የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና አመራሮች ምግብ እንዳይገባላቸው ተከለከሉ
-ህዝብ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ ቀርቧል
9ኙ ፓርቲዎች በትብብር ለሚያዘጋጁትና ሰማያዊ ፓርቲ ለሚያስተባብረው የህዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚደረገው የአደባባይ ህዝባዊ ስብሰባ ሲቀሰቅሱ እና ታሳሪዎቹን ለመጠየቅ ወደ ፖሊስ ጣቢያ በሄዱበት ወቅት የታሰሩት 6 የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ምግብ እንዳይገባላቸው ተከለከሉ፡፡
በሌላ በኩል ለነገው የአደባባይ ህዝባዊ ስብሰባ በአብዛኛው የአዲስ አበባ ክፍሎች ስኬታማ ቅስቀሳ መደረጉን የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ገልጸዋል፡፡ይህ በእንዲህ እንዳለ አገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚገኙ ለውጥ ፈላጊ ኢትዮጵያውያን፤ ህዝቡ በአደባባይ ስብሰባው እንዲሳተፍ በስልክ (በመደወልም ሆነ መልዕክት በመላክ)፣ በማህበራዊ ድህረገጽና ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ የበኩላቸውን እንዲያደርጉ፣ ለአንድ ወሩ መርሃ ግብርም ሆነ በሌላ የትግሉ አካል ሁለገብ ድጋፍና ተሳትፎ እንዲያደርጉ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ጥሪ አድርጓል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከቅስቀሳው ጋር በተያያዘ የታሰሩትን የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና አመራሮች ለመጠየቅ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ባቀኑበት ወቅት የታሰሩት አቶ ወሮታው ዋሴና አቶ ብርሃኑ ተክለያሬድም በምሽት መለቀቃቸውን ፓርቲው አስታውቋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ እሁድ ህዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም. የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር በአዲስ አበባ ቀበና ቤለር የጠሩት ህዝባዊ ስብሰባ በፖሊስ መበተኑ ተገለፀ፡፡