በአዲስ አበባ የኮሌራ በሽታ አስጊ ደረጃ ላይ መድረሱን የተባበሩት መንግሥታት የውስጥ መልዕክት ልውውጦች አጋላጡ
(አዲስ ሚዲያ) በአዲስ አበባ በንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የአካባቢ ንፁህና ጉድለት ችግር ምክንያት ከተከሰተው አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) የከተማዋ ነዋሪዎችን ጤና ማናጋት ከጀመረ ሶስተኛ ሳምንቱን አስቆጥሯል፡፡ በንፁህ የውሃ አቅርቦት እና በአካባቢ ንፁህና ጉድለት ምክንያት የሚከሰተው የኮሌራ በሽታ በከተማው መዛመት፤ ዓለም አቀፍ ተቋማት ሰራተኞችን ጨምሮ በርካታ ነዋሪዎችን ለከፋ በሽታ መዳረጉ ታውቋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ባለፈው ሰኞ ሐምሌ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በከተማዋ ለሚገኙ ለሌሎች የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሰራተኞች ባሰራጨው የውስጥ መልዕክት መሰረት፤ ሰራተኞቹ የኮሌራ ክትባት እንዲወስዱ አሳስቧል፡፡ በተለይ ኮሌራ በተበከለ ምግብና ውሃ አማካኝነት የሚዛመትና በንፁህና ጉድለት የሚከሰት በሽታ ሲሆን፤ ወዲያውኑ ተገቢውን ህክምና በጤና ተቋማት ማድረግ ካልተቻለ፤ በአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት የሰውነትን ፋሳሽ በመሳጣት ለሞት እንደሚዳርግ ይታወቃል፡፡
በሽታውን በተመለከተ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሀገር ቤት በመንግሥት ቁጥጥር ስር ለሚገኙ መገናኛ ብዙኃን በሰጠው መግለጫ፤ አተት የተከሰተው የወንዝ ውሃ በሚጠቀሙ ዜጎች ላይ እንደሆነ እና ለዚህም በወንዝ ዳር አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች የመፀዳጃ እና ፍሳሽ ማስወገጃዎቻቸውን ከወንዝ በማገናኘታቸው እንደሆነ በቃል አቀባዩ አህመድ ኢማኖ በኩል አስታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ከሆነ፤ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር የንፁህ የመጠጥ ውሃ ተገቢው ቁጥጥርና ክትትል ባለመደረጉ እና በከተማዋ በተከማቸው ቆሻሻ አማካኝነት እንደሆነ የከተማዋ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ምንጮች ማረጋገጣቸው ተነግሯል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የከተማው የንፁህ መጠጥ ውሃ ጥራት ባልተጠበቀበት ሁኔታ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የከተማው ነዋሪ በመጪው 2009 ዓ.ም. ከዚህ ቀደም ከሚከፍለው የቧንቧ ውሃ ተጨማሪ ክፍያ ማሻሻያ ሊጣልበት እንደሆነም ሪፖርተር ጋዜጣ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የአዲስ አበባ ደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃነት በ1 ቢሊዮን ወጪ በሰንዳፍ ተገንብቷል ቢባልም፤ ሰራ የተባለው ግንባታ ወጪ ከግንባተው ጋር አብሮ ሊድ እንዳይመችል የተጠቆመ ሲሆን፤ ይልቁንም በአካባቢው ያሉ የሰንዳፋ ነዋሪዎች ከአካባቢ ብክለት በሚመጡ በሽታዎች እንዲጋለጥ በማድረጉ፤ የአዲስ አበባ ቆሻሻ በከፍተኛ ወጪ ተሰራ በሚባለው ሰንዳፋ የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ እንዳይደፋ ተቃውሞና እገዳ ማድረጋቸው ታውቋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ የአዲስ አበባ አስተዳደር ለደረቅ ቆሻሻ መጣያ ባለመኖሩ መፍትሄ ባለማበጀቱ ከዚህም በኋላ አዲስ አበባን ለውሃና አየር ወለድ በሽታ ሊያጋልጥ እንደሚችል ተሰግቷል፡፡ የከተማው መስተዳደር ከሰንዳፋ ነዋሪዎች ጋር ቀደም ሲል ያለምንም ድርድርና ምክክር አለመገንባቱ ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ የጥራት ችግር ያለበት በመሆኑ ነዋሪውን ለበሽታ በማጋለጡና ተቃውሞ በመቅረቡ አስተዳደሩ ሌላ መፍትሄ እስኪያዘጋጅ የአዲስ አበባ ቆሻሻ በየመንደሩ ባለበት እንዲቆይ ተደርጓል፡፡ ይህም ከወቅቱ የክረምት ዝናብ ጋር ተዳምሮ በቀላሉ ወደተለያዩ የከተማው ወንዞችና ጉዳት ወደደረሰባቸው የንፁሃ ውሃ ማስተላለፊያ መስመሮች በመቀየጥ፤ አሁን ከተከሰተው የኮሌራ በሽታ በተጨማሪ ለተለያየ ውሃ ወደለድ በሽታ ሊያደርግ እንደሚችል የአስተዳደሩ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ባለሙያዎች ስጋታቸውን ገልፀዋል፡፡
እንደ ከተማዋ የአካባቢ ጥበቃ ባለሙያ ገለፃ ከሆነ፤ በከተማ እየሰሩ ባሉ መሰረተ ልማት እና የተለያዩ የግል ግንባታዎች ምክንያት በርካታ የንፁህ የመጠጥ ውሃ ማስተላለፊያ መስመሮች ከጥቅም ውጭ ሆነው ከከተማ ፍሳሽ ማስወገጃ ጋር በመገናኘታቸው እንደሆነ እና ችግሩንም በአጭር ጊዜ ለማስተካከል አስቸጋሪ እንደሆነ በተለይ ለአዲስ ሚዲያ አስታውቀዋል፡፡ ስለሆነም፤ ችግሩ እስኪቀረፍ የከተማው ነዋሪ አቅሙ የፈቀደ ከከተማው የባንቧ ውሃ ከመጠቀም ተቆጥቦ ሌሎች አማራጮችን አሊያም ውሃን በደንብ አፍልቶ በማቀዝቀዝ እንዲጠቀሙ አሳስበዋል፡፡ በተጨማሪም፤ አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት ምልክት የታየባቸው ሰዎች በአስችኳይ በአቅራቢያቸው ወዳለ የህክምና ጣቢያ እንዲሄዱና ተገቢውን የህክምና ክትትል እንዲያደርጉ መክረዋል፡፡
በተከሰው የኮሌራ ወረርሽን በሽታ በርካታ ህፃናትና እናቶች ሰለባ ሆነው በከተማዋ ባሉ ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች ተኝተው ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ በበሽታው ታመው የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው ከሚገኙ የከተማው ነዋሪዎች በስተቀር ህይወታቸው ያለፈ ስለመኖሩ እስካሁን የተገረጋገጠ መረጃ ማግኘት አልተቻለም፡፡ መንግሥት በስታውን እና መንስዔውን ከመገናኛ ብዙኃን ለመደበቅ ቢሞክርም፤ ዓለም ተቋማት የሚሰሩትን ጨምሮ በርካታ ነዋሪዎች የችግሩ ሰለባ በመሆናቸው በየ ህክምና ተቋሙ የሚሰጡ ውጤቶች ላይ ኮሌራ መሆኑን የሚገልፅ ማስረጃ እንዳይወጣ ያደረገው ጥረት በህክምና ባለሙያዎች ሊጋለጥ ችሏል፡፡ መንግሥት ችግሩን ለመሸፋፈን ከመሞከርና ከማስተባበል ባለፈ እየወሰደ ስላለው የማስተካከያ ርምጃ በግልፅ ያለው ነገር የለም፡፡
ዘጠነኛ ወሩን ባስቆጠረው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞ፤ የመንግሥት የግድያ ርምጃ ተጠናክሮ ቀጥሏል
(አዲስ ሚዲያ) በኦሮሚያ ክልል ዘጠነኛ ወሩን ያስቆጠረው ህዝባዊ ሰላማዊ ተቃውሞ ላይ መንግሥት እየወሰደ ያለው የግድያ ርምጃ ተጠናክሮ መቀጠሉ ታውቋል፡፡ ዛሬ ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሐረርጌ አወዳይ ከተማ በነበረው ህዝባዊ ሰላማዊ ተቃውሞ 6 ሰዎች በልዩ አልሞ ተኳሽ የፀጥታ ኃይል ሲገደሉ፤ በዊልቸር የሚንቀሳቀስ አካል ጉዳተኛን ጨምሮ 20 ያህሉ መቁሰላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በፀጥታ ኃይሉ ተኩስ የቆሰሉ ሰዎችም በሐረር እና ድሬዳዋ ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው መሆን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
በተመሳሳይም በሐረማያ ህዝባዊ ተቃውሞ መቀስቀሱ የተጠቆመ ሲሆን፤ በተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ታዳሚው ላይ በመንግሥት በተወሰደ ርምጃ ጉዳት መድረሱ ቢነገርም እስካሁን በዝርዝር ለማወቅ አልተቻለም፡፡ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በህዝቡ ላይ የወሰዱትን የኃይል ርምጃ ተከትሎ በተለይ የአወዳይ ከተማ ነዋሪ ከአዲስ አበባ ሐረር እና ጅግጅጋ መንገድን ሙሉ ለሙሉ ዘግቶ እንደነበር ተጠቁሟል፡፡ በዚህ በተገባደደው ሳምንት በምዕራብ አርሲ እና ምዕራብ ሐረርጌን ጨምሮ በተለያዩ የክልሉ የወረዳ ከተሞች ጭምር የተለያዩ ህዝባዊ ተቃውሞች መደረጋቸውና ይህንንም ተከትሎ በቅርቡ ከአዳማ ዩኒቨርስቲ የተመረቀ ተማሪን ጨምሮ ሌሎች ንፁሃን ዜጎችም በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን በመግለፅ የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትወርክ ዘገባ አመልክቷል፡፡
ባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ጊኒጪ ከተማ ዳግም በተቀሰቀሰው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞ እስካሁን ከ500 በላይ ንፁሃን ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን እና በርካቶችም ቆስለው ህክምና ሲከታተሉ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ይህ ዘጠነኛ ወሩን ባስቆጠረው በዚህ ህዝባዊ ተቃውሞ ከ30 ሺህ በላይ ዜጎች እንደታሰሩ የመብት አራማጆች ያስታወቁ ሲሆን፤ አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ የተለያዩ ጋዜጠኞች እና ፖለቲከኞችም ለእስር ተዳርገዋል፡፡
አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ በቃሊቲ እና ቂሊንጦ ወህኒ ቤቶች የሚከገኙ የተለያዩ የፖለቲካ እና የህሊና እስረኞች በወህኒ ቤቱ አስተዳደርና በሌሎች የፍትህ አካላት እየተፈፀመባቸው ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት በመቃወም ላለፉት 10 ቀናት የርሃብ አድማ በመምታቸው ራሳቸውን ስተው በጉሉኮዝ እገዛ እንደነበሩ ፍርድ ቤት ከቀረባ አቤቱታ መረዳት ተችሏል፡፡
በጎንደር ታላቅ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰልፍ ተደረገ
(አዲስ ሚዲያ) ዛሬ እሁድ ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ጀምሮ መዳረሻውን በጎንደር ፋሲለደስ መስቀል አደባባይ ያደረገ ታላቅ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰልፍ ተደረገ፡፡ የተቃውሞ ሰልፉ ዋነኛ ምክንያት ባለፈው ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. የማዕከላዊ መንግሥት የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ጥያቄ አንሺ ኮሚቴ አባላት ከሚኖሩበት ጎንደር ከተማ በሌሊት አፍኖ ወስዶ በማሰሩ፣ ከኮሚቴ አባላት መካከልም ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ እቤታቸው ሊያፍኑ የሄዱትን የፀጥታ አካላት ህጋዊ ከሆናችሁ በቀን መምጣት ትችላላችሁ፣ በሌሊት ህገወጥነት በሚል በተፈጠረ አለመግባባት የ11 የፅጥታ ኃይሎች እና 3 ሲቪሎች መገደላቸው ይታወቃል፡፡ ይህንንም ተከትሎ መንግሥት የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ጥያቄ አቅራቢዎችን እና የፀጥታ ኃይሉ ላይ የአፀፋ ርምጃ የወሰዱትን ጨምሮ የመንግሥትን ርምጃ በማውገዝ እና ተቃውሞ ያቀረቡ የአካባቢውን ህዝብ ወንጀለኛ አድርጉ በሚዲያ በማቅረቡ የተቆጣው ህዝብ፤ ተቃውሞውን በአደባባይ ለማቅረብ ያቀረበው ጥያቄ ውድቅ በመደረጉ ህዝቡ በራሱ ተነሳሽነት የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ እንዲወጣ እንዳደረገው ከአስተባባሪዎቹ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከጎንደር ፋሲለደስ ከተማ በተጨማሪ በደቡብ ጎንደር በእስቴ ወረዳ መካነ ኢየሱስ ከተማ፣በምዕራብ በለሳ እና ማክሰኝት ከተማ ተመሳሳይ ጥያቄ መነሻ ያደረገ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መደረጉ ታውቋል፡፡ በተለይ በጎንደሩ ሰልፍ የተለያዩ የኃይማኖት አባቶች በተቃውሞ ሰልፉ ላይ ተገኝተው ንግግር ማድረጋቸውን የዓይን እማኞች አረጋግጠዋል፡፡
በዛሬው ተቃውሞ ሰልፍም የተለያዩ መፈክሮች የተደመጡ ሲሆን፤ በዋናነትም የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ ሕገ-መንገሥታዊ መብት ነው፣ የሻዕብያ ተላላኪ ህወሃት እንጂ ወልቃይት አይደለም፣ በግፍ የታሰሩ የወልቃይት አማራ ማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት በአስቸኳይ ይፈቱ፣…የሚሉትን ጨምሮ በርካታ መፈክሮች እንደተሰሙ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተቃውሞ፤ ታሪክ ምስክር ነው ወልቃይት አማራ ነው ፣ አማራ ለኢትዮጵያ የግዛት አንድነትና ሉአላዊነት የተዋደቀ ታላቅ አርበኛ ሕዝብ ነው ፣ ዘረኝነትን አጥብቀን እናወግዛለን ፣ የትግራይን ሕዝብ እናከብራለን፤የህወሓትን አፋኝ የአገዛዝ ፖሊሲ አጥብቀን እናወግዛለን፣አማራነት ይከበር፣ በኦሮሞ እህት ወንድሞቻችን ላይ የሚደርሰውን ግፍና በደል አጥብቀን እንቃወማለን፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነት ይፈልጋል፣ በኦሮሚያ የሚደረገው በወንድምና እህቶቻችን ላይ ግድያ ይቁም፣ ኢቢሲና ሌሎች መንግስታዊ ሚዲያዎች የጎንደርንና አካባቢውን ህዝብ ይቅርታ ይጠይቁ የሚሉ መሪ ቃሎች ተደምጠዋል፡፡
በተጨማሪም የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ እስኪመለስ ድረስ ትግሉ ይቀጥላል፣አማራነት ወንጀል አይደለም፣ የትግራይ ወሰን ተከዜ ነው፣ ወልቃይት የአማራ ነው ፣ የሐብታሙ አያሌዉ ከአገር የመዉጣት እግድ በአስቸኳይ ይነሳለት፣ ዜጎችን በፖለቲካ አመለካከታቸዉ ማሰርና ማሰቃየት ይቁም፣ በፖለቲካ አመለካከታቸዉ የታሰሩ የፖለቲካና የህሊና እስረኞች በአስቸኳይ ይፈቱ እና የህወሓት የበላይነት ይቁም የሚሉ መፈክሮች ጎልተው ተሰምተዋል፡፡
ይህ ህዝባዊ ተቃውሞ ከሳምንት በፊት እውቅና ተጠይቆ በመንግሥት ተከልክሎ የነበረ ሲሆን፤ በድጋሚ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ እውቅና ለሚመለከተው የመንግሥት አካል ቢገባም፤ መንግሥት ለህዝባዊ የተቃውሞ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ እውቅና አለመስጠቱን ከማስጠንቀቂያ አዘል መልዕክት ጋር በኢቢሲ እና ኤፍቢሲ ቢያሳውቅም ህዝቡን ለተቃውሞ ከመውጣት ማገድ አልቻለም፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ መንግሥት ህዝባዊ ተቃውሞ ሰልፍ እውቅና መንፈጉን በስሩ ባለ መገናኛ ብዙኃን ከመግለፁ በተጨማሪ በጎንደር ከፍተኛ የመከላከያ፣ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ፣ የአማራ ክልል ልዩ ኃይል እና የከተማው ሚሊሻ አባላት በበብዛት በከተማው እንዲሰፍሩ መደረጉ ታውቋል፡፡
ተቃውሞ ምንም እንኳ የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄን መነሻ ያድርግ እንጂ፤ ለዓመታት በአማራ ማኀበረሰብ ላይ በመንግሥት በተለይም በህወሓት/ኢህአዴግ አማራ ክልልን ጨምሮ በተለያየ የኢትዮጵያ ክፍል እየተፈፀመ ያለውን የሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ የመብት ጥሰት ተባብሶ መቀጠሉ አንዱ የተቃውሞ አካል መሆኑን የሰልፉ ታዳሚዎች ሲያስተጋቡ ተስተውሏል፡፡
በነበረው ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍም፤ በሰውም ሆነ በንብረት ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት ሳያስከትል በሰላም መጠናቀቁን የተሳታፊዎችን ጨምሮ ዓይን እማኞች እውቅና የነፈገው የመንግሥት አካል አስታውቀዋል፡፡ በሰልፉ ላይም በኢህአዴግ የስልጣን ዘመን በ25 ዓመታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ አረንጓዴ፣ ቢጫ ቀይ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ በብዛት ሲውለበለብ ታይቷል፡፡