Monthly Archives: November, 2014

የነፃነቴ ዋጋ ነብሴ ነው!!

ግርማ ሰይፉ ማሩ
girma seifuመረጃ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ጠቃሚ ነው ብሎ መንገር ለቀባሪ እንደማርዳት ነው፡፡ የተሟላ መረጃ የሰውን ልጅ ሙሉ ያደርገዋል፡፡ መረጃን አጣሞ ማቅረብ ደግሞ የሰውን ልጅ ውሳኔ ለማጣመም ካልሆነ በስተቀር ግቡ ምን ሊሆን እንደሚችል አይገባኝም፡፡ በሰሞኑ ሰው በላው የኢትዮጵያ ፖለቲካ በጥርሱም በጥፍሩም ዘመቻ የጀመረው እኔ ላይ ነው፡፡ ዓላማው ግልፅ ነው፡፡ በነፃነት የማሰብ መብቴን ለድርድር እንዳቀርብ ነው፡፡ ለነፃነቴ ያለኝን ዋጋ የማያውቁ ሰዎችን ይህንን ለማድረግ ቢሞክር ካላቸው የመረጃ እጥረት ወይም ማወቅ ባለመፈለጋቸው ነው፡፡ አንዳንድ ቅን ሰዎች ሰህተት እንደሰራው አድርገው ይቅርታ እንድጠይቅ፤ ይቅርም እንድባል አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ በቅን ልቦና ላደረጋችሁት ምስጋናዬ ይድረሳችሁ፡፡

ነገር ግን በሰጠሁት አስተያየት ያልተስማማ ሰው በሃሰብ ልዮነት መለያየት እያለ ይቅርታ ጠይቄ፤ ይቅርታም ተደርጎልኝ ወደ እነሱ ሃሳብ እንድገበ መፈለጉ ምን ዓይነት ከፍተኛ ችግር ያለበት አስተሳሰብ እንደሆነ የተረዱት አይመሰለኝም፡፡ ይህ ደግሞ በጣም አስገራሚ የሚሆነው የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ደጋፊ፣ ለግለሰብ ነፃነት እንቆማለን የሚሉ ወገኖች መሆናቸው ነው፡፡ ለሃሳብ ነፃነት የማይቆም እንዴት አድርጎ ለመድበላ ፓርቲ ስርዓት ግንባታና የግለሰብ ነፃነት እንደሚያከብር አይገባኝም፡፡

ጫጫታ ወደ ፈጠረው አጃንዳ ስገባ፡፡ አንድነት ፓርቲ የምርጫ ግብረ ሀይል ማቋቋሙን ለህዝብ በይፋ ለማሳወቅ እና በቀጣይ ሳምንት ስለሚያደርገው የህሊና እስረኞች ስለሚታሰብበት ፕሮግራም መግለጫ በሰጠንበት ወቅት በፍፁም ጠቃሚ ያልሆነ የተቃዋሚ ጎራውን በተለይ በሀገር ውስጥ ለምንገኝ ሰዎች የማይጠቅም (በኢቲቪ ቢቀርብ የማይገርም) ጥያቄ ቀረበ፡፡ ጥያቄው በእስር ላይ የሚገኙ የቀድሞ አንድነት አባል የነበሩ ታሳሪ ስም ጠርቶ በአንድነት አቋም እኝህ ሰው የህሊና እስረኛ ናቸው ብላችሁ ታምናላችሁ ወይ? የሚል ነበር፡፡ የሰጠሁት መልስ የማንንም ታሳሪ ስም ማንሳት ሳያስፈልግ የአንድነት ፓርቲ አባል ሆኖ የሌላ ፓርቲ አባል መሆን ትክክል እንዳልሆነ፣ ከአንድነት ጋር በትግል ስትራቴጂ ከማይመሳሰሉት ጋር ብቻ ሳይሆን በትግል ከሚመሳሰሉትም ጋር ቢሆን የተሻለ ወደሚለው መጠቃለል እንጂ ሁለት ቦታ መሆን ትክክል እንዳልሆነ አስረድቻለሁ፡፡ በማስከተልም “በፀረ ሽብር” ህግ መንግሰት እየከሰሰ የሚያስራቸው ሰዎች አንዳንዶቹ በወንጀል ህግ ሊያስጠይቅ የሚችል ሰህተት አልሰሩም የሚል ድምዳሜ እንደሌለኝ አሰረግጬ ተናግሬያለሁ፡፡ ለምሳሌ በፈንጂ ስው የገደለ ሰው በወንጀለኛ ህግ መጠየቅ እና መቀጣት አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህ እምቴ አሁን ፅኑ ነው፡፡ የ “ፀረ ሽብር” የሚባለውን ህግ በይፋ አሸባሪ ህግ ነው፡፡

ፖለቲከኞች እና ጋዜጠኞች አሸባሪ እየተባሉ የሚታሰሩ ያሉት የአራት ኪሎን ወንበር ስለሚያሸብሩ ነው የሚል አቋሜን ከብዙዎቹ ተችዎቼ በላይ እና ከማንም በማያንስ መልኩ ሃሳቤን በነፃነት አራምጃለሁ፡፡ ይህን ሳራምድ ማንንም ለማስደስት ሳይሆን አምኜበት ነው፡፡ አንድነት የ “ፀረ ሽብር” የሚባለው ህግ እንዲሰረዝ የተገበረውን “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” ዘመቻ በቁርጠኝነት ከመሩት አንዱ ስሆን፤ በተለይ በደሴ ከተማ የተደረገውን የሚሊዮኖች ድምፅ ዘመቻ በቦታው ተገኝቼ የመራሁት እኔ ነኝ፡፡ ይህን ሁሉ የምዘበዝበው በዚህ ህግ ላይ ያለኝን ግልፅ አቋም በድጋሚ ለማረጋገጥ ነው፡፡

በእኔ በኩል የአቋም ለውጥ ሳይኖር እሳት ጭረው ቤንዝን እያርከፈከፉ ያሉት ግለሰቦችና ቡድኖች ለምን ተፈጠሩ? የሚለው ነው፡፡ በእኔ እምነት የአንድነት በምርጫው የመሳተፍ ውሳኔ በትግል ስልታቸው ላይ የሚፈጥረው ጫና ስለሚያስጨንቃቸው ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡ ምርጫ መሳተፍ ትክክል አይደለም ብሎ መሟገት ሲያቅታቸው የፈጠሯት ስልት ነች፡፡ አንድነት ምርጫ መሳተፍ ሲወስን በምንም መመዘኛ የመወዳደሪያው ሜዳ ምቹ ነው የሚል ግምገማ ላይ ደርሶ አይደለም፡፡ የፖለተካ ምዕዳሩ ጠበበ ብቻ ሳይሆን ዝግ ነው የሚል ግምገማ ላይ ደርሶዋል፡፡ ልዩነቱ ማስከፈቻ መንገዱ ምን ይሁን የሚለው ነው፡፡ በህዝብ ድምፅ የተዘጋው የፖለተኪ በር ይከፈታል ነው አንድነት ያለው፡፡ በዚህ ውሳኔ የማይስማማ ሊኖር እንደሚችል ይገመታል፡፡ በዚህ ደረጃ ወርዶ ግን በጥርስና በጥፍር ለመናከስና ለመቧጨር መሞከር ግን ያስተዛዝባል፡፡

የግል ሰሜቴን ለመግለፅ እሰከ ዛሬ ድረስ ለሚቀርብልኝ ሙገሳና የማጀገኛ ቃለቶችን ተመርኩዥ ልቤ አላበጠም፡፡ አንድ ቀን ያለአግባብ ከፍ አድርገው ከሰቀሉ ቦታ ላይ አውርዶ የሚከሰክስ ማህበረሰብ አባል መሆኔን አውቃለሁ፡፡ ያለ አግባብ በእራሳቸው ስሜት ሊወስዱኝ የፈለጉት ከፍታ ላይ ስለአልሄድኩኝ አሁን ሊያወርዱኝ አይችሉም፡፡ እደግመዋለሁ ለነፃነቴ የምሰጠውን ዋጋ የማያውቁ ሰዎች ምንም ሊሞክሩ ቢችሉም ነፃነቴን ለኢህአዴግ አሳልፌ አልሰጥም ስል በተቃዋሚ ጎራ ለተሰለፈ አሳልፌ እሰጣለሁ ማለት አይደለም፡፡ ለነፃነቴ የመደብኩት ዋጋ ነብሴን ነው፡፡ ስም፣ ዝና፣ ክብር፣ ገንዘብ፣ ወዘተ እንዳይመስላችሁ!!!!! ነብሴን ነው፡፡

ለብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ አቀባበል ተደረገ፤ ፍቅረ ንዋይን በማሸነፍ ከሊቀ ጳጳሱ ጋራ በመመካከር እንዲሠሩ ማሳሰቢያ ተሰጠ

  • ‹‹የቤተ ክርስቲያን ሓላፊነት የአገር ነው፤ ቤተ ክርስቲያንን ልናስቀድም ይገባል›› ፓትርያርኩ  
  • ‹‹ገንዘብን አሸንፉት፤ መቃብርን አትርሱት›› /ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ
  • ‹‹ሕዋሳት ድርሻ አላቸው፤ ሕዋሳቱ ካልታዘዙ ግን ችግር ይፈጠራል›› /አቡነ ቀሌምንጦስ
  • ‹‹ሀገረ ስብከቱን የሚያመሰቃቅለው አሉባልታና ሐሰት መወገዝ አለበት›› //ሥራ አስኪያጁ
  • ‹‹ያልምዶት እንጂ እንኳን ደስ ያለዎት አንልዎትም›› /አስተያየት ሰጭ የደብር አለቃ
  • ‹‹ንግግር ከማብዛት ይልቅ ወደፊት በየሥራችን ብንመዘን›› /ሌላው የደብር አለቃ

abune kelemintos

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፤ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ እና የከምባታ ሐዲያ ጉራጌና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ

ቅዱስ ሲኖዶስ በወርኃ ጥቅምት የመጀመሪያ ዓመታዊ መደበኛ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባው፣ የከንባታ ሐዲያ ጉራጌና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ኾነው እንዲሠሩ መድቧቸዋል፡፡ በምደባ ውሳኔው መሠረት ኅዳር ፱ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. በሀገረ ስብከቱ የስብሰባ አዳራሽ በተከናወነ መርሐ ግብር ለብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡

 

‹‹የመጣነው ሥራቸውን በቡራኬ ለማስጀመር ነው፤ብፁዕነታቸው ደግ አባትና ጠንቃቃ መነኵሴ በመኾናቸው ይህን ከተማ ያስተካክሉታል ብለን እናምናለን፤ ኹላችኁም ትተባበሯቸዋላችኹ፤ ኹሉም መሪውን ይከተላልና፡፡››/ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ/

ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ጋራ ስምንት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የሀገረ ስብከቱ እና የሰባቱም ክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት የሥራ ሓላፊዎችና ሠራተኞች፣ ከ160 በላይ ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ምክትል ሊቃነ መናብርትና ጸሐፊዎች የተገኙበት ይኸው የአቀባበል መርሐ ግብር፣‹‹ለብፁዕነታቸው በተደራቢነት የተሰጠውን ሥራ በቡራኬ ለማስጀመር››የተዘጋጀ መኾኑን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ተናግረዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ደግ አባትና ጠንቃቃ መነኵሴ መኾናቸው እንደሚታወቅ የጠቀሱት ቅዱስነታቸው፣ ‹‹ትልቅና ጥንቃቄ የሚፈልግ ከተማ›› ያሉትን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት እንደሚያስተካክሉት እምነታቸውን ገልጸዋል፡፡

ችግሮች ሲፈጠሩ ከሐሜትና መነቃቀፍ ይልቅ ግራና ቀኝ አስፍቶ በማየት እየተወያዩ መሥራት ቅድስትና ልዕልት ለኾነችው ቤተ ክርስቲያናችን እንደሚበጅ ቅዱስነታቸው አመልክተው÷ ‹‹የቤተ ክርስቲያን ሓላፊነት የአገር ሓላፊነት በመኾኑ ከኹሉም በፊት ቤተ ክርስቲያንን ልናስቀድም ይገባል፤ የተሠየምነው ቅድስናዋንና ሕጓን ጠብቀን ለመኖር ነው፤›› በማለት አስገንዘበዋል፡፡ የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት የተቸገሩ የገጠር አብያተ ክርስቲያንን ለመርዳት ቅርበት እንዳላቸውና ሊኖራቸውም እንደሚገባ በመግለጽ ስለ አስተዋፅኦዋቸው አመስግነዋቸዋል፤ ‹‹አዲስ አበባ ሰላም ከኾነች ኹሉም ሰላም ይኾናል›› ያሉት አቡነ ማትያስ የአህጉረ ስብከት ኹሉ ማእከል በኾነው አዲስ አበባ ለሰላም፣ ለልማትና መልካም አስተዳደርን ለማስፈን ሊቀ ጳጳሱን በመደገፍና ከሊቀ ጳጳሱ ጋራ በመመካከር መሥራት እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል – ‹‹ኹላችኁም ትተባበሯቸዋላችኹ፤ ኹሉም መሪውን ይከተላልና፡፡››abune matiyas

‹ለኹለት ጌቶች መገዛት አይገባም፤ ገንዘብን ወድዳችኹ አይታችኁታል፤ እስኪ ደግሞ ንቃችኹ እዩት›› /የሰሜን ምዕራብ ሸዋ – ሰላሌ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ/

ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ቃለ ምዕዳንና መመሪያ ቀደም ብሎ የመርሐ ግብሩን ትምህርት የሰጡት የሰሜን ምዕራብ ሸዋ – ሰላሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ ናቸው፡፡ አንድ ሰው ወይ ለእግዚአብሔር ወይ ለገንዘብ እንጂ ለኹለት ጌታ መገዛት እንደማይችል የጠቀሱት ብፁዕነታቸው÷ ገንዘብን ንቀው ለእግዚአብሔር የተገዙ አባቶች ግን ማትረፋቸውን በዋቢነት አስረድተዋል፡፡ እነቅዱስ እንጦንስን እነጻድቁ ገብረ ክርስቶስን ለምኑልን፤ አማልዱን ብለን የምንጸልየውም ገንዘብን ንቀው ለእግዚአብሔር ስለተገዙ ነው፡፡ ‹‹ገንዘብን አሸንፉት፤ መቃብርን አትርሱት፤ ሰው ገንዘብ ቆጥሮ ሥልጣንም አግኝቶ ትቶት ይሔዳልና፤››ሲሉም በአጽንዖት መክረዋል፡፡

የዓለም መናኸርያ፣ የአፍሪቃ መዲና፣ የፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት አዲስ አበባ÷ ትንሽ ጉድፍ ጎልቶ የሚታይባት በመኾኑ አመራሯ ጥንቃቄን እንደሚጠይቅ በ፳፻፫ ዓ.ም. በንቡረ እድ አባ ገብረ ማርያም ገብረ ሥላሴ ዋና ሥራ አስኪያጅነት ሀገረ ስብከቱን በሊቀ ጳጳስነት የመሩት ብፁዕነታቸው ተናግረዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የተጣለባቸው አደራ፣ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩን እንዲረዱ እና አዲስ አበባን እንዲያስተካክሉ መኾኑን ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ አስታውቀዋል፡፡ አዲስ አበባ ብዙ ችግሮች ቢኖሩባትም ሕግ ፈጻሚዎች መኾን እንዳለብን በአጽንዖት ያመለከቱት ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ አበክረው እንዳሳሰቡት፣ እያንዳንዱ የራሱን ጉድፍ ካጸዳ አዲስ አበባ በአንድ ቀን ልትጸዳ ትችላለች፤ ኹሉም የየራሱን ድርሻ ከተወጣና በቅንነት ከሠራ ልትስተካከል ትችላለች፡፡

abune kewestosብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በቀድሞው የሸዋ ሀገረ ስብከት መዋቅር በአዲስ አበባ በስብከተ ወንጌል ለብዙ ጊዜ ሲያገለግሉ እንደነበር ብፁዕነታቸው አስታውሰዋል፡፡ በደብረ ሊባኖስ ገዳም በጸባቴነት፣ በደብረ ከርቤ ደብረ ጽጌ ማርያም እና በደብረ ብርሃን ሥላሴም በእልቅና ባገለገሉበት ወቅትም በርካታ ነገሮችን በማስተካከላቸው አኹን ፓትርያርኩን እንዲረዱ ሲመደቡ ፈተናውን ለመወጣት እንደሚያስችላቸው ገልጸዋል፡፡ ለዚኽም ‹‹እርሳቸው ፓትርያርኩን ሲረዱ እኛ [የሀ/ስብከቱ፣ የክፍላተ ከተማና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን አገልጋዮችና ሠራተኞች] ደግሞ ብፁዕነታቸውን መርዳት ይጠበቅብናል›› ብለዋል፡፡

‹‹በአሉባልታና በሐሰት አሸናፊ ለመኾን አይቻልም፤ ሀገረ ስብከቱን የሚያመሰቃቅለው አሉባልታና ሐሰት መወገዝ አለበት›› /የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኰንን/

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ከጥቅምት ፳፩ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. ጀምሮ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ኾነው የተመደቡበትን የሹመት ደብዳቤ በንባብ ያሰሙት የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኰንን የሀ/ስብከቱንና የክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ሓላፊዎችንና ሠራተኞችን በመወከል ባሰሙት ንግግር÷ ‹‹እኛ የቅዱስ ሲኖዶሱን ትእዛዝ እናከብራለን፤ በዚኹም መሠረት ብፁዕ አባታችንን ተቀብለናቸዋል›› ብለዋል፡፡

እንደ ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ አዲስ አበባ መልካም ነገሮች የሞሉባትን ያኽል ውስብስብ ነገሮችም አሉባት፤ የውስብስቡ ቋጠሮ ሊፈታና ሊስተካከል የሚችለውም ኹሉም የድርሻውን ሲወጣ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች በአሉባልታና በሐሰት አሸናፊ ለመኾን እንደሚሯሯጡ ያስታወቁት ሊቀ አእላፍ ቄስ በላይ፣ በሀ/ስብከቱ ነገሮችን የሚያመሰቃቅለው አሉባልታና ሐሰት መወገዝ እንዳለበት ከመግለጻቸውም ባሻገር ‹‹በክርስትና አሸናፊነት ሰላምና ቸርነት ማድረግ ነው፤ በጎውን ብናደርግ መልካሙን ብንሠራ መልካም ስም ማትረፍ እንችላለን፤›› ብለዋል፡፡ ለዚኽም ‹‹የብፁዕነታቸውን መመሪያ ሕግ በሚፈቅደው መሠረት ለማስፈጸምና በትእዛዙ መሠረት ለመጓዝ ቃል እንገባለን፤›› በማለት ንግግራቸውን አጠቃልለዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ከተገኙት ከአምስት መቶ ያላነሱ የገዳማትና አድባራት ተወካዮች መካከል የአራት አድባራት አስተዳዳሪዎች በሰጡት አስተያየት፣ ከብፁዕነታቸው መመሪያ እየተቀበሉ በመታዘዝና በመመካከር ተግተው ለመሥራትና የድርሻቸውን ለመወጣት ዝግጁ መኾናቸውን አስታውቀዋል፡፡

‹‹እንኳን ደስ ያለዎት ሳይኾን ያጽናዎት፤ ያልምዶት ማለት እፈልጋለኹ›› ያሉት የደብረ ይባቤ ቅዱስ ያሬድ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ሰላም ፀጋይ ግደይ፣ በሀገረ ስብከቱ አገልግሎታቸው ብዙ ሊቃነ ጳጳሳትና ሥራ አስኪያጆች ተመድበው ማለፋቸውን ገልጸው ‹‹ብፁዕ አባታችን ረዥም ጊዜ እንዲቆዩ እኛ ሰላማውያን መኾን ይገባናል፤ ምእመናን ከእኛ መልካም ነገር ይሻሉ፤ እኛም በጎና መልካም እንኹን›› ብለዋል፡፡ አዲስ አባቶች ተመድበው በመጡ ቁጥር የተወሰኑ ግለሰቦች ከሌላው ጎልተው የሚታዩበትና ለሌሎች ትኩረት የሚነፈገበት ኹኔታ መታረም እንደሚገባው ያሳሰቡትም ‹‹ትንሽ አለቃ፣ ትልቅ አለቃ የለም፤ ኹላችንም የቅዱስ ፓትርያርኩ እንደራሴዎች ነን፤ በቅዱስ ሲኖዶስ ነው የተሠየምነው›› በማለት ነው፡፡

‹‹ችግሮች እንዲወገዱ እኛም ጥረት እናደርጋለን›› ያሉት የታዕካ ነገሥት በኣታ ለማርያም ገዳም ሊቀ ሊቃውንት፣ ሀገረ ስብከቱም ለጉዳዮች አፋጣኝ መፍትሔ መስጠት እንዳለበት፣ ጉዳዮች በተገቢና በተቀላጠፈ አሠራር ከታዩ የነበረው የመልካም አስተዳደር ችግር እንደሚፈታተስፋቸውን ገልጸዋል፡፡ የቀበና ምሥራቀ ፀሐይ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ÷ የመናገር/የአነጋገር ችግር እንደሌለና የሔደውን መውቀስ የመጣውን ማወደስ ልማድ መኾኑን ተችተው፣ ‹‹ንግግር ከማብዛት ይልቅ ወደፊት በየሥራችን ብንመዘን፤ ይህን ብፁዕነትዎ በሒደት ይለዩት፤ አኹን ግን ብፁዕነታቸውን ተቀብለናልና በዚኹ ብናበቃ›› ሲሉ የአስተያየቱ ክፍለ ጊዜ ተጠቃሎ ወደ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ቃለ ምዕዳንና መመሪያ ሽግግር ተደርጓል፡፡

ተስማምቶና ተግባብቶ፣ ምስጢር ጠብቆና ምስጢራውያን ኾኖ መሥራት የብፁዕነታቸው ንግግር ዋነኛ ትኩረት ነው፡፡ ‹‹ኹሉን ማድረግ የሚችል አምላክ ይህችን ጊዜ ስለሰጠን እናመሰግነዋለን›› በማለት ንግግራቸውን የጀመሩት ብፁዕነታቸው፣ ‹‹ወደ ታላቁ ከተማ ተመድቤ ስመጣ ቅዱስ ፓትርያርኩን እንድረዳ ነው፤›› ካሉ በኋላ ዓላማቸው ሰላምን ማስፈንና ቤተ ክርስቲያንን ማስፋፋት እንደኾነ አስታውቀዋል፤ ኹላችንም የቤተ ክርስቲያን እንደራሴዎች ስለኾን ሕጉን ጠብቀን መጓዝ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ ብፁዕነታቸው አክለውም ‹‹ኹሉም የአካላችን ሕዋሳት ልዩ ልዩና የየራሳቸው ድርሻ አላቸው፤ ሕዋሳቱ አልታዘዝም ካሉ ግን ችግር ይፈጠራል፤ ተግባብተን ተደማምጠን መሥራት አለብን፤ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ምስጢር ነው፤ ምስጢር ጠብቀንና ምስጢራውያን ኾነን ልንጓዝ ይገባል፤ ሥራ በምንሠራበት ወቅት መሰናክል፣ መውደቅና መነሣት ይኖራል፤ ይህንንም በመተባበርና በመከባበር ማረም ይገባል፤ ከቅዱስ አባታችን መመሪያ እየተቀበልን እንሠራለን፤››ብለዋል፡፡

ወደፊት በሥራ መተያየትና መመዘን እንደሚገባ በቀበና መሥራቀ ፀሐይ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የተሰጠውን አስተያየት የተጋሩት ብፁዕነታቸው፣ ንግግራቸውን የቋጩት ለተሰብሳቢው ኹሉ መነጋገርያ ኾኖ በዋለው ተከታዩ ቃል ነበር – ‹‹የቅድሙ ተናጋሪ እንዳሉት ለወደፊቱ በሥራ መተያየት ያስፈልጋል፤ የሥራ መርሐ ግብር እናወጣለን፤ ኹሉንም በየድርሻውና በየደረጃው እናስተናግዳለን፤ በሥራው ሰዓት በቢሮ እንድትስተናገዱ እንጂ ወደ መኖርያዬ እንድትመጡብኝ አልፈልግም፡፡››

ከሰባት መቶ ያላነሱ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ የክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት እና የገዳማትና አድባራት የአስተዳደር ሓላፊዎችና ሠራተኞች በተገኙበት በዚኹ የአቀባበል መርሐ ግብር÷ ለሰባቱ ክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ሓላፊዎች የአስተያየት መስጫ መርሐ ግብር አለመያዙ ቅሬታ አሥነስቷል፡፡ በአንዳንድ ተሳታፊዎች ዘንድም ሀገረ ስብከቱ ለክፍለ ከተማ የሥልጣን መዋቅር ነፍጎታል ለሚሉት ትኩረት ቀጣይ ማሳያ ተደርጎ ተወስዷል፡፡

ለሀገረ ስብከቱ የገዘፈና የተመሰቃቀለ የመልካም አስተዳደር ዕጦት እንደ አንድ መንሥኤ የተወሰደው፣ የወረዳ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች በቃለ ዐዋዲው የተደነገገው ሥልጣን ተከፍሎ አለመሰጠትና ሥራቸውን አለመሥራታቸው እንደነበር ያስታወሱት ሓላፊዎቹ፣ የክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች ሥራቸውን ለመሥራት የሚያስችል ችግር ፈቺ አደረጃጀት ቢዘረጋም በአፈጻጸም/በተግባር ደረጃቸው ተጠብቆ የሥራ ድርሻቸውን የሚያከናወኑበት ሥልጣን አላቸው ለማለት አዳጋች እንደኾነ ገልጸዋል፡፡ ከሀገረ ስብከቱ ጋራ ሽሚያ በሚመስል አኳኋን የሠራተኛ ምደባ፣ ዝውውርና ዕድገት እንዲኹም ሌሎች መንፈሳዊና ልማታዊ ተግባራት ባለመናበብ ሲፈጸሙ የነበረበትን ኹኔታ በመገምገም፣ በሀገረ ስብከቱ እና በክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች መካከል ግልጽ የሥራ ክፍፍል የሚያስቀምጥ ጊዜያዊ መመሪያ በጋራ ስምምነት ተዘጋጅቶ እንደነበር ጠቅሰዋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ይኹንታና የአፈጻጸም አቅጣጫ የሰጠበትና የብዙኃኑን ካህናትና ምእመናን ተቀባይነት ያረጋገጠው የመዋቅር የአደረጃጀትና የአሠራር ጥናት በሥራ ላይ እስኪውል ድረስ በሀገረ ስብከቱና በክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶቹ የተስማሙበት ይኸው ጊዜያዊ መመሪያእንዲሠራበት ተደጋጋሚ ውሳኔ ቢተላለፍም ባለመተግበሩ በአኹኑ ወቅት በክፍላተ ከተማ /ቤቶቹ ተሟሙቶ ለሚታየው የአሠራር ኹኔታበመንሥኤነት ተቀምጧል፡፡

ኹሉንም በየድርሻውና በየደረጃው በማስተናገድ ሰላምን ለማስፈንና ቤተ ክርስቲያንን ለማስፋፋት ቃል የገቡት ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ÷ በሀገረ ስብከቱ እና በክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች መካከል ተፈጥሮ ለቆየው የአሠራር ክፍተት ተገቢውን ትኩረት ከመስጠት ባሻገር ለችግሩ ዘለቄታዊ መፍትሔ ለሚያስገኘውና ወደ ትግበራ ምዕራፍ መሸጋገር ሲገባው በእጅጉ የዘገየውን የመዋቅር የአደረጃጀትና የአሠራር ጥናት አፈጻጸም በመምራት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትን የተቋማዊ ለውጥ አርኣያ እንደሚያደርጉት ተስፋ አለን፡፡ የኾኑ ግለሰብ ሓላፊዎች ከቦታ ወደ ቦታ መዘዋወር ብቻ ሳይኾን በጥናት የተደገፈውና የብዙኃኑን ተቀባይነት ያረጋገጠው የተቋማዊ ለውጥ እንደሚያስፈልግ ተጠቁሟል፡፡

ምንጭ ፡-ሐራ ተዋህዶ

 

የአዲስ አበባ አስተዳደር ለህዝብ ሰላምና ደህንነት ሲባል በሰማያዊ ፓርቲ ላይ እርምጃ እወስዳለሁ ማለቱ ተገለፀ

  • “ማስጠንቀቂያውን እንደ ቁም ነገር አንቆጥረውም” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት

    • “ስርዓቱ ምን ያህል ዝቅጠት ውስጥ እንደገባ ያሳያል” አቶ ግርማ በቀለ

    የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ህዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም ሰማያዊ ፓርቲ ያስተባበረው የ9ኙ ፓርቲዎች የአደባባይ ህዝባዊ ስብሰባ ፀረ ህገ መንግስት በመሆኑና ነዋሪዎችን ሰላምና ፀጥታ በማወኩ በቀጣይ ተመሳሳይ እንቅስቃሴ ካደረገ ለህዝብ ሰላምና ደህንነት ሲባል እርምጃ እወስዳለሁ ሲል አስጠነቀቀ፡፡

    አስተዳደሩ ትናንት ህዳር 11 ቀን 2007 ዓ.ም በጻፈው ደብዳቤ፤ ህዳር 6 ቀን “ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ” በሚል በሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ለህዝብ የተሰራጨው በራሪ ወረቀት ህገ ወጥ መሆኑን፣ ህዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም በኢንጅነር ይልቃል ጌትነት መሪነት ሊደረግ የነበረው አደባባይ ስብሰባ ህገ ወጥ እንደነበርና በወቅቱ የስብሰባው ተሳታፊዎች ከፖሊስ ጋር ግብ ግብ ከመግጠማቸውም በተጨማሪ የአካባቢውን ህዝብ ሰላምና ፀጥታ አውከዋል ሲል ከሷል፡፡ አስተዳደሩ አክሎም ፓርቲው የአደባባይ ብጥብጥና ሁከት በመፍጠሩ እርምጃ እወስዳሉ ሲል ማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ልኳል፡፡

    በሌላ በኩል ሰማያዊ ፓርቲ በቀን ህዳር 5 ቀን 2007 ዓ.ም ለአስተዳደሩ የእውቅና ደብዳቤ ያስገባ መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን የሰማያዊ ፓርቲና የትብብሩ አመራሮች አስተዳደሩ የላከው ደብዳቤ ከገዥው ፓርቲ ፍርሃት የመነጨ በመሆኑ ከእንቅስቃሴያቸው እንደማይገታቸው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገርናቸው የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብርና የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ደብዳቤው ስርዓቱ የደረሰበትን መጠነ ሰፊ የፍርሃት ደረጃና ትግሉን ይበልጥ አጠናክረን መቀጠል እንዳለብን የሚያሳይ ነው ሲሉ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

    pressreleaseማስጠንቀቂው የደረሰው ሰማያዊ ፓርቲና የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ‹‹የረዥም ጊዜ የመንግስት ታሪክ ባላት አገር የከተማ አስተዳደር ነኝ ያለ አካል እንዲህ አይነት ደብዳቤ መጻፉ ኢትዮጵያ ምን ያህል ውድቀት እንደገጠማትና እኛም እንደ ህዝብ የውርደት ካባ መከናነባችንን በግልጽ የሚያሳይ ነው፡፡ እንደ ሰማያዊ አሊያም የትብብሩ ሊቀመንበርነት ሳይሆን እንደ አንድ ይህን ያህል ውርደት እንደገጠማት አገር ዜጋ ሀፍረት ይሰማኛል፡፡›› ሲሉ አስተዳደሩ የላከው ደብዳቤ ላይ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

    ማስጠንቀቂያው በቀጣይ የፓርቲውም ሆነ የትብብሩ እንቅስቃሴ ላይ የሚያመጣው ችግር ካለ በሚል ለኢንጅነር ይልቃል ላነሳነላቸው ጥያቄም ‹‹ደብዳቤው የኢህአዴግ ፍርሃት ገደብ መልቀቁንና ትግሉም ይበልጥ መጠናከር እንዳለበት የሚያሳይ ነው፡፡ ኢህአዴግ ሰላማዊ ህዝባዊ እንቅስቃሴን ብቻ ሳይሆን የራሱን ጥላም አለማመን ደረጃ ላይ መድረሱን ያሳያል፡፡ እኛ ይህን የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ እንደቁም ነገር አንቆጥረውም፡፡ ይበልጡንም ለትግሉ በተጠናከረ መንገድ እንድንነሳሳ ይገፋፋናል›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡

    በተመሳሳይ የትብብሩ ፀሐፊና የኦሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ሊቀመንበር የሆኑት አቶ ግርማ በቀለ ‹‹ማስጠንቀቂያው ትብብሩ በየሳምንቱ ያቀዳቸውን መርሃ ግብሮች ለማደናቀፍ ያለመ ነው፡፡ ከአንድ የመንግስት መስሪያ ቤት እንዲህ አይነት አሳፋሪ ደብዳቤ መጻፉ ስርዓቱ ምን ያህል ዝግጠት ውስጥ እንደገባ ያሳያል፡፡ ሆኖም ማስጠንቀቂያው ከእንቅስቃሴያችን አይገታንም፡፡ እንዲያውም ለዚህ የስርዓቱ ዝቅጠት የሚመጥን ስልት ነድፈን በጋራ እንድንሰራ ያደርገናል፡፡›› ማለታቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

አንድነት ፓርቲ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለህሊና እስረኞች” የሚል ዘመቻ ማዘጋጀቱን ይፋ አደረገ

udjአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ (አንድነት) ፓርቲ ከህዳር 14 እስከ 20 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚቆይ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለህሊና እስረኞች” የሚል የሶሻል ሚዲያ ዘመቻ አዘጋጅቷል። በዚህ ዘመቻ ለመንግስት ባለስልጣናት፣ ለታዋቂ ግለሰቦች፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተቋማትና ለልዩ ልዩ የሚዲያ ድርጅቶች በኢንተርኔትና በሶሻል ሚዲያ በኩል መልዕክት በመላክ በሀገራችን ያሉት የፖለቲካ እስረኞች ሁኔታና አያያዝ በተመለከተ መረጃ በመስጠት ተገቢ የሆነ አያያዝ እንዲኖራቸው፤ ከእስር እንዲፈቱ፣ በሰላማዊ መንገድ የሚታገሉትን ማሰርና ማዋከብ እንዲቆም በመንግስት ላይ አዎንታዊ ተፅዕኖ ለመፍጠር ያለመ እንደሆነ ፓርቲው አስታውቋል። በዚህ ዘመቻ ላይ ሁሉም የዘመቻው ደጋፊና በሀገሪቱ ዴሞክራሲያው ስርዓት እንዲመሰረትና የዜጎች ሰብዓዊ መብት እንዲከበር የሚሹ ሁሉ ከላይ ለተጠቀሱት ግልሰቦችና ተቋማትን ጨምሮ ሚሊዮኖች ለሚያውቁትና ተፅዕኖ ማሳደር ይችላል ለሚሉት ሰው ሁሉ መልዕክት በኢንተርኔትና በሶሻል ሚዲያ በመላክ ድምፃቸውን ያሰሙ ዘንድ ዛሬ ህዳር 11 ቀን 2007 ዓ.ም. አዲስ አበባ በሚገኘው ዋና ጽህፈት ቤቱ በሰጠው መግለጫ ጥሪውን አቅርቧል፡፡

ፓርቲው ከዚህ በፊት ከህዝቢ ከፍተኛ ድፍ ያስገኘለትን “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” እና “…ለመሬት ባለቤትነት” የሚሉ የተለያዩ ህዝባዊ ስብሰባዎችን እና የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎችን አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች ማድረጉ ይታወቃል፡፡  የዛሬውን ሙሉ ዝርዝር መግለጫ ከታች ይመልከቱ፡፡

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)
UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)

ምርጫ ሲባል አማራጭ ሳያሳጡ መሆን ይኖርበታል!!!
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

በሀገራችን ኢትዮጵያ ለአምስተኛ ጊዜ ሀገራዊ ምርጫ እንደሚደረግ በመንግስት በኩል በከፍተኛ ደረጃ የፕሮፓጋንዳ መሳሪያ ሆኖ እያገለገለ ይገኛል፡፡ ነገር ግን ከዚህ በፊት የተከናወኑት አራት ምርጫዎች ያየን እንደሆነ በሀገራችን የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት ግንባታ ወደፊት ሊወስዱ እንዳልቻሉ እሙን ነው፡፡ ይህም ሆኖ የኢትዮጵያ ህዝብ ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ያለውን ፍላጎት በተለያየ መንገድ ሲገልፅ ቆይቷል፡፡ በተቃራኒው መንግስትና ገዢው ፓርቲ በፍፁም መለየት በሚያስቸግር ሁኔታ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታ ሆነው ተቀናጅተው ለአንድ ለአውራ ፓርቲ ግንባታ እየሰሩ እንደሆነ ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ ይህ የመንግሥትና የገዢው ፓርቲ ተግባር ምርጫን ያለ አማራጭ እንዲሆነ እያደረገው እንደሆነ ለመረዳት አስቸጋሪ አይደለም፡፡

በቅርቡ የአንድነት ፓርቲ አባላት ላይ በሁሉም የሀገሪቱ ክፍሎች ዘመቻ በሚባል ደረጃ እየተካሄደ ያለው አፈናና እስር፤ ከዚህም ባሻገር ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከህዝብ ጋር እንዳይገናኙ ክልከላውና ወከባው ተጠናከሮ መቀጠሉ፤ ገዥው ቡድን የምር ተቃዋሚ ፓርቲ ናቸው ብሎ የሚያስባቸው ፓርቲዎች ለማዳከምና ከምርጫው ውድድር ውጪ ለማድረግ ያለው ቁርጥ አቋም የሚያሳይ ነው። ይህ የገዢው ቡድን አካሄድ በሀገራችን ዴሞክራሲያዊ የሆነ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት እንዲመሰረት ፍላጎት እንደሌለው በደንብ የሚያረጋግጥ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ህዝብ ነፃና ፍትሐዊ በሆነ ምርጫ የሚፈልገውን ፓርቲ እንዲመርጥ እድል ሊጠሰው ሲገባ በሥርዓቱ በእኩል ነፃና ፍትሐዊ ምርጫ እንዳያካሄድ የተለያዩ ጫናዎች እየተደረጉበት የሚካሄዱት ምርጫዎች ሁሉ ትርጉም አልባ እየሆኑ ይገኛሉ፡፡ ይህ የገዢው ቡድን ሀላፊነት የጎደለው እንቅስቃሴ በተግባር የሚደግፈው ከሠላማዊ ትግል ይልቅ የኃይልና የአመፅ መንገድ እንደሚሆን የተረዳ አይመስልም፤ ይልቁንም በሠላማዊ መንገድ እየተንቀሳቀሱ ያሉትን ፓርቲዎች ወደ አላስፈላጊ መስመር በመግፋት ሀገራችን ወደ ብጥብጥና ወደ እርስ በእርስ ጦርነት እንድትገባ የሚያደርግ ሁኔታ እየተከተለ ነው የሚገኘው። በሥልጣን ላይ ያሉት ወገኖች ይህ አሳሳቢ ሁኔታ በትክክል እንዳያዩ ጭፍን የሥልጣን ጥም ጋርዷቸዋል፡፡

በቀጣይ ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚደረገው ምርጫም በመንግስት በኩል የመድበለ ፓርቲን ስርዓት ለማጎልበት ምንም ዓይነት ምቹ ሁኔታ እንዳይፈጠር ከአሁኑ የተለያዩ እንቅፋቶችን በመደርደር ላይ ነው። የአንድነት አመራሮችና አባላት በግፍ በማሰር ፓርቲው በምርጫው እንዳይሳተፍ ከፍተኛ የሆነ ጫና እየተደረገ ቢሆንም አንድነት ፓርቲ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ሆኖ ህዝቡ እንዲሳተፍ በመቀስቀስና በማበረታታት የተዘጋውን የዴሞክራሲ በር በምርጫ ካርዱ ሊያስከፍት እንደሚችል ከፍተኛ እምነት አለው፡፡

ከሁሉም በላይ ደግሞ እንደከዚህ ቀደሙ ኢህአዴግ ደጋፊዎቼ የሚላቸውን ብቻ በመራጭነት አስመዝግቦ ምርጫ የሚያደርግበት ሁኔታ ማብቃት ይኖርበታል ብለን እናምናለን፡፡ ይህ ተግባራዊ እንዲሆን በእኛ በኩል ደጋፊዎቻችን በመራጭነት እንዲመዘገቡ ከማበረታት ጀምሮ የህዝብና የፓርቲ ታዛቢ በመሆን የምርጫ ሂደቱን በሙሉ በንቃት እንዲከታተል እንዲሳተፍ የበኩላችንን ጥረት በማድረግ የ2007 ሀገራዊ ምርጫ ከጅማሮው ህዝባዊ እንዲሆን ትግላችንን እንቀጥላለን፡፡ ይህ እርምጃም ህዝቡን የስልጣን ባለቤት ለማድረግ ወሳኝ እርምጃ ነው የሚል እምነት አለን፡፡

የኢትዮጵያ ህዝብ በገዥው ቡድን መልካም ፍቃድ ወይም በማንኛውም ውጫዊ ተፅዕኖ የፖለቲካ ምህዳሩን እንደማይሰፋ ሊገነዘብ ይገባል። ምህዳሩ የሚሰፋውና ትክክለኛ የሆነ ዴሞክራሲያዊ ለውጥ የሚኖረው ህዝቡ በጠቅላላ ከፍርሀት ቆፈን ተላቆ በሙሉ ልብ ለመብቱ ሲቆም፣ ለፓርቲዎች ተገቢው ድጋፍ ሲሰጥ፤ ከፍ ሲልም ወደ ትግሉ ሲቀላቀል መሆኑ መገንዘብ ያስፈልጋል።

በዚህ አጋጣሚ አንድነት ፓርቲ ከህዳር 14 እስከ 20 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚቆይ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለህሊና እስረኞች” የሚል የሶሻል ሚዲያ ዘመቻ አዘጋጅቷል። በዚህ ዘመቻ ለመንግስት ባለስልጣናት፣ ለታዋቂ ግለሰቦች፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተቋማትና ለልዩ ልዩ የሚዲያ ድርጅቶች በኢንተርኔትና በሶሻል ሚዲያ በእኩል መልዕክት በመላክ በሀገራችን ያሉት የፖለቲካ እስረኞች ሁኔታና አያያዝ በተመለከተ መረጃ በመስጠት ተገቢ የሆነ አያያዝ እንዲኖራቸው፤ ከእስር እንዲፈቱ፣ በሰላማዊ መንገድ የሚታሉትን ማሰርና ማዋከብ እንዲቆም በመንግስት ላይ አዎንታዊ ተፅዕኖ ለመፍጠር ያለመ ነው። በዚህ ዘመቻ ላይ ሚሊዮኖች ለሚያውቁትና ተፅዕኖ ማሳደር ይችላል ለሚሉት ሰው ሁሉ መልዕክት በኢተርኔትና በሶሻል ሚዲያ በመላክ ድምፃቸውን ያሰሙ ዘንድ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
ህዳር 11 ቀን 2007 ዓ.ም.
አዲስ አበባ

………..//………//…………

የሴቶች ጉዳይ ይመለከተናል የምትሉ ከወዴት ናችሁ? የእህታችን የሐና ጉዳይ የሁላችንም ጉዳይ ነው!!

ብስራት ወልደሚካኤል

በቅርቡ በመዲናችን አዲስ አበባ አንዲት የ16 ዓመት ባለ ብዙ ተስፋዋ የ10ኛ ክፍል ተማሪ የነበረችው  እህታችን ሐና ላላንጎ ለክፉ ድርጊታቸው ቃላት በማይገልፃቸው 5 ጨካኝ ወንዶች ከሰብዓዊነት በራቁ አረመኔ ወንዶች ያውም በቀን ከትምህርት ቤት ወደ መኖሪያ ቤቷ በተሳፈረችበት ታክሲ ስትሄድ  ሾፌር፣ረዳትና ሌሎች ግብር አበሮቻቸው ታግታ ለቀናት በመፈራረቅ ተደፍራ ህይወቷ አልፏል፡፡ ዜናው እጅግ ዘግናኝ ከመሆኑ የተነሳ ለመግለፅ ያስቸግራል፡፡ የልጆቹን ድርጊት አንዳንዶቹ ከሌሎች የቤትና የዱር እንሰሳ ድርጊት ጋር ሊያይዙ ይሞክራሉ፡፡ እውነታው ግን የትኛውም እንሰሳ ምስያውን ያውም ተስፈኛ የስንት ታናሽ እህቱን፣ ልጁን ወይንም ወገኑን በጅምላ አግቶና አስገድዶ ደፍሮ የሚገል ፍጡር የለም፡፡

ሐና ላይ  አረመኔዎች የፈፀሙት ድርጊት በምንም የሚገለፅ አይደለም፡፡ እጅግ ልብን የሚናካና አሳዛኛ ተግባር ነው፡፡  የድርጊቱ ፈፃሚዎችም የማያዳግም እርምጃ ወይም ቅጣት  በአደባባይ ሊያገኙ ይገባል፡፡ ምንም እንኳ ዛሬ ያቺ ተስፈኛ ለግላጋ ወጣት በህይወት ኖራ የአረመኔዎችን ቅጣት በዓይኗ ለማየት ባትታደልም  ለሌሎች አረመኔዎች ማስተማሪያ እንዲሆን እና ሌሎች እህቶቻችንም ቀና ብለው በሀገራቸው በኩራትና በነፃነት ይንቀሳቀሱ ዘንድ ለሐና ተብሎ የሚሰጠው ፍትህ የሁሉም ነው ብዬ አምናለሁ፡፡

በርግጥ ኢትዮጵያ ውስጥ ፍትህ በሌለበት ፍትህ መጠየቅ ህልም ቢሆንም፤ እነኚህ የድርጊቱ ፈፃሚ አረመኔዎች ግን በምንም መልኩ ተገቢውን ለሰሩት አሰናዋሪ ጭካኔ ለተሞላበት ተግባር ተገቢውን ቅጣት ሊያገኙ ይገባል የሚል እምነት አለኝ፡፡

እዚህ ላይ በጣም የገረመኝ  ጥያቄ የፈጠረብኝ ነገር አለ፡፡ ይኸውም በኢትዮጵያ ያሉ የሲቪክ ተቋማት በተለይም የሰቶች ጉዳይ ቅንጅት፣ ማኀበራት፣ …የሚባሉ ተቋማት ባለፈው 2004 ዓ.ም. የበረራ አስተናጋጇ (ሆስተሷ) አበራሽ ኃይላይ ላይ በቀድሞ ባለቤቷ ተወሰደ በተባለው የበቀል እርምጃ የአካል መጉደል ደርሶባታል በሚል ከፍተኛ ተቃውሞ ከማድረግ በተጨማሪ በቅንጡ ሸራተን አዲስ ሆቴል ተደጋጋሚ መግለጫ እስከመስጠት ደርሰው እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ ለዚህም እኔው ራሴ ከዚህ ቀደም በምሰራበት ጋዜጣ ለጉዳዩ ከ2 ጊዜ ያላነሰ የዜና ሽፋን በመስጠት በመግለጫዎቹና ተቃውሞዎቹ ላይ ልክ እንደሌሎቹ የሙያ አጋሮች በተደረገ ጥሪ ተገኝቼ የታዘብኩት እውነታ ነበር፤ከሙያ በተጨማሪ በግሌም ጥቃቶችን የምቃም ነኝና፡፡ ያኔም ሆነ አሁን በካሚላት፣ በአበራሽ ላይም ሆነ በማንኛውም ሴትም ሆነ ወንድ ላይ በአጠቃላይ በማንኛውም የሰው ልጅ ላይ የሚፈፀም ኢ-ሰብዓዊ ድርጊትን አጥብቄ የምቃወመው ተግባር ነው፡፡ ይሁን እንጂ በተማሪ ሐና ላይ በተፈፀመው አሰቃቂ ተግባር ያኔ ለነ አበራ ኃይላይ ይደረግ የነበረው እንቅስቃሴ ዛሬ የት ሄደ? ለምን?

ሀሀሀእኔ እስከሚገባኝ ሐናም አበራሽም ሆነች ካሚላት ሁሉም ሴቶች፣ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ሁሉም ወገኖቻችን ናቸው፡፡ ስለዚህ ሌሎች ተቋማትም ሆኑ ሴቶች ላይ ትኩረት አድርገው የሚሰሩ ተቋማት ከሐና ጎን ሲቆሙ አላየሁም፤ ወይም አልተገነዘብኩም፤ ለምን? ሁሉም ላይ የሚፈፀም ጥቃት እኩል ድጋፍ ሊደረግ ይገባል፤ ቢቻል ያኔ መግለጫ ለመስጠት ጋዜጠኞችን ሲጨቀጭቁ የነበሩ ይመለከተናል የሚሉ  የሴቶች ማኀበራትና ተቋማት ዛሬ ከወዴት ናችሁ? ማንኛውም ሴት ላይ የሚፈፀም ጥቃት በእኩል ትኩረት በመስጠት ከጎናቸው መሆናችንን ልናሳይ የሚገባ ይመሰለኛል፡፡

በርግጥ ይህን ስል ጉዳዩ ወንዶችን አይመለከትም ማለቴ አይደለም፤ በደንብ ይመለከተናል፡፡ ምክንያቱም ሰው በመሆናችን ብቻ ሴትም ሆነ ወንድ ላይ የሚፈፀም ጥቃት የሰው ልጅ ላይ በመሆኑ ይመለከተናል፡፡ ግዴታችንም ነው፡፡ ከዛ በተጨማሪ እስኪ ማነው እናቱን የሚጠላ? ማነው እህቱ ላይ ሌላ ሰው የዚህን ዓይነት አሰቃቂ ድርጊት እንዲፈፀም የሚፈቅድ? እስኪ ማነው ልጁ ላይ እንዲህ እንዲፈፀም የሚፈቅድና ቢፈፀም ደስተኛ የሚሆን? ማንም ያለ አይመስለኛም፤ሊኖርም አይገባም፡፡ ጉዳዩ የሁላችንም ነው የምላው ለዚህ ነው፡፡

በሀገሪቱ ተመሳሳይ ድርጊት ከእንግዲህ እንዳይፈፀም  ተገቢውን ፍትህ ከመስጠት በተጨማሪ ለሌሎች እህቶቻችን ቢያንስ ድርጊቱን እናወግዛለን ፣ ከጎናችሁ ነን፤ ተገቢው ፍትህ መሰጠት አለበት የሚሉ የተቃውሞ ድምፆች በጋራ በወድሞቻችን እና እህቶቻችን ሊዘጋጅ የሚገባ ይመስለኛል፡፡ አለበለዚያ ድርጊቱ ነገም ሊቀጥል ይችላል፡፡ አሁንም ይሄ የሐናም ሆነ የነ ካሚላትና አበራሽ ላይ የተፈፀሙ ድርጊቶች አዲስ አበባ በመሆናቸው ለአደባባይ በቁ እንጂ…በየ ክልል ከተሞችና በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ከተጠቀሱት የሚልቅ ድርጊቶች እንደሚፈፀሙ ይታመናል፡፡ ይህ ሁሉ እንዲቀር ሴት ወንድ በሚል የፖለቲካ ፍጆታ መድረክ ከማድመቅ በዘለለ በእውነት ለሁሉም ልንደርስላቸው ይገባል፡፡

ንፁሃንን አሸባሪ እያለ በግፍ የሚያስረውና የሚያሰቃየው መንግስትስ የህፃናትና ተማሪዎችን ደህንነት ያውም በአዲስ አበባ እንዴት መታደግ አቃተው; ስንቱን የግለሰብ ምስጢር እየበረበረ የሚከታተል ደህንነትስና ፖሊስስ ንፁሃንን ከማደን ተላቆ ወንጀለኞችን በማደን እና ለፍርድ ከማቅረብ ረገደ እንዴት ነው?

ሐና…ፈጣሪ ነፍስሽን በገነት ያኖረው ዘንድ ተመኘሁ…

አሁንም…ፍትህ ለሐና ! ፍትህ ለሐና!!….ፍትህ ለሐና…!!