ኣሸጎዳ የንፋስ መብራት ማመንጫ ሃይል ዲናሞ በመቃጠሉ ምክንያት ከጥቅም ውጭ ሆነ
በመቀሌ ምስራቃዊ ክፍል የሚገኝ የኣሸጎዳ በንፋስ የሚሰራ ኤለክትሪክ ማመንጫ ሃይል በዲናሞ መቃጠል ምክንያት ከስራ ውጭ መሆኑ ታውቋል። የተቃጠለው ዲናሞ 150 ሜጋዋት የማመንጨት ኣቅም የነበረው ሲሆን ምክንያቱ ባልታወቀ ምክንያት በመቃጠሉ ሃይል የማመንጨት ኣቅሙ ሙሉ በሙሉ ማቆሙ ታውቋል።
የተቃጠለው ዲናሞ ቅያሪ በሃገር ውስጥ እንደሌለና ከፈረንሳይ ሃገር እንደሚመጣ ታውቋል። የህወሓት የ40 ዓመት የልደት በዓል እንደ ታላቅ ውጤትና ማጣፈጫ ተደርጎ ሊወሰደ ታስቦ የነበረ ሲሆን ባልታወቀ ምክንያት መቃጠሉ በክልሉ ከፍተኛ ባለስልጣናት ከፍተኛ ቁጣና ድንጋጤ መፍጠሩ ታውቋል።
የትግራይ ባለስልጣናት እንደ ግዝያዊ መፍትሄ ኣድርገው የወሰዱት የየካቲት በዓል እስኪያልፍ ከፈርንሳይ በክራይ እንዲመጣና ብልሸት እንዳልደረሰው ኣስመስሎ በማሳለፍ በዓሉ ከተጠናቀቀ በሗላ ዲናሞው ወደ ፈረንስይ እንዲመለስ የሚል ትእዛዝ ኣስተላልፈዋል።
የህወሓት ባለስልጣናት የየካቲት በዓል ታዳሚዎች ኣሳፋሪ በሆነ ድራማ ኣጭበርብረው ለመመልስ ከፈረንሳይ ዲናሞ ተከራይተው ካሳዩሗቹ በሗላ ተመልሰው ወደ መጣበት ይመልሱታል። ህወሓት የዲናሞው መቃጠል ለየካቲት በዓል ማክበርያ ካወጣችው 1 ቢልዮን ብር ወጪ የምታወጣው ተጨማሪ ግዙፍ ብር ይሆናል።
ሰማያዊ ፓርቲ ጽህፈት ቤቱን እንዲለቅ ክስ ቀረበበት
• በወር 40 ሺህ ብር ኪራይና 250,000 ብር ለ‹‹ኪሳራ›› እንዲከፍል ተጠይቋል
ሰማያዊ ፓርቲ የካ ክ/ከተማ በቀድሞው መጠሪያው ቀበሌ 15 እንዲሁም በአዲሱ መጠሪያው ወረዳ 6 የቤት ቁጥር 460 የሆነውን ጽ/ቤቱን 25000 ሺህ ብር ቅጣት ከፍሎ እንዲለቅ በአከራዮቹ በኩል ክስ ቀረበበት፡፡ በከሳሽ እነ አቶ ሚስጥረ ሽበሽ የተመሰረተው ክስ ‹‹ቤቱን ለቀው ለማስረከብ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው …በወር ብር 40,000 (አርባ ሺህ ብር) ሒሳብ ከጥር 16 ቀን 2007 ጀምሮ ቤቱን ለቀው እስከሚያስረክቡ ድረስ ባልተነጣጠለ ኃላፊነት እንዲከፍሉን›› ያሉ ሲሆን ‹‹ከሳሽ ቤቱን ለማደስ ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር በገባነው ውል መሰረት የደረሰብንን 250 ሺህ ብር ኪሳራ እንዲተኩልን›› ሲሉ ከሰዋል፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት በሚፈልግባቸው ጊዜያት የቀበሌ ካድሬዎች አከራዮቹና ደላሎቹ ለፓርቲው እንዳያከራዩ ሲያስጠነቅቁ የቆዩ ሲሆን በተለይ በጥር ወር 2007 ዓ.ም ይህ ጽ/ቤት እንዳይከራይ ግፊት የማድረጉ ተግባር ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡
ድብደባ ከተፈጸመባቸው ሁለት የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች መካከል የአንደኛው ሕይወቱ አለፈ
ታምሩ ጽጌ
–ተጠርጣሪዎቹ በቁጥጥር ሥር ውለው በምርመራ ላይ ናቸው
በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አካባቢ በሚገኘው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ፋኩልቲ፣ ሁለት ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲው የጥበቃ ሠራተኛ ድብደባ ተፈጽሞባቸው አንደኛው ሕይወቱ ማለፉ ተረጋገጠ፡፡
ጥር 23 ቀን 2007 ዓ.ም. የግማሽ ዓመት ፈተናቸውን ካጠናቀቁት የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች መካከል፣ ሙሉቀን ከበደና ታምራት አባተ የተባሉ ተማሪዎች በዕለቱ ድብደባ እንደተፈጸመባቸው ታውቋል፡፡ ተማሪዎቹ ፈተናቸውን እንዳጠናቀቁ ከግቢ ወጥተው ሲዝናኑ ካመሹ በኋላ ወደ ማደሪያ ክፍላቸው ሲመለሱ፣ ፀደቀ አድማሱ ከሚባለው ተጠርጣሪ የጥበቃ ሠራተኛ ጋር መጋጨታቸውን ከፖሊስ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
ተማሪዎቹ ወደ ዩኒቨርሲቲው ግቢ ሊገቡ ሲሉ ተጠርጣሪው እንዲቆሙ ሲያደርጋቸው ተማሪ መሆናቸውን የሚያረጋግጡበትን መታወቂያ ቢያሳዩም፣ ከተጠርጣሪው ጋር ሊግባቡ ባለመቻላቸው ድብድቡ መጀመሩ ታውቋል፡፡ ተጠርጣሪው በወቅቱ ይዞት በነበረው የእንጨት ዱላ ደጋግሞ ሲደበድባቸው የተመለከተ ሾፌር፣ ሌሎች የተኙ ጥበቃዎችን በማስነሳቱ የተፈጠረው ድብድብ የቆመ ቢሆንም፣ ተማሪዎቹ በደረሰባቸው ድብደባ ተጎድተው ስለነበር በአቅራቢያቸው በሚገኘው ጥሩነሽ ቤጂንግ ጠቅላላ ሆስፒታል መወሰዳቸውም ተጠቁሟል፡፡
ታምራት አባተ የተባለው ተማሪ በጥሩነሽ ቤጂንግ ጠቅላላ ሆስፒታል በተደረገለት ሕክምና የተረፈ ቢሆንም፣ የደረሰበት ድብደባ ከባድ በመሆኑ ለተጨማሪ ሕክምና ሪፈር የተደረገው ተማሪ ሙሉቀን፣ በጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በሕክምና ላይ እያለ ጥር 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ሕይወቱ ማለፉ ታውቋል፡፡ ፖሊስ በድብደባው ተሳትፈዋል በማለት በቁጥጥር ሥር ያዋላቸውን ተጠርጣሪ የዩኒቨርሲቲውን የጥበቃ ሠራተኞችን ፍርድ ቤት አቅርቦ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ በመጠየቅ በምርምራ ላይ መሆኑን ሪፖርተር ጋዜጣ ዘግቧል፡፡
አያት የመኖሪያ ቤቶች ስራ ድርጅት በሊዝ ወስዶ መሠረቱ ወጥቶ ያለቀ ቦታ ለኢሊሌ ሆቴል ተወሰነ
ታምሩ ጽጌ
–መሠረቱን ለማውጣት ከ3.7 ሚሊዮን ብር በላይ እንደወጣበት ተገልጿል
በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ካዛንቺስ ከኢንተር ኮንቲኔንታል ሆቴል ወረድ ብሎ የሚገኘውን፣ ከቂርቆስ ክፍለ ከተማ አስተዳደር አያት አክሲዮን ማኅበር በሊዝ የወሰደውና መሠረቱ ወጥቶ ያለቀ ቦታ፣ ፊት ለፊቱ ለሚገኘው ኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል በፍርድ ቤት ውሳኔ ተሰጠ፡፡
ከ20 በላይ ክሶች ተመሥርቶባቸውና ጥፋተኛ ተብለው 11 ዓመታት የእስርና የገንዘብ ቅጣት ተወስኖባቸው በእስር ላይ የሚገኙት አቶ አያሌው ተሰማ ከፍተኛ ባለድርሻ የሆኑበት አያት አክሲዮን ማኅበር፣ ቦታውን በሊዝ የወሰደው ከአራት ዓመታት በፊት ነበር፡፡ ስፋቱም 1,696 ካሬ ሜትር ነው፡፡ አክሲዮን ማኅበሩ ቦታውን በሊዝ የወሰደው ባለ16 ፎቅ ለመኖሪያና ለቅይጥ የንግድ ሥራ ሕንፃ ለመገንባት ነበር፡፡
የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ቦታውን በሊዝ ያስተላለፈው ለልማት መሆኑን በመግለጽ፣ አያት አክሲዮን ማኅበር ምንም ዓይነት ግንባታ አላካሄደም በማለት በሊዝ አዋጁ የተፈቀደው የመጠበቂያ ጊዜ እንዳለፈ አስታውቆ ካርታውን ማምከኑም ተጠቁሟል፡፡
የኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል ባለቤት አቶ ገምሹ በየነ ቦታው ከሆቴላቸው ፊት ለፊት በቅርበት ላይ መሆኑን በመግለጽ፣ መሰጠት ያለበት ለመኪና ማቆሚያ (ፓርኪንግ) ለእሳቸው መሆኑን ለክፍለ ከተማው በማመልከታቸው ጉዳዩ ወደ ፍርድ ቤት ማምራቱም ተገልጿል፡፡ የሆቴሉን ባለቤት አቶ ገምሹንና ቂርቆስ ክፍለ ከተማ አስተዳደርን በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ፍትሐ ብሔር ችሎት የከሰሰው አያት አክሲዮን ማኅበር፣ ለመሠረት ማውጫ ከ3.7 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንዳወጣበትና ካርታው ከመምከኑ በፊት ሊነገረው ሲገባ፣ በድብቅ ማምከኑ ተገቢ እንዳልሆነ በመግለጽ ሲከራከር ከርሟል፡፡
ጉዳዩን ሲመረምር የከረመው ፍርድ ቤቱ ማኅበሩ ቦታውን በተነጠቀ ወይም ካርታው በመከነ በ15 ቀናት ውስጥ ለአስተዳደሩ የቦታ አመላለስ ይግባኝ ሰሚ ጉባዔ ማቅረብ እንደነበረበት አስታውቋል፡፡ ያንን ሳያደርግ ወደ ፍርድ ቤት መምጣቱ (ክስ መመሥረቱ) ሕጉን ያከበረ አካሄድ አለመሆኑን በመጠቆም፣ 1,696 ካሬ ሜትር ስፋት ያለው ቦታ ለኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል መሰጠቱ ተገቢ መሆኑን በውሳኔው አስታውቋል፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ
የኦሕዴህ አባላት በሰማያዊ ምልክት ሊወዳደሩ ነው
- “ለአንድ አላማ እንታገላለን” አቶ ግርማ በቀለ
- “መሰባሰባችን ትግሉን ያጠናክረዋል” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት
የኦሞ ሕዝቦች ዲሞክራሲያዊ ህብረት (ኦሕዲኅ) አባላት በሰማያዊ ፓርቲ ምልክት ለመወዳደር መወሰናቸውን የኦሕዲኅ ሊቀመንበር አቶ ግርማ በቀለ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጹ፡፡ ‹‹ጥቅምት 26/2006 ዓ.ም ፓርቲው ባደረገው ጠቅላላ ጉባኤ አባላቱና አመራሩ ከአገር አቀፍ ፓርቲዎች ጋር በውህደት መስራት እንዳለባቸውና በኦሕዲኅ ስም የሚደረገው የመጨረሻ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲሆን ወስነው ነበር›› ያሉት ሊቀመንበሩ የፓርቲው እጩዎች በሰማያዊ ፓርቲ ስምና ምልክት መመዝገባቸው አባላቱና አመራሩ ‹‹አገራዊ ፓርቲ ጋር በውህደት አሊያም በሌላ መንገድ አብረን መስራት አለብን፡፡›› በሚል በጠቅላላ ጉባኤው ያስተላለፉት ውሳኔ አካል ነው ብለዋል፡፡
አቶ ግርማ ፓርቲያቸው ከሰማያዊ ጋር ሆኖ ለመታገል የተነሳበትን ምክንያትም ‹‹አሉ ከሚባሉት 70 ያህል ፓርቲዎች አብዛኛዎቹ የክልል ፓርቲዎች ናቸው፡፡ የክልል ፓርቲዎች በአገራችን ፖለቲካ ፋይዳ ያለው ለውጥ እያመጡ አይደለም፡፡ የክልል ፓርቲዎች ሲጠናከሩም ቢሆን ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው እንደሚያመዝን ተረድተናል፡፡ በተቃራኒው አገር አቀፍ ፓርቲዎች ሲጠናከሩ የተሻለ ለውጥ ማምጣት ይችላሉ›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡ አቶ ግርማ አክለውም ‹‹እስካሁን የክልልና አገራዊ ፓርቲ ተባብለን ተበታትነን ቆይተናል፡፡ አሁን ግን የተሻለ ለውጥ ለማምጣት አንድ አይነት ጥያቄ አንስተን፣ በአንድ አላማ ለመታገል ወስነናል፡፡ አንድነት ኃይል በመሆኑ በኢትዮጵያ ፖለቲካ የተሻለ ለውጥ እንደምናመጣ የሚል ትልቅ ተስፋ አለን›› ብለዋል፡፡
ፓርቲው ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ስምምነት በመፈረሙ አባላቱ በሰማያዊ ፓርቲ ስር ሆነው እንዲወዳደሩ ለምርጫ ቦርድ ባስገባው ደብዳቤም ‹‹የዚህ ስምምነት አላማ ፈራሚዎች ለ2007 ዓ.ም አጠቀላይ አገራዊ ምርጫ አባላትን በጋራ በአንድ የመወዳደሪያ ምልክት ማቅረብ፣ ማለትም የአንዱ ፓርቲ አባልና አመራር በሌላው ፓርቲ ሥምና ምልክት የሚወዳደሩበትን ሁኔታ ማመቻቸት፣ ስምምነት ሲደረስም ተግባራዊ ማድረግ ነው›› ብለዋል፡፡
በተመሳሳይ የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት የቀድሞ የአንድነት አባላት ወደ ሰማያዊ ፓርቲ መምጣታቸውን አስታውሰው አሁንም የኦሕዲኅ አባላት በሰማያዊ ፓርቲ ስር ለመወዳደር በፓርቲው ጥላ ስር መሰባሰባቸው ሰላማዊ ትግሉን እንደሚያጠናክረው ገልጸዋል፡፡ ‹‹በአንድነት መቆማችንና መሰባሰባችን ትግሉን ያጠናክረዋል፡፡ ኢህአዴግ የአንድነት አመራሮችና አባላት ወደ ሰማያዊ በመምጣታቸው፣ ሰማያዊም እጁን ዘርግቶ በመቀበሉ ከፍተኛ ፍርሃት ተፈጥሮበታል፡፡›› ብለዋል፡፡ ኢ/ር ይልቃል አክለውም ‹‹አሁንም ሌሎች ፓርቲዎች መቀላቀላቸው ለኢህአዴግ ትልቅ ስጋት ነው፡፡ ይህም በመሆኑ በቴሎቪዥንና በራዲዮ እጩ ያቀረቡ ፓርቲዎችን ሲያስተዋውቅ የሰማያዊን ስም ሳይጠቅስ ቀርቷል፡፡ በተቃራኒው በሬዲዮና በቴሊቪዥን ሰማያዊ ተቋማትን አይቀበልም እያለ በሀሰት እየወነጀለ ያለው የተቃውሞ ጎራው በአንድነት በመቆም እየተጠናከረ በመምጣቱ ነው፡፡›› ሲሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት በሰማያዊ ስር መሰባሰባቸው ያለውን ፋይዳ መግለፃቸውን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡




