አዳማ የኤድስ ተጠቂዎች ማደርያን ወደ መቅዲ ባርና ሬስቶራንት ቀየረች?!
የትነበርክ ታደለ
ይህ የምስራች እንዳይመስላችሁ! እጅግ ዘግናኝ አሳፋሪና አሳዛኝ የሀገራችን እውነታ ነው። ከአመታት በፊት ሀገር በኤች አይቪ የደረሰባትን የጭለማ ድባብ አንረሳውም! እርግጥ አሁንም ገና ከሀዘኑ ሙሉ በሙሉ አልተላቀቅንም። በዝያ የጭለማ ዘመን፣ መፍትሄ ከሀገር ውስጥም ከውጭም ሲፈለግ፣ ወጣቱ በየቦታው ሲረግፍ፣ ቤተሰብ ሲበተን አዳማ ውስጥ አንድ ሰው ተገኘ።
ይህ ሰው መስፍን ፈይሳ ይባላል። መስፍን ራሱም የቫይረሱ ተጠቂ መሆኑን ይፋ አውጥቶ በመናገር የሱ ቢጤ ወገኖቹን ለመርዳት ቆርጦ ተነሳ። እሱ እንደሚናገረው ማዳበርያ ከረጢት አንገቱ ላይ አስሮ በየደጃፉ እየዞረ ምግብ እየለመነ የሰበሰባቸውን ወገኖቹን መመገብ ያዘ።
እየቆየ ጥረቱ ፍሬ አፍርቶ በሀገር አቀፍ ደረጃ እውቅና የተሰጠውና ከ5000 ሰዎች በላይ የተረዱበት “መስፍን ፈይሳ ኢኒሼቲቭ በጎ አድራጎት” ተቋቋመ።
ይህ ተቋም አሁን “መቅዲ ባርና ሬስሮራንት ተብሎ ወጣቶች ቀንና ለሊት የሚጨፍሩበት፣ በሺሻ ጢስ የሚታጠኑበትና ህልማቸውን የሚነጠቁበት ቦታ ሆኗል።
ከሰአታት በፊት ግለሰቡ በፌስ ቡክ ገጹ ላይ በለቀቀው ቪዲዮ እንዳስታወቀው በጉልበት ከሀገር እንድወጣ ካደረጉኝ በኋላ ተቋሙን አፈራርሰው አራት ሚሊየን የሚገመት ንብረት ዘርፈው ጉዳተኞቹን በትነው ህንጻውን ከኤች አይቪ መከላከያነት ወደ ማሳራጫነት አዙረውታል ብሏል።
እጅግ የሚደንቀው ደግሞ ይህ ተቋም (አሁን መቅዲ ባር) የሚገኘው ከአዳማ ዩኒቨርስቲ አጠገብ መሆኑ ነው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተለያዩ አለማቀፍ ሚዲያዎች እንደሚዘግቡት ሀገራችን ውስጥ ዝሙት በርካሽ የሚሸጥባቸው ስፍራዎች ዩኒቨርስቲዎች ባሉበት አካባቢ ነው።
በተለይ ደግሞ አዳማ ናዝሬት በዚህ ግምባር ቀደም ተጠቃሿ ናት። አንድ የቅርብ ጊዜ መረጃ እንደሚያሳየው አዳማ 230.000 ነዋሪዎች ያላት ስትሆን ከዚህም ውስጥ ካሉት ሴቶች 5000 ዝሙት አዳሪዎች ናቸው። ይህም ማለት ከመቶ አምስት ፐርሰንቱ በዚሁ ስራ የሚተዳደሩ ናቸው። ልብ በሉ ይህ ቁጥር የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን አይጨምርም።
እንግዲህ ይህንን አይነት ጉድ የተሸከመች ከተማ እንዴት ባለ አስተዳደር እጅ ብትወድቅ ነው የህዝብን ሁለንተናዊ ጤንነት ከመጠበቅ ሀላፊነቱ እየሸሸ በግለሰብ የተቋቋመ ተቋም ለማፈረስ የተደፈረው?
እጅግ በጣም የሚገርመው ደግሞ ይህ ተቋም ሲጀመር የመሰረት ድንጋይ የጣሉት በአሁን ሰአት የክልሉ ፕሬዚዳንት የሆኑት ኦቦ ሙክታር ከድር መሆናቸው ነው። (አቡነ ጳውሎስም በቦታው ነበሩ)
እና ምነው? ኦቦ ሙክታር አዳማ ውስጥ ምን እየተካሄደ ማወቅ አይችሉም ማለት ነው? ለአንድ ትልቅ አላማ ራሳቸው በቦታው ድረስ ሄደው መሰረት የጣሉለት ተቋም እጅግ በሚያሳፍርና በሚያዋርድ ሁኔታ ተሽቆልቁሎ ሲጠፋ ምንም አልሰሙም ማለት ነው? አዳማ የኦሮሚያ ዋና ከተማ ነች! ይህንን ሳይስሙና ሳያዩ ወለጋ ጫፍ ወይም አርሲ ቦረና ስላለው እንዴት ሊሰሙ ይችላሉ? ነው ወይስ በዚህ ጉዳይ ላይ የሳቸው ይሁንታ አለበት? እውነት ለመናገር መልስ ሊሰጡበት የሚገባ ጥያቄ ነው።
የአዳማ ህዝብስ ቢሆን በራሱ ጉዳይ ላይ ከሱ የተሻለ ማን ሊጠይቅለት ይችላል? ግለሰቡ እንደተናገሩት ወደዚህ ባርና ሬስቶራንት ልጆቻችሁ እየሄዱ እያያችሁ ዝም ብትሉ በልጆቻችሁ ህይወት ላይ ፈርዳችኋል።
መንግስትም ቢሆን እነ መቄዶኒያን የመሳሰሉ ወገንን ከጎዳና የሚሰበስቡ ተቋማት ነገ በተመሳሳይ መንገድ እንደማይፈርሱና ወደ ሺሻ ቤትነት እንደማይቀየሩ ምን ማስተማመኛ ይሰጠናል? ትውልድ እየጠፋ ነው! ህግ እየተጣሰ ነው! የምንፈልገውን እያጣን የማንፈልገው እየተጫነብን በዚህ ላይ ለጩሀታችን ዝምታ እየተመለሰልን ነው! ነገ አጣብቂኙ ለሀገር ነውና መቅዲ ባር በአስቸኳይ ወገኖቻችን ወደ ሚረዱበት ተቋምነት ይመለስልን! ወገን በጭፈራ ቤት አይታከምም!
እነ ዘመነ ምህረት የእምነት ክህደት ቃላቸው ሰጡ
• “ሽብር ተፈፅሞብኛል እንጅ አሸባሪ አይደለሁም”
• “ፍትህ ቢኖር ኖሮ እኔ ሳልሆን ወያኔና ግብረ አበሮቹ ነበሩ እዚህ መቆም የነበረባቸው” አቶ ጌትነት ደርሶ
• “የተከሰስኩት ድርቡሽ እንኳ ያልደፈረውን የጎንደር ጥምቀት ላይ ፈንጅ ልታፈነዳ ነበር ተብዬ ነው፡፡ ምርመራ ላይ ግን ለምን የመኢአድ አባል ሆንክ ይሉኛል” አቶ ዘመነ ምህረት
ዘመነ ምህረት የክስ መዝገብ በሽብርተኝነት የተከሰሱት የቀድሞው መኢአድ ምክትል ፕሬዝደንት አቶ ዘመነ ምህረትና ሌላኛው የመኢአድ አባል የሆነው አቶ ጌትነት ደርሶ ዛሬ ጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ የልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ለዛሬ ቀጠሮ የሰጠው አቶ ዘመነ ምህረት ማረሚያ ቤቱ ውስጥ በደል እየደረሰበት መሆኑን ባመለከተው መሰረት ማረሚያ ቤቱ ጉዳዩን አጣርቶ እንዲያቀርብ፣ እንዲሁም በዚሁ መዝገብ 3ኛ ተከሳሽ የነበረው የመኢአድ አባል መለሰ መንገሻ ክስ የተለየ ይዘት ስላለው ክሱ ተለጥሎ እንዲታይና የቀሪዎቹን የእምነት ክህደት ቃል ለመቀበል ነው፡፡
ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹን የእምነት ክህደት ቃል እንዲሁ እየሰማሁ እመዘግባለሁ ብሎ የነበር ቢሆንም አቶ ዘመነ ምህረት ‹‹በድምፅ እንዲቀዳልኝ እፈልጋለሁ›› በማለቱ የሁለቱም ተከሳሾች የእምነት ክህደት ቃል በድምፅ እንዲቀረፅ ተደርጓል፡፡1ኛ ተከሳሽ አቶ ዘመነ ምህረት የጎንደር ጥምቅት ላይ ፈንጅ ሊያፈነዳ እንደነበር መከሰሱን ሲገልፅ ‹‹ሰው አይደለም እንሰሳት እንኳን የማይደፍሩትን፣ ድርቡሽ እንኳን ያልደፈረውን ጥምቀት እኔ በክስትና ሀይማኖትና ባህል ተኮትኩቼ ያደኩትን ሰው ፈንጅ ልታፈነዳበት ነበር መባሌ ያሳዝናል›› ብሏል፡፡ በሌላ በኩል ግን በምርመራ ወቅት ‹‹ለምን የመኢአድ አባል ሆንክ? ለምን የኢህአዴግ አባል አልሆንክም?›› እንደተባለ የገለፀው አቶ ዘመነ ይህም ‹‹ሊበሏት ያሰቧትን አሞራ ዥግራ ነሽ ይሏታል ነው›› ሲል እሱን ለማሰር የተቀነባበረ ሴራ መሆኑን ገልፆል፡፡ አቶ ዘመነ ምህረት አክሎም የታሰረው ኤርትራ እንዳትገነጠል ሲታገሉ የኖሩትን፣ እንዲሁም የሰላማዊ ትግሉ ፈር ቀዳጅ የሆኑት ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ያስጀመሩትን ትግልን የመኢአድ አመራር ሆኖ እያስቀጠለ በመሆኑ እንደሆነ ገልፆል፡፡ በመሆኑም ወንጀሉን እንዳልፈፀመው የገለፀ ሲሆን ‹‹ከተጠቀሰው መካከል ግን የማምነው አለኝ፡፡ ኢህአዴግን ዛሬም ነገም እታገለዋለሁ›› ብሏል፡፡
2ኛ ተከሳሽ የሆነው አቶ ጌትነት ደርሶ በበኩሉ ‹‹ሽብር ተፈፅሞብኛል እንጅ እኔ አሸባሪ አይደለሁም›› ብሏል፡፡ አቶ ጌትነት አክሎም ‹‹ፍትህ ቢኖር ኖሮ እዚህ መቆም የነበረኝ እኔ ሳልሆን ወያኔና ግብረ አበሮቹ ነበሩ ነበሩ፡፡ እዚህ መቆም የነበረበት መሳሪያን ተገን አድሮጎ ለ3 ወር ጨለማ ቤት ዘግቶ ጭካኔ የፈፀመብኝ ወያኔ ነበር›› ሲል ወንጀሉን እንዳልፈፀመው ክዶ ተከራክሯል፡፡
ምንም እንኳ ፍርድ ቤቱ ባለፈው ቀጠሮ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አቶ ዘመነ ምህረት ተፈፀመብኝ ያለውን በደል አጣርቶ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም የማረሚያ ቤቱ ተወካይ ‹‹የደረሰኝ መረጃ የለም›› ብለዋል፡፡ ዛሬም በድጋሜ አቤቱታውን ያቀረበው አቶ ዘመነ ምህረት ‹‹እኛ እየራበን ነው፡፡ ምግቡን እንሰሳት እንኳን ሊበሉት አይችሉም፡፡ ቤተሰቦቼ እንዳይጠይቁኝ ተደርጓል፡፡›› በማለት ከተያዙበት ጥር 10 ቀን 2007 ጀምሮ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት እየተፈፀመባቸው መሆኑን ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ የዘር መድሎ እየደረሰባቸው እንደሆነ እና ሽንት ቤት ጥግ እንዲተኙ መደረጋቸውንም ለፍርድ ቤቱ አመልክቷል፡፡ ዛሬ ለፍርድ ቤቱ ቅሬታ በማቅረቡም ከማረሚያ ቤቱ ስቃይ ሊገጥመው እንደሚችል ስጋቱን የገለፀው አቶ ዘመነ ጉዳያቸው በተዘዋዋሪ ችሎት እንዲታይ ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የ3ኛ ተከሳሽ ክስ ከእነ ዘመነ ምህረት ክስ ተነጥሎ በሌላ ችሎት እንዲታይ ብይን የሰጠ ሲሆን አንደኛ ተከሳሽ በማረሚያ ቤቱ ላይ ያሰማቸው አቤቱታዎችን ማረሚያ ቤቱ አጣርቶ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በሁለቱ ተከሳሾች ላይ የሰው ምስክር ለማቅረብም ለህዳር 3 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ-ኢትዮጵያ
ከእስር የተለቀቁት የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች ምስጋና አቀረቡ
በድንገት ከያለንበት ተይዘን እንደታሰርነው አፈታታችንም ግራ የሚያጋባ ነበር፡፡ ተመሳሳይ ክሶች ቀርበውብን እያለ ግማሾቻችን ‹ክስ ተቋርጦላችኋል› ተብለን ተፈታን፣ ግማሾቻችን ደግሞ ‹ነፃ ናችሁ› (ከሳሽ በነፃነታችን ላይ ይግባኝ መጠየቁ እንዳለ ሁኖ) ተብለን ይሄው ወጥተናል፡፡ ቀሪ ክስ ይዘን በዋስ ወጥተን እየተከራከርንም ያለን አለን፡፡ በዚህ ሁሉ መሃል የሁላችንም ዕምነት ግን አንድም ቀን ሊያሳስረን የሚገባ ወንጀል አለመፈፃችን ማመናችን ነው፡፡ መፈታታችን ጥሩ ሁኖ፤ መታሰር በፍፁም የማይገባን ነበርን፡፡ መፃፋችን እና ሕግ እንዲከበር መጠየቃችን ሀገሪቱ አገራችን እንድትሻሻል እና ሁላችንም ዜጎች የተሻለ ህይወት አንዲኖራቸው ከመሻት ባለፈ ሌላ ነገር አልነበረውም/የለውም፡፡ ነገር ግን ይህን በማድረጋችን ተገርፈናል፣ ተዘልፈን-ተሰድበናል፣ ታስረናል ተሰደናልም፡፡ ይህ በፍጹም አይገባንም ነበር፡፡
የእኛ መታሰር ፖለቲካዊ ንቃት የፈጠረላቸው ሰዎች እንዳሉ ሲነግሩን ደስ ይለናል፡፡ በእኛ መታሰር ምክንያት ለመጠየቅና ለመፃፍ በጣም እንደሚፈሩ የሚነግሩን ሰዎች ስናገኝ ደግሞ እናዝናለን፡፡ የመታሰራችን ጉራማይሌ ስሜት እንደዚህ ነው፡፡ ሳይገባን በመታሰራችን የነቁ መኖራቸውን በማወቃችን የምነደሰተውን ያክል፤ ሳይገባን በመታሰራችን የተሰበሩና ከተዋስኦ መድረኩ የራቁ እንዳሉ ስናውቅ እጅግ እናዝናለን፡፡
መታሰር በደል ነው፡፡ ብዙ ነገር ያጎድላል፡፡ መታሰር መልካም ነው፡፡ ብዙ ነገር ያስተምራል፡፡ እኛ በመታሰራችን ሀገራችን የበለጠ እንድናውቃት ሁነናል፡፡ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ ነፃነት አሁንም ብዙ ዋጋ እንደሚያስከፍል ተረድተናል፡፡ ሕግን መከታ አድርገው የኖሩ ‹ስም የለሽ› ዜጎች ሕጉ ሲከዳቸውና እነሱ ላይ ‹በላ› ሲያመጣባቸው ታዝበናል፡፡ ከሁሉም በላይ ፍትህ የሌለባት ሀገር ለዜጎቿ የማትመችና አገር እንደሆነች አይተናል፡፡
በእስራችን ወቅት የተለያዩ በደሎች በተቋም ደረጃ ደርሰውብናል፡፡ ግን አገር ነውና ከይቅርታ የሚያልፍ አይደለም፡፡ ለበደላችሁን አካላት እናንተ ይቅርታ ባትጠይቁንም፤ እናንተ የፈለጋችሁትን ባለማድረጋችንና ሕግን መሰረት አድርገን በመኖራችን ስላስከፋናችሁ እባካችሁ ይቅር በሉን፡፡
በዚህ ሁሉ መሃል ግን እናንተ አላችሁ፡፡ ጓደኞቻችንም ናችሁ፤ ዘመቻ አድራጊዎችም ናችሁ፤ ቤተሰቦቻችንም ናችሁ፤ ጠያቂዎቻችንም ናችሁ፤ ጠበቆቻችንም ናችሁ፣ የመንፈስ አጋሮቻችንም ናችሁ ርቀት ሳይገድባች የጮሃችሁልን አለም አቀፍ የመብት ጠያቂዎችም ናችሁ … በመታሰራችን የተረዳነው አንዱ ትልቅ ነገር የናንተን መልካምነት፣ የናንተን አጋርነት እና የናንተን የማይሰለች ድካምና ፍቅር ነው፡፡ እናንተ ባትኖሩ ‹አጭሩ› የእስር ጊዜያችን ይረዝምብን ነበር፤ ‹ቀላሏ› እስር ትከብድብን ነበር፡፡ ምስጋና ለናንተ፤ እስራችን ‹አጭር› – ፈተናችን ‹ቀላል› እንዲሆን አድርጋችሁልናልና፡፡
እናንተ ወዳጆቻችን ለሁሉም ነገር – እልፍ ምስጋና፡፡
እናመሰግናለን!
የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች
የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንደሌሉ ገለፀ
• “የስርዓቱን ሽፍትነት ያመላክታል” 3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛ
• “የሚቀርብልን ምግብ ለእንሰሳትም መቅረብ የማይገባው ነው” 2ኛ ተከሳሽ አቶ አሸናፊ አካሉ
በዘመነ ካሴ የክስ መዝገብ ከ2ኛ -5ኛ መዝገብ ለተከሰሱት አቶ አሸናፊ አካሉ (2ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ደናሁን ቤዛ (3ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን (4ኛ ተከሳሽ) እና አቶ አንሙት የኔዋስ (5ኛ ተከሳሽ) በመከላከያ ምስክርነት የተጠቀሱት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት እንደሌሉ ማረሚያ ቤቱ ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛው ወንጀል ችሎት በላከው ደብዳቤ ገልፆአል፡፡ 19ኛ ወንጀል ችሎት ሀምሌ 29 ቀን 2007 ዓ.ም የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸውን ለምን እንዳላቀረበ እንዲያብራራ፣ እንዲሁም ለምስክርነት እንዲያቀርብ ለዛሬ ለጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም ለአራተኛ ጊዜ ቀጠሮ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው ቃሊቲ እንደሌሉ በደብዳቤ አሳውቋል፡፡
ተከሳሾቹ ማረሚያ ቤቱ ሲያጉላላቸው ቆይቶ አሁን የለም ማለቱ ትክክል እንዳልሆነ የገለፁ ሲሆን 2ኛ ተከሳሽ አቶ አሸናፊ አካሉ ማረሚያ ቤቱ ምላሽ የሰጠው በአራተኛው ትዕዛዝ መሆኑን ጠቅሶ የፍርድ ሂደታቸውን ከሚገባው በላይ እያጓተተ እንደሆነ ለፍርድ ቤቱ ገልፆአል፡፡ ‹‹መከላከል ከጀመርን አንድ አመት ከስድስት ወር ሆነ፡፡ በግዞት ነው ያለነው፡፡ የሚቀርብልን ምግብ ለእንሰሳትም መቅረብ የማይገባው ነው›› ያለው አቶ አሸናፊ የማረሚያ ቤቱን ምላሽ ‹‹ፌዝ ነው›› ብሎታል፡፡
3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛ በበኩሉ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን በመከላከያ ምስክርነት ሲጠቅሱ አቃቤ ህግ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ የሞትና የእድሜ ልክ ፍርደኛ እንደሆኑ በመጠቆም ተቃውሞ አሰምቶ እንደነበር፣ የእድሜ ልክና የሞት ፍርደኛ ቃሊቲ እንደሚታሰር ገልፆ ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው እንደሌሉ መግለፁ ‹‹የስርዓቱን ሽፍትነት ያመላክታል›› ብሏል፡፡ ‹‹የእድሜ ልክ ወይንም የሞት ፍርደኛ የት ነው የሚታሰረው?›› ሲልም ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
3ቱ ተከሳሾች የፀረ ሽብር ግብረ ኃይሉና ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ አንዳርጋቸውን እንደያዙ በቴሊቪዥን መግለፃቸውን አስታውሰው አሁንም ለሁለቱ አካላት ደብዳቤ እንደሚፅፉ ለፍርድ ቤቱ አሳውቀው የነበር ቢሆንም ከ6ኛ-9ኛ ያሉት ተከሳሾች ማረሚያ ቤቱ በፈጠረው ችግር የአቶ አንዳርጋቸውን ምስክርነት ለመስማት የፍርድ ሂደታቸው እየተጓተተባቸው በመሆኑ የአቶ አንዳርጋቸው ምስክርነት ቀርቶ ብይን እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡
ሆኖም ግን 4ኛ ተከሳሽ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን ‹‹ከአንዳርጋቸው ጋር ተገናኝተህ መመሪያ ተቀብለሃል ስለተባልኩ አቶ አንዳርጋቸው መጥቶ መመስከር አለበት›› ሲል አሁንም አቶ አንዳርጋቸው እንዲቀርቡለት ጥያቄውን አቅርቧል፡፡ ፍርድ ቤቱም 4ኛ ተከሳሽ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንዲቀርቡለት የሚያቀርበውን አቤቱታ ተመልክቶ ይገኙበታል ተብሎ ለታሰበው ተቋም ትዕዛዝ ለመስጠት ለጥቅምት 23 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ መሰጠቱን ነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የሎሚ መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ የ18 ዓመት እስራትና የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት ተላለፈበት
የሎሚ መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ የ18 ዓመት እስራትና የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት እንዲሁም በመፅሔት አሳታሚ ድርጅቱ ላይ የ200 ሺህ ብር ቅጣት ተወስኖበታል። ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ ከዓመት በፊት የሶስት ዓመት ከ3 ወር እስራት እንደተፈረደበት ይታወሳል።
ከ800 ሺህ ብር በላይ ታክስ በማጭበርበርና በሌሎች 14 ክሶች ጥፋተኛ የተባለው የሎሚ መጽሄት ዋና ስራ አስኪያጅ በ18 ዓመት ጽኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጣ ተወሰነ።
ውሳኔውን የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 8ኛ የወንጀል ችሎት ነው ያስተላለፈው።
ተከሳሾቹ ዳዲሞስ ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር እንዲሁም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ታዬ ግዛው ናቸው።
የፌደራል ገቢዎች እና ጉሙሩክ ባለስልጣን አቃቤ ህግ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው፥ ድርጅቱም ሆነ ስራ አስኪያጁ ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ ክሱ እስከተመሰረተበት ድረስ ለተከታታይ 5 ዓመታት ኦዲት አልተደረጉም።
በዚህ ሂደትም ድርጅቱም ሆነ ግለሰቡ የታክስ ማጭበርበሮችን ሲያከናውን ቆይቷል ሲል የአቃቤ ህግ ክስ ያስረዳል።
የተጨማሪ እሴት ታክስ እና የገቢ ግብር መሰወር የሚለውም በወንጀል ድርጊቱ ማስረጃዎች ጉዳይ ሲሆን፥ እንደ አቃቤ ህግ ገለጻ በዚህ ሂደት ውስጥ ድርጅቱ እና ስራ አስኪያጁ ለመንግስት መግባት የነበረበትን ከ800 ሺህ ብር በላይ አሳጥተዋል ይላል።
በዚህ የክስ መዝገብም ግለሰቡ በችሎቱ አልቀረበም።
ይህን ተከትሎም የክስ ሂደቱ በሌሉበት እንዲቀጥል በተሰጠው በይን መሰረት አቃቤ ህግ የሰው እና የሰነድ ማስረጃዎችን ለፍርድ ቤቱ አቅርቧል።
ጉዳዩን ሲመለክት የቆየው የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 8ኛ የወንጀል ችሎት በተከሳሾች ላይ የቀረበው ማስረጃ ወንጀሉን ስለመፈጸማቸው የሚያረጋግጥ ነው ሲል ቅጣቱን አስተላልፏል።
የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ስምንተኛ የወንጀል ችሎት ዛሬ በዋለው ችሎት ዳዲሞስ ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት በ200 ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲሁም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ግዛውታዬ ላይ ደግሞ የ18 ዓመት ጽኑ እስራት እና የ100 ሺህ የገንዘብ ቅጣት አስተላልፏል።
የድርጅቱ ሎሚ መፅሔት (ዳዲሞስ ኢንተርቴይመንት) ባለቤትና ማኔጅንግ ዳይሬክተሩ አቶ ግዛው ታዬ ከዚህ በፊት “አመጽ በማስነሳት እና መሰል የሽብርተኝነት ወንጀሎች” ክስ ተመስርቶበት በ50 ሺህ ብር ዋስ ከተለቀቀ በኋላ መሰደዱ ይታወቃል፡፡ የአሁኑ ክስና ፍርድም ተከሳሹ በሌለበት ተወስኗል፡፡
ፍርድ ቤቱ ያሳለፈውን ውሳኔ በተመለከተ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽንን/ሬዲዮ ፋናን/ ዋቢ በማድረግ ቃልኪዳን ትዩብ ዘግቧል፡፡





