ኢትዮጵያውያን በቤልጂየም ብራሰልስ የአውሮፓ ህብረት ዋና ጽህፈት ቤት ፊትለፊት የተቃውሞ ሰልፍ አደረጉ
ዛሬ አርብ ጥቅምት 29 ቀን 2007 ዓ.ም. በተለያዩ የአውሮፓ ሀገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን፤ ገዥው ስርኣት በዜጎች ላይ እየፈፀመ ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት በመቃወም የአውሮፓ ህብረት ዋና ፅህፈት በሚገኘው ቤልጂየም ብራሰልስ ፊት ለፊት የተቃውሞ ሰልፍ አደረጉ፡፡ ሰልፈኞቹ መንግስት በሽብር ስም አስሮ ክስ የመሰረተባቸውን እና የፈረደባቸውን የኢትዮጵያ የህሊናና የፖለቲካ እስረኞችን ፎቶ ግራፎችን በመያዝ፣ በተለያየ የሀገሪቱ አካባቢ በመንግስት የጅምላ ጭፍጨፋ ሰለባ የሆኑ ዜጎችን በማሰብና በሀገሪቱ እየደረሰ ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት በግልፅ በመኮንን፤ የአውሮፓ ህብረት ሀገራትም እንዲህ ዓይነት ድርጊቱ በዜጎቹ ላይ ከሚፈፅም ስርዓት ጋር ትብብር ማድረጋቸው አቁመው ፖሊሲያቸውንና አቋማቸውን እንዲመረምሩ የሚጠይቅ ደብዳቤም ለህብረቱ ፅህፈት መግባቱን በስፍራው የነበሩ ምንጮች አስታውቃል፡፡
ሰልፈኞቹ ተቃውሟቸውን በብራሰልስ የአውሮፓ ህብረት ዋና ፅህፈት ካደረጉ በኋላ በከተማው ወደሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በመሄድ በሀገሪቱ እየተፈፀመ ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ማውገዛቸውን ተሰምቷል፡፡ የተቃውሞ ሰልፉን አስመልክቶ ከአውሮፓ ህብረትም ሆነ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ የተገኘውን ዝርዝር ምላሽ በተመለከተ መረጃው እንደደረስን እናቀርባለን፡፡
ኢህአዴግ በክልል የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችን ማሰርና መደብደቡን ቀጥሏል
የታሰሩ አመራሮች የአንድነት፣መኢአድ፣ ሰማያዊ እና አረና ፓር እና የሲቪክ ተቋም አመራር ይገኙበታል፡፡ እነኚህም ከአንድነት ከሰሜን ጎንደር ምዕራብ አርማጭሆ አቶ አንጋው ተገኝ፣ አቶ አባይ ዘውዱ፣ አቶ እንግዳው ዋኘው እንዲሁም ከመተማ አቶ በላይነህ ሲሳይ እና አቶ አለባቸው ማሞ ጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም.፤ ከበመቀሌ የአንድነት አባል የሆነው አቶ ሺሻይ አዘናው ደግሞ ጥቅምት 26 2007 ዓም ተይዘው እስካሁን ባልታወቀ ስፍራ በመንግስት ፀጥታ ኃይሎች ታፍነው መሰወራቸው ተጠቁሟል፡፡
በተመሳሳይ ወቅት ሌሎች የአንድነት አመራሮች ከወረታ አቶ አለበል ዘለቀ፣ከምዕራብ ጎጃም ደጋ ዳሞት ወረዳ አቶ ጥላሁን አበበ በመንግስት ፀጥታ ይሎች ታፍነው ወዳልታወቀ ቦታ መታሰራቸው ፓርቲው አስታውቋል፡፡ ሌላው የአንድነት ፓርቲ የወላይታ ዞን አመራሮች አቶ ማሞ ጎሙ፣ አቶ ወኖ መናሳ እና አቶ አልታዬ አቦታ በመንግስት የደህንነት ኃይሎች ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈፀመባቸውና የህክምና ዕርዳታም እየተደረገላቸው እንደሆነ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ይህንንም አስመልክቶ አንድነታ ፓርቲ ድርጊቱን በመቃወምና በማውገዝ ጥቅምት 28 ቀን 2007 ዓ.ም. መግለጫ ማውጣቱ ታውቋል፡፡
ከመኢአድ የቀድሞው የፓርቲው ዋና ፀሐፊነ አመራር ተስፋዬ ታሪኩ ከጎጃም ደጀን በፀጥታ ኃይሎች ታፍነው መወሰዳቸው እንዲሁም ከሰማያዊ ፓርቲ ደግሞ የሰሜን ጎንደር የዞን አመራር የሆኑት አቶ አግባው ሰጠኝ ጎንደር ከተማ ውስጥ ጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም. በተመሳሳይ በመንግስት የፀጥታ ኃይሎች ታፍነው ወዳልታወቀ ስፍራ እንደሰወሯቸው ፓርቲዎቹ አስታውቀዋል፡፡ በተያያዘ ዜና ከአረና ትግራይ ፓርቲ ደግሞ በትግራይ ክልል የሚገኙ አመራሮቹና አባሎቹ ቀሺ ብርሃኑ ቀባዕ፣ኣቶ ኣያሌው ጣዕምያለው፣,አቶ ሓለፎም ገብረዝጊ እና ቀሺ ገብረእግኣብሄር ካሳዬ ጥቅምት 26 ቀን 2007 ዓ.ም.በተመሳሳይ በፀጥታ ኃይሎች ታፍነው መወሰዳቸውን ፓርቲው አስታውቋል፡፡ የኢህአዴግ መንግስት መጪውን ምርጫ 2007 ዓ.ም. ከወዲሁ ታሳቢ በማድረግ ከላይ የተጠቀሱ የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ ወጣት አመራሮችን ማሰር፣ መሰወርና መደብደቡን አጠናክሮ መቀጠሉ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ የመግባባት፣ አንድነትና ሰላም (ሰላም) ማህበር የተሰኘው የሲቪክ ተቋም ስራ አስኪያጅ አቶ ፋንታሁን ብርሃኑ ጥቅምት 23 ቀን 2007 ዓ.ም.መታሰራቸው ተጠቁሟል፡፡ አቶ ፋንታሁን ማኀበራቸው በህግ የተፈቀደለትንና የቆመለትን ዓላማ ለማስፈፀም ሲንቀሳቀሱ አዲስ አበባ ሽሮ ሜዳ አካባቢ ተይዘው መታሰራቸውን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ ያመለክታል፡፡
በተለይ የፓርቲዎቹ ወጣት አመራሮች ላይ በተከታታይ እየደረሰ ያለውን እስርና ድብደባ ምክንያት በተመለከተ ምላሽ እንዲሰጡ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤት ጥረት ቢደረግም አልተሳካም፡፡ በተለይ ከሚያዚያ 2006 ኣ.ም. ጀምሮ ኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት ጋዜጠኞችን፣ ብሎገሮችን እና ወጣት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በጅምላ ማሰሩን አጠናክሮ መቀጠሉን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡