ሁለት ኢትዮጵያውያን ካይሮ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን በራፍ ራሳቸውን አቃጠሉ
ሁለት ኢትዮጵያውያን ካይሮ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን በራፍ ራሳቸውን አቃጠሉ። በቅርቡ ኦሮሚያ ከተካሄደው መጠነ ሰፊ ግድያና እስራት ሸሽተው ግብጽ መድረሳቸው የተገለጸው እነዚህ ሁለት የኦሮሞ ተወላጅ የሆኑ ኢትዮጵያውያን፣ ራሳቸውን ያቃጠሉት በተቃውሞ መሆኑን ተመልክቷል።
ሁለቱ ኢትዮጵያውያን ራሳቸውን በማቃጠል ተቃውሟቸውን የገለጹት የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን የካይሮ ቢሮ የስደተኝነት ጥያቄያቸው ውድቅ በማድረጉ እንደሆነም መረዳት ተችሏል። በግብፅ ካይሮ የሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን (UNHCR) በርካታ ኢትዮጵያውያን የጥገኝነት ጥያቄ ውድቅ በማድረጉ ብዙዎች በባህር ወደ አውሮፓ ለመሻገር በሚያደርጉት ጉዞ ህይወታቸው ማለፉ ይታወቃል።
ለጊዜው ስማቸው ያልታወቀው ኢትዮጵያውያን መቃጠላቸውን ተከትሎ ፖሊስ በስፍራው መድረሱን እና ራሳቸውን ካቃጠሉት ኢትዮጵያውያን አንዱ ቆዳው ጉዳት መታየቱን ተጠቁሟል፡፡ የሁለቱም ጤንነት አሁን በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ እስካሁን ለማወቅ አልተቻለም።
የእነ ኦሞት አግዋ ላይ ዛሬም የአቃቤ ህግ ምስክር ሳይሰማ ተቀጠረ
ከመጋቢት 2007 ዓ.ም ጀምሮ የዋስ መብት በፍርድቤት ተከልክለው በእስር የሚገኙት እነ ኦሞት አግዋ ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. የህግ አማካሪና ጠበቃቸው አመሃ መኮንን በህመም ምክንያት ችሎት ባለመገኘታቸው መዘገቡ የአቃቤ ህግ ምስክር ለመስማት ብቻ ለዘጠነኛ ጊዜ ተቀጥሯል፡፡
አንደኛ ተከሳሽ ኦሞት አግዋ ጠበቃችን አመሃ መኮንን ታመው ሆስፒታል የተኙ ስለሆነ ያለእርሳቸው ውክልና ምስክር እንዳይሰማብን ፍርድቤቱ አጭር ቀጠሮ ይስጠን ሲሉ ሶስቱንም ተከሳሾች ወክለው ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡
በዕለቱ ችሎት አቃቤ ህግ አሉኝ ካላቸው ሰባት ምስክሮች መካከል ሶስቱ በችሎቱ ምስክርነታቸውን ለመስጠት ቀርበው ነበር፡፡
ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለአቃቤ ህግ ምስክር ለመሆን የመጡት ቄስ ሽብሩ ኦጅራ በተደጋጋሚ መጥተው ሳይመሰክሩ ተመልሰውብኛል ስለዚህ እንዲመሰክሩ ይደረግልኝ ብሎ ለተከራከረው አቃቤህግ፣ ዳኛ ታረቀኝ አማረ የስነስርዓት ህጉ ተከሳሾች ያለጠበቃቸው ውክልና እንዲከራከሩ አይፈቅድም በሚል ጥያቄውን ውድቅ አድርገውታል፡፡
የአቃቤ ህግ ምስክር ቄስ ሽብሩ ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለምስክርነት ለመጡበት የሁለት ቀን ትራንስፖርት እና አበል እንዲከፈላቸው እንዲሁም ዛሬ የቀረቡ ምስክሮች ያለምንም የፍርድቤት መጥሪያ ሌሎች ተጨማሪ የአቃቤህግ ምስክሮች በጠቅላላ በቀጣይ ቀጠሮ ነሐሴ 9 ቀን 2008 ዓ.ም እንዲቀርቡ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ወንጀል ክስ ቀርቦባቸው ክሳቸው ከነሐሴ 29 ቀን 2007 ዓ. ም ጀምሮ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት አየታየ የሚገኛው የእነ ኦሞት አግዋ ሶስት ተከሳሾች ያሉበት(ኦሞት አጉዋ፣ አሽኔ አስቲን እና ጀማል ኡመር ) የክስ መዘገብ ላይ አቃቤ ህግ ምስክሮችን ማሰማት የጀመረው መጋቢት 6 ቀን 2008 ዓ.ም ነው፡፡
ምንጭ፡- EHRP
መንገድ ለመስራት የተዋዋለ የህንድ ኩባንያ ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ ይዞ ተሰወረ
በቅርቡ አንድ ቢሊዮን ብር አካባቢ የሚደርስ የመንገድ ፕሮጄክት ተሰጥቶት የነበረ አንድ የህንድ ስራ ተቋራጭ ኩባንያ የተረከበውን ስራ ሳያጠናቅቅ ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ ይዞ ከሃገር ኮበለለ።
በዚሁ ፕሮጄክት ስር ይሰሩ የነበሩ ከ200 በላይ ሰራተኞች ሊከፈላቸው የሚገባ የአንድ ወር ከግማሽ ደሞዝ ሳይከፈላቸው መቅረቱን በመግለጽ ላይ መሆናቸው ታውቋል።
የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን በበኩሉ የ958 ሚሊዮን ብር የመንገድ ፕሮጄክት ተሰጥቶት ስራውን ሳያጠናቅቅ የተሰወረው ኩባንያ ከሃገር ይዞ የወጣውን ገንዘብ ለማስመለስ ህጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቋል።
ኤስ ኢ ደብሊው (S.E.W) የተሰኘው ኩባንያ ከሶስት አመት በፊት 66 ኪሜ ርዝመት ያለው ከሃዋሳ ጭኮ የሚደርስ መንገድ እንዲሰራ ውል ተሰጥቶት የነበረ ሲሆን፣ መንገዱ በተያዘው ወር ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቅ እንደነበር ታውቋል።
ይሁንና፣ በስራው ላይ ከፍተኛ መጓተት ታይቶበታል የተባለው ኩባንያው እስካሁን ድረስ 22 ኪሎሜርት ብቻ እንደሰራ የመንገዶች ባለስልጣን ድርጅት ከሃገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ገልጿል።
ድርጅቱ የ958 ሚሊዮን ብር ፕሮጄክት ተሰጥቶት የነበረ ሲሆን፣ በሶስት አመት ውስጥ ምን ያህል ገንዘብ እንደወሰደ የተገለጸ ነገር የለም።
የህንዱ ኩባንያ በአጠቃላይ የተሰጠው ገንዘብ ከመግለፅ ተቆጥቦ የሚገኘው የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን፣ ድርጅቱ በስሩ ለሚሰሩ ሃገር በቀል ድርጅቶች መክፈል የነበረበትን ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ ከሃገር ይዞ መውጣቱን ይፋ አድርጓል።
ከአፍሪካ ልማት ባንክ በተገኘ የገንዘብ ብድር ስራውን ሲሰራ የቆየው የህንዱ ኩባንያ ከሁለት ሳምንት በፊት ፕሮጄክቱ አጓትቷል ተብሎ የተሰጠው ኮንትራትን እንዲቋረጥ ተደርጎ እንደነበር ታውቋል።
ይሁንንና፣ የኮንትራቱ መቋረጥን ተከትሎ የኩባንያው ሃላፊዎች ገንዘቡን ይዘው ከሃገር እንደወጡ የተገለጸ ሲሆን፣ ኩባንያው በአጠቃላይ ስለተከፈለው ገንዘብ ምርመራ እየተካሄደ መሆኑን ለመረዳት ተችሏል።
ከወራት በፊት በተመሳሳይ ሁኔታ በጋምቤላ ክልል በእርሻ ስራ ላይ የተሰማሩ የህንድ ባለሃብቶች የተረከቡትን ብድር ሳያወራርዱ ከሃገር መኮብለላቸውን የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ገልጾ እንደነበር ይታወሳል።
በርካታ የህንድ ኩባንያዎች በአሁኑ ወቅት በስኳር ፋብሪካ እና በመንገዶች እንዲሁም በተለያዩ የኢንቨስትመንት ስራዎች ላይ ተሰማርተው እንደሚገኙ የኢሳት ዘገባ አመልክቷል።
በእነ በቀለ ገርባ የሰብዓዊ መብት ጥሰት አቤቱታ ላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላለፈ
*ወህኒ ቤት ለአቶ በቀለ ገርባ የታዘዘውን መድሃኒት ፈልጌ ማግኘት አልቻልኩም ብሏል
በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ በሽብር ተከሰው በቂሊንጦ እስር ቤት የሚገኙት እነ በቀለ ገርባ (22 ሰዎች) የእስር ቤቱ አስተዳደር የሰብዓዊ መብት ጥሰት እያደረሰባቸው መሆኑን ሰኔ 15 ቀን 2008 ዓ.ም ለፍርድ ቤት ባቀረቡት አቤቱታ ላይ ችሎቱ ውሳኔ አሳልፏል፡፡
ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት (ጉዳያቸውን ያይ የነበረው 19ኛ ወንጀል ችሎት እንደነበር ይታወሳል 19ኛ ችሎት ለሁለት ተከፍሎ አዲስ 4ተኛ ችሎት የሽብር ጉዳዮችን ማየት ጀምሯል) በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታና በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ሰኔ ቀን 2008 ዓ.ም የሰጠውን መልስ ተመልክቶ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡
ተከሳሾች ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም ወደ ፍርድ ቤት ሲወሰዱ ድብደባ እንደደረሰባቸው፣ ልብሶቻቸው እንደተወሰዱባቸው፣ በጨለማ ቤት ስለመታሰራቸው፣ በህክምና የታዘዘን መድሃኒት እንዳያገኙ ስለመደረጋቸው፣ ቤተ መጽሐፍት እንዳልተሟላላቸው፣ በቤተሰቦቻቸው እንዳይጎበኙ ገደብ እንደተጣለባቸው፣ ገንዘብ እንደተወሰደባቸው እና ሌሎች የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እንደደረሱባቸው አቤቱታ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር በበኩሉ አቤቱታቸውን ‹‹የተቋሙን ስም ለማጥፋት›› የቀረበ ነው ሲል አጣጥሎ መልስ መስጠቱ ይታወቃል፡፡
በዚህ ላይ ፍርድ ቤቱ ዛሬ ውሳኔውን አሳውቋል፡፡ በዚህ መሰረት በሀኪም የታዘዘን መድሃኒት ማግኘት አልቻልንም በሚል ተከሳሾች ላቀረቡት አቤቱታ ፍርድ ቤቱ የእስር ቤቱ አስተዳደር ተጠርጣሪዎቹ መድሃኒቱን እንዲያገኙ እንዲፈቅድ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ ተከሳሾች ድብደባ ደርሶብናል፣ ገንዘብም ተወስዶብናል በሚል ያቀረቡት አቤቱታን በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ድርጊቱ ተፈጽሞ ከሆነ ወንጀል ስለሆነ አስፈላጊውን ማጣራት አድርገው ተከሳሾች በህግ ሊጠይቁ የሚገባቸው ስለሚሆን በዚህ የክስ መዝገብ ውሳኔ ሊሰጥበት አይችልም ብሏል፡፡
ተከሳሾች በጨለማ ክፍል መታሰራቸው ህግን ያልተከተለና የሰብዓዊ መብት ጥሰት መሆኑን በተመለከተ ያቀረቡት አቤቱታ ላይ ፍርድ ቤቱ ‹‹በማረሚያ ቤቱ በኩል ጨለማ ቤት የለም ተብሏል፤ ተከሳሾች ደግሞ ጨለማ ክፍል ታስረናል ብለዋል፡፡ ይህ ጉዳይ ማጣራትን የሚጠይቅ ስለሆነ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ጉዳዩን አጣርቶ ለሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም አስተያየቱን ይስጥበት›› የሚል ውሳኔ አስተላልፏል፡፡
የቤተ መጽሐፍትና የቴሌቪዥን አለመሟላትን እና የቤተሰብ ጥየቃ ሰዓትን በተመለከተ በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታ ፍርድ ቤቱ ‹የማረሚያ ቤቱን አስተዳደራዊ አሰራር የሚመለከት ስለሆነ ውሳኔ አንሰጥበትም› በሚል አልፎታል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ አቶ ደጀኔ ጣፋ በቤተሰብ መጎብኘት ህገ መንግስታዊ መብታችን እንጂ የአስተዳደር ጉዳይ ነው ተብሎ የሚታለፍ እንዳልነበር በመጥቀስ በውሳኔው ላይ ቅሬታቸውን ለችሎቱ አሰምተዋል፡፡
ሌላ የተሰሙ አቤቱታዎች
ፍርድ ቤቱ ቀደም ብሎ በተከሳሾች ለቀረቡት አቤቱታዎች ውሳኔ ቢያሳልፍም ዛሬም ሌሎች አቤቱታዎች ቀርበውለታል፡፡ በዋናነት አቶ በቀለ ገርባ የታዘዘላቸውን መድሃኒት አለማግኘታቸውን በተመለከተ የቀረበ አቤቱታ ሲሆን፣ አቶ በቀለ መድሃኒት ከታዘዘላቸው ሁለት ወራት ቢቆጠርም መድሃኒቱን ማግኘት አለመቻላቸውን ገልጸዋል፡፡
የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር ዋና ኦፊሰር የሆኑት ተሾመ ስዩም በጽሁፍና በቃል በሰጡት መልስ እንደተመለከተው ለአቶ በቀለ ገርባ በሀኪም የታዘዘላቸው መድሃኒት በአስተዳደሩ ባለሙያዎች በመንግስትና በከነማ መድሃኒት ቤቶች ተፈልጎ ሊገኝ አልቻለም፡፡ ‹‹መድሃኒቱ ተፈልጎ አለመገኘቱንና የሚችሉ ከሆነ በቤተሰብ በኩል እንዲሞክሩ ለአቶ በቀለ ነግሬያቸዋለሁ›› ብለዋል ዋና ኦፊሰሩ፡፡
አቶ በቀለ ገርባ በበኩላቸው በኦፊሰሩ የተሰጠው መልስ ስህተት ነው ብለዋል፡፡ ‹‹ዛሬ ፍርድ ቤት እንደምቀርብ አውቀው የተዘጋጁበት መልስ ነው፡፡ ለእኔ የነገሩኝ ነገር የለም›› ብለዋል አቶ በቀለ፡፡ ፍርድ ቤቱ ይህን በተመለከተ ማረሚያ ቤቱ በቤተሰብ በኩል መድሃኒቱ ተገዝቶ እንዲገባ እንዲፈቅድ ማሳሰቢያ በመስጠት አልፎታል፡፡
ሌላው አቶ በቀለን ከሚኖሩበት አዳማ ከተማ ተመላልሰው ከሚጠይቋቸው ቤተሰቦቻቸው መካከል ልጃቸው ቦንቱ በቀለ ባለተገለጸ ምክንያት አባቷን በእስር ቤት እንዳትጠይቅና ምግብ እንዳታደርስላቸው መከልከሏን የአቶ በቀለ ጠበቃ ለችሎት በመግለጽ፣ ልጃቸው አባቷን እንድትጠይቅና ስንቅ እንድታቀብላቸው እንዲፈቀድላት ችሎቱን ጠይቀዋል፡፡ ችሎቱ ዋና ኦፊሰር ተሾምን ስለጉዳዩ ቢጠይቅም፣ ኦፊሰሩ ‹የማውቀው ነገር የለም፣ ግን ለሚመለከታቸው አካላት አሳውቃለሁ› የሚል መልስ ሰጥተዋል፡፡
በሌላ በኩል 22ኛ ተከሳሽ የስዋህሊኛ ቋንቋ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው በተደጋጋሚ አቤቱታ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ ስዋህሊኛ አስተርጓሚ ኬንያ ኤምባሲ ጭምር ተፈልጎ ማግኘት እንዳልተቻለ ተገልጹዋል፡፡ በመሆኑም ተከሳሹ በመጠኑ እግሊዝኛ ቋንቋ ስለሚረዱ የእንግሊዝኛ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው በጠበቃቸው በኩል አሳስበዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የመቃወሚያ ብይን ለማሰማት ለሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ ይታወሳል፡፡
ምንጭ፡- EHRP