Tag Archives: Ethiopian Protest

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መራዘም እና የሚያስከትለው መዘዝ

ብስራት ወልደሚካኤል

ያለምንም የተፈጥሮ አደጋ ምክንያት የአስችኳይ ጊዜ አዋጅ አውጥቶ ላለፉት 6 ወራት ከቆየ በኋላ ለተጨማሪ 4 ወራት ማራዘሙን ገዥው ስርዓት ይፋ አድርጓል:: ይሄ የሚያሳየው ህወሓት/ኢህአዴግ ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ የማስተዳደር አቅሙ መዳከሙን፥ ህዝባዊ ተቀባይነት ማጣቱን እና ህዝባዊ እምቢተኝነቱ በወታደራዊ እዝ የተዳፈነ ቢመስልም ጭራሽ እንዳልጠፋ ነው የሚነግረን::

Siraje Fergesa

በርግጥ የአዋጁ መራዘም የዜጎችን መብት በማፈን እና በመጨቆን ተጨማሪ የመብት ጥሰትን ዕድል የሚከፍት ነው። ይሁን እንጂ ስርዓቱ አዋጁን ህዝባዊ ተቃውሞዎችን ለማፈን የተጠቀመበት ቢሆንም በሌላ በኩል በራሱ ላይ ተጨማሪ የማያባራ ችግር እየፈጠረ ይገኛል። ምክንያቱም በህዝባዊ የፖለቲካ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መብቶች ጥያቄ ተቃውሞ ምክንያት አስቸኳይ አዋጅ በታሰሩበት ሀገር ምንም ዓይነት የመብት ዋስትና ስለማይኖር ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባ የኢንቨስትመንት፥ የቱሪስት፥የዕርዳታ እና ትብብር እንቅስቃሴዎች በእጅጉ ይቀንሳሉ አሊያም ይቆማሉ::

በዚህም የውጭ ምንዛሪ እና የሀገር ውስጥ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ይገደባል/ይደክማል:: ምክንያቱም በዜጎች የመብት ጥያቄ ምክንያት በአስቸኳይ አዋጅ ወታደራዊ ዕዝ ውስጥ ባለች ሀገር ውስጥ ምንም የደህንነት ዋስትና ስለማይኖር ደፍሮ መዋዕለ ነዋይ የሚያፈስ ባለሃብትና ጎብኚ አይኖርም:: ይህን ተከትሎ ከዚህ በፊት ሀገር ውስጥ የነበሩ የውጭ ባለሃብቶች በስራቸው የነበሩ ሰራተኞቻቸውን በማሰናበት ጓዛቸውን ጠቅልለው እንዲሄዱ በማድረግ የስራ አጡን ቁጥር በእጅጉ እንዲጨምር ያደርጋል::

በተጨማሪም የንግድ እንቅስቃሴ መዳከም እና የአቅርቦት እንዲሁም የሸቀጦችና መሰረታዊ ፍጆታዎች ዋጋ የበለጠ እየናረ እንዲሄድ ያደርገዋል:: ይሄ ደግሞ ለህዝባዊ ተቃውሞ ተጨማሪ ጉልበት ይሰጠዋል:: በመላ ሀገሪቱ ችግሮቹን ለመቆጣጠር የሚያስችል የገንዘብም ሆነ ፈቃደኛ የሚሆን የሰው ኃይል አይኖርም:: ስለዚህ የአስችኳይ ጊዜ አዋጁ መራዘም የዜጎችን መብቶችን ከመጨፍለቅ በተጨማሪ የመብት ጥያቄዎች እንዲበራከቱና ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በማድረግ የስርዓቱን ውድቀት ያፋጥነዋል::

ምናልባት ገዥው ስርዓት የተፈጠረውን የውጭ ምንዛሪ እና የገንዘብ ችግር በጊዜያዊነት ለመቅረፍ ሲባል በሀገሪቱና በዜጎች ላይ ዘመን ተሻጋሪ የሆኑ ሌሎች ጎጂ ርምጃዎችንም ሊወስድ ይችላል:: ከነዚህም አንዱ በሀገሪቱ አሉ የሚባሉና እስካሁን በከፊል በሽርክናም ሆነ በሙሉ በሽያጭ ወደግል ያልተላለፉ የመንግሥት/የህዝብ የንግድ ኩባንያዎች እና ተቋማትን ለሽያጭ ሊያቀርብ ይችላል:: በዚህም የደህንነት ዋስትና በሌለበትና በእቸኳይ አዋጅ ወታድራዊ ዕዝ ስር ባለ ሀገር ነገ ምን ሊፈጠር እንደሚችል ስለምይታወቅ፤ ምናልባት በኢትዮጵያና በቀጠናው ላይ የፖለቲካ የበላይነት ለመያዝ ዙሪያ ጥምጥም ከሚያንዣብቡ የአረብ ባህረ-ሰላጤ ሀገራት በስተቀር የሚደፍር አይኖርም:: ይሄ ደግሞ ለስርዓቱ ተጨማሪ ራስ ምታት ነው::

ስለዚህ ያለው ብቸኛ የመፍትሄ አማራጭ ከተለመደውና ከተሰላቸው የስርዓቱ ኋላ ቀር ብልጣብልጥነት ፖለቲካ አካሄድ በመውጣት፤ የአስችኳይ ጊዜ አዋጁን ማንሳት፥ ከትዕቢትና እብሪት በዘለለ የህዝቡን ጥያቄ በተገቢው መንገድ በቀናነት መስማትና መመለስ፥ በግፍ የታሰሩ የህሊና እና የፖለቲካ እስረኞችን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መፍታት፥ ለህዝብና ለሀገር መብትና ጥቅም ከቆሙ በሀገር ውስጥና በውጭ ካሉ ተፎካካሪ የፖለቲካ ጅርጅቶች/ፓርቲዎች ጋር በገለልተኛ አካላት የሚመራና ገለልተኛ ስፍራ ግልፅ ድርድር ማድረግ ግድ ይላል። እንዲሁም ሐሳብን በነፃት የመግለፅና የፕሬስ ነፃነት ትግበራን ጨምሮ ቢያንስ በሀገሪቱ ሕግ መንግሥት ወረቀት ላይ የሰፈሩ መሰረታዊ የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ተግባራዊ እንዲሆኑ ማድረግ።

ገዥው ስርዓት የህዝቡን ጥያቄ ወደጎን በመግፋት ወደተለመደው አፈና እና ጭቆና ለመመለስ ጊዜ መግዣ ይሆነኛል በሚል በሌለ ገንዘብና አቅም ወጣቱን በማይጨበጥ ማናባዊ የኢኮኖሚ አብዮት ለማታለል ከመሞከር ይልቅ፤ በሰጥቶ መቀበል መርህ ተግባራዊ የሚሆን ስምምነት ላይ በመድረስ የወታደራዊ ዕዙን በመደበኛ/ሲቭል አስተዳደር በመመለስ የአፈና የግድያ ተልዕኮ ፈፃሚ እና አስፈፃሚ የደህንነትና ወታደራዊ አካላት ከህገወጥ ድርጊታቸው ታቅበው ወደ መደበኛ ስፍራዎቻቸውና ስራዎቻቸው እንዲመለሱ ማድረግ የተሻሉ አማራጮች ናቸው:: አለበለዚያ አሁን ባለው መንገድ ነገሮች የሚቀጥሉ ከሆነ ችግሮቹ ተባብሰው በመቀጠል የሀገሪቱን እና የህዝቡን ህልውና እና ደህንነት አደጋ ላይ ከመጣል ባለፈ የስርዓቱን ውድቀት ያፋጥነው እንደሆነ እንጂ መፍትሄ ሊሆን አይችልም::

ዶክተር መረራ ጉዲና እና ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ክስ ተመሰረተባቸው

(አዲስ ሚዲያ) ከ3 ወር በፊት በአውሮፓ ፓርላማ ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ተጋብዘው ንግግር ያደረጉት ዶ/ር መረራ ጉዲና ወደ ሀገር ቤት ሲመለሱ ከአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ተይዘው ለ 3 ወራት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ከታሰሩ በኃላ የካቲት 16 ቀን 2009 ዓ።ም በገዥው መንግሥት ጠቅላይ አቃቤ ህግ አማካኝነት በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት ክስ ተመሰረተባቸው።

merera-gudina-and-berehanu-nega

ዶክተር  መረራ ጉዲና እና ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ

የቀድሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር የነበሩት እና የኦፌኮ ሊቀመንበር እንዲሁም የመድረክ ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት ዶክተር መረራ ክስ የተመሰረተባቸው፥ በአውሮፓ ህብረት በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ንግግር ለማድረግ ተጋብዘው ሲመለሱ የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራር እና ሊቀመንበር ከሆኑት ከፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ጋር ታይተዋል በሚል እንደነበር ይታወቃል።

በዶ/ር መረራ ስም የተከፈተው በዚሁ የክስ መዝገብ ፥ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ሁለተኛ ተከሳሽ ፣ አቶ ጃዋር መሃመድ ሶስተኛ ተከሳሽ በመሆን በልይሉበት ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡ ሶስቱም ተከሳሾች የተከሰሱት በወንጀለኛ መቅጫ ህጉን የተለያዩ አንቀጾች በመተላለፍ ሲሆን አራተኛ እና አምስተኛ ተከሳሽ የሆኑት የኢትዮጵያ ሳተላይ ቴሌቪዥን ( ኢሳት) እና ኦሮሞ ሚዲያ ኔትወርክ ( ኢኤም ኤን) ሲሆኑ፥ ተቋማቱ የፀረ ሽብር ህጉን በመተላለፍ ተከሰዋል፡፡

ዶ/ር መረራ ሌላ ተጨማሪ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን መተላፍ በሚል ክስ ተመስቶባቸዋል፡፡ የክሱ ጭብጥም ተከሳሾች በዋና አድራጊነት ሽብር ተግባር መፈጸማቸውን እና ለኦሮሚያ እና አማራ ክልል አመጾች ማነሳሳት እና ንብረት መውደም ተጠያቂ መሆናቸው በክሱ ላይ ተጠቅሷል።

የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤትም ክሱን ለማየት ለየካቲት 24 ቀን 2009 ዓ ም ቀነ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

በተለይ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ከዚህ በፊት በሌሉበት በነ ጄነራል ተፈራ ማሞ የክስ መዝገብ የሞት ፍርድ የተፈረደባቸው ሲሆን፥ በነ አቶ አንዱዓለም አራጌ የክስ መዝገብ ደግሞ የዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት የተፈረደባቸው ሲሆን፥ የአሁኑ ከነ ዶ/ር መረራ ጉዲና ጋር የተመሰረተባቸው ክስ ለሶስተኛ ጊዜ መሆኑ ታውቋል።

መንግሥት ከህዳር 2008 ዓ ም ጀምሮ በተለይ በኦሮሚያ ፥ በአማራ ክልል እና በደቡብ ክልል ኮንሶ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀ ህዝባዊ አመፅን ተከትሎ በርካታ ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት ወታደራዊ ኃይል ሲገደሉ፥ በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ሲታሰሩ ከ15 ሺህ ያላነሱ በተለያየ ጊዜ ከእስር መልቀቁን መንግሥስት ቢያስታውቅም አሁንም ድረስ ህዝባዊ አመፁን ተከትሎ የታሰሩና ሰብዓዊ መብቶቻቸው እየተጣሰ ያሉ ዜጎች መንግሥስት ከእስር ልቅቄያቸዋለሁ ክሚለው ቁጥር እንደሚልቅ ይግመታል።

ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፊት መንግሥት በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ አማካኝነት ለህዝባዊ አምፁ ተጠያቂ ራሱ መንግሥት እና አመራሮች እንደሆኑ ቢይሳውቁም፥ ለግድያ፥ እስርና እንግልት የተዳረጉት ግን ሰላማዊ ዜጎች መሆናቸውን የሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች መግለፃቸው ይታወሳል።

በዮናታን ተስፋዬ ላይ መከላከያ ምስክሮች መሰማት ጀመሩ

ቀደም ባሉ ቀናት በዋለው ችሎት በጊዜ እጥረት ምክንያት መከላከያ ምስክሮችን ለመስማት ባለመቻሉ ታህሳስ 26 ቀን 209 ዓ. ም. ተቀጥሮ ነበር። ዮናታን ተስፋዬ እንዲከላከሉለት ከዘረዘራቸው የሰው ምስክሮች ከአንዱ (ዶ/ር መረራ ጉዲና) በስተቀር የተቀሩት መከላከያ ምስክሮች መቅረባቸውን የዮናታን ጠበቃ የሆኑት አቶ ሽብሩ በለጠ ለችሎት አሳውቀዋል፡፡ መከላከያ ምስክሮች መሰማት ከመጀመራቸው በፊት አቶ ዮናታን የራሱን የምስክርነት ቃል አቅርቧል፡፡

yonatan-tesfaye

ዮናታን ተስፋዬ

“በፌስቡክ አካውንቴ እፅፍ የነበረው ሃሳቤን ለመካፈል ፈቃደኛ ለሆኑት ጓደኞቼ ብቻ ነው፡፡ ህዝብ ቀስቅሷል የሚባለው ነገር የማይመስል ነገር ነው፡፡ እድሉን አግኘቼ እንኳን ለህዝብ ደርሶ ቢሆን የሽብርን ድርጊት የሚያበረታታ አይደለም የፃፍኩት ነገር፡፡ በሃገሪቷ ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ የሚገልፁ እና የሚዳስሱ ናቸው፡፡ እንዚህን ሃሳቦች ከጓደኞቼ ጋር መወያየቴ ሃሳቤን በነፃነት የመግለፅ መብቴን መጠቀሜ ነው፡፡ “ህግ መጨቆኛ መሳሪያ ሲሆን፡ አመፅ የህሊና ህግ ይሆናል፡፡” የሚለው ሃሳብ የተፈጥሮ እና አለም ዓቀፋዊ ህግ ነው፡፡ ማንም ሊቀይረው አይችልም፡፡ የፍልስፍና መርህም ነው፡፡ ምናልባትም ያን የተናገርኩ ጊዜ የሚሰማ አካል ቢኖር ኖሮ ይሄ ሁላ ችግር ባልደረሰም ነበር፡፡ በህዳር 2008 ዓ.ም. አካባቢ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን የሚገኘው ጭልሞ ጫካ ለባለሃብት ከተሸጠ በኋላ ህብረተሰቡ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ አድርገዋል፡፡ ምናልባትም ጥያቄያቸው በትክክለኛው አግባብ ቢያዝ ተቃውሞው አይስፋፋም ነበር፡፡ እኔም የሚደርሰው ጉዳት እንዲቀንስ የበኩሌን አስተዋፅኦ ማድረግ ነበረብኝ፡፡ መንግስት የህብረተሰቡን ደህንነት መጠበቅ ሲኖርበት በተቃራኒው የመንግስት አካል ህብረተሰቡ ላይ ጉዳት ሲያደርስ በተለያየ መንገድ ህዝቡ ራሱን እንዲከላከል የተለያየ ሃሳብ አቅርቤአለሁ፡፡ የአንድ ሰው ህይወት ዋጋ አለው፡፡ እኔ ከመታሰሬ ቀደም ብሎ 62 የዩቨርስቲ ተማሪዎች ተገድለው ነበር፡፡ እነዚህ ተማሪዎች ነገ ይህችን ዓለም ሊቀይሩ ይችሉ የነበሩ ናቸው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያምን ጨምሮ የተለያዩ የመንግስት አካላት ችግሩ የተከሰተው በመልካም አስተዳደር እጦት መሆኑን አምነው ይቅርታም የጠየቁበት ጉዳይ ነው። አንድ ሚሊዮን ብር ከሚያወጣ ንብረት ይልቅ የአንድ ሰው ህይወት ዋጋ አለው፡፡ ለምሳሌ አንድ ሹፌር 20 ተሳፋሪ ይዞ ፍሬን እምቢ ቢለው መኪናውን አጠገቡ የሚገኝ ግንድ ወይም ግንብ አጋጭቶ ቢያቆመው፡ ሹፌሩ መኪናው ላይ በደረሰው አደጋ ሊቀጣ አይገባውም፡፡ በአደባባይ ሰዎች ሲሞቱና ሲገደሉ እነርሱን ዲፌንድ ማድረግ ነበረብኝ፡፡ ይህንንም ሃሳቤን የመግለፅ መብቴን ተጠቅሜ የተለያየ ሃሳብ አቅርቤያለሁ፡፡ ይሄ ጥፋት የሚባል ከሆነ እቀበለዋለሁ፤ ለኔ ክብሬ ነው፡፡ ፍርዱን ከታሪክ እና ከእግዚአብሄር አገኘዋለሁ፡፡” ይህን የምስክርነት ቃሉን ዮናታን ካቀረበ በኋላ የሙያ ምስክርነታቸውን የሚሰጡትን ሶስት ምስክሮች ጠበቃው ዘርዝረዋል፡፡

የህግ ባለሙያ የሆኑት ዶ/ር ያእቆብ ኃይለማርያም እና የፍልስፍና መምህሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ የሙያ ምስክርነታቸውን የሚሰጡ ሲሆን ዮናታን የፃፈው ፅሁፍ ሃሳብን ከመግለፅ ነፃነት አንፃር እና ኢትዮጵያ ከፈረመቻቸው ህጎች አንፃር ገደቡን ያለፈ አለመሆኑን እንደሚያስረዱ፤ እንዲሁም ሶስተኛው የሙያ ምስክር ጦማሪ እና የመብት አራማጅ በፍቃዱ ሃይሉ ደግሞ በፌስቡክ በግለሰብ አካውንት የሚለጠፉ ፖስቶች ከመደበኛ ሚዲያ እና ከዜና ድህረገፆች የሚለይበትን እንደሚያስረዳ ጠበቃው አቶ ሽብሩ በጭብጥነት አስመዝግበዋል፡፡ አቃቤ ህግ በሶስቱም የሙያ ምስክሮች ላይ ተቃውሞ እንዳለው ከተናገረ በኋላ ህግን መተርጎም ያለበት ፍርድ ቤት እንደሆነ ከዚህም ካለፈ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ማየት እንዳለበት ጠቅሶ ምስክሮች የፍርድ ቤቱን ሚና መውሰድ ስለሌለባቸው የመጀመሪያዎቹ ሁለት ምስክሮች [ዶ/ር ያእቆብ እና ዶ/ር ዳኛቸው] መሰማት የለባቸውም በማለት እንዳይሰሙ ሲል ጠይቋል፡፡ በፍቃዱ የሚመሰክርበትን ጭብጥም በተመለከተ ከክሱ ጋር የማይገናኝ ስለሆነ መመስከር የለበትም ብሎ ለችሎቱ ተቃውሞውን አሰምቷል፡፡

ጠበቃ አቶ ሽብሩም “አቃቤ ህግ ዮናታንን ወንጀል ሰርቷል ብሎ ምስክር ሲያሰማ የዳኞችን ሚና ወሰደ አልተባለም፡፡ የደንበኛዬ የመከላከል መብት በሰበብ አስባብ ሊጣስ አይገባም፡፡” ብለው ከተናገሩ በኋላ ዶ/ር ያዕቆብ እና ዶ/ር ዳኛቸው ከልምዳቸው እና ከትምህርት ዝግጅታቸው አንፃር የዮናታን ፅሁፍ ከገደብ አለማለፉን በተረዱት መጠን እንደሚያስረዱ፤ በፍቃዱ የሚመሰክረውም ዮናታን የተከሰሰበት የሽብርተኝነት ህግ አንቀፅ 6 በህትመት ደረጃ ስለሚፃፉ ሽብርተኝነትን የሚያበረታቱ ፅሁፎች ስለሚል ልዩነቱን እንዲያስረዳ ነው በማለት ምስክሮቹ የሚመሰክሩበትን ጭብጥ አግባብነት አስረድተዋል፡፡ ዳኞችም የግራ ቀኙን ሃሳብ ከሰሙ በኋላ ምስክሮች ከተሰሙ በኋላ ቃሉ ተመዝኖ መጨረሻ ላይ የሚታወቅ በመሆኑ ምስክሮች እንዲሰሙ ወስነዋል፡፡

በመጀመሪያ ለመመስከር የቀረቡት ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማርያም ናቸው፡፡ የህግ ምሩቅ መሆናቸውን፣ የህግ አማካሪ እና በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ መምህር መሆናቸውን ገልጸው በሩዋንዳ የዘር ማጥፋት ወንጀል አጣሪ ቡድን አባል ሆነው እንደሰሩ እና በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የህግ አማካሪ ሆነው እንደሰሩ ገልፀዋል፡፡ ስለሽብር ወንጀል ምንነት እና ከዮናታን ፅሁፍ ጋር አያይዘው እንዲመልሱ ተጠይቀው፤ “የሽብር ወንጀል አስከፊ ነው፤ ከጦር ወንጀል እና ከዘር ማጥፋት ጋር የሚሰለፍ ነው፡፡ የሽብር ወንጀል ዓለም አቀፍ ወንጀል ነው፡፡ አንድን ሽብር ፈጣሪ የትኛውም ሃገር ቢሄድ የሚጠየቅ ነው የሚሆነው፡፡ በኬኒያ እና ሌሎች የአለማችን ክፍሎች በርካታ ህዝቦች ያለቁበትን ሁኔታዎች በአለም አቀፍ ሁኔታም የሽብር ድርጊት የሚባሉ ናቸው፡፡” ካሉ በኋላ የዮናታንን በፌስቡ ከጓደኞቹ ጋር ለመወያየት የፃፋቸው ሃሳቦች ከጠቀሷቸው አለም አቀፍ የሽብር ድርጊቶች ጋር አንድ ማድረግ የሽብርተኝነት ድርጊትን ማቃለል እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም የፀረ ሽብር ህጉ ህገመንግስቱን እና ኢትዮጵያ በአለም አቀፍ ደረጃ የተቀበለቻቸውን ህጎች እንደሚጥስም ተናግረዋል፡፡

ቀጥሎ ለመመስከር የቀረቡት ዶ/ር ዳኛቸው ናቸው፡፡ የህግ ፍልስፍና ትምህርት የተማሩ መሆናቸውን እና መምህር መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ እአአ ከ 1948 ዓ. ም. ጀምሮ የተካሄዱ አራት አለም አቀፋዊ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎችን በመጥቀስ እነዚህ ድንጋጌዎች ማእከል ያደረጉት የመናገር መብትን መሆኑን እንዲሁም ንግግር በይዘቱ እንደማይፈተሽ እና ማንም ዜጋ ሃሳብ የማዋቀር መብት እንዳለው ድንጋጌዎቹ በግልፅ ያሰፈሩት ጉዳይ መሆኑን ጠቅሰዋል -ዶ/ር ዳኛቸው፡፡ እነዚህን ህጎች ኢትዮጵያ ከመቀበል ባለፈ ከመጀመሪያው ጀምሮ በማርቀቁ ሂደት ተሳታፊም እንደነበረች ገልፀዋል። ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት መኖር ለመንግስት ቅቡልነትን እንደሚያመጣ ዲሞክራሲም የሚለካው በዚህ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ “ፅሁፉን አይቼዋለሁ፡፡ እምነቱን አሳይቷል፡፡ የራስክን አይዲዎሎጂ ፃፍክ ነው የሚለው ክሱ፡፡ እኔ እዚህ ሃገር ከመጣሁ ስምንት አመት ሆኖኛል፡፡ ስምንት አመት ሙሉ የራሴን አይዲዮሎጂ መንግስትን እየተቃወምኩ ስፅፍ ነበር፡፡ አልታሰርኩም፡፡ እሱም መታሰር አልነበረበትም፡፡ ልጁ [ዮናታን] የፃፈው ስህተት ሊሆን ይችላል፡፡ እኔ አስተማሪው ብሆን ፅሁፎቹን አይቼ ሲ እና ዲ ልሰጠው እችላለው፡፡ ያ ማለት ግን ወንጀል ሰርቷል ማለት አይደለም፡፡ መንግስት ጥሩ ነው የማለት መብት እንዳለ ሁሉ መንግስት ጥሩ አይደለም የማለት መብትም መኖር አለበት፡፡ ንግግር እና ፅሁፍን በመፍቀድ ከሚመጣው ችግር ንግግር እና ፅሁፍን በመገደብ የሚመጣው ችግር ይበልጣል፡፡” ካሉ በኋላ አቃቤ ህግ ፍርድ ቤት የመመስከር ፍቃድ አሎት ወይ ብሎ ሲጠይቃቸው፡ የትምህርት ዝግጅታቸውን፣ የስራ ልምዳቸውን እና ከዚህ ቀደምም በፍርድ ቤት መስክረው እንደሚያውቁ ገልፀው፤ ፍርድ ቤት ለመመስከር ፍቃድ የት እንደሚሰጥ አላውቅም፤ የሚሰጥ አካል አለ? የት ነው የማገኘው? በማለት በችሎት የነበረውን ሁሉ ፈገግ አሰኝተዋል፡፡

በሶስተኛ ደረጃ የሙያ ምስክርነቱን የሰጠው ጦማሪ እና አክቲቪስት በፍቃዱ ኃይሉ ነው፡፡ አቶ በፍቃዱ በማኔጅመንት ኢንፎርሜሽን ሲስተም የመጀመሪያ ዲግሪ እንዳለው፤ በመደበኛ (ህትመት እና ራዲዮ)፣ በማህበራዊ ሚዲያ እና የዜና ድህረገፆች ያለውን ልምድ ተናግሯል፡፡ማህበራዊ ሚዲያን ለመጠቀም እያንዳንዱ ሰው አካውንት ሊኖረው እንደሚገባ፤ የሚፅፉትንም ለማየት ጓደኞች ሊኖሩ እንደሚገቡ፤ መደበኛ ሚዲያ በዋነኝነት ለሽያጭ የሚቀርብ እና ከማህበራዊ ሚዲያ የበለጠ ተደራሾች እንደሚኖሩት፤ የዜና ድረገፅን ለመጠቀም ኢንርኔት አጠቃቀም ከማወቅ በዘለለ የግል አካውንት መፍጠር እንደማያስፈልግ ተናግሯል፡፡ ስለ ግለሰብ ፌስቡክ አካውንት፣ የፌስቡክ ፔጅ እና ፋን ፔጅ ልዩነቶች አስረድቷል፡፡ ዮናታን ስለፃፈው ፅሁፍ ተጠይቆ፤ ፅሁፎቹን እንደሚያውቃቸው፤ የፖለቲካ ፓርቲ አመራር እንደመሆኑ በኢትዮጵያ ወቅታዊ ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ መወያየት እና መፃፍ እንደሚወድ ተናግሯል፡፡ በወቅቱ በነበረው ተቃውሞ በመንግስት የተገደሉ ወጣቶችን በመቃወም ሲፅፍ እንደነበር፤ እንዲያውም የወጣቶችን ደህንነት አደጋ ላይ ለመጣል እና ለማሸበር ሳይሆን በተቃራኒው የወጣቶችን ደህንነት ለማስጠበቅ ሲታገል እንደነበረ ተናግሯል አቶ በፍቃዱ፡፡

መንግስት ወጣቶችን ይገድላል ወይ ተብሎ ለአቶ በፍቃዱ ከዳኞች ለቀረበለት ጥያቄ፤ የመንግስት ፀጥታ አካላት ወጣቶችን መግደላቸው ዩንቨርሳል ትሩዝ እንደሆነ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ባወጣው ሪፓርት እንኳን 173 ሰዎች በፀጥታ አካላት መገደላቸው የተገለፀ መሆኑን ገልፇል። ይህን የሙያ ምስክርነት ለመስጠት ፈቃድ እንዳለው አቃቤ ህግ ጠይቆት፤ በአዲስ አበባ መስተዳደር በሚተላለፍ የራዲዮ ፕሮግራም ፕሮዳክሽን ማኔጀር ሆኖ እንሰራ፤ የውይይት የመፅሄት ዋና አዘጋጅ ሆኖ እንደሰራ፤ የሚፅፋቸው ፅሁፎች በአዘጋጅነት ይሰራበት የነበረውን የውይይት ጋዜጣን ጨምሮ የተለያዩ የህትመት ሚዲያዎች ላይ ይታተሙ እንደነበረ፣ ዞን ዘጠኝ የተባለ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ የሚጦምር ቡድን አባል እንደሆነ እና በቅርቡም አዲስ ስታንዳርድ የሚባል የመፅሄት ድረገፅ ላይ ፅሁፍ እንደታተመለት በመግለፅ ልምዱን በአጭሩ አብራርቷል፡፡ ይህም ልምዱ በጉዳዩ ላይ ለመመስከር ብቁ እንደሚያደርገው ተናግሮ፤ “ምስክርነት ለመስጠት ፈቃድ የሚሰጥ አካል የለም” ብሏል።

በመቀጠል የምስክርነት ቃላቸውን የሚሰጡት የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ አመራር የሆኑት አቶ ሙላቱ ገመቹ እና አቶ በቀለ ገርባ መሆናቸውን የተከሳሽ ጠበቃ አቶ ሽብሩ ተናግረው፤ በህዳር 2008 ዓ. ም. በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ አካባቢዎች የጀመረበትን ምክንያት እና የነበረውን ሁኔታ እንደሚያስረዱለት በጭብጥነት አሲዟል።

አቃቤህግ አሁንም በምስክሮቹ ላይ ተቃውሞ እንዳለው ለፍርድ ቤት አሳውቋል። ምስክሮቹ በህግ ጉዳይ ላይ መመስከር እንደማይችሉ እና ተገቢነት የሌለው መሆኑን በመናገር ምስክሮቹ እንዳይመሰክሩ ጠይቋል። የተከሳሽ ጠበቃ በበኩላቸው ይህን ጉዳይ በተመለከተ የምስክር መስማት ሂደቱ ሲጀምር ተመሳሳይ ጥያቄ አቃቤ ህግ አንስቶ ውሳኔ ተሰጥቶት ያለፈ ጉዳይ መሆኑን በተጨማሪም ምስክሮቹ የፓለቲካ ፓርቲ አመራር እንደመሆናቸው መጠን የሞያውቁትን የሰሙትን እና ያዩትን የሚመሰክሩ መሆናቸውን ገልፀው ምስክሮቹ የሚመሰክሩበትን ጭብጥ አግባብነት አስረድቷል። ዳኞች የግራቀኙን ክርክር አድምጠው የምስክሮቹን የሚመሰክሩበት ጭብጥ ይዘት በኋላ ላይ የሚመዘን በመሆኑ፤ ተከሳሽ እራሱን የመከላከል መብቱን ከመጠበቅ አንፃር ምስክሮቹ ቢሰሙ እንደሚሻል ጠቁመው የምስክሮቹ የመሰማት ሂደት እንዲቀጥል አዘዋል።

በቅድሚያ ለመመስከር የቀረቡት አቶ ሙላቱ ገመቹ ናቸው። አቶ ሙላቱ በ2008 ዓ. ም. ስለተነሳው ኦሮሚያ ስለተነሳው ተቃውሞ መንስኤ ስለሆነው ነገር ሲናገሩ፤ ከ2007 ዓ. ም. ምርጫ በኋላ ተቃውሞ እየበረከተ መምጣቱ፣ በኦፌኮ በኩል ሰላማዊ በሆነ መንገድ የተነሱትን ጥያቄዎች ለመመለስ ጥረት ሲደረግ እንደነበረ፣ ህዳር ወር ላይ 2008 ዓ. ም. በጊንጪ ከተማ የከተማው አስተዳደር 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የነበረውን ለመኖሪያ ቤት መስሪያ ወሰዱ መባሉን ተከትሎ ተማሪዎች ተቃውሞ እንደጀመሩ፤ ተማሪዎቹም ትምህርት ቤቱን ማስመለስ መቻላቸውን፤ የከተማው ስታዲየምም በተመሳሳይ መልኩ ተወስዶ ሲከፋፈሉት ተቃውሞ ተነስቶ እንደነበረ፤ የጭልሞ ጫካ ለባለሃብቶች መሸጥ ህዝብ ላይ ቅሬታ እንደፈጠረ እና ተቃውሞ እንደተነሳ፤ በዚህም ሳቢያ ከጊንጪ አካባቢ ብቻ 70 የኦፌኮ አባላት እንደታሰሩባቸው ገልፀዋል። ይሄ በእንዲህ እንዳለም የተቀናጀ ማስተር ፕላን የተባለው ፕላን ይተግበር መባሉ ብዙ ተቃውሞ ማስነሳቱን ገልፀዋል አቶ ሙላቱ።

ዳኞች ቀጣዩ ምስክር [አቶ በቀለ ገርባ] ጭብጡ ተመሳሳይ ስለሆነ አዲስ ነገር የሚመሰክሩት ከሌላ ባይሰሙ የሚል አስተያየት አቅርበው ነበር፤ ሆኖም ጠበቃ ሽብሩ ቀድመው ከመሰከሩት ምስክር [አቶ ሙላቱ ገመቹ] የተለየ ሚመሰክሩት እንዳለ በመናገራቸው ዳኞችም ባልተመሰከረበት የጭብጥ ሃሳብ ላይ ብቻ እንዲመሰክሩ አዘዋል።

በኦሮሚያ የተነሳው ተቃውሞ ማስተር ፕላኑን ተቃውመው እና ጭልሞ ጫካ ለግለሰቦች በመሰጠቱ ምክንያት እንጂ ዮናታን በፃፈው ፅሁፍ እንዳልሆነ አቶ በቀለ ገልፀዋል። በተጨማሪም ፅሁፎቹ ህዝቡ ያነሳው ተቃውሞ በሰላማዊ መንገድ እንዲመለስ ለማድረግ እንደሆነ ተናግረዋል።

የመከላከያ የምስክርነት ቃላቸውን ለመስጠት ቀርበው የነበሩት አባቱ ቀሲስ ተስፋዬ ረጋሳ፣ ጓደኛው አቶ ኤፍሬም፣ እህቱ ገዳምነሽ እንዲሁም ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በእለቱ ችሎት ለመስማት ጊዜ ስላለቀ በቀጣይ ቀጠሮ እንዲቀርቡ ተነግሯቸዋል። በዛሬው ቀን ያልቀረቡት ምስክር ዶ/ር መረራ ጉዲና ያሉበትን ቦታ ጠበቃ ሽብሩ ከገለፁ በኋላ ዳኞች መጥሪያ እንዲደርሳቸው እና ፓሊስ በቀጣይ ቀጠሮ ቀን እንዲያቀርባቸው ትእዛዝ ሰጥተዋል።

ቀሪ መከላከያ ምስክሮችን ለመስማት ለጥር 18 ቀን 2009 ዓ. ም. ቀጠሮ ተይዟል።
ምንጭ፦ EHRP

እውቁ ፖለቲከኛ እና የኦፌኮ/መድረክ ከፍተኛ አመራር ዶ/ር መረራ ጉዲና ታሰሩ

(አዲስ ሚዲያ)የኦሮሞ ፌደራሊስት ሊቀመንበር እና የኢትዮጵ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንደነግ ግንባር (መድረክ) ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና ታሰሩ፡፡ ዶ/ር መረራ የታሰሩት በቤልጂየም ብራሰልስ የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ በተጋበዙት መሰረት ንግግር አድርገው ረቡዕ ህዳር 21 ቀን 2009 ዓ.ም. ወደ ሀገር ቤት ሲመለሱ አዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ሲደርሱ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መታሰራቸው ታውቋል፡፡ ዶ/ር መረራ የታሰሩት አብረዋቸው ከነበሩ ከሁለት የቅርብ ቤተሰቦቻቸው ጋር እንደነበርም ታውቋል፡፡

dr-merera-gudina-aau

ገዥው የህወሓት/ኢህአዴግ መንግሥት በበኩሉ ዶክተር መረራ የታሰሩት “በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መመሪያ ቁጥር አንድ አንቀጽ 2 ላይ የተመለከተውን መመሪያ ተላልፈው በመገኘታቸው እና ከአርበኞች ግንቦት 7 መሪ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ጋር ተገናኝተው መግለጫ ሰጥተዋል“ በሚል መሆኑን በልሳኑ ፋና ብሮድካሲቲንግ ኮርፖሬት ዘገባ ይፋ አድርጓል፡፡

መንግሥት ባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. የተቀሰቀሰውን የኦሮሚያ ክልል የፀረ አገዛዝ ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ፤ በተመሳሳይ መልኩ ሐምሌ 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በአማራ ክልል እና በደቡብብ ክልል ኮንሶ የተዛመተውን ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ተከትሎ ከ1400 በላይ ዜጎች ሲገደሉ ከአንድ ሺህ ያላነሱ በፀጥታ ኃይሎች ወታደራዊ ርምጃ የቆሰሉ ሲሆን፤ ከ50 ሺህ ያላነሱ ዜጎች በእስር ላይ እንደሚገኙ የፖሊስ መረጃዎችና የሰብዓዊ መብት አራማጆች መረጃ አመልክቷል፡፡የህወሓት/ኢህአዴግ ደጋፊዎችም ዶ/ር መረራ በአውሮፓ ፓርላማ ንግግር ማድረጋቸውን ተከትሎ እንደሚታሰሩ የሚያመለክት ቅስቀሳ ሲያደሩ እንደነበረም መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

በተለይ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀውን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞውን ተከትሎ ገዥው መንግሥት መስከረም 28 ቀን 2009 ኣ.ም ጀምሮ ለ6 ወራት ተግባረዊ የሚደረግ የአስቸኳይ ዚጌ አዋጅ አውጥቷል፡፡ አዋጁ ተግባራዊ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ ጋዜጠኞች፣ የተለያዩ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት፣ የመብት አራማጆችንና ሲቭል ማኀበረሰቡን ጨምሮ በአንድ ወር ብቻ ከ11,706 ማሰሩን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡

ዶ/ር መረራ ጉዲና በቅርቡ በጡረታ እንዲሰናበቱ ከመደረጋቸው በፊት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህርነት ለ28 ዓመታት ያገለገሉና የፓርላማ አባል የነበሩ ሲሆን፤ ላለፉት 20 ዓመታትም በሀገሪቱ ፖለቲካ ባላቸው ተሳትፎ በበርካታ ኢትዮጵያውያን ዘንድ የሚታወቁና ከፍተኛ ተቀባይነት እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ ቀደም ሲል የፓርቲያቸው ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ፣ ዋና ፀሐፊያቸው አቶ ደጀኔ ጣፋ፣ የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ አቶ ደስታ ዲንቃን ጨምሮ በርካታ አመራሮችና አባሎቻቸው ከአንድ ዓመት በፊት መታሰራቸው ይታወቃል፡፡

በአማራ ክልል በአገዛዙ ወታደሮችና በነፃነት አርበኞች መካከል ውጊያ እየተካሄደ ሲሆን፤ ከሁለቱም ወገን ጉዳት መድረሱ ተገለፀ

(አዲስ ሚዲያ)በአማራ ክልል በተለይም በሰሜንና ደቡብ ጎንደር ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች የገዥው ስርዓት በደል እና ጭቆናን የተቃወሙ የአማራ ተጋድሎ አርበኞች እና የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ ድርጅት የነፃነት ኃይሎች ከመንግሥት ወታደሮች ውጊያ ማካሄዳቸው ተገለጠ፡፡ በተለይ ካለፈው ሐሙስ ህዳር 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ በዋናነት በሰሜን ጎንደር ምዕራብ እና ላይ አራማጭሆ፣ ሳንጃ፣ ደንብያ፣ ጃን አሞራ፣ ዳባት፣ ደባርቅ እና ወገራ ወረዳዎች፤ እንዲሁም በወልቃይት አካባቢ ቃፍታ ሑመራ እና ጠገዴ ተከታታይ ውጊያ መደረጉን እና አሁንም በተጠቀሱ አካባቢዎች ውጊያዎቹ የቀጠሉ መሆናቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

kefagn-amhara-resistance

የአማራ ተጋድሎ መብት አራማጆችም በተለያዩ የሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች የተጋድሎው አርበኞች ከአገዛዙ ወታደራዊ ኃይሎች ጋር ውጊያ መግጠማቸውን እና ከ70 ያላነሱ የአገዛዙ መንግሥት ወታደሮች ሲገደሉ ከአማራ ተጋድሎ በኩል 2 ያህል አርበኞች መገደላቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ አገዛዙን ስርዓት ለመጣል በይፋ ሁለገብ ትግል እያደረገ የሚገኘውና በፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የሚመራው የአርበኞች ግንቦት 7 ለፍትህና ለነፃነት ንቅናቄ በተለያዩ የሰሜን ጎንደር ዞን ወረዳዎች አውደ ውጊያዎች በአገዛዙ ወታደራዊ ኃይሎች ላይም ተደጋጋሚ ጥቃት በመክፈት ድል መቀዳጀቱን በመግለፅ ከንቅናቄው ወገን በወቅቱ አዛዥ የነበሩት ሻለቃ መሳፍንት ጥጋቡን (ገብርዬ) ጨምሮ የተወሰኑ ታጋዮቹ እንደተሰዉ ይፋ አድርጓል፡፡ በነበረው ውጊያም ንቅናቄው በርካታ የአገዛዙ ወታደሮችን መግደሉን፣ ማቁሰሉን እና መማረኩንም ይፋ አድርጓል፡፡

ገዥው መንግሥት በበኩሉ በሰሜን ጎንደር ዞን እና በምዕራብ ትግራይ ዞን የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ ኃይሎች ጋ ውጊያ መኖሩን እና በወቅቱ የንቅናቄው መሪ የነበሩት ሻለቃ መሳፍንት ጥጋቡን ገድሎ 70 ያህል የንቅናቄው ወታደሮችን መማረኩን በስሩ በሚቆጣጠረው የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ይፋ አድርጓል፡፡ ይሁን እንጂ ከአገዛዙ በኩል ስለደረሰ ጉዳት የጠቀሰው ነገር የለም፡፡ እንደ አካባቢው የዓይን እማኞች በበኩላቸው አገዛዙ ተጨማሪ በርካታ ወታደሮችን ከነ ሙሉ ትጥቃቸው ወደ ስፍራው ማንቀሳቀሱን እንደተመለከቱ ይናገራሉ፡፡ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በርካታ የአገዛዙ ወታደራዊ ተሸከርካሪዎች ጎንደር ከተማን ጨምሮ በተለያዩ የክልሉ የዞን እና የወረዳ ከተሞች እንደሚታዩ ተጠቁሟል፡፡

tplf-soldiers-logistic

አገዛዙ ተግባራዊ ያደረገውን የ6 ወር አስቸኳይ አዋጅ ተከትሎ ከአማራ ክልል ብቻ ከ 19 ሺህ ያላነሱ ሰላማዊ ዜጎችን በተለያዩ የክልሉና የፌደራል እስር ቤቶች በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስቱ መታሰራቸውን የአማራ ተጋድሎ የመብት አራማጆች እና የአካባቢው የፖሊስ መረጃ ምንጮች የጠቆሙ ሲሆን፤ የተጠቀሰው አሀዝ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፊት በነበሩ ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ ወቅት የታሰሩትን ቁጥር ሳይጨምር እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ የአገዛዙ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የአንድ ወር የወሰደውን ርምጃን ይፋ ባደረገበት ወቅት በአጠቃላይ 11,706 ያህል ዜጎች መታሰራቸውን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡

እንደ መረጃ ምንጮች ጥቆማ ከሆነ፤ በአማራ ክልል ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. የወልቃይት ጠገዴ ሁመራ የአማራ ማንነት የመብት ጥያቄ መነሻ አድርጎ በነበረው ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ ተቃውሞ ተከትሎ በአገዛዙ በርካታ ሰላማዊ ዜጎች መገደላቸው፣ መታሰራቸውና ለከፋ ስቃይ መዳረጋቸው ያስቆጣቸው የአማራ ማኀበረሰብ አባላት መካከል በርካታ ሰዎች ራሳቸውን ” ከፋኝ” በሚል በየአካባቢው የጎበዝ አለቃ በሚመራ የአማራ ተጋድሎ ራሳቸውን አደራጅተው በአገዛዙ ላይ የአፀፋ እርምጃ መውሰድ እንደጀመሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡