አንድነት ፓርቲ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለህሊና እስረኞች” የሚል ዘመቻ ማዘጋጀቱን ይፋ አደረገ
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ (አንድነት) ፓርቲ ከህዳር 14 እስከ 20 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚቆይ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለህሊና እስረኞች” የሚል የሶሻል ሚዲያ ዘመቻ አዘጋጅቷል። በዚህ ዘመቻ ለመንግስት ባለስልጣናት፣ ለታዋቂ ግለሰቦች፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተቋማትና ለልዩ ልዩ የሚዲያ ድርጅቶች በኢንተርኔትና በሶሻል ሚዲያ በኩል መልዕክት በመላክ በሀገራችን ያሉት የፖለቲካ እስረኞች ሁኔታና አያያዝ በተመለከተ መረጃ በመስጠት ተገቢ የሆነ አያያዝ እንዲኖራቸው፤ ከእስር እንዲፈቱ፣ በሰላማዊ መንገድ የሚታገሉትን ማሰርና ማዋከብ እንዲቆም በመንግስት ላይ አዎንታዊ ተፅዕኖ ለመፍጠር ያለመ እንደሆነ ፓርቲው አስታውቋል። በዚህ ዘመቻ ላይ ሁሉም የዘመቻው ደጋፊና በሀገሪቱ ዴሞክራሲያው ስርዓት እንዲመሰረትና የዜጎች ሰብዓዊ መብት እንዲከበር የሚሹ ሁሉ ከላይ ለተጠቀሱት ግልሰቦችና ተቋማትን ጨምሮ ሚሊዮኖች ለሚያውቁትና ተፅዕኖ ማሳደር ይችላል ለሚሉት ሰው ሁሉ መልዕክት በኢንተርኔትና በሶሻል ሚዲያ በመላክ ድምፃቸውን ያሰሙ ዘንድ ዛሬ ህዳር 11 ቀን 2007 ዓ.ም. አዲስ አበባ በሚገኘው ዋና ጽህፈት ቤቱ በሰጠው መግለጫ ጥሪውን አቅርቧል፡፡
ፓርቲው ከዚህ በፊት ከህዝቢ ከፍተኛ ድፍ ያስገኘለትን “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” እና “…ለመሬት ባለቤትነት” የሚሉ የተለያዩ ህዝባዊ ስብሰባዎችን እና የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎችን አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች ማድረጉ ይታወቃል፡፡ የዛሬውን ሙሉ ዝርዝር መግለጫ ከታች ይመልከቱ፡፡
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)
UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
ምርጫ ሲባል አማራጭ ሳያሳጡ መሆን ይኖርበታል!!!
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ
በሀገራችን ኢትዮጵያ ለአምስተኛ ጊዜ ሀገራዊ ምርጫ እንደሚደረግ በመንግስት በኩል በከፍተኛ ደረጃ የፕሮፓጋንዳ መሳሪያ ሆኖ እያገለገለ ይገኛል፡፡ ነገር ግን ከዚህ በፊት የተከናወኑት አራት ምርጫዎች ያየን እንደሆነ በሀገራችን የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ግንባታ ወደፊት ሊወስዱ እንዳልቻሉ እሙን ነው፡፡ ይህም ሆኖ የኢትዮጵያ ህዝብ ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ያለውን ፍላጎት በተለያየ መንገድ ሲገልፅ ቆይቷል፡፡ በተቃራኒው መንግስትና ገዢው ፓርቲ በፍፁም መለየት በሚያስቸግር ሁኔታ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታ ሆነው ተቀናጅተው ለአንድ ለአውራ ፓርቲ ግንባታ እየሰሩ እንደሆነ ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ ይህ የመንግሥትና የገዢው ፓርቲ ተግባር ምርጫን ያለ አማራጭ እንዲሆነ እያደረገው እንደሆነ ለመረዳት አስቸጋሪ አይደለም፡፡
በቅርቡ የአንድነት ፓርቲ አባላት ላይ በሁሉም የሀገሪቱ ክፍሎች ዘመቻ በሚባል ደረጃ እየተካሄደ ያለው አፈናና እስር፤ ከዚህም ባሻገር ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከህዝብ ጋር እንዳይገናኙ ክልከላውና ወከባው ተጠናከሮ መቀጠሉ፤ ገዥው ቡድን የምር ተቃዋሚ ፓርቲ ናቸው ብሎ የሚያስባቸው ፓርቲዎች ለማዳከምና ከምርጫው ውድድር ውጪ ለማድረግ ያለው ቁርጥ አቋም የሚያሳይ ነው። ይህ የገዢው ቡድን አካሄድ በሀገራችን ዴሞክራሲያዊ የሆነ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት እንዲመሰረት ፍላጎት እንደሌለው በደንብ የሚያረጋግጥ ነው፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ ነፃና ፍትሐዊ በሆነ ምርጫ የሚፈልገውን ፓርቲ እንዲመርጥ እድል ሊጠሰው ሲገባ በሥርዓቱ በእኩል ነፃና ፍትሐዊ ምርጫ እንዳያካሄድ የተለያዩ ጫናዎች እየተደረጉበት የሚካሄዱት ምርጫዎች ሁሉ ትርጉም አልባ እየሆኑ ይገኛሉ፡፡ ይህ የገዢው ቡድን ሀላፊነት የጎደለው እንቅስቃሴ በተግባር የሚደግፈው ከሠላማዊ ትግል ይልቅ የኃይልና የአመፅ መንገድ እንደሚሆን የተረዳ አይመስልም፤ ይልቁንም በሠላማዊ መንገድ እየተንቀሳቀሱ ያሉትን ፓርቲዎች ወደ አላስፈላጊ መስመር በመግፋት ሀገራችን ወደ ብጥብጥና ወደ እርስ በእርስ ጦርነት እንድትገባ የሚያደርግ ሁኔታ እየተከተለ ነው የሚገኘው። በሥልጣን ላይ ያሉት ወገኖች ይህ አሳሳቢ ሁኔታ በትክክል እንዳያዩ ጭፍን የሥልጣን ጥም ጋርዷቸዋል፡፡
በቀጣይ ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚደረገው ምርጫም በመንግስት በኩል የመድበለ ፓርቲን ስርዓት ለማጎልበት ምንም ዓይነት ምቹ ሁኔታ እንዳይፈጠር ከአሁኑ የተለያዩ እንቅፋቶችን በመደርደር ላይ ነው። የአንድነት አመራሮችና አባላት በግፍ በማሰር ፓርቲው በምርጫው እንዳይሳተፍ ከፍተኛ የሆነ ጫና እየተደረገ ቢሆንም አንድነት ፓርቲ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ሆኖ ህዝቡ እንዲሳተፍ በመቀስቀስና በማበረታታት የተዘጋውን የዴሞክራሲ በር በምርጫ ካርዱ ሊያስከፍት እንደሚችል ከፍተኛ እምነት አለው፡፡
ከሁሉም በላይ ደግሞ እንደከዚህ ቀደሙ ኢህአዴግ ደጋፊዎቼ የሚላቸውን ብቻ በመራጭነት አስመዝግቦ ምርጫ የሚያደርግበት ሁኔታ ማብቃት ይኖርበታል ብለን እናምናለን፡፡ ይህ ተግባራዊ እንዲሆን በእኛ በኩል ደጋፊዎቻችን በመራጭነት እንዲመዘገቡ ከማበረታት ጀምሮ የህዝብና የፓርቲ ታዛቢ በመሆን የምርጫ ሂደቱን በሙሉ በንቃት እንዲከታተል እንዲሳተፍ የበኩላችንን ጥረት በማድረግ የ2007 ሀገራዊ ምርጫ ከጅማሮው ህዝባዊ እንዲሆን ትግላችንን እንቀጥላለን፡፡ ይህ እርምጃም ህዝቡን የስልጣን ባለቤት ለማድረግ ወሳኝ እርምጃ ነው የሚል እምነት አለን፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ በገዥው ቡድን መልካም ፍቃድ ወይም በማንኛውም ውጫዊ ተፅዕኖ የፖለቲካ ምህዳሩን እንደማይሰፋ ሊገነዘብ ይገባል። ምህዳሩ የሚሰፋውና ትክክለኛ የሆነ ዴሞክራሲያዊ ለውጥ የሚኖረው ህዝቡ በጠቅላላ ከፍርሀት ቆፈን ተላቆ በሙሉ ልብ ለመብቱ ሲቆም፣ ለፓርቲዎች ተገቢው ድጋፍ ሲሰጥ፤ ከፍ ሲልም ወደ ትግሉ ሲቀላቀል መሆኑ መገንዘብ ያስፈልጋል።
በዚህ አጋጣሚ አንድነት ፓርቲ ከህዳር 14 እስከ 20 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚቆይ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለህሊና እስረኞች” የሚል የሶሻል ሚዲያ ዘመቻ አዘጋጅቷል። በዚህ ዘመቻ ለመንግስት ባለስልጣናት፣ ለታዋቂ ግለሰቦች፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተቋማትና ለልዩ ልዩ የሚዲያ ድርጅቶች በኢንተርኔትና በሶሻል ሚዲያ በእኩል መልዕክት በመላክ በሀገራችን ያሉት የፖለቲካ እስረኞች ሁኔታና አያያዝ በተመለከተ መረጃ በመስጠት ተገቢ የሆነ አያያዝ እንዲኖራቸው፤ ከእስር እንዲፈቱ፣ በሰላማዊ መንገድ የሚታሉትን ማሰርና ማዋከብ እንዲቆም በመንግስት ላይ አዎንታዊ ተፅዕኖ ለመፍጠር ያለመ ነው። በዚህ ዘመቻ ላይ ሚሊዮኖች ለሚያውቁትና ተፅዕኖ ማሳደር ይችላል ለሚሉት ሰው ሁሉ መልዕክት በኢተርኔትና በሶሻል ሚዲያ በመላክ ድምፃቸውን ያሰሙ ዘንድ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
ህዳር 11 ቀን 2007 ዓ.ም.
አዲስ አበባ
………..//………//…………
የሴቶች ጉዳይ ይመለከተናል የምትሉ ከወዴት ናችሁ? የእህታችን የሐና ጉዳይ የሁላችንም ጉዳይ ነው!!
ብስራት ወልደሚካኤል
በቅርቡ በመዲናችን አዲስ አበባ አንዲት የ16 ዓመት ባለ ብዙ ተስፋዋ የ10ኛ ክፍል ተማሪ የነበረችው እህታችን ሐና ላላንጎ ለክፉ ድርጊታቸው ቃላት በማይገልፃቸው 5 ጨካኝ ወንዶች ከሰብዓዊነት በራቁ አረመኔ ወንዶች ያውም በቀን ከትምህርት ቤት ወደ መኖሪያ ቤቷ በተሳፈረችበት ታክሲ ስትሄድ ሾፌር፣ረዳትና ሌሎች ግብር አበሮቻቸው ታግታ ለቀናት በመፈራረቅ ተደፍራ ህይወቷ አልፏል፡፡ ዜናው እጅግ ዘግናኝ ከመሆኑ የተነሳ ለመግለፅ ያስቸግራል፡፡ የልጆቹን ድርጊት አንዳንዶቹ ከሌሎች የቤትና የዱር እንሰሳ ድርጊት ጋር ሊያይዙ ይሞክራሉ፡፡ እውነታው ግን የትኛውም እንሰሳ ምስያውን ያውም ተስፈኛ የስንት ታናሽ እህቱን፣ ልጁን ወይንም ወገኑን በጅምላ አግቶና አስገድዶ ደፍሮ የሚገል ፍጡር የለም፡፡
ሐና ላይ አረመኔዎች የፈፀሙት ድርጊት በምንም የሚገለፅ አይደለም፡፡ እጅግ ልብን የሚናካና አሳዛኛ ተግባር ነው፡፡ የድርጊቱ ፈፃሚዎችም የማያዳግም እርምጃ ወይም ቅጣት በአደባባይ ሊያገኙ ይገባል፡፡ ምንም እንኳ ዛሬ ያቺ ተስፈኛ ለግላጋ ወጣት በህይወት ኖራ የአረመኔዎችን ቅጣት በዓይኗ ለማየት ባትታደልም ለሌሎች አረመኔዎች ማስተማሪያ እንዲሆን እና ሌሎች እህቶቻችንም ቀና ብለው በሀገራቸው በኩራትና በነፃነት ይንቀሳቀሱ ዘንድ ለሐና ተብሎ የሚሰጠው ፍትህ የሁሉም ነው ብዬ አምናለሁ፡፡
በርግጥ ኢትዮጵያ ውስጥ ፍትህ በሌለበት ፍትህ መጠየቅ ህልም ቢሆንም፤ እነኚህ የድርጊቱ ፈፃሚ አረመኔዎች ግን በምንም መልኩ ተገቢውን ለሰሩት አሰናዋሪ ጭካኔ ለተሞላበት ተግባር ተገቢውን ቅጣት ሊያገኙ ይገባል የሚል እምነት አለኝ፡፡
እዚህ ላይ በጣም የገረመኝ ጥያቄ የፈጠረብኝ ነገር አለ፡፡ ይኸውም በኢትዮጵያ ያሉ የሲቪክ ተቋማት በተለይም የሰቶች ጉዳይ ቅንጅት፣ ማኀበራት፣ …የሚባሉ ተቋማት ባለፈው 2004 ዓ.ም. የበረራ አስተናጋጇ (ሆስተሷ) አበራሽ ኃይላይ ላይ በቀድሞ ባለቤቷ ተወሰደ በተባለው የበቀል እርምጃ የአካል መጉደል ደርሶባታል በሚል ከፍተኛ ተቃውሞ ከማድረግ በተጨማሪ በቅንጡ ሸራተን አዲስ ሆቴል ተደጋጋሚ መግለጫ እስከመስጠት ደርሰው እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ ለዚህም እኔው ራሴ ከዚህ ቀደም በምሰራበት ጋዜጣ ለጉዳዩ ከ2 ጊዜ ያላነሰ የዜና ሽፋን በመስጠት በመግለጫዎቹና ተቃውሞዎቹ ላይ ልክ እንደሌሎቹ የሙያ አጋሮች በተደረገ ጥሪ ተገኝቼ የታዘብኩት እውነታ ነበር፤ከሙያ በተጨማሪ በግሌም ጥቃቶችን የምቃም ነኝና፡፡ ያኔም ሆነ አሁን በካሚላት፣ በአበራሽ ላይም ሆነ በማንኛውም ሴትም ሆነ ወንድ ላይ በአጠቃላይ በማንኛውም የሰው ልጅ ላይ የሚፈፀም ኢ-ሰብዓዊ ድርጊትን አጥብቄ የምቃወመው ተግባር ነው፡፡ ይሁን እንጂ በተማሪ ሐና ላይ በተፈፀመው አሰቃቂ ተግባር ያኔ ለነ አበራ ኃይላይ ይደረግ የነበረው እንቅስቃሴ ዛሬ የት ሄደ? ለምን?
እኔ እስከሚገባኝ ሐናም አበራሽም ሆነች ካሚላት ሁሉም ሴቶች፣ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ሁሉም ወገኖቻችን ናቸው፡፡ ስለዚህ ሌሎች ተቋማትም ሆኑ ሴቶች ላይ ትኩረት አድርገው የሚሰሩ ተቋማት ከሐና ጎን ሲቆሙ አላየሁም፤ ወይም አልተገነዘብኩም፤ ለምን? ሁሉም ላይ የሚፈፀም ጥቃት እኩል ድጋፍ ሊደረግ ይገባል፤ ቢቻል ያኔ መግለጫ ለመስጠት ጋዜጠኞችን ሲጨቀጭቁ የነበሩ ይመለከተናል የሚሉ የሴቶች ማኀበራትና ተቋማት ዛሬ ከወዴት ናችሁ? ማንኛውም ሴት ላይ የሚፈፀም ጥቃት በእኩል ትኩረት በመስጠት ከጎናቸው መሆናችንን ልናሳይ የሚገባ ይመሰለኛል፡፡
በርግጥ ይህን ስል ጉዳዩ ወንዶችን አይመለከትም ማለቴ አይደለም፤ በደንብ ይመለከተናል፡፡ ምክንያቱም ሰው በመሆናችን ብቻ ሴትም ሆነ ወንድ ላይ የሚፈፀም ጥቃት የሰው ልጅ ላይ በመሆኑ ይመለከተናል፡፡ ግዴታችንም ነው፡፡ ከዛ በተጨማሪ እስኪ ማነው እናቱን የሚጠላ? ማነው እህቱ ላይ ሌላ ሰው የዚህን ዓይነት አሰቃቂ ድርጊት እንዲፈፀም የሚፈቅድ? እስኪ ማነው ልጁ ላይ እንዲህ እንዲፈፀም የሚፈቅድና ቢፈፀም ደስተኛ የሚሆን? ማንም ያለ አይመስለኛም፤ሊኖርም አይገባም፡፡ ጉዳዩ የሁላችንም ነው የምላው ለዚህ ነው፡፡
በሀገሪቱ ተመሳሳይ ድርጊት ከእንግዲህ እንዳይፈፀም ተገቢውን ፍትህ ከመስጠት በተጨማሪ ለሌሎች እህቶቻችን ቢያንስ ድርጊቱን እናወግዛለን ፣ ከጎናችሁ ነን፤ ተገቢው ፍትህ መሰጠት አለበት የሚሉ የተቃውሞ ድምፆች በጋራ በወድሞቻችን እና እህቶቻችን ሊዘጋጅ የሚገባ ይመስለኛል፡፡ አለበለዚያ ድርጊቱ ነገም ሊቀጥል ይችላል፡፡ አሁንም ይሄ የሐናም ሆነ የነ ካሚላትና አበራሽ ላይ የተፈፀሙ ድርጊቶች አዲስ አበባ በመሆናቸው ለአደባባይ በቁ እንጂ…በየ ክልል ከተሞችና በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ከተጠቀሱት የሚልቅ ድርጊቶች እንደሚፈፀሙ ይታመናል፡፡ ይህ ሁሉ እንዲቀር ሴት ወንድ በሚል የፖለቲካ ፍጆታ መድረክ ከማድመቅ በዘለለ በእውነት ለሁሉም ልንደርስላቸው ይገባል፡፡
ንፁሃንን አሸባሪ እያለ በግፍ የሚያስረውና የሚያሰቃየው መንግስትስ የህፃናትና ተማሪዎችን ደህንነት ያውም በአዲስ አበባ እንዴት መታደግ አቃተው; ስንቱን የግለሰብ ምስጢር እየበረበረ የሚከታተል ደህንነትስና ፖሊስስ ንፁሃንን ከማደን ተላቆ ወንጀለኞችን በማደን እና ለፍርድ ከማቅረብ ረገደ እንዴት ነው?
ሐና…ፈጣሪ ነፍስሽን በገነት ያኖረው ዘንድ ተመኘሁ…
አሁንም…ፍትህ ለሐና ! ፍትህ ለሐና!!….ፍትህ ለሐና…!!