዘውዴ በህግ የምትፈልጉኝ ከሆነ ሲነጋ መምጣት ትችላላችሁ በማለታቸው በተፈጠረው አለመግባባትና ግጭት በግድ እጅ እንዲሰጡ በኃይል በመንቀሳቀሳቸው ኮሎኔሉ እርምጃ መውሰዳቸው ተሰምቷል። ለምንግሥት የፀታ ኃይል እጃቸውን እንዲሰጡ በኃይል የተጠየቁት ኮሎኔል ደመቀ ዘውዴ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው፤ ቤታቸው በፀጥታ ኃይል መከበቡን ተሰምቷል፡፡ በተፈጠረው አለመግባባት ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት በመገደላቸው በህዝቡ በተወሰደ የአፀፋ እርምጃ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎችም መገደላቸውን የኢሳት ዘገባ አመልክቷል፡፡

መንግሥት ማክሰኞ ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጎንደርና ወልቃይት አካባቢን በተመለከተ ማምሻውን በሰጠው መግለጫ በተፈጠረው አለመግባባት 3 የልዩ ሃይል ፖሊሶች ሲገደሉ፣ 5 መቁሰላቸውን አስታውቋል። ይሁን እንጂ መንግሥት ለግጭቱ መንስኤ የወልቃይት ማንነት መብት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላትን በቁጥጥር ስር ለማዋል መሆኑን ከመግለፅ በመቆጠብ በቁጥጥር ስር ያዋላቸውን እና ለማዋል የፈለጋቸውን የወለወቃይት ማንነት መብት አስተባባሪ ኮሚቴ አባላትን ከኤርትራ መንግሥት ጋር በማያያዘ ሲወነጅል ተሰምቷል፡፡
በያዝነው 2008 ዓ.ም. ቀደም ሲል የወልቃይት ማንነት መብት ጥያቄ አቅራቢ ኮሚቴ አባላት መካከል አቶ ሲሳይ ሊላይ የሚባሉ የኮሚቴ አባል በትግራይ ክልል ልዩ ኃይል ታግተው ከተሰወሩ በኋላ በአካባቢው ውጥረት መንገሡን ተከትሎ ወህኒ ቤት በማሰር ለፍርድ ማቅረባቸው አይዘነጋም፡፡ የእስርና ፍርድ ጉዳያቸውም በሰቲት ሁመራ መቀጠሉ ታውቋል፡፡
ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ፤ በጎንደር የመንግሥት የኃይል ርምጃን በመቃወም ህዝቡ ንብረትነቱ የህወሓት/ኢህአዴግ የሆነውን ሰላም የህዝብ ማመላለሻ አውቶቡስ፣ በተጨማሪ ሌላ መለስተኛ የፀጥታ ኃይሉ ተሽከርካሪ እና በጎንደር ከሚገኙ የህወሓት የንግድ ኩባንያ መደብሮች መካከል የተወሰኑት ላይ የማቃጠል ርምጃ መወሰዱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በተቃውሞው ከጎንደር አዲስ አበባ ያሉ መንገዶችም በድንጋይ ተዘግተው ታይተዋል፡፡