ወጣቶቹ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በድብቅ ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ተደረገ
ከአራት ወራት በፊት በሽብር ስም በአዲስ አበባ የፌደራሉ ወንጀል ምርመራ “ማዕከላዊ” የሚገኙት የአንድነት ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች አቶ አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሺ፤ የሰማያዊ እና የአረና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች አቶ የሺዋስ አሰፋና አቶ አብርሃ ደስታ ዛሬ ጥቅምት 20 ቀን 2007 ዓ.ም. ከሰዓት በድብቅ ልደታ ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ መደረጋቸውንና ነገ ጠዋት በድጋሚ ልደታ ፍርድ እንደሚቀርቡ የፍኖተ ነፃነት ዘገባ ያስረዳል፡፡
የህሊና እስረኞቹ እንደተለመደው አራዳ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ በሚል የትግል አጋሮችቸው እና ደጋፊዎቻቸውና ጋዜጠኞች ከቀኑ 7 ሰዓት ጀምሮ እስከ 11፡30 በቀጠሮው ስፍራ ቢጠብቁም፤ ፖሊስ በድብቅ ልደታ ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ማድረጉ ተሰምቷል፡፡ ታሳሪዎቹ ልደታ ፍርድ ቤት እንደሚገኙ መረጃ የደረሳቸው የአንድነት ፓርቲ አመራሮች በስፍራው ሲደርሱ አቶ ሀብታሙ አያሌው፣አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣አቶ የሺዋስ አሰፋና አቶ አብርሃ ደስታ በመኪና ውስጥ ሆነው ወደ ማዕከላዊ ሲወሰዱ መመልከታቸውን ተናግረዋል፡፡ ቀደም ብሎም የልደታው ፍርድ ቤት “ጉዳዩን የሚያይ ዳኛ የለም” በማለት ለነገ ጠዋት ጥቅምት 21 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ መሰጠቱም ተጠቁሟል፡፡
ምንጭ፡- ፍኖተ ነፃነት
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በተመሰረተበት ክስ 3 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈረደበት
የቀድሞ የፍትህ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅና መስራች፣ የአዲስ ታየምስ መፅሔት፣ የልዕልና ጋዜጣ በመጨረሻም የፋክት መፅሔት ባልደረባና አዘጋጅ የሆነው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በተመሰረተበትና ጥፋተኛ በተባለበት 3 ክሶች መካከል በአንዱ ክስ ብቻ የ3 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈረደበት፡፡ጋዜጠኛው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቃቤ ህግ በመሰረተበት ክስ ጥፋተኛ የሚል ብይን ከሰጠ በኋላ ቅጣት የተጣለበት በ2004 ዓ.ም. በፍትህ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በነበረበት ወቅት በፃፋቸው ፅሑፎችን መሰረት አድርጎ መሆኑ ታውቋል፡፡
ጋዜጠኛው የተፈረበት፤ዛሬ ጥቅምት 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በዋለው ችሎትም ጋዜጠኛው ጥፋተኛ ከተባለበት 3 ክሶች መካከል በአንዱ ክስ ብቻ የ3 ዓመት ፅኑ እስራት ቅጣት ተጥሎበታል፡፡ በዚህም መሰረት ጋዜጠኛ ተመስገን በፀጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ስር እንደሆነ፤ወደ አቃቂ ቂሊንጦ ወደሚገኘው ወህኒ ቤት ተወስዷል፡፡
የጋዜጠኛው ተከላካይ ጠበቃ አቶ አምሃ መኮንን ቅጣቱን እና ፍርዱን በሚመለከት ይግባኝ እንደሚጠይቁ የተገለፀ ሲሆን፤ በቅጣት ፍርዱ አቃቤ ህጉም ሆኑ ተከላካይ ጠበቃው የቅጣት ማክበጃም ሆነ ማቅለያ አለመጠየቃቸው ተጠቅሟል፡፡ በኢትዮጵያ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝን ጨምሮ የታሰሩት ጋዜጠኞች እና ብሎገሮች ቁጥር 18 መድረሱ ታውቋል፡፡
ኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት በፃፉት ፅሑፍ የተከሰሱ፣የታሰሩም ሆነ የተፈረደባቸው ጋዜጠኞችም የሉም የሚል ተደጋጋሚ ማስተባበያ ቢሰጥም፤ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ጨምሮ ከታሰሩት 18 ጋዜጠኞችና ብሎገሮች መካከል 15ቱ ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞችና ብሎገሮች የቀረበባቸው ክስናም ሆነ ፍርድ ከስራቸው ጋር በተያያዘ በፃፉትና በተናገሩት መሆኑ የተመሰረተባቸው ክስ ያመለክታል፡፡
ጋዜጠኞቹ እና የዞን 9 ብሎገሮቹ ለጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ተጠየቀባቸው
- ኤዶምና ማህሌት የመብት ጥሰት እንደተፈጸመባቸው ቅሬታ አቅርበዋል
የዞን 9 ብሎገሮቹና ሶስቱ ጋዜጠኞች ያቀረቡት መቃወሚያ ‹‹ተቀባይነት የለውም›› ተብሎ ለጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ተቀጠረባቸው፡፡ ጦማሪያኑና ጋዜጠኞቹ የተከፈተባቸው ክስ አግባብ አለመሆኑን የሚገልጽ ስምንት ገጽ የክስ መቃወሚያ አቅርበው የነበረ ቢሆንም አቃቢ ህግ ‹‹ክሱ ምንም ችግር የለበትም፣ የሚሻሻል ነገር የለውም፡፡›› በሚል መቃወሚያውን ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡
ቃሊቲ እስር ቤት ታስረው የሚገኙት ኤዶም ካሳዬና ማህሌት ፋንታሁን ማረሚያ ቤቱ ውስጥ የመብት ጥሰት እንደሚፈጸምባቸው ቅሬታቸውን አቅርበዋል፡፡ ሁለቱ ታሳሪዎች በፍርድ ሂደት ላይ ያሉ ቢሆንም እስር ቤቱ ውስጥ ‹‹አሸባሪ›› የሚል ስም እንደሚሰጣቸው ቅሬታ ያቀረቡ ሲሆን ከዚህም በተጨማሪ ‹‹ቤተሰብ ብቻ ነው የሚጠይቀን፡፡ ከቤተሰብ ውስጥም የምንጠየቅው ስማቸውን ባስመዘገቡት ብቻ ነው፡፡ ያም ሆኖ የምንጠየቀው ለ10 ደቂቃ ነው፡፡ ለመጠየቅ የሚመጡ ቤተሰቦቻችንም ድብደባ ይፈጸምባቸዋል፡፡›› በሚል ቅሬታቸውን አቅርበዋል፡፡
ባለፈው ችሎቱ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ኃላፊ ታሳሪዎቹ ይደርስብናል በሚሉት በደል ዙሪያ ለዛሬ ቀርበው እንዲያስረዱ ተጠይቀው የነበር ቢሆንም ሳይቀርቡ ቀርተዋል፡፡ ዛሬ ያልተገኙት የማረሚያ ቤቱ ኃላፊ ለጥቅምት 25/2007 ዓ.ም ቀርበው ያስረዳሉ ተብሎ የነበር ቢሆንም ኤዶምና ማህሌት ‹‹ይህ የመብት ጉዳይ ስለሆነ አጭር ቀጠሮ ሊሰጥልን ይገባል፡፡›› በማለታቸው ማረሚያ ቤቱ ውስጥ እየተፈጸመብን ነው ያሉትን በደል ብቻ ለማየት ጥቅምት 11 ቀን 2007 ዓ.ም.ቀነ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡ የማረሚያ ቤት ኃላፊው ቀርበው ያስረዳሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ኤዶምና ማህሌት ለዋናው ክስም ጥቅምት 25 ደግመው ይቀርባሉ፡፡
በዛሬው ችሎት የታሰሪዎቹ ቤተሰቦች፣ የአገር ውስጥና የውጭ ጋዜጠኞች፣ የኤምባሲና የተቋማት ተወካዮችን ጨምሮ በርከት ያለ ታደሚ ተገኝቶ ተከታትሏል፡፡ ጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም አቃቢ ህግ ያቀረበው ክስና ጦማሪያኑና ጋዜጠኞቹ ያቀረቡት የክስ መቃወሚያ ላይ ምርመራ ተደርጎ ሌላ የፍርድ ሂደት ይጀመራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ-ኢትዮጵያ ጋዜጣ
በቅርቡ የተሰደደው ጋዜጠኛ ሚሊዮን ሹሩቤ ህይወቱ አለፈ
የማራኪ መፅሔት ባለቤት እና ማኔጂንግ ዳይሬክተር የነበረው ጋዜጠኛ ሚሊዮን ሹሩቤ በስደት በሚገኝበት ናይሮቢ ኬኒያ ጥቅምት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. በድንገት ህይወቱ ማለፉን ከማኀበራዊ ገፆች የተገኙ መረጃች እና ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት በጅምላ ያደረገውን የመፅሔቶች እና ጋዜጣ ክስ እና የበርካታ ጋዜጠኞችን እና ብሎገሮችን እስርን ፍርሃት ተከትሎ በቅርቡ ከተሰደዱ ጋዜጠኞች መካከል ጋዜጠኛ ሚሊዮን ሹሩቤ አንዱ ነበር፡፡
ጋዜጠኛው በስደት ኬኒያ ከሚገኝበት አንድ ናይሮቢ ሆስፒታል በህክምና ሲረዳ ቢቆይም ህይወቱን ማትረፍ እንዳልተቻለ ታውቋል፡፡ ጋዜጠኛው ከኢትዮጵያ ከተሰደደ ገና ሁለት ወር እንኳ እንዳልሞላው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ጋዜጠኛው ህይወቱ እስካለፈበት ድረስ በኢትዮጵያ ነፃ ፕሬስ ውስጥ ከ12 ዓመታት በላይ እንዳገለገለና የድርሰት ስራም እንዳለው ተጠቁሟል፡፡
ጋዜጠኛ ሚሊዮን በተወለደ በ33 ዓመቱ በስደት ናይሮቢ ኬንያታ ናሽናል ሆስፒታል ቢያርፍም፤የቀብር ስነስርዓቱ እሁድ ጥቅምት 9 ቀን 2007 ዓ.ም. በትውልድ አካባቢው ይርጋ ጨፌ ከተማ ቅድስት ኪዳነ ምህረት ቤተ ክርስቲያን ተፈፅሟል፡፡ ጋዜጠኛው የአንድ ወንድ ልጅ አባት ነበር፡፡
አዲስ ሚዲያም በጋዜጠኛው ሞት የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን እየገለፀ፤ ለጋዜጠኛ ሚሊዮን ፈጣሪ ነፍሱን በገነት እንዲያኖር፤ ለቤተሰቦቹ፣ለወዳጅ ዘመዶቹና አድናቂዎቹ መፅናናትን ይመኛል፡፡
ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው በገዛ ፍቃዳቸው ሥልጣናቸውን ሲለቁ፤ አቶ በላይ ፍቃዱ ቀጣዩ ፕሬዘዳንት በመሆን ተመርጠዋል
የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ብሔራዊ ምክር ቤት ዛሬ ጥቅምት 2 ቀን 2007 ዓ.ም. በነበረው ስብሰባ ፕሬዚዳንቱ ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው ሪፖርት ካቀረቡ በኋላ፤ ከውስጥና ከውጭ በተፈጠሩ አንዳንድ የማያሰሩ ችግሮች፣ ካለባቸው የሥራ ጫና እና ፓርቲው ወደፊት አንድነቱን ጠብቆ ለ2007 ምርጫ አሸናፊ ሆኖ እንዲወጣ በማሰብ ስልጣናቸውን በቃዳቸው መልቀቃቸውን ይፋ ማድረጋቸው ተጠቁሟል፡፡
ምክር ቤቱም በፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ መሰረት የፕሬዘዳንቱን ጥያቄ በአድናቆት ተቀብሎ፤ ፓርቲውን በፕሬዘዳንትነት በመምራት መጪውን ምርጫ ውጤታማ ለማድረግ እንዲያስችል 1ኛ. አቶ በላይ ፈቃዱ፣2ኛ. አቶ ደረጀ ኃይሉ እና 3ኛ. አቶ ትዕግስቱ አወሉን በዕጩነት በማቅረብ፤አቶ በላይ ፈቃዱን በፕሬዘዳንት መርጧል፡፡ ምርጫውም በምስጢር ድምፅ አሰጣጥ እዛው በፓርቲው ምክር ቤት የተከናወነ ሲሆን፤በመጨረሻም አቶ በላይ ፈቃዱ በከፍተኛ ድምፅ ማሸነፋቸው መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ከምርጫው ውጤት በኋላ አቶ በላይ በቀጣይ የስልጣን ጊዜያቸው ፓርቲውን ለመምራት ቃለ መሐላ የፈፀሙ መሆናቸውን የፍኖተ ነፃነት ዘገባ ያስረዳል፡፡ አቶ በላይ ጠንካራ የፖለቲካ ልምድና ተሳትፎ ካላቸው የፓርቲው ወጣት አመራሮች መካከል በውጤታማነት ከሚጠቀሱት አንዱ እንደሆኑ የተጠቆመ ሲሆን፤የትምህርት ደረጃቸውም በስታስቲክስ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የመጀመሪያ ድግሪ (BSc) እና በኢኮኖሚ ፖሊሲ አናሊስስ የማስተርስ ድግሪ (MSc) ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ያላቸው ሲሆን፤ በስራ ልምዳቸውም በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አገልግለዋል፡፡ አቶ በላይ ወደ ፓርቲው ፕሬዘዳንትነት ከመምጣታቸው በፊት፤ በራሳቸው የጥናትና ምርምር ድርጅት በማኔጂንግ ዳይሬክተርነት ያገለግሉ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡
ፓርቲው መጪውን 2007 ዓ.ም. ምርጫ እንዲያሸንፍ ትልቅ ሚና ይኖራቸዋል በሚል ከአባላትና ከደጋፊዎች ትልቅ ተስፋ እንደተጣለባቸውና ኃላፊነታቸውንም በስኬት ሊወጡ እንደሚችሉ ተገምቷል፡፡