Monthly Archives: April, 2015

በኬንያ ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ በአል-ሸዓባብ በተፈፀመ ጥቃት የሟቾች ቁጥር 147 ደርሷል

Garissa-University-College attack

በኬንያ ሰሜን ምስራቅ  በምትገኘው ጋሪሳ የሶማሊያው ታጣቂ አል-ሸዓባብ ሐሙስ ጠዋት መጋቢት 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ግቢ ውስጥ በመግባት በከፈተው ጥቃት ሁለት የዩኒቨርስቲው ጠባቂዎችን፣ሶስት የፖሊስ ኦፊሰሮችን እና 142 ተማሪዎች በአጠቃላይ 147 ሰዎች መገደላቸውን የሀገሪቱ የውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር ጆሴፍ ነካይዘሪ ለመገናኛ ብዙኃን ይፋ አድርገዋል፡፡ በጥቃቱ ከሟቾች በተጨማሪ 79 ተማሪዎች የቆሰሉ ሲሆን፤ ቁጥራቸው እስካሁን በውል ያልታወቀ በታጣቂው ኃይል ታግተው እንደነበር ተጠቁሟል፡፡

ይህንንም ተከትሎ የሀገሪቱ ፕሬዘዳንት ኡሁሩ ኬኒያታ በፖሊስ እጥረት ምክንያት አላስፈላጊ ዋጋ መክፈል የለብንም በማለት ከፍተኛ የፖሊስ ቁጥር እንዲጨምርና ወደስልጠና እንዲገቡ  ትዕዛዝ መስጠታቸውን አደጋው በደረሰ ቀን ባስተላለፉት የሀዘን መግለጫ ላይ አስታውቀዋል፡፡ የሶማሊው ታጣቂ አልሸዓባብ በኬንያ ንፁሃን ላይ የሚያደርሰው ጥቃት እየተበራከተ ሲሆን፤ ከዚህ በፊት በናይሮቢ ዌስትጌት የንግድ ማዕከል ውስጥ በፈፀመው ጥቃት 67 ሰዎች መግደሉ ይታወሳል፡፡ ከዛም በኋላ የሐሙሱን የጋሪሳ ዩኒቨረድስቲ ኮሌጅን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በርካታ ጥቃቶችን መፈፀሙ ይታወቃል፡፡ የጥቃቲ ኢላማዎችም ሙስሊም ያልሆነ ማንኛውም አካል ሲሆን፤ በተለይ ክርስቲያኖች ላይ ጥቃቱ መጨመሩን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

እንደ ሀገሪቱ ፖሊስ መጃ መሰረት ከ2004 ዓ.ም. እስከ ታህሳሥ 2007 ዓ.ም. ብቻ የአልቃይዳ ክንፍ በሆነው በሶማሊያው እስላማዊ ታጣቂ አልሸዓባብ የተገደሉ ኬኒያውያን ቁጥር 312 ደርሶ ነበር፡፡ በጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ የተፈፀመውን የጅምላ ግድያ ጨምሮ በሶማሊያው ታጣቂ አል-ሸዓባብ የተገደሉ ኬንያውያን  459 ደርሷል፡፡

Garissa-University-College attack

በዩኒቨርስቲ ኮሌጁ ተማሪዎች ላይ ታጣቂው  ከፈፀመው የጅምላ ግድያ በኋላ አራት የታጣቂ ቡድኑ አባላት ሲገደሉ፣ አምስት ተጠርጣሪ የቡድኑ አባላት በቁጥጥር  መዋላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ውስጥ የተገደሉ ሰዎችን ማንነት ለመለየትና ወደ የቤተሰቦቻቸው ለመላክ አሰከሬናቸው ወደ ናይሮቢ መላኩም ታውቋል፡፡

ጋሪሳ ከናይሮቢ ሰሜን ምስራቅ 367 ኪሎ ሜትር ስትርቅ፤ ከኬንያ ሶማሊያ ድንበር ያላት ርቀት  ደግሞ 147 ኪሎ ሜትር ነው፡፡ የታጣቂ ቡድኑ በተመሳሳይ መልኩ በዩጋንዳ የትምህርት ተቋማት ላይ ጥቃት ለመፈፀም ዕቅድ እንዳለው ተጠቁሞ፤ የዩጋንዳ የደህንነትና ፀጥታ አካላት የሀገሪቱን ደህንነት ከመቼውም ጊዜ በላቀ በተጠንቀቅ ላይ ሆነው እንዲጠብቁ መደረጉንም የዩጋንዳ ከፍተኛ ፖሊስ ኦፊሰርን ጠቅሶ የአውስትራሊያው ኤቢሲ ዘግቧል፡፡

በኬንያ መንግሥት ተፈላጊው መሐመድ መሐሙድ

በኬንያ መንግሥት ተፈላጊው መሐመድ መሐሙድ

በተለይ ከጥቃቱ በስተጀርባ ዋና አቀናባሪና በጋሪሳ ከተማ የእስላማዊ ትምህርት ቤት መምህር እንደነበር የተጠቆመው መሐመድ መሐሙድ የገደለ ወይም ያለበትን የጠቆመም እንዲሁም ይዞ ለሚያስረክብ የኬንያ መንግሥት ፖሊስ 215 ሺህ የአሜሪካን ዶላር (200 ሚሊዮን የኬንያ ሽንልንግ)እንደሚሰጥ ቃል ገብቷል፡፡ ጥቃቱን በተመለከተ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋነ ፀሐፊ ባን ኪ ሙንን ጨምሮ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ማኀበረሰቦች ያወገዙት ሲሆን፤ ታጣቂው አልሸዓባብ በበኩሉ ድርጊቱ የፈፀመው ከኬንያ ጋ ጦርነት ውጊያ ላይ ስለሆንን ነው ማለቱን የቢቢሲ ዘገባ አመልክቷል፡፡

እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ 28 ቀን ቀጠሮ ተጠየቀባቸው

ከግራ ወደቀኝ  ፍቅረማሪያም አስማማው፣ ብርሃኑ ተክለያሬድና ኢየሩሳሌም ተስፋው

ከግራ ወደቀኝ ፍቅረማሪያም አስማማው፣ ብርሃኑ ተክለያሬድና ኢየሩሳሌም ተስፋው

የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት የሆኑት ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ፍቅረማሪያም አስማማውና እየሩሳሌም ተስፋው ትናንት መጋቢት 21 አራዳ ምድብ ችሎት ቀርበው 28 ቀን ተቀጠረባቸው፡፡ ፖሊስ እነ ብርሃኑ ተክለያሬድን ‹‹ለግንቦት 7 አባላትን መልምለው ወደ ኤርትራ በመላክና ቡድኑን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ ሲሄዱ ተይዘዋል›› ብሏል፡፡

ጠበቃው እነ ብርሃኑ ተ/ክለያሬድ ለግንቦት ሰባት ሲመለምሉም ሆነ አባል ሲሆኑ የሚያሳይ ተጨባጭ መረጃ እንደሌለ በመግለጽ የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅላቸው ገልጸዋል፡፡ ይሁንና ፖሊስ ‹‹ማህበራዊ ሚዲያ ላይ የምመረምራቸው ጉዳዮች አሉ፡፡ ሌሎች የምንይዛቸው ግብረ አበሮችም አሉ፡፡ መረጃ ያጠፉብናል፡፡›› በሚል ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቆ 28 ቀን ተፈቅዶለታል፡፡ ሚያዚያ 19 ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎም ይጠበቃል፡፡

ፖሊስ ሌሎች ሰዎች ይዘውት የተነሱትን መሳሪያ በማሳየትም እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ ግንቦት ሰባትን ሊቀላቀሉ እንደነበር ለማሳየት በመረጃነት አቅርቧል፡፡ ጠበቃው በበኩላቸው ‹‹የማህበራዊ ሚዲያ ላይ ምርመራ ለማድረግና መረጃዎችን ለማሰባሰብ ተጠርጣዎቹን ማሰር ተገቢ አልነበረም፡፡ ሌሎች ሰዎች የያዙትን መረጃ እነሱን ለመክሰስ መጠቀም ተገቢ አይደለም፡፡›› ሲሉ ተቃውመዋል፡፡

በሌላ በኩል ከተጠርጣሪዎቹ መካከል አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ የታሰረበት ቤት መብራት ስለማይጠፋ አይኑ ላይ ለከፍተኛ ችግር እንዳደረሰበት ቅሬታ አቅርቧል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ለ15 ደቂቃ ፀኃይ እንዲሞቁ ከሚፈቀድላቸው ውጭ ወደ ከታሰሩበት ቤት ውጭ መውጣት እንደማይፈቀድላቸውና ቤተሰቦቻቸውም እንዲጠይቋቸው እየተደረገ አለመሆኑን በቅሬታ አቅርበዋል፡፡

የዞን9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን የአቃቤ ህግ ምስክሮች ቃል

z9

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በ19ኛው ወንጀል ችሎት እየታየ ያለው የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን ምስክሮችን አሰምቶ በአወዛጋቢ መልኩ ለሚቀጥለው መጋቢት 30 ቀጠሮ ይዞ ተጠናቋል፡፡

ከእለቱ ዋዜማ ቃለ መሃላ ፈጽመው ሳይሰሙ የቀሩት ምስክሮች የተሰሙ ሲሆን ቃለ መሃላ በቀደመው ቀን በመግባታቸው ቀጥታ ወደ ምስክርነት ቃላቸው ተገብቷል፡፡ በሃያ ስድስተኛው የፍርድ ቤት ውሎ ተሰሙት ምስክሮች

7ተኛ ምስክር -ተስፋዬ መንግስቴ የመሰከሩት አቤል ዋበላ ላይ ሲሆን ከመንገድ ላይ ፓሊስ ሲፈትሹ አንዲታዘቡ ጠይቋቸው ቤቱ እና መስሪያ ቤቱ የተገኘው ሲዲ መጽሄቶች እና መጸሃፍት ላይ ሲገኙ አይቼ ፈርሜያለው አቤልም ፈርሟል ብለዋል፡፡

8ተኛ ምስክር- አቶ በረከት ጌታቸው በተመሳሳይ መንገድ ላይ ፓሊስ ታዘቡልኝ ብሎ የበፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ መታዘባቸውን በፍቃዱ የፈረመባቸው ነገሮች ላይም መፈረማቸውን ተናግረዋል፡፡ ጽሁፎቹ አማርኛ እና አንግሊዘኛ ከመሆናቸው ውጪ የሚያስታውሱት ይዘት አንደሌለ ተናግረዋል፡፡

9ኛ ምስክር – አቶ አንድነት ስሜ ይባለሉ አጥናፍ ብርሃኔ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ቤቱ የተገኙ ወረቀቶች ላይ እሱም ፈርሟል አኔም ፈርሜያለው ብለዋል፡፡ የተገኙት ወረቀቶች አማርኛ እና እንግሊዘኛ ሲሆኑ ሴኩሪቲ ኢን ኤቦክስ የሚል መጽሃፍ አለበት ብለዋል፡፡ በይዘቱ ላይ አቃቤ ህግ አንዲመሰክሩ ቢጠይቅም ጠበቆች በይዘቱ ላይ ለመመስከር ስላልተመዘገቡ አንዳይመሰክሩ ተቃውሞ አቅርበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ እንዲመሰክሩ ቢፈቅድም ምስክሩ ምንም ይዘት አንደማያስታውሱ ተናግረዋል፡፡

10ኛ ምስክር -አቶ ታምራት ዓለሙ የሚባሉ ሲሆን አቤል ዋበላ ቤት ሲፈተሽ እንደነበሩ በመግለጽ ምስክርነታቸውን አሰምተዋል፡፡ አቤል የፈረመባቸው ነገሮች ላይ ፈርመናል ያሉ ሲሆን የነጻነት ጎህ ሲቀድ መጽሃፍ እስልምና በኢትዬጲያ የሚል መጽሃፍ አዲስ ጉዳይ መጽኄቶች አና እምነት እና ተስፋ በኢትዬጲያ የሚሊ ጽሁፎች ተገኝተዋል፡፡ ሲዲም ተገኝቷል ብለዋል፡፡ የፍተሻውን ቀን ሚያዝያ 11 ነው ብለዋል፡፡ ( ጦማሪ አቤል የታሰረው ሚያዝያ 17 አንደሆነ ይታወቃል)

11ኛ ምስክር አቶ ፋሲል ግርማ ሲሆኑ በፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ቤት ውስጥ ተገኙት እቃዎች እና ሰነዶች ላይ ተከሳሹ ሲፈርም እኛም ፈርመናል ብለዋል፡፡ የተገኙትን ሰነዶች ብዛትና ይዘት እንደማያሰታውሱም ተናግረዋል፡፡

12ኛ ምስክር አቶ ደረጀ አበበ የኮንስትራክሽን እና ቢዝነስ ባንክ ባልደረባ ሲሆኑ ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ ቢሮ ሲፈተሽ ፓሊስ ታዘቡ ብሏቸው አንደነበሩ እና ተገኙት ወረቀቶች ላይ ፈርመው ቢሮውን ዘግተው መውጣታቸውን ገልጸዋል፡፡ በወቅቱ የፈረሙበትን ወረቀት ይዘት የማያስታውሱት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

13ኛ ምስክር አቶ አክሊሉ ሃይለማርያም ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ስሙን ብቻ ነው የማስታውሰው በማለት ያዬትን ተናግረዋል፡፡ ፈረንሳይ ለጋሲዬን አካባቢ ያለው ቤቱ ሲፈተሽ የተገኙ አማርኛ እና እንግሊዘኛ ጽሁፎች የግል ማስታወሻዎች ሲም ካርድ እና መጽሃፍት የተገኙ ሲሆን ሁሉም ላይ በፍቃዱም ሲፈርም እኔም ፈርሜያለሁ ብለዋል፡፡

በ14ኛ ምስክርነት አቶ የማነ ብርሃኔ የተባሉ ግለሰብ ቀርበው የነበር ቢሆንም አቃቤ ህግ ‹የተለየ ነገር አያስረዱልኝም› በሚል ምስክሩ ሳይደመጡ እንዲመለሱ ፍርድ ቤቱን ጠይቆ ምስክርነታቸው ሳይሰማ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ አጠቃላይ 41 ምስክሮችን እንዳስመዘገበ በመጥቀስ ትናንት ካስመዘገባቸው 17 ምስክሮች ውጭ ሌሎቹን ፖሊስ በአድራሻቸው ፈልጎ እንዳጣቸው በመግለጽ ማቅረብ አለመቻሉን አስረድቷል፡፡ በሌላ በኩል ግን 8ኛ፣ 9ኛ እና 27ኛ ላይ አቃቤ ህግ ያስመዘገባቸው ምስክሮች መጥሪያ ደብዳቤ ደርሷቸው እንዳልተገኙለት ገልጹዋል፡፡

Ethiopia-Federal-High-Court-300x194

ፍርድ ቤቱ የጠበቆችን (የተከሳሾችን) አስተያየት ጠይቆ ነበር፡፡ በዚህም ጠበቆቹ አሉ የተባሉትን ምስክሮች ፌደራል ፖሊስ ሌሎችን በአድራሻቸው ፈልጎ ማቅረብ ይገባው እንደነበር፣ እግዚቢት ላይ የተመሰከሩት ቃሎችን ፍ/ቤቱ እንዳይመዘግባቸው ማመልከት፣ እንዲሁም ያልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ምስክር መስማቱ ተገቢ እንዳልሆነ በአስተያየታቸው አስረድተዋል፡፡ በመሆኑም አቃቤ ህግ ቀሪ ምስክሮችን ማሰማት ካለበትም ምስክሮቹን በተሰጠው ቀን ( የማስረጃ መስማት ለሶሰት ተከታታይ ቀናት አንደተቀጠረ ይታወሳል) እንዲያቀርብ በማሳሰብ የደንበኞቻቸው የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብት በፍርድ ቤቱና በአቃቤ ህግ በኩል እንዲከበር ጠይቀዋል፡፡ በተለይ ባልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ይህን ያህል ጊዜ መውሰዱ ተገቢ አይደለም ብለዋል ጠንካራ ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡ ጦማሪ ናትናኤል በበኩሉ ‹‹አቃቤ ህግ ያቀረበውን ሰምተናል፤ እኛ ብቻችንን አይደለም የታሰርነው፤ ቤተሰቦቻችንና ጓደኞቻችንም አብረውን ታስረዋል፡፡ በህሊና እና በኢኮኖሚ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰብን ነው፡፡ ስለዚህ ይሄ ሁሉ ‹ውሳኔው ላይ አብሮ እንዲታይልን እናመለክታለን ብሏል፡፡

ፍርድ ቤቱ የጠዋት ምስክር መስማቱን ሂደት አጠናቆ ለከሰአት ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ከሰጠ በኋላ ከሰአት በኋላ ሁለት ጉዳዬች ብይን ሰጥቷል፡፡ የመጀመሪያው የምስክሮች ቃል ከመዝገቡ ጋር አንዲያያዝ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ቀሩ የተባሉት ሶስት ምስክሮች ታስረው ለመጋቢት 30 አንዲቀርቡ እና አቃቤ ህግ ተጨማሪ ምስክሮች አሉኝ ካለም አንዲያቀርብ ነው፡፡በዚህም መሰረት ለሶስት ቀን የታቀደው ምስክሮችን መስማት በአንድ ቀን ከግማሽ ተጠናቋል፡፡ ጠበቆች አቃቤ ህግ ቀድሞ በተወሰነው ቀን ምስክሮችን ሊያቀርብ ሲገባ ሌላ ቀነ ቀጠሮ መሰጠት የለበትም በማለት ያቀረቡትን ተቃውሞ ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ በበኩሉ ምስክሮቹን በፌደራል ፓሊስ እያስፈለኩ ስለሆነ ተከሳሾ ማረሚያ ቤት እንዳሉ ለፍለጋው ጊዜ ይሰጠኝ ብሎ ነበር ፡፡

ጠበቆቹ አቃቤ ህግ የእግዚቢት ሰነዶችን በተመለከተ የመዝገብ ቁጥሩን ገልጾ እንዲቀርብ በጠየቁት መሰረት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡ በትዕዛዙ መሰረት አቃቤ ህግ ዛሬ የመዝገብ ቁጥሩን ይዞ መቅረብ የነበረበት ቢሆንም፣ ጠበቆቹ ይህንኑ ጉዳይ በማንሳት ሲጠይቁ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ አልሰጠንም በሚል ክዷል፡፡

ምንጭ፡- ዞን 9 ማኀበራዊ ገፅ

ፍትህ መረገጡን በአደባባይ አስመስክረናል፤ሃላፊነታችንንም ተወጥተናል!

ተክሌ በቀለ  (የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት)

ተክሌ በቀለ (የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት)

ለኔ እዉነተኛው የአንድነት ፓርቲ ትናንት መጋቢት 23 ቀን 2007 ዓ.ም. በፍርድ ቤት ውሳኔ ተቀብሯል፡፡ዱባና ቅል አበቃቀሉ ለየቅል እንደሆነ ቀድም ሲል አውቀናል፡፡ ዳኛ ብርቱኳንም፣ ፍርህይወትም ዳግም አልተከሰቱም፡፡ እንደ ኢህአዴግ የምርጫ ውጤት 99.6 ከመቶ አመራሩና አባላቱ በምርጫ ቦርድ እንዲበተኑ የተበየነበት እንዲሁም በደጋፊዎች የተገዛ ንብረት ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ በመንግስት ታጣቂ ፖሊሶች የተዘረፈበት አንድነት የፍትህ ተቋሙን ለመፈተሸ ምርጫ ቦርዱን መክሰሱ ይታወቃል፡፡

ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድን መክሰሳችን አግባብ እንዳልሆነ አንቀጽ ተጠቅሶ ከማስፈራሪያ ጋር ክሱ ዉድቅ ተደርጓል፡፡ በዚህም ፍትህ መረገጡን ባደባባይ አስመስክረናል፤ሃላፊነታችንንም ተወጥተናል፡፡ ቀጣዩን በቀጣይ ሂደት የምናየዉ ይሆናል፤እንደሚፈልጉት ተበትነን አንቀርም፡፡ አንድነቶች በያለንበት እንረጋጋ!!

ታላቋ ምዕራብ አፍሪካዊት ሃገር ናይጀሪያ እዚህ የደረሰችዉ ዉድ ዋጋ ከፍላ ነዉ፡፡ ከናይጀሪያም በላይ ዋጋ ብንከፈልም በልተዉ በማይጠግቡ በሎች ትግሉ እየተነጠቀ ዛሬም እዛዉ ላይ ነን፡፡ ታላቅዋ የምስራቅ አፍሪካ ኮከብ ሀገረ ኢትዮጵያ በልማት ስም ክብሯ እንዲወርድ እየተደረገች ትገኛለች፡፡ እናም በዲፕሎማሲ፤በዲሞክራሲ፤በኢኮኖሚም ይሁን በሁለንተናዊ ልማት የአለም ማህበረሰብ በአፍሪካ ትኩረት ናይጀሪያ ሆናለች፡፡ ኢትዮጵያ የምትፈለገዉ ለክፍለ አሁጉሩ የደህንነት አጋርነት ብቻ ነዉ፡፡

የናይጀሪያ ተፎካካሪ ፓርቲዎችና(የተቀናቃኝ ፓርቲዎች ትብብርና ዉህደት ያስከተለዉን ዉጤትም ልብ ይሏል) የተወዳዳሪ ግለሰቦች ሚና ቀላል ባይሆንም ለናይጀሪያ ተስፋ የሆናት ግን ህዝቡ ነዉ፡፡ የኢትዮጵያችንም የለዉጥ ተስፋ ህዝቡ ነዉ፡፡ በዚህ ወቅት የተቃዋሚ የፖለቲካ ሃይሎች አሰላለፍም የጎላ ድርሻ ይኖረዋል፡፡

በዞን 9 ብሎገሮችና ጋዜጠኞች ክስ ላይ ፍርድ ቤቱ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን መስማት ጀመረ

Ethiopia-Federal-High-Court-300x194

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ቀናት የሚቆየው የማስረጃ መስማት ውሎ ዛሬ ምስክሮችን በማስማት ተጀምሯል፡፡ በዚህም መሰረት አቃቤ ህግ ጉዳዬን ያስረዱልኛል ያላቸውን 17 ምስክሮች ያስመዘገበ ሲሆን 15ቱ በፍርድ ቤቱ ተገኝተው ቃለ መሃላ ፈጽመዋል፡፡ አቃቤ ህግ ችሎቱ በዝግ ችሎት አንዲሆን የጠየቀ ሲሆን ምስክሮቼ እና የቤተሰቦቻቸውን ደህንነት ለመጠበቅ ችሎቱ በዝግ ሊሆን ይገባል የሚለውን አቤቱታውን ጠበቆች በከፍተኛ ደረጃ ተቃውመውታል፡፡ ምስክሮቹ የጭብጥ ምስክሮች ሳይሆኑ ፍተሻን የታዘቡ የደረጃ ምስክሮች በመሆናቸው እና ስማቸውም በግልጽ ተከሳሾች ጋር ስለደረሰ ምንም አይነት የደህንነተ ስጋት የለባቸውም ከሚለው የጠበቆች ክርክር በኋላ ፍርድ ቤቱ በጉዳዬ ላይ ተወያይቶ ለመወሰን ረፍት ወስዷል፡፡ በዚህም መሰረት የአቃቤህግን አቤቱታ ውድቅ በማድረግ ችሎቱ በግልጽ ሆኖ መስክሮች ምስክርነታቸውን እነዲያሰሙ ታዟል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አቃቤ ህግ ያቀረባቸው ምስክሮች አነማን ላይ አንደሚመሰክሩ እና ምን አንደሚመሰክሩ በተጠየቀው መሰረት ፍርድ ቤቱም በጠበቆቹ ስለተነሱት ነጥቦች የአቃቤ ህግን ምላሽ ጠይቋል፡፡ አቃቤ ህግም በዛሬው ዕለት የቀረቡት ምስክሮች በ2ኛ፣ በ3ኛ፣ በ5ኛ፣ በ6ኛ፣ በ7ኛ እና 8ኛ ተከሳሾች ( በስድስቱ የዞን9 ጦማርያን ላይ እና በጋዜጠኛ አስማማው ላይ ) ላይ እንደሚመሰክሩ ገልጾ የፌደራል ወንጀል ምርመራ ቡድን በብርበራ ያገኛቸው ማስረጃዎች ከተከሳሾች የተገኙ ስለመሆናቸው ያስረዱልኛል ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡

ዞን9

በምላሹም መሰረት የአቃቤ ህግ ምስክሮች ምስክርነታቸው ሰጥተዋል፡፡ ምስክርነታቸው ሲሰጡ በነበረበት ወቅት የተከሳሾችን ስም አለማወቅ አንዲሁም የተከሳሾችን መልክ አለመለየት የመሳሰሉት ጉዳዬች የተስተዋሉ ሲሆን ምስክርነታቸውን የሰጡት ሰዎች ስም ዝርዝር እና የምስክርነታቸው ጭብጥ በአጭሩ አንደሚከተለው ነው ፡፡

1.ሙሉጌታ መዝገቡ ለማ – ናዝሬት ነዋሪ ነኝ መአከላዊ ምርመራ ለግል ጉዳይ ሄጄ ፓሊስ ታዛቢ ምስክር አንድሆን ጠይቆኝ በዚያ መሰረት ምስክር ሆኜ ተገኝቻለሁ፡፡ ከአቤል ከኮምፒውተሩ ላይ ጽሁፍ ሲወጣ እና ሲፈርም አይቼ እኔም ፈርሜያለሁ ፡፡ የጽሁፉን ይዘት አላነበብኩም አንዳንድ ቦታ አፍሪካ ሪቪው ኬንያ የሚል ቃል አይቻለሁ የሚል ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡

2.በለጡ አበበ ዮሴፍ ይባላሉ፡፡ እድሜያቸው 32 ሲሆን ከፍተኛው ፍርድ ቤት የካ ምድብ ሰራተኛ ናቸው፡፡ አዲስ አበባ ነዋሪ ሲሆኑ በማን ላይ ለመመስከር እንደመጡ ሲጠየቁ በስም እንደማያስታውሱት ገልጸው በአካል ግን ለይተው አሳይተዋል፡፡ መስካሪዋ በ6ኛ ተከሳሽ ዘላለም ክብረት ላይ የሚመሰክሩ ሲሆን በተለየ ስም ሲጠሩት ተስተውለዋል
“የሽብርተኝነት ጉዳይ የሚያመለክት ይመስለኛል፡፡ ወደ 70 ገጽ አማርኛና 10 ገጽ እንግሊዝኛ ጽሁፍ ተገኝቷል፡፡ ያየሁትን አይቼ ፈርሜያለሁ፡፡” ካሉ በኋላ ተከሳሹስ ፈርሟል ተብለው ሲጠየቁ መጀመሪያ አላስታውስም ቢሉም እንደገና ሲጠየቁ ግን አዎ ፈርሟል ብለዋል፡፡

3.እታፈራሁ ጌታቸው ወልዴ የሚባሉ ሲሆን እድሜያቸው 36 ነው፡፡ በመንግስት ት/ቤት በአስተዳደር ሰራተኛነት የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ ማን ላይ እንደሚመሰክሩ ሲጠየቁ ፍቃዱ እና…..(ስሙ ጠፍቶባቸው ቆይተው) እ…አጥናፉ ብለዋል፡፡ በአካል ደግሞ በፍቃዱን አሳዩ ሲባሉ አጥናፍን አሳይተዋል፡፡ የምስክርነት ቃላቸውም ማእከላዊ ምርመራ ለግል ጉዳይ ሄደው ጽሁፎች ሲታተሙ ማየታቸውንና በፍቃዱ በፍቃደኛነት ሲፈርም ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ስለጽሁፎቹ ሲጠየቁ “የአማርኛ ጽሑፎች ናቸው፡፡ 60 ገጽ የሚሆን ‹ወያኔ ይውደም› ምናምን የሚል ጽሑፍ አይቻለሁ፡፡ እንግሊዝኛም አለው 10 ገጽ ይሆናል፡፡ በምስል ከውጭ ሰው ጋር ሆነው የሚነጋገሩትም አይቻለሁ፡፡ ይዘቱ ግን ግር ይለኛል፡፡” ብለዋል፡፡ አጥናፍን አስመልክቶ ደግሞ ‹‹የእሱንም በዚያው መልኩ ነው ያየነው፡፡ ዕለቱም ግንቦት 16/2006 ነው፡፡ ኮምፒውተሩ ላይ የነበሩትን ጽሁፎች እዚያ ለነበሩት ሲያሳይ ነበር፡፡ ጽሑፎችን አይቻቸዋለሁ….‹የጨለማው ቀን….የጨለማው ንጉስ› የሚል አይቻለሁ፡፡ ‹ኢትዮጵያ አንድ ናት› የሚልም አይቻለሁ፡፡ ወደ 30 ገጽ ይሆናል፡፡ ሁሉም ፕሪንት ተደርጎ ሁላችንም ፈርመንበታል፡፡››ብለዋል

ሶስቱ ምስክሮች ከተሰሙ በኋላ ጠበቆች በሂደቱ ላይ አስተያየት አለን በማለት፣ ዶክመንቶቹ ፕብሊክ ዶክመንት ናቸው በአደባባይ የተጻፉ ጽሁፎቻቸው እና በማንኛውም ቦታ የሚገኙ ስለሆኑ ዶክመንቶቹን ክደን አልተከራከርንም የእኛ ክርክር ዶክመንቶቹ ለወንጀል ስራ የሚበቁ አይደሉም ነውና በዚህ ጭብጥ ዙሪያ ምስክር መስማቱ ያብቃልን የሚል ጥያቄ አንስተዋል፡፡አቃቤ ህግ በበኩሉ ሁሉም ምስክሮች አንዲሰሙልኝ እፈልጋለሁ በማለቱ ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ ያስረዱልኛል ካለ ይቀጥል በማለቱ ምስክሮቹ ቀጥለዋል፡፡ ጠበቆች መስቀለኛ ጥያቄ ሳይጠይቁ ተከታዬቹ ምስክሮች መሰማታቸው ቀጥሏል፡፡

4.አራተኛው ምስክር አፈወርቅ ካሳ ይባላሉ፡፡ የግል ሰራተኛ ሲሆኑ እድሜያቸው 46 ነው፡፡‹‹ቀኑ ሚያዝያ 18/2006 ነው፡፡ የተከሳሹ አስማማው ቤት ጠዋት 3፡00 አካባቢ ሲፈተሸ ታዛቢ ነበርኩ፡፡ ጋዜጦች፣ መጽሔቶች፣ ፓስፖርት…ብዙ ወረቀቶች ላይ ‹‹አዎ የእኔ ናቸው›› እያለ ሲፈርም አይቻለሁ፡፡ እኔም ፈርሜያለሁ፡፡ ቤተሰቦቹም ቤት ውስጥ ነበሩ፡፡ አብዛኛው ያየሁት የግል መጽሄቶችን ነው፡፡ ማህተምም አይቻለሁ፡፡ ደሞ ቢሮው ሄደን ላፕቶፕ፣ ፍላሽ፣ ሲዲ፣ መጽሔቶች አይቻለሁ፡፡ ፖሊስ የሚፈልገውን እየለየ ፈርመናል፡፡ ወደቢሮው የሄድነው በመኪና ነበር፡፡ ከዛ ደግሞ አድራሻችንን ይዘው ስለነበር ሰኔ 4….አይ 14/2006 ነው መሰለኝ ከማዕከላዊ ተጠርተን ላፕቶፕ ላይ የነበረውን ስዕሎችና የእንግሊዝኛ ንግግሮች ሲወጡ አይቻለሁ፡፡ የእኔ ነው ብሎ ሲፈርም እኛ ታዛቢዎችም ፈርመናል፡፡›› ብለው ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡

5.አምስተኛ ምስክር አጌና አንከና ይባላሉ፡፡ እድሜያቸው 48 ሲሆን ነዋሪነታቸው አ.አ ነው፡፡ የሚመሰክሩት ደግሞ በ3ኛ ተከሳሽ ናትናኤል ላይ ነው፡፡ የምስክርነት ቃላቸው፣ ‹‹ሰኔ 17/2006 ለግል ጉዳይ ማዕከላዊ ነበርኩ፡፡ ከቀኑ 8፡00 ታዛቢ ሁነኝ ብሎ ፖሊስ ጠይቆኝ ታዝቤያለሁ፡፡ ላፕቶፑ ላይ አማርኛ ጽሑፎች አይቻለሁ፡፡ ጽሑፎቹ የተከሳሹ ስለመሆናቸው አምኖ ሲፈርምባቸው ታዛቢዎችም ፈርመናል፡፡ ይዘቱን ግን አላነበብኩትም፤ አልተረዳሁትም፡፡ የገጹን ብዛትም አላስታውስም፡፡›› የሚል የምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡

6.ስድስተኛ ምስክር ገብረጨርቆስ ገብረመስቀል ይባላሉ፡፡ የ50 ዓመት የመንግስት ሰራተኛ ናቸው፡፡ ምስክሩ በአስማማው ላይ ለመመስከር እንደመጡ ቢናገሩም በአካል ግን ለይተው አላወቁትም፡፡ እንዲያውም አስማማውን አሳዩ ሲባሉ አቤልን አሳይተዋል፡፡

ከፍርድ ቤቱ ውሎ በኋላ አስተያየታቸው የሰጡት የተከሳሾች ጠበቆች አቃቤ ሀግ ያቀረባቸው ምስክሮች ወረቀት ሲፈረም አየን ከማለት ውጪ ምንም አይነት ለሂደቱ ቁም ነገር ያለው ምስክርነት የሚሰጡ አይደሉም ፡፡ ተከሳሾች ተገኘባቸው የተባለው ጽሁፍ የአደባባይ ዶክመንት ከመሆኑም በላይ አልተገኘብንም ብለን ክደን አልተከራከርንም በይዘቱ ላይ ክርክር ስላልተደረገ መስቀለኛ ጥያቄ ለማቅረብም ብዙ አልጨነቅንም ብለዋል፡፡አቃቤ ሀግ የወንጀሉን የመጀመሪያ ደረጃ ጭብጥ የሚያሳዬ ምስክሮችን ያቅርብ አይቅርብ የሚታወቅ ነገር የለም፡፡ የማስረጃ ማሰማት ሂደቱ ነገ ይቀጥላል፡፡

በተቃራኒው ምሳቸውን ችሎት ውስጥ የተመገቡት ሁሉም እስረኞች በጠንካራ መንፈስ ሆነው ሲጨዋወቱ እና ሲነጋገሩ ተስተውለዋል፡፡ የችሎቱ ተሳታፌዎች በምስክሮች መደናበር እየሳቁ ነበረ ሲሆን የዞን9 ወዳጆች አጋሮች ቤተሰብና ጋዜጠኞች ተገኝተዋል፡፡

ምንጭ፡-ዞን 9 ማኀበራዊ ገፅ