ፍትህ መረገጡን በአደባባይ አስመስክረናል፤ሃላፊነታችንንም ተወጥተናል!
ለኔ እዉነተኛው የአንድነት ፓርቲ ትናንት መጋቢት 23 ቀን 2007 ዓ.ም. በፍርድ ቤት ውሳኔ ተቀብሯል፡፡ዱባና ቅል አበቃቀሉ ለየቅል እንደሆነ ቀድም ሲል አውቀናል፡፡ ዳኛ ብርቱኳንም፣ ፍርህይወትም ዳግም አልተከሰቱም፡፡ እንደ ኢህአዴግ የምርጫ ውጤት 99.6 ከመቶ አመራሩና አባላቱ በምርጫ ቦርድ እንዲበተኑ የተበየነበት እንዲሁም በደጋፊዎች የተገዛ ንብረት ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ በመንግስት ታጣቂ ፖሊሶች የተዘረፈበት አንድነት የፍትህ ተቋሙን ለመፈተሸ ምርጫ ቦርዱን መክሰሱ ይታወቃል፡፡
ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድን መክሰሳችን አግባብ እንዳልሆነ አንቀጽ ተጠቅሶ ከማስፈራሪያ ጋር ክሱ ዉድቅ ተደርጓል፡፡ በዚህም ፍትህ መረገጡን ባደባባይ አስመስክረናል፤ሃላፊነታችንንም ተወጥተናል፡፡ ቀጣዩን በቀጣይ ሂደት የምናየዉ ይሆናል፤እንደሚፈልጉት ተበትነን አንቀርም፡፡ አንድነቶች በያለንበት እንረጋጋ!!
ታላቋ ምዕራብ አፍሪካዊት ሃገር ናይጀሪያ እዚህ የደረሰችዉ ዉድ ዋጋ ከፍላ ነዉ፡፡ ከናይጀሪያም በላይ ዋጋ ብንከፈልም በልተዉ በማይጠግቡ በሎች ትግሉ እየተነጠቀ ዛሬም እዛዉ ላይ ነን፡፡ ታላቅዋ የምስራቅ አፍሪካ ኮከብ ሀገረ ኢትዮጵያ በልማት ስም ክብሯ እንዲወርድ እየተደረገች ትገኛለች፡፡ እናም በዲፕሎማሲ፤በዲሞክራሲ፤በኢኮኖሚም ይሁን በሁለንተናዊ ልማት የአለም ማህበረሰብ በአፍሪካ ትኩረት ናይጀሪያ ሆናለች፡፡ ኢትዮጵያ የምትፈለገዉ ለክፍለ አሁጉሩ የደህንነት አጋርነት ብቻ ነዉ፡፡
የናይጀሪያ ተፎካካሪ ፓርቲዎችና(የተቀናቃኝ ፓርቲዎች ትብብርና ዉህደት ያስከተለዉን ዉጤትም ልብ ይሏል) የተወዳዳሪ ግለሰቦች ሚና ቀላል ባይሆንም ለናይጀሪያ ተስፋ የሆናት ግን ህዝቡ ነዉ፡፡ የኢትዮጵያችንም የለዉጥ ተስፋ ህዝቡ ነዉ፡፡ በዚህ ወቅት የተቃዋሚ የፖለቲካ ሃይሎች አሰላለፍም የጎላ ድርሻ ይኖረዋል፡፡
በዞን 9 ብሎገሮችና ጋዜጠኞች ክስ ላይ ፍርድ ቤቱ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን መስማት ጀመረ
በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ቀናት የሚቆየው የማስረጃ መስማት ውሎ ዛሬ ምስክሮችን በማስማት ተጀምሯል፡፡ በዚህም መሰረት አቃቤ ህግ ጉዳዬን ያስረዱልኛል ያላቸውን 17 ምስክሮች ያስመዘገበ ሲሆን 15ቱ በፍርድ ቤቱ ተገኝተው ቃለ መሃላ ፈጽመዋል፡፡ አቃቤ ህግ ችሎቱ በዝግ ችሎት አንዲሆን የጠየቀ ሲሆን ምስክሮቼ እና የቤተሰቦቻቸውን ደህንነት ለመጠበቅ ችሎቱ በዝግ ሊሆን ይገባል የሚለውን አቤቱታውን ጠበቆች በከፍተኛ ደረጃ ተቃውመውታል፡፡ ምስክሮቹ የጭብጥ ምስክሮች ሳይሆኑ ፍተሻን የታዘቡ የደረጃ ምስክሮች በመሆናቸው እና ስማቸውም በግልጽ ተከሳሾች ጋር ስለደረሰ ምንም አይነት የደህንነተ ስጋት የለባቸውም ከሚለው የጠበቆች ክርክር በኋላ ፍርድ ቤቱ በጉዳዬ ላይ ተወያይቶ ለመወሰን ረፍት ወስዷል፡፡ በዚህም መሰረት የአቃቤህግን አቤቱታ ውድቅ በማድረግ ችሎቱ በግልጽ ሆኖ መስክሮች ምስክርነታቸውን እነዲያሰሙ ታዟል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አቃቤ ህግ ያቀረባቸው ምስክሮች አነማን ላይ አንደሚመሰክሩ እና ምን አንደሚመሰክሩ በተጠየቀው መሰረት ፍርድ ቤቱም በጠበቆቹ ስለተነሱት ነጥቦች የአቃቤ ህግን ምላሽ ጠይቋል፡፡ አቃቤ ህግም በዛሬው ዕለት የቀረቡት ምስክሮች በ2ኛ፣ በ3ኛ፣ በ5ኛ፣ በ6ኛ፣ በ7ኛ እና 8ኛ ተከሳሾች ( በስድስቱ የዞን9 ጦማርያን ላይ እና በጋዜጠኛ አስማማው ላይ ) ላይ እንደሚመሰክሩ ገልጾ የፌደራል ወንጀል ምርመራ ቡድን በብርበራ ያገኛቸው ማስረጃዎች ከተከሳሾች የተገኙ ስለመሆናቸው ያስረዱልኛል ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡
በምላሹም መሰረት የአቃቤ ህግ ምስክሮች ምስክርነታቸው ሰጥተዋል፡፡ ምስክርነታቸው ሲሰጡ በነበረበት ወቅት የተከሳሾችን ስም አለማወቅ አንዲሁም የተከሳሾችን መልክ አለመለየት የመሳሰሉት ጉዳዬች የተስተዋሉ ሲሆን ምስክርነታቸውን የሰጡት ሰዎች ስም ዝርዝር እና የምስክርነታቸው ጭብጥ በአጭሩ አንደሚከተለው ነው ፡፡
1.ሙሉጌታ መዝገቡ ለማ – ናዝሬት ነዋሪ ነኝ መአከላዊ ምርመራ ለግል ጉዳይ ሄጄ ፓሊስ ታዛቢ ምስክር አንድሆን ጠይቆኝ በዚያ መሰረት ምስክር ሆኜ ተገኝቻለሁ፡፡ ከአቤል ከኮምፒውተሩ ላይ ጽሁፍ ሲወጣ እና ሲፈርም አይቼ እኔም ፈርሜያለሁ ፡፡ የጽሁፉን ይዘት አላነበብኩም አንዳንድ ቦታ አፍሪካ ሪቪው ኬንያ የሚል ቃል አይቻለሁ የሚል ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡
2.በለጡ አበበ ዮሴፍ ይባላሉ፡፡ እድሜያቸው 32 ሲሆን ከፍተኛው ፍርድ ቤት የካ ምድብ ሰራተኛ ናቸው፡፡ አዲስ አበባ ነዋሪ ሲሆኑ በማን ላይ ለመመስከር እንደመጡ ሲጠየቁ በስም እንደማያስታውሱት ገልጸው በአካል ግን ለይተው አሳይተዋል፡፡ መስካሪዋ በ6ኛ ተከሳሽ ዘላለም ክብረት ላይ የሚመሰክሩ ሲሆን በተለየ ስም ሲጠሩት ተስተውለዋል
“የሽብርተኝነት ጉዳይ የሚያመለክት ይመስለኛል፡፡ ወደ 70 ገጽ አማርኛና 10 ገጽ እንግሊዝኛ ጽሁፍ ተገኝቷል፡፡ ያየሁትን አይቼ ፈርሜያለሁ፡፡” ካሉ በኋላ ተከሳሹስ ፈርሟል ተብለው ሲጠየቁ መጀመሪያ አላስታውስም ቢሉም እንደገና ሲጠየቁ ግን አዎ ፈርሟል ብለዋል፡፡
3.እታፈራሁ ጌታቸው ወልዴ የሚባሉ ሲሆን እድሜያቸው 36 ነው፡፡ በመንግስት ት/ቤት በአስተዳደር ሰራተኛነት የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ ማን ላይ እንደሚመሰክሩ ሲጠየቁ ፍቃዱ እና…..(ስሙ ጠፍቶባቸው ቆይተው) እ…አጥናፉ ብለዋል፡፡ በአካል ደግሞ በፍቃዱን አሳዩ ሲባሉ አጥናፍን አሳይተዋል፡፡ የምስክርነት ቃላቸውም ማእከላዊ ምርመራ ለግል ጉዳይ ሄደው ጽሁፎች ሲታተሙ ማየታቸውንና በፍቃዱ በፍቃደኛነት ሲፈርም ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ስለጽሁፎቹ ሲጠየቁ “የአማርኛ ጽሑፎች ናቸው፡፡ 60 ገጽ የሚሆን ‹ወያኔ ይውደም› ምናምን የሚል ጽሑፍ አይቻለሁ፡፡ እንግሊዝኛም አለው 10 ገጽ ይሆናል፡፡ በምስል ከውጭ ሰው ጋር ሆነው የሚነጋገሩትም አይቻለሁ፡፡ ይዘቱ ግን ግር ይለኛል፡፡” ብለዋል፡፡ አጥናፍን አስመልክቶ ደግሞ ‹‹የእሱንም በዚያው መልኩ ነው ያየነው፡፡ ዕለቱም ግንቦት 16/2006 ነው፡፡ ኮምፒውተሩ ላይ የነበሩትን ጽሁፎች እዚያ ለነበሩት ሲያሳይ ነበር፡፡ ጽሑፎችን አይቻቸዋለሁ….‹የጨለማው ቀን….የጨለማው ንጉስ› የሚል አይቻለሁ፡፡ ‹ኢትዮጵያ አንድ ናት› የሚልም አይቻለሁ፡፡ ወደ 30 ገጽ ይሆናል፡፡ ሁሉም ፕሪንት ተደርጎ ሁላችንም ፈርመንበታል፡፡››ብለዋል
ሶስቱ ምስክሮች ከተሰሙ በኋላ ጠበቆች በሂደቱ ላይ አስተያየት አለን በማለት፣ ዶክመንቶቹ ፕብሊክ ዶክመንት ናቸው በአደባባይ የተጻፉ ጽሁፎቻቸው እና በማንኛውም ቦታ የሚገኙ ስለሆኑ ዶክመንቶቹን ክደን አልተከራከርንም የእኛ ክርክር ዶክመንቶቹ ለወንጀል ስራ የሚበቁ አይደሉም ነውና በዚህ ጭብጥ ዙሪያ ምስክር መስማቱ ያብቃልን የሚል ጥያቄ አንስተዋል፡፡አቃቤ ህግ በበኩሉ ሁሉም ምስክሮች አንዲሰሙልኝ እፈልጋለሁ በማለቱ ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ ያስረዱልኛል ካለ ይቀጥል በማለቱ ምስክሮቹ ቀጥለዋል፡፡ ጠበቆች መስቀለኛ ጥያቄ ሳይጠይቁ ተከታዬቹ ምስክሮች መሰማታቸው ቀጥሏል፡፡
4.አራተኛው ምስክር አፈወርቅ ካሳ ይባላሉ፡፡ የግል ሰራተኛ ሲሆኑ እድሜያቸው 46 ነው፡፡‹‹ቀኑ ሚያዝያ 18/2006 ነው፡፡ የተከሳሹ አስማማው ቤት ጠዋት 3፡00 አካባቢ ሲፈተሸ ታዛቢ ነበርኩ፡፡ ጋዜጦች፣ መጽሔቶች፣ ፓስፖርት…ብዙ ወረቀቶች ላይ ‹‹አዎ የእኔ ናቸው›› እያለ ሲፈርም አይቻለሁ፡፡ እኔም ፈርሜያለሁ፡፡ ቤተሰቦቹም ቤት ውስጥ ነበሩ፡፡ አብዛኛው ያየሁት የግል መጽሄቶችን ነው፡፡ ማህተምም አይቻለሁ፡፡ ደሞ ቢሮው ሄደን ላፕቶፕ፣ ፍላሽ፣ ሲዲ፣ መጽሔቶች አይቻለሁ፡፡ ፖሊስ የሚፈልገውን እየለየ ፈርመናል፡፡ ወደቢሮው የሄድነው በመኪና ነበር፡፡ ከዛ ደግሞ አድራሻችንን ይዘው ስለነበር ሰኔ 4….አይ 14/2006 ነው መሰለኝ ከማዕከላዊ ተጠርተን ላፕቶፕ ላይ የነበረውን ስዕሎችና የእንግሊዝኛ ንግግሮች ሲወጡ አይቻለሁ፡፡ የእኔ ነው ብሎ ሲፈርም እኛ ታዛቢዎችም ፈርመናል፡፡›› ብለው ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡
5.አምስተኛ ምስክር አጌና አንከና ይባላሉ፡፡ እድሜያቸው 48 ሲሆን ነዋሪነታቸው አ.አ ነው፡፡ የሚመሰክሩት ደግሞ በ3ኛ ተከሳሽ ናትናኤል ላይ ነው፡፡ የምስክርነት ቃላቸው፣ ‹‹ሰኔ 17/2006 ለግል ጉዳይ ማዕከላዊ ነበርኩ፡፡ ከቀኑ 8፡00 ታዛቢ ሁነኝ ብሎ ፖሊስ ጠይቆኝ ታዝቤያለሁ፡፡ ላፕቶፑ ላይ አማርኛ ጽሑፎች አይቻለሁ፡፡ ጽሑፎቹ የተከሳሹ ስለመሆናቸው አምኖ ሲፈርምባቸው ታዛቢዎችም ፈርመናል፡፡ ይዘቱን ግን አላነበብኩትም፤ አልተረዳሁትም፡፡ የገጹን ብዛትም አላስታውስም፡፡›› የሚል የምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡
6.ስድስተኛ ምስክር ገብረጨርቆስ ገብረመስቀል ይባላሉ፡፡ የ50 ዓመት የመንግስት ሰራተኛ ናቸው፡፡ ምስክሩ በአስማማው ላይ ለመመስከር እንደመጡ ቢናገሩም በአካል ግን ለይተው አላወቁትም፡፡ እንዲያውም አስማማውን አሳዩ ሲባሉ አቤልን አሳይተዋል፡፡
ከፍርድ ቤቱ ውሎ በኋላ አስተያየታቸው የሰጡት የተከሳሾች ጠበቆች አቃቤ ሀግ ያቀረባቸው ምስክሮች ወረቀት ሲፈረም አየን ከማለት ውጪ ምንም አይነት ለሂደቱ ቁም ነገር ያለው ምስክርነት የሚሰጡ አይደሉም ፡፡ ተከሳሾች ተገኘባቸው የተባለው ጽሁፍ የአደባባይ ዶክመንት ከመሆኑም በላይ አልተገኘብንም ብለን ክደን አልተከራከርንም በይዘቱ ላይ ክርክር ስላልተደረገ መስቀለኛ ጥያቄ ለማቅረብም ብዙ አልጨነቅንም ብለዋል፡፡አቃቤ ሀግ የወንጀሉን የመጀመሪያ ደረጃ ጭብጥ የሚያሳዬ ምስክሮችን ያቅርብ አይቅርብ የሚታወቅ ነገር የለም፡፡ የማስረጃ ማሰማት ሂደቱ ነገ ይቀጥላል፡፡
በተቃራኒው ምሳቸውን ችሎት ውስጥ የተመገቡት ሁሉም እስረኞች በጠንካራ መንፈስ ሆነው ሲጨዋወቱ እና ሲነጋገሩ ተስተውለዋል፡፡ የችሎቱ ተሳታፌዎች በምስክሮች መደናበር እየሳቁ ነበረ ሲሆን የዞን9 ወዳጆች አጋሮች ቤተሰብና ጋዜጠኞች ተገኝተዋል፡፡
ምንጭ፡-ዞን 9 ማኀበራዊ ገፅ
የመድረክ ከፍተኛ አመራርና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህሩ አቶ በቀለ ገርባ ከእስር ተለቀቁ
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርና የቀድሞው የኦሮሞ ፌደራሊስት ንቅናቄ፣ የአሁኑ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ/መድረክ ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት አቶ በቀለ ገርባ ከነሐሴ 2003 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ከቆዩ በኋላ መጋቢት 21 ቀን 2007 ዓ.ም. ተለቀዋል፡፡ አቶ በቀለ ገርባ መንግሥት በዜጎች ላይ በፈፀማቸውና እየፈፀማቸው ባሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ጉዳይ ከአምንስቲ ኢንተርናል ጋር ቃለ መጠይቅ ካደረጉ በኋላ የኦነግ አባል ናቸው በሚል በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ ወንጀል ችሎት 8 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸው ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ተከላካይ ጠበቆቻቸውና አቶ በቀለ የታሰሩት ያለምንም ወንጀል እንደሆነ፣መንግሥት የኦነግ አባል ብሎ የመሰረተባቸው ክስ እንደማይመለከታቸው፣ እሳቸው በወቅቱ በሀገር ውስጥ በሰላማዊ መንገድ እየታገለ ያለው የኦፌዲን/መድረክ አመራር መሆናቸውን በማስረጃ ቢከራከሩም ፍርድ ቤቱ ሳይቀበለው በመቅረቱ ለፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ መጠየቃቸው ይታወሳል፡፡
እነ አቶ በቀለ ገርባ የከፍተኛው ፍርድ ቤት ውሳኔ በመቃወም ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ካሉ በኋላ የ8 ዓመቱ ፅኑ እስራት ወደ 3 ዓመት ከ7 ወር የተቀነሰ ሲሆን፤ ይሄንንም ይግባኝ ብለው ወደ ፌደራሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ቢሄዱም የ3 ዓመት ከ7 ወር ፍርድ በመፅናቱ በእስር ቆይተዋል፡፡ አቶ በቀለ ገርባ በህጉ መሰረት በአመክሮ ከእስር መፈታት የነበረባቸው ከአንድ ዓመት በፊት ጥር 2006 ዓ.ም. ቢሆንም፤ ዝዋይ የሚገኘውም ሆነ አቃቂ ቂሊንጦ የሚገኘው ወህኒ ቤት ፈቃደኛ ባለመሆናቸው 4ኛ ዓመት ድረስ በእስር ሊቆዩ ችለዋል፡፡ መረጃዎች እንደጠቆሙት ከሆነ አቶ በቀለ ገርባ የተለቀቁት ከነበሩበት እስር ቤት ከተለቀቁ በኋላ ከባለቤታቸው ወ/ሮ ሐና ጋር እየተጓዙ ከእስር ቤቱ ብዙም ሳይርቁ፤ በወህኒ ቤቱ ጠባቂዎች ቆይ ሌላ የሚጣራ ጉዳይ አለ በሚል ተመልሰው እስር ቤት ካስገቧቸው በኋላ በጭለማ ሞጆ ከተማ አካባቢ ተወስደው መለቀቃቸው ተጠቁሟል፡፡ አቶ በቀለ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ከማስተማራቸው በተጨማሪ የዶክተሬት ዲግሪ ማጠናቀቂያቸው ላይ መታሰራቸው አይዘነጋም፡፡ በአሁን ወቅት የኦፌኮ/መድረክ አመራር አቶ ኦልባና ሊሊሳን፣ የአድነት ከፍተኛ አመራር አቶ አንዱዓለም አራጌ እና ጋዜጠኛ እስንክንድር ነጋን ጨምሮ በርካታ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮችና አክቲቪስቶች በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡
የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች የእምነት ክህደት ቃላቸውን ‘ሰጡ’
“ኢትዮጵያ ውስጥ ብቸኛው አሸባሪ ህወሓት/ኢህአዴግ ነው” አብርሃ ደስታ
“የጦር ችሎት በሚመስል ችሎት እየተንገላታን ነው” የሺዋስ አሰፋ
በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና ሌሎች በተመሳሳይ መዝገቡ የተካተቱ ተከሳሾች በተከሰሱበት ድርጊት ላይ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጡ፡፡
የሰማያዊ፣ የአንድነት እና የዓረና ትግራይ ፓርቲ አመራሮችን ጨምሮ 10 ተከሳሾች መጋቢት 10 ቀን 2007 ዓ.ም በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ 19ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡ ሲሆን ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ ላይ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ በዚህ መሰረት ከአንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ጀምሮ፣ “በክሱ ላይ የተመለከተውን ድርጊት ፈጽመዋል ወይስ አልፈጸሙም?” የሚል ተመሳሳይ ጥያቄ ለእያንዳንዳቸው የቀረበላቸው ሲሆን ብዙዎቹ ተከሳሾች ምላሻቸውን በቀጥታ ለመስጠት አለመፈለጋቸውን አሳይተዋል፡፡
1ኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ለቀረበለት ጥያቄ፣ “በአቃቤ ህግ እና በፖሊስ ተቀነባብሮ የቀረበብኝን ክስ በተመለከተ ለክሱ እውቅና ላለመስጠት ምንም አልልም፡፡ በክሱ ላይ አስተያየት በመስጠት ለጸረ-ሽብር አዋጁ እውቅና መስጠት አልፈልግም” የሚል መልስ በመስጠቱ ፍርድ ቤቱ ክሱን ክዶ ቃል እንደሰጠ አድርጎ መዝግቦታል፡፡
2ኛ ተከሳሽ ሀብታሙ አያሌው በበኩሉ “በክሱ ላይ የተመለከተውን ድርጊት እንዳልፈጸምኩ እንኳን እኔ ከሳሾቼም በደንብ ያውቃሉ፡፡ ከሳሾቼ እኔ ድርጊቱን የመፈፀም ፍላጎቱም ሀሳቡም እንደሌለኝ ያውቃሉ” ብሏል፡፡
3ኛ ተከሳሽ ዳንኤል ሺበሽ ደግሞ፣ “እኔ ስለ ሽብር የሰማሁት ከአልቃይዳው መሪ ኦሳማ ቢላደን እና መለስ ዜናዊ ነው፡፡ እኔ አሸባሪ አይደለሁም፤ ሀሳቡም ሆነ ፍላጎቱም የለኝም፡፡ ባህሌና እምነቴም አይፈቅድልኝም” ሲል ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡
4ኛ ተከሳሽ አብርሃ ደስታ “አሸባሪ ማለት የፖለቲካም ሆነ ሌላ ዓላማውን ሰላማዊ ዜጎችን በማሸበር ለማስፈፀም የሚሰራ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ብቸኛው አሸባሪ ድርጅት ህወሓት/ኢህአዴግ ነው፡፡ እኔ ደግሞ የዚህ አሸባሪ ድርጅት ተቃዋሚ ነኝ” ብሏል፡፡
5ኛ ተከሳሽ የሺዋስ አሰፋ በበኩሉ፣ “በመጀመሪያ ለመጨረሻ ጊዜ ስለሆነ የምናገረው እንዳታቋርጡኝ አደራ እላለሁ፡፡ ክሱ ቅንብር ነው፡፡ ዳኞችም ህጉ የሰጣቸው ነጻነት አይታይባቸውም፡፡ ይህ 19ኛ ወንጀል ችሎት የጦር ችሎት ነው የሚመስለኝ፡፡ ስለሆነም የጦር ችሎት በሚመስል ችሎት እየተንገላታን ነው” ሲል ተናግሯል፡፡ የሺዋስ በዳኞች በተደጋጋሚ ንግግሩ እንዲቅረጥ ተደርጓል፡፡ በመጨረሻም ክሱን ክዶ ቃል ሰጥቷል በሚል ተመዝገቦለታል፡፡
6ኛ ተከሳሽ ዮናታን ወልዴ፣ “የተዘጋጀብኝን ክስ ያለፍቃዴ እንድተውን እየተገደድኩ ነው” ብሏል፡፡
7ኛ ተከሳሽ አብርሃም ሰለሞን ደግሞ፣ “የተቀነባበረ ክስ ላይ ምንም ማለት አይቻልም” ብሏል፡፡
8ኛ ተከሳሽ ሰለሞን ግርማ፣ “ነፃ ሰው ነኝ፡፡”
9ኛ ተከሳሽ ባህሩ ደጉ “ባህሉንና ፈጣሪውን ከሚያከብር ማህበረሰብ ወጥቼ አሸባሪ ልሆን አልችልም” ሲል አስረድቷል፡፡
10ኛ ተከሳሽ ተስፋዬ ተፈሪ ደግሞ፣ “ድርጊቱን አልፈጸምኩም” ብሏል፡፡
በአጠቃላይ ተከሳሾች ክሱ ላይ የተጠቀሰውን ድርጊት ክደው ቃል በመስጠታቸው አቃቤ ህግ ምስክሮችን እንዲያሰማ ለግንቦት 13፣ 14፣ 15 ቀን 2007 ዓ.ም ለተከታታይ 3 ቀናት ምስክር እንዲሰማ ቀጠሮ መሰጠቱን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክታል፡፡
የአንድነት ፓርቲ “ቀብር” ላይ እንገናኝ፤ መቃብሩ ላይም እርም እናዉጣና የአንድነት ሃይሎች ዳብረን እንወጣ ዘንድ ትግሉ ግድ ይለናል!
በአብዛኛዎቻችን ኢትዮጵያዉያን አንድ ጥሩ ባህል አለን፡፡የምንወደዉንና የሚመቻንን ሰዉ በሞት ስናጣ እርም የማዉጣት ባህል፤ ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ሆኖ አገኘሁት፡፡ሠዉና የፖለቲካ ድርጅ ባይገናኙም በጉልበተኛ ሃይል እንዲገናኙ ሲደረግ ከማገናኘት ዉጪ ምርጫ የለንምና እናገናኛቸዋልን፡፡
አቅምና ሁኔታዎች በፈቀዱት መጠን የወቅቱን ያገራችን ችግር በመፍታት በኩል የራሱን አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት፤ የኢህአዴግ ሰዎችን ጨምሮ ያብዛኛዉ ተራማጅ ኢትዮጵያዊ ቤት እንዲሆን አድርገን ስንገነባዉ(ሲፈጥሩትም ለዚህ ኣላማ ነበር ተብሎ ይታመናል) የነበረዉን አንድነት ፓርቲን በፖለቲካዊ ዉሳኔ የሆነዉ እንዲደርስበት ተደርጓል፡፡አማራጭ እንዲኖር የማይፈልጉት በከፍተኛ የመንግስት ሃላፊነት የተመደቡቱ ጥቂት የህወሓት ቡድኖች የማይጠቅማቸዉን ዉሳኔ እንደወሰኑ ይታወቃል፡፡ ተዉኔቱ በማን ተዘጋጅቶ እነማን እንደተጫወቱትና እነማን ደግሞ ለህዝቡ እንዳደረሱት በተደጋጋሚ ገልጸነዋል፡፡
ፓርቲዉን በተለያዩ ስሞች ሲከሱና ሲፈርጁ ቆይተዉ አመራሩንም በእስርና ድብደባ እያሹ እንዳልተንበረከከና ይበልጥ መጠናከሩን ሲያረጋግጡ ለዚህ ዉሳኔ በቅተዋል፡፡ በ40 ዓመታት ታሪኩ ፓርቲዎችን በመብላትና ከዉስጥና ከዉጭ የሚነሳ ልዩነትን በማቻቻል ሳይሆን በማጥፋት የሚታቀወቀዉ ጥቂት የህወሓት ቡድን አንድነት ፓርቲን ከማጥፋት አሁን ወደ መረጠዉ ደረጃ እንዲወርድ አድርጓል፡፡ታሪክ ሁሉን ይፈርዳል፡፡በጨለማዉ ዘመን ግፍ የተፈፀሞባቸዉ ቡድኖችና የፈሰሰዉ ደምም ተደብቆ ኣልቀረም፡፡ፖለቲካችንን ለማዘመንና ያለፈዉ ግፍ ሁሉ ባይረሳም በይቅር መታለፍ አለበት ብለን ለተነሳን ሃይሎችም እድሉን (በጉልበት በህዝብ ሃብትና በያዙት ስልጣን ተጠቅመዉ) ዘግተዉብናል፡፡ በደም መጨማለቅ በዚህ ያበቃ ዘንድ አሁንም እንታገላለን፡፡የፖለቲካ ትግሉ ሂደትም አይቆምም፡፡ያዉም ይብልጥ የመጠናከር እድል አግኝቷል ተብሎ ይታመናል፡፡የሚያቆመዉ ሃይል የለም፤መጪዉ ግዜ የለዉጥ ነዉ፡፡ለዉጡ እንደይሰረቅና ለሁሉም ይመች ዘንድ የጋራ ትስስርን እንደሚጠይቅ እሙን ነዉ፡፡
ለግዜዉ ከጀርባ ያለዉን ፖለቲካዊ ግፊት ለሌላ ፖለቲካዊ ትግል ትተን የምርጫ ቦርድ ዉሳኔን በመቃወም ክስ መስርተን ወደ ፍርድ ቤት ተብየዉ ወስደንዋል፡፡ ወደ ህግ ለመዉሰድ ስንወስን የፓርቲ ስምና አርማ አስጨንቆን አይደለም፡፡ የደጋፊዎችና አባላት ንብረት ለይምሰልም ቢሆን ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ ፖለቲካዊ ዉሳኔ እንግበዉ በመጡ ከህዝብ ግብር በተሰበሰበ ደሞዝ የሚተዳደሩ የክፍለ ከተማ ፖሊስ ሃይሎች ( ህዝባዊ ሃለፊነትን የተሸከመ ተቋም በፖለቲካ እዝና ዉሳኔ የፓርቲን ንብረት ይዘርፋል የሚል እምነት አልነበረንም) ስለተዘረፈብን ሃላፊነታችንን ለመወጣትና ታሪካዊ እልባት እንዲኖረዉ ለማስቻል ነዉ፡፡እንጂማ ራእያችን በእያነዳንዳችን ዉስጥ ቢሆንም የወቅቱ ትግል ግን የነፃነት መሆኑን አጥተነዉ አይደለም፡፡
በወቅቱ የብሔራዊ ስራ አስፈፃሚዉ የወሰነዉ ዉሰኔ የመድብለ ፓርቲ ስርኣቱ ከምን ግዜዉም በላይ ፈተና ላይ መዉደቁና አዲስ ፓርቲ መመስረት ችኮላና ህዝቡን ስርአቱ ለመድብለ ፓርቲ አሁንም ይመቻል፤ጥፋቱ የኛ ነዉ ብሎ መዋሸት መሆኑ፤እስኪያጠፋቸዉ ድረስ ሌሎች ፓርቲዎች ጋ መቀላቀል በተላይም ከምርጫዉ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ ተስፋ ያላቸዉ አባላት የግል ምርጫቸዉ መሆኑንና አመራሩም ይህን እንደማይቃወም፤የፓርቲዉ አባላት ጉዳዩ በፍ/ቤት እስኪቋጭ ድረስ አመራሩን እንዲጠብቁ ይሀም ለብሔራዊ ምክር ቤቱ ከሰዓት እንዲቀርብና ተወያይቶ ዉሰኔ እንዲሰጥበት የተስማማ ሲሆን በወቅቱ ሁለት አባላት ብቻ አልተገኙም፡፡ከሰኣት ቢሮዉ የፖሊስ ደንብ በለበሱ የመንግስት አካላት ተዘረፈ፡፡ይህ ደግሞ አእላፍ ወንድሞቻችን ላለፉት 40-50 አመታት በተለያየ ጉራ ተሰልፈዉ በተሰዉለት በተላይም በትግረዋይ ደም/ የትግል ዉጢት ሌላዉ ቀልድ እንደመሆኑ ጉዳዩ አብዛሃዉ የአንድነት ደጋፊና አባል በመሆኑ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንወስደዋለን ባልነዉ መሰረትእየታየ ይገኛል፡፡በመሆኑም ጉዳዩን መከታተል የእያነዳንዱ የአንድነት አባልና ደጋፊ የህሊና እዳ ይመስለኛል፡፡በአንድነት ቀብር ላይ አሁንም አንድነታችንን በማረጋገጥ ባብዛሃ ዉሳኔ ቀጣዩን መንድ መጓዝ እንጂ ልንለያይ የሚጋብዝን መንገድ መከተል ያለብን አይምስለኝም፡፡ካለፉት የተቃዉሞ ጎራ በጎዉን ትምህርት መቅሰም የሚኖርብን እንዳለ ይሰማኛል፡፡በችኮላ ፓርቲ ለመመስረት የሚደረግ ሩጫ የስልጣን ሀይልነትን ከማረጋገጥ ባለፈ ለህዝባችን ፋይዳ አለዉ ብየ አልገምትም፡፡ ምርጫቸዉ ላደረጉት ጓዶቼ ግን ስህተት ቢሆን ምርጫቸዉን አከብራለሁ፡፡
ጉዳያችንን ወደ ፍርድ ቤት ስንወስደዉ በፍትህ ተቋማቱ ምናልባትም በሰላማዊ ትግል ስልት ስርኣቱን ለመለወጥ ከሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች መካከል ከቀድሞዉ ቅንጅት ቀጥሎ የግፍ ፍርድ ሲበየንበት የነበረዉ ፓርቲ አንድነት እንደሆነ ስተነዉም አይደለም፡፡ ዱባና ቅል አበቃቀሉ ለየቅል የሚለዉ ብሂል እንዳለ ሆኖ ብርቱኳን መደቅሳ፤ዳኛ ፍረህይወት እና ሌሎች (ለህሊናቸዉ የተገዙ ዳኞች አልፎ አልፎም ቢሆን) የተገኙት በዚህ አፋኝ ስርኣት በዘረጋዉ መዋቅርና በህዝባችን ዘንድ እምነት በታጣባቸዉት የፍትህ ተቀዋማት ውስጥ ነዉ፡፡ታድያ እየተፈተኑ የሚወድቁትን ተቋማት ሳይሆን ግለሰብ ዳኞችንም ለመፈተን ይህን ታሪካዊ ክስ ስናቀርብ የግለሰቦችን የህሊና ዳኝነትንም ተስፋ ባለመቁረጥ ጭምር ይሆናል፡፡ ሁሌም እንደምንለዉ ፓርላማ ተቀምጦ የተከበሩ እየተባሉ ለመጠራት ሳይሆን ትግላችን ለለዉጥ ነዉና ድንክየዉን አንድነት ቢመለሱልንም ባይመሉሱልንም፤ የህዝብ ከሆነዉ ትግል መሃል ሆነን ፖለቲካዉን ከመስራት አንታቀብም፡፡ዉሳኔዉም በሁሉም የለዉጥ ሃይሎች ቀጣይ እንቅስቃሴ የራሱ የሆነ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡የአንድነት ልጆች ህወሓት ለመደዉ የጥባጥቤ ጨዋታዉ ቦታ ይኖረናል ተብሎ አይታሰብም፡፡አንድነታቸንን እንደ ጠበቅን የሚቀብሩት ከሆነ የአንድነት ፓርቲ “ቀብር” ላይ እንገናኝ፤ መቃብሩ ላይም እርም እናዉጣና የአንድነት ሃይሎች ዳብረን እንወጣ ዘንድ ትግሉ ግድ ይለናል!
ላለፉት አምስት አመታት ብዙዎቹ በእስር የሚማቅቁበት የተሰደዱለትና የቆሰሉ፤ የደሙለት ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡የብዙ ወገኖችን እና ተቋማትን የፍትህ ጥያቄ በማዉሳት ባደባባይ የጮኸዉ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡በኢትዮጵያዊነት ማእቀፍ ዉስጥ የብሄረሰቦችን እና የቡድኖችን መሰረታዊ የፖለቲካ ጥያቄ ለመመለስ ቁርጠኝነት የነበረዉ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡ የህዝብን ጥያቄዎች በጠራ መልኩ በማዉሳት ድምጻቸዉን ከሚያሰሙ ፓርቲዎች ዉስጥ ተጠቃሹ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡የቅርርብ፤የመደማመጥና የመከባበር ፖለቲካ እንዲኖር ባሳለፋቸዉ አጭር አመታት ጥረት ያደረገ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡ በዚህም ከህዝብ ብቻ ሳይሆን ለሃገራቸዉ በጎዉን ለዉጥ የሚሹ በርካታ የኢህኣዴግ ተራ አባላትና አንድንድ ባለስልጣናትም ጭምር በበጎ አይን ይመለከቱት እንደነበር ገምግመናል፡፡ በዚህ ወቅት አወንታዊ ተፅእኖ ያመጣል ተብሎ በመፈራቱ ግን ከ40 አመት በኃላም ትቂቱ የህወሓት ቡድን በለመደዉ ስልቱ በልቶታል፡፡
ይህን ድርጊት ለዉጥ ፈላጊ ሃይሎች በጥሞና ይከታተሉታል ተብሎ ይገመታል፡፡የምትችሉ ሁሉ ፍርድ ቤት በመገኘት እስከ ታሪካዊዉ ዉሳኔ እለት ድረስ ሂደቱን ለመዘገብና ለታሪክ ምስክር ለመሆን፤ እንዲሁም አጋርነታችሁን ለመግለፅ ትገኙ ዘንድ የክብር ጥሪ ተላልፏል፡፡እዉነተኛ አንድነት ነባር አመራር፤አባለትና ደጋፊዎች ጉዳዩን በአንድነት እንቋጭኛ እንደስማቸን በአንድነት ቦይ እንፈስ ዘንድ ጥሪ አቀርባለሁ፡፡
አቶ ተክሌ በቀለ (የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት)





