የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት ጥያቄ…
ከዚህ ቀደም በቤጌምድር (ጎንደር) ጠቅላይ ግዛት የነበሩና ህወሓት/ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ የትግራይ ክልል ስር ያሉት የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ “እኛ አማራ ነን፣ ያለፈቃዳችን ተገደን ነው ወደ ትግራይ የተካለልነው፣ የአማራ ማንነት ጥያቄያችን ተመልሶ ወደነበርንበት ጎንደር አማራ እንጠቃለል” የሚል ጥያቄን ቢያነሱም፤ ከመንግሥት በኩል እስካሁን ምላሽ አላገኙም፡፡ የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ አባላት ተገደው ያለፈቃዳቸው ወደ ትግራይ እንድንጠቃለል ተደርገናል ከሚለው ጥያቄ በተጨማሪ አማራ በመሆናችን ብቻ በትግራይ ክልል አስተዳደር ከፍተኛ በደል ተፈፅሞብና፤እየተፈፀመብንም ይገኛል በማለት የቀደመው የአማራ ማንነታችን ተመልሶ ወደነበርንበት ጎንደር አስተዳደር አማራ ክልል ለመጠቃለል አንዱ ምክንያታቸው እንደሆነ በተደጋጋሚ ሲገልፁ ይስተዋላል፡፡
እንደ ጥያቄ አቅራቢ ኮሚቴዎች አገላለፅ፤የነበረው የወልቃይት ጠገዴ አስተዳደር ወሰን ክልልም በሰሜን ተከዜ ወንዝ፣ በሰሜን ምዕራብ ኤርትራ፣ በምስራቅ የቀድሞው ትግራይ ጠቅላይ ግዛት ፣ በምዕራብ ሱዳን በደቡብ የቀድሞው ቤጌምድር (የአሁኑ ጎንደር) አስተዳደር አካል እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ አካባቢውም በአሁን ወቅት በትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን በሚል አስተዳደር ስር በ3 ወረዳዎች የተዋቀሩት ቃፍታ ሁመራ፣ ወልቃይት እና ጠገዴ ወረዳዎች በቀድሞ ቤጌምድር (ጎንደር) ጠቅላይ ግዛት ወልቃይት ጠገዴ አውራጃ አስተዳደር እንደነበርም ጠቁመዋል፡፡ ለዚህም የተለያዩ ቀደምት የአስተዳደር ሰነዶችን እና የአማራ ማንነትን ያረጋግጣሉ የሚሏቸው መረጃዎችን አያይዘው በሕገ-መንግሥቱ መሰረት ጥያቄ ቢያቀርቡም ከሚመለከተው አካል እስካሁንም ምላሽ አለማግኘታቸውን ገልፀዋል፡፡
በተለይ የወልቃይት ጠገዴ ማኀበረሰብ ተወካዮች የአማራ ማንነት ጥያቄ ይዘው ላለፉት 25 ዓመታት ጀምሮ ጥያቄ ያቀርቡ እንደነበር እንደሚያውቁ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲአዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) ሊቀመንበር ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ አስታውሰዋል፡፡ ፕሮፌሰሩ ይህን ያስታወሱት ባለፈው ከኦሮሚያ እና በሌሎች ሀገራዊ ወቅታዊ ጉዳይ በተያያዘ መድረክ በዋና ጽህፈት ቤቱ በሰጠው መግለጫ ላይ ነበር፡፡
የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላቱም በተለያየ ጊዜ በተለያየ መገናኛ ብዙኃን እንደገለፁት ከሆነ፤ አማራ ሆነው ሳለ ሳይወዱ በግድ ወደ ትግራይ መጠቃለላቸውን፣ ልጆቻቸውም ከአፍ መፍቻ አማርኛ ውጭ ተገደው በትግርኛ እንዲማሩ መደረጉን፣ የአካባቢው ህዝብ ከአማርኛ በተጨማሪ አረብኛ እና ትግርኛም ባላቸው የድንበር ግንኙነት አማካኝነት መናገር ቢችሉም፤ ባህላቸውን እና ማንነታቸውን የሚገልፁበት ቋንቋ አማርኛ መሆኑን እና የማንነት ስነ ልቦናቸውም አማራ እንደሆነ፤ ይህንንም ላለፉት 25 ዓመታት በተደጋጋሚ ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላትና ተቋማት ጥያቄ ሲያነሱ ግድያ፣ እስራት፣ ድብደባ፣ ማስፈራራትና ስደት እንደደረሰባቸው፣ ከጥያቄው ጋር በተያያዘ የትግራይ ክልል መስተዳደር ግድያን ጨምሮ የተለያዩ በደሎችንም ይፈፅም እንደነበርና አሁንም እየፈፀመ እንደሆነ ሲያነሱ ይደመጣል፡፡
የአማራ ማንነት ፈቃዳችን ሳይጠየቅ ተገደን እንድንጠቃለል ተደርገናል ለሚሉት የትግራይ ክልል መስተደዳደርና በፌደራሉ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ጥያቄን የሚያቀርቡ ተወካዮች በአዲስ አበባም ለተወሰኑ ቀናት በፖሊስና ደህንነት አባላት ታግተው መለቀቃቸው የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮን ጨምሮ በተለያየ መገናኛ ብዙኃን የተዘገበ ሲሆን፤ በተለይ የትግራይ ክልል አስተዳደርና እና የክልሉ ምዕራባዊ ዞን የመንግሥት ኃላፊዎች አሁንም ከፍተኛ ማስፈራሪያ እና ዛቻ እየፈፀሙ መሆኑን የኮሚቴው አባላት ገልፀዋል፡፡ አዲሱን የአስተዳደር ክልል መዋቅር የመሰረተው ኢህአዴግ መንግሥት እና የትግራይ ክልል መስተዳደር ቀድሞ የነበረውን የአማራ ስነ ህዝብ ስብጥር፣ ባህል እና ማንነትን ለማጥፋትና መቀየር ላለፉት 25 ዓመታት ሙሉ ሲሰሩ ተቃውሞ ብናቀርብም ሰሚም አላገኘንም፣ እንደወንጀለኛም ተቆጥረናል ሲሉ ቅሬታ ያቀርባሉ፡፡ ከዛ በተጨማሪ የእኛ የአማራ ማንነት እንደሌለ ተቆጥሮና ተክዶ ልጆቻችን በአማርኛ እንዳይማሩና እንዳይናገሩ፣ በአማራ ማንነታቸው እንዲያፍሩና የነበረውን የአማራ ማንነት ባህል እንዳያንፀባርቁ ተደርገዋል፤ በግድም የትግርኛ ቋንቋ እንዲነገሩ፣ የትግራይ ማንነት ባህልን ብቻም እንዲያንፀባርቁ ተደርገዋል፤ይህም ህገ-መንግሥቱን እንደሚፃረር ብናነገርም የከፉ በደሎች ተፈፅመውብናል ይላሉ፡፡
በተለይ አካባቢውን በተመለከተ በአጼ ኃይለስላሴ ዘመን የትግራይ ጠቅላይ ግዛት አስተዳዳሪ የነበሩትና የአጼ ዮሐንስ 4ኛ የልጅ ልጅ የሆኑት ልዑል መንገሻ ስዩም ወልቃይት ጠገዴ በሳቸው ዘመንም ሆነ ከዛ በፊት ወልቃይት ጠገዴ በትግራይ አስተዳደር ስር እንዳልነበር እንደሚያውቁ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ገልፀው ነበር፡፡ የትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን አስተዳደር ሃላፊ በኩላቸው ወልቃይት ጠገዴ የትግራይ እንደሆነ እና ከዛ ጋ ተያይዞ የሚነሳ የማንነት ጥያቄ የህዝቡ እንዳልሆነ ከመግለፃቸው በተጨማሪ የአማራ ማንነት ጥያቄ የሚያነሱ ተወካዮች የሚቃወም ሰልፍም በአካባቢው ተደርጎ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የአማራ ማንነት ጥያቄን ለሚያነሱ ማኀበረሰብ አባላትና ተወካዮች ጥያቄያቸው መፍትሄ አሊያም ህዝባዊ ውሳኔ ያገኝ ዘንድ ባሉበት ወልቃይት ጠገዴ ህዝባዊ ስብሰባና ሰልፍ ቢጠይቁም በትግራይ ክልልም ሆነ በክልሉ ምዕራባዊ ዞን አስተዳደር ሊፈቀድ ባለመቻሉ የማኀበረሰቡ ተወካዮች ህዝባዊ ስብሰባዎቻቸውን በአጎራባች የአማራ ክልል ከተሞች ለማድረግ መገደዳቸውን ተናግረዋል፡፡
በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ስለ ኦሮሚያው ተቃውሞ እና ስለ ጎንደር የቅማንት ማኀበረሰብ ማንነት ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ችግር ቢገልፁም፤ ስለ ወልቃይ ጠገዴ አማራ ማንነት ጥቄን ግን ሳያነሱት ከማለፋቸው በተጨማሪ በጥቅሉ ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ከማንነት ጋር በተያያዘ ያልተመለሰ ጥያቄ የለም ሲሉ ተደምጠዋል፡፡ አዲስ ሚዲያ ባለው መረጃ መሰረት የብሔረሰብ ማንነት እና የራስ አስተዳደር ጋ በተያያዘ በትግራይ ወልቃይት ጠገዴን እና በኣማራ ክልል ምላሽ አግኝቷል ከተባለው የቅማንት ማኀበረሰብ ማንነት ጥያቄ በተጨማሪ በኦሮሚያ፣ በደቡብ እና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች ከክልሎቹ እስከ አዲስ አበባው ፌዴሬሽን ምክር ቤት ድረስ እስካሁንም ምላሽ ያላገኙ በርካታ ጥያቄዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡
አቶ ኃይለማርያም በኦሮሚያ የተነሳው ተቃውሞ ምክንያት መንግሥታቸው እና ፓርቲያቸው መሆኑን ቢገልፁም፤ ህዝባዊ ተቃውሞው እንደቀጠለ ነው
ባለፈው ህዳር አጋማሽ 2008 ዓ.ም. በድጋሚ የጀመረው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞ በተለያዩ የክልሉ ከተሞች እና ወረዳዎች ቀጥሏል፡፡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ከሆነ በተቃውሞው ላይ መንግሥት እየወሰደ ያለው የኃይል እርምጃም ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፤ በዚህም የሟቾች ቁጥር መጨመሩ ታውቋል፡፡ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ተቃውሞን ለማፈን እና ለማርገብ እየተወሰደ ባለው የኃይል እርምጃ ከሚገደሉት በተጨማሪ ጉዳት የደረሰባቸውና የታሰሩ ሰዎች ቁጥርም ጨምሯል፡፡ ተቃውሞን እና የርሃቡን ሁኔታ ለመዘገብ ባለፈው የካቲት 28 ቀን 2008 ዓ.ም.ወደ ምስራቅ የሀገሪቱ ክፍል ለዘገባ ተንቀሳቅሰው የነበሩት የብሉምበርግ ዘጋቢ ዊሊያም ዳቪሰን እና ለተለያየ መገናኛ ብዙኃን በኢትዮጵያ ወኪል ሆና የምትሰራው ጄሲ ፎርትንና አስተርጓሚያቸው በኢትዮጵያ የፀጥታ ሃይሎች ያለምንም ማብራሪያ ከአዋሽ ከተማ ወደ አዲስ አበባ በፌዴራል ፖሊስ ታጅበው እንዲመለሱ ከተደረገ በኋላ አዳር ታስረው መለቀቃቸውን አስታውቀዋል፡፡ ጋዜጠኞቹም ለአንድ ቀን ከታሰሩ በኋላ መለቀቃቸውንም ጋዜጠኞቹ በማኀበራዊ ገፆቻቸው ላይ ይፋ አድርገዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርም ደሳለኝ ባለፈው ሳምንት መጋቢት 2 ቀን 2008 ዓ.ም. የመንግሥታቸውን የ6 ወር የስራ አፈፃፀም ሪፖርት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡበት ወቅት፤ በኦሮሚያውም ሆነ በአማራ ክልል ጎንደር እና በሌሎች አካባቢዎች የተፈጠረው ችግር በመንግሥታቸው አስተዳደር ውስጥ ባለ የመልካም አስተዳደር አለመኖር፣ ሙስና እና ኪራይ ሰብሳቢነት ችግር መሆኑን እና በሌላ አካል ላይ ጣት መቀሰር እንደማይፈልጉ በመጥቀስ ለዚህም መንግሥትና እና ፓርቲያቸው ኢህአዴግ ኃላፊነቱን እንደሚወስድ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ጠቅላይ ሚኒስትሩ እና የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሚኒስተር አቶ ጌታቸው ረዳን ጨምሮ የተለያዩ የመንግሥት ኃላፊዎች ከህዝባዊ ተቃውሞው ጀርባ ኦነግ፣ አርበኞች ግንቦት 7 ፣ የኤርትራ መንግሥት እና በሀገር ቤት በይፋ የሚንቀሳቀሰውን ኦፌኮ/መድረክን ተጠያቂ ሲያደርጉ የነበረ ቢሆንም፤ በፓርላማው የሪፖርት ውሎ ግን የተለየ ምክንያት ሲሰጡ ተስተውሏል፡፡
እንደ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አባባል ከሆነ የህዝባዊ ተቃውሞ ምክንያት ማንም ላይ ማላከክ አይቻልም፣ ኦሮሚያ ስለተነሳ ሌላ ቦታ ችግር የለም ማለት አይደለም፣ ይሄ ሁሉ ባለው ብልሹ አሰራር የተፈጠረ ችግር ነው፣ ለዚህም መንግሥት ኃላፊነቱን በመውሰድ ህዝቡን ይቅርታ ይጠቃል ብለዋል፡፡ ምንም እንኳ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኦሮሚያም ሆነ በአማራ ክልል በተለይ የቅማንት ማኀበረሰብ የማንነት ጥያቄ ጋ ተያይዞ ለተፈጠረው ችግር መንግሥታቸውና ፓርቲያቸው ኃላፊነቱን እንደሚወስድ ቢገልፁም ህዝባዊ ተቃውሞውን ተከትሎ መንግሥት የወሰደውን እና እየወሰደ ያለውን የኃይል እርምጃ ሲቃወሙ የነበሩ የፖለቲካ ፓርቲ አባላትና አመራሮች፣ ጋዜጠኞች እና ተማሪዎችን ጨምሮ ከ4 ሺህ በላይ ስለታሰሩት፣ ከ270 በላይ ስለተገደሉትና በርካቶች ስለቆሰሉ ዜጎች ጉዳይ ከመናገር ተቆጥበዋል፡፡
በተለይ በኦሮሚያ ክልሉን ያስተዳድራል የሚባለውና የኢህአዴግ አባል ድርጅት የሆነው ኦህዴድ መዕከላዊ ኮሚቴ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ በቅርቡ በአዳማ/ናዝሬት ባደረገው ድንገተኛ ልዩ ስብሰባ አቶ ዳባ ደበሌ እና አቶ ዘለዓለም ጀማነህ የተባሉ የክልሉና የፌደራል ከፍተኛ ኃላፊዎችን ከነበሩበት የክልሉም ሆነ የፌደራል ስልጣን ማንሳቱን ይፋ ቢያደርግም ህዝባዊ ተቋውሞው ግን ይህ እስከተጠናቀረበት ድረስ ቀጥሏል፡፡
ህዝባዊ ተቃውሞ መቀጠሉን ተከትሎ መንግሥት በቅርቡ የካቲት 16 ቀን 2008 ዓ.ም ሌሊት በምዕራብ ሸዋ ዞን ቶኬ ኩታዬ ወረዳ ጎሮሶሌ ከተማ ውስጥ ሞቱማ ፈዬራ የተባለ የ20 ዓመት ወጣትና የ10ኛ ክፍል ተማሪን ጨምሮ የተለያዩ ዜጎች መገደላቸው ተጠቁሟል፡፡
ለአራት ወራት የዘለቀውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ በፀጥታ ኃይሉ የሚወሰደው የኃይል እርምጃዎች እንዳሳሰበቸው የገለፁ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ባለፈው የካቲት 30 ቀን 2008 ዓ.ም. “እኛ ሽብርተኞች አይደለንም ፤ የኦሮሞ ሕዝብን መግደል አቁሙ” የሚሉ መፈክሮችን በመያዝ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ 6 ኪሎ ዋናው ግቢ አካባቢ ተነስተው ወደ አሜሪካ ኤምባሲ ሲያቀኑ የነበሩ ተማሪዎች በፖሊስ ድብደባ ሰልፉ እንደተበተነ እና በርካታ ተማሪዎችም ታፍሰው መታሰራቸው ተጠቁሟል፡፡ ተማሪዎችም ሰላማዊ መሆናችንን ለመግለፅ ነጭ ጨርቅ እያውለበለብን ነበር ያሉ ሲሆን መንግሥት ለምን ሰልፉን እንደበተነ እና ተማሪዎችን እንዳሰራቸው እስካሁን የገለፀው ነገር የለም፡፡