ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ዋስትና ተከለከለ
ከሽብርተኝነት ክስ ነጻ ተብሎ በመደበኛ የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ እንዲከላከል ብይን የተሰጠው የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው የዋስትና ጥያቄው ውድቅ ተደርጎበታል፡፡
የፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ታህሳስ 13 ቀን 2009 ዓ.ም ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ከቀረበበት የሽብር ክስ ነጻ በማለት ክሱ ወደ መደበኛ የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ ተቀይሮ አንቀጽ 257 (ሀ) ላይ የተመለከተውን እንዲከላከል ሲል ብይን መስጠቱ ይታወሳል፡፡

ይህን ተከትሎ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ቋሚ የመኖሪያ አድራሻ እንዳለውና ለአንድ አመት በእስር መቆየቱን በማንሳት አሁን ተከላከል የተባለበት የህግ ክፍል የዋስትና መብት እንደማይከለክል ጠቅሶ የዋስ መብቱ እንዲከበርለት ታህሳስ 19 ቀን 2009 ዓ.ም ፍርድ ቤቱን ጠይቆ ነበር፡፡ በዕለቱ አቃቤ ህግ ተከሳሹ በዋስ ቢወጣ ከሀገር ሊወጣ ስለሚችል የዋስትና ጥያቄው ውድቅ እንዲደረግለት ተቃውሞውን አሰምቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ ታህሳስ 25 ቀን 2009 ዓ.ም በተነሳው የዋስትና ጥያቄ ላይ መርምሮ ብይን ሰጥቷል፡፡ በዚህ መሰረት ተከሳሹ በዋስ ቢወጣ ‹‹ከሀገር ሊወጣ እንደሚችል ግምት የተወሰደ በመሆኑ›› የዋስትና ጥያቄው ተቀባይነት አላገኘም ሲል ፍርድ ቤቱ ዋስትና ከልክሎታል፡፡ ፍርድ ቤቱ ተከሳሹ በዋስ ቢወጣ ከሀገር ሊወጣ ይችላል የሚለውን ግምት ለመውሰድ የቀረበለት ማስረጃ ስለመኖሩ በብይኑ ላይ አላመለከተም፤ አቃቤ ህግ ተቃውሞውን ባስመዘገበበት ወቅትም ተቃውሞውን በማስረጃ አስደግፎ አላቀረበም ነበር፡፡
‹‹ተከሳሹ ተከላከል የተባለበት የህግ አንቀጽ በመርህ ደረጃ ዋስትና ባያስከለክልም፣ በሁኔታ የሚከለከልበት ጊዜ ግን ስለመኖሩ ተመልክቷል፡፡ እኛም ይህን ተከሳሹ ከሀገር ሊወጣ ይችላል የሚለውን ሁኔታ አይተን በሙሉ ድምጽ ተከሳሹ ዋስትናው ይነፈግ ብለን ወስነናል›› ብሏል ችሎቱ የዳኞችን ውሳኔ በተመለከተ ሲገልጽ፡፡
ፍርድ ቤቱም መከላከያ ምስክሮችን ለመስማት ሌላ ተለዋጭ ቀጠሮ ለየካቲት 7 ቀን 2009 ዓ.ም ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፦ EHRP
የዳዊት ፈተና

በፈቃዱ ሃይሉ
አዋሽ ሰባት በነበረኝ “የተሀድሶ” ቆይታዬ ተዋውቄያቸው ከወደድኳቸው ሰዎች መካከል ሁለት ዳዊት በሚል ሥም የሚጠሩ ወጣቶች ነበሩበት። አሁን የማጫውታችሁ ግን ስለ ዲያቆኑ ዳዊት ነው። ዲያቆን ዳዊት ተወልዶ ያደገው ትግራይ ውስጥ ነው። የሚያገለግለው ሥላሴ ካቴድራል ነው። የፖለቲካ ተሳትፏቸው እምብዛም እንደሆኑትና በአዲስ አበባ እንደሚኖሩት አብዛኛዎቹ የትግራይ ተወላጆች የሚያውቀውም፣ የሚያምነውም፣ የሚወደውም ኢሕአዴግን ብቻ ነበር።
“ነበር” ያልኩት ያለምክንያት አይደለም። እንዳጋጣሚ ሆኖ፣ ዲያቆን ዳዊት የተመደበው ኢያስጴድ እና እኔ የነበርንበት (20 ምናምን ሰው የነበረበት) የውይይት ቡድን ውስጥ ነበር። ቡድናችን በፍርሐት ታዝቦ የሚያልፈው ነገር አልነበረውም። በውጤቱ ደግሞ የውይይቱ አባላት በሙሉ የተሰላ ምላጭ ሆነዋል ማለት ይቻላል። ታዲያ ዲያቆን ዳዊት አንድ ቀን ግምገማ ላይ “ከዚህ በፊት የነበራችሁ ዕውቀት ምን ይመስላል? አሁንስ ምን ተማራችሁ?” የሚል ጥያቄ ሲነሳ፣ “እኔ እዚህ ከመምጣቴ በፊት ኢሕአዴግን ብቻ ነበር የማውቀው፤ ቅዱስም ይመስለኝ ነበር። አሁን ግን ብዙ ነገር ሰምቻለሁ። ብዙ በደል እንደሚፈፅም አውቄያለሁ። ሰነዶቹን የሚያዘጋጁት ሰዎች ዕውቀትም እዚህ ከሚታደሱት ሰዎች ዕውቀት ያነሰ መሆኑን ተምሬያለሁ” ብሎ እርፍ አለ።
ዳዊት በጣም ጥሩ ሰው እንደሆነ ከቀረቤታው ያስታውቃል። ኢሕአዴግንም ሲመለከተው የኖረው በየዋህነት ይመስላል። “እንዴት ታሰርክ?” ብዬ ስጠይቀው፣ “እኔ ራሴ ላይ ቀለም አብዮት ታውጆብኛል” አለኝ። አከአዲስ አበባ የተጋዙት ብዙዎቹ የሆነ ፀበኛዬ ቂም በቀል መወጫ ሆኜ ነው የመጣሁት ብለው ያምናሉ – በጥቆማ። ዲያቆን ዳዊትም የሚያምነው እንዲያው ነው። ምናልባት ቤተክርስቲያን ውስጥ ባለ ፉክክር መጥቶ ይሆናል ብዬ ገምቼ፣ “እንዴት ነው ቤተክርስቲያኖቹ የአማራ እና የትግሬ ተብለው ተከፋፍለዋል የሚባለው እውነት ነው?” ብዬ ጠየቅኩት። “ከፖለቲካው አይብስም ብለህ ነው?” አለኝ።
ዲያቆን ዳዊት እኔና ኢያስጴድን ትግራይ ወስዶ ሊያስጎበኘን ቃል ገብቷል። ምክንያቱ ደግሞ ‘የአንድ ብሔር የበላይነት’ የሚል ነገር ስንናገር በመስማቱ ነው። ጉዳዩ ግን በተሐድሶው ወቅት ተፈርቶ በደንብ ያልተወራ ጉዳይ ነው።
ኮማንደር አበበ፣ ራሳቸው የትግራይ ተወላጅ የሆኑ፣ ከስድስቱ ለመጨረሻዎቹ ሦስት የሥልጠና ሰነዶች የኃይል (አማርኛ ተናጋሪዎች ሁሉ የተሰበሰብንበት) መድረክ መሪ (መዝጊያ ንግግር አድራጊ) ነበሩ። አንድ ቀን፣ በግምገማ ወቅት ተጠይቀው መልስ ያላገኙ ጉዳዮችን ሰብስበው መጡ። ከጉዳዮቹ አንዱ “በኢትዮጵያ የአንድ ብሔር የበላይነት አለ” የሚለው ነበር። ኮማንደሩ “መልስ ለመስጠት ጥያቄው ቢብራራልኝ፣ የቱ ብሔር ነው በየቱ ላይ የበላይ የሆነው?” አሉና ጠየቁ። ዝምታ።
ፈራ ተባ እያልኩ እጄን አውጥቼ “የሚባለው የትግራይ የበላይነት እንደሆነ፣ ነገር ግን አባባሉ የትግራይ ገበሬ የኦሮሞን ወይም የአማራን ገበሬ ይጨቁናል፣ ወይም የበላዩ ይሆናል ማለት ሳይሆን፣ የልሒቃኑ የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካ አመራር እና በማበብ ላይ ያሉ ቢዝነሶች ላይ ያለውን የበላይነት እንደሚመለከት” አስረዳሁ። ከዚያ በኋላም ብዙ አስተያየቶች ተከተሉ። ለምሳሌ አንድ የገረመኝ አስተያየት ሰጪ (በሙያው መምህር የሆነ ወጣት) በእናቱ ትግሬ መሆኑን ገልጦ፣ “ምናልባት የሚፈቱኝ ከሆነ ብዬ የተያዝኩ ዕለት ጣቢያ ብሔር ስጠየቅ ‘ትግሬ’ ልል ነበር፤ አፍሬ ተውኩት” ብሎ አማረረ። በመቀጠልም፣ “እንዲያውም፣ እዚህ ከመጣነው ውስጥ በናቱም ባባቱም ትግሬ የሆነ ሰው የመጣ አይመስለኝም፤ ያውም አምስት የምንሞላ አይመስለኝም” አለ። ነገር ግን ይህ አካሔድ የትግራይን ተወላጅ ሁሉ እየጠቀመ አለመሆኑን ሲያስረዳ “እናቴ የጋራ ኩሽናችንን ተጠቅማ በሌሊት እንጀራ ስትጋግር በመቀደሟ የተናደደችው ጎረቤታችን ‘ምን ይደረግ እሷ የዘመኑ ሰው ናት’ ስትል ሰምቼ በጣም ነበር ያዘንኩት” በማለት አስረዳ።
ኮማንደር አበበ “እውነቱን ልንገራችሁ” አሉን፣ “ለዚህ ሁሉ ‘ሁከትና ብጥብጥ’ መንስኤ የሆነው ይሄ አስተሳሰብ ነው። ጠላቶቻችን ለዓመታት በኢሳት እና ኦኤምኤን እንዲሁም በፌስቡክ ሲያራግቡት የነበረው የጥላቻ ፕሮፓጋንዳ ውጤት ነው ይሄ” አሉ። “የትግራይ ሕዝብ፣ እንዲያውም ሕወሓት ለራሱ ትልቅ ቆርሶ ወሰደ እንዳይባል በይሉኝታ እየተበደለ ያለ ሕዝብ ነው” በቁጭት ስሜት ሊያስረዱን ሞከሩ። “በርግጥ፣” አሉ “የትግራይ ተወላጅ ሆነው ሙሰኞች አሉ፣ ሌቦች አሉ፤ ነገር ግን የኦሮሞ ተወላጅ ሌቦችም አሉ፣ የአማራ ተወላጅ ሌቦችም አሉ። በጥቂት ሰዎች ሥም የአንድ ብሔር ሕዝብ መወቀስ የለበትም”።
በማግስቱ ዲያቆን ዳዊት ከኮማንደሩ የተሻለ የነገሩን ውስብስበነት አስረዳኝ። ዳዊት “እኔ በጦርነቱ ጊዜ አባቴን አጥቻለሁ፤ አሁን ደግሞ የትግራይ ተወላጅ ስለሆንኩ ብቻ በሕወሓት ጥፋት አብሬ እወቀሳለሁ። ያገኘሁት ጥቅም ምንድን ነው?” ነበር ያለኝ።
ዲያቆን ዳዊት ግቢው ውስጥ ከብዙዎቻችን የተሻለ የመንቀሳቀስ ነጻነት ነበረው። ማታም ግቢው ውስጥ አምሽቶ እንደሚገባ የክፍሉ ልጆች ነግረውኛል። ይህንን ነጻነት ጠይቆ አላመጣውም። የአነጋገር ዘዬው ላይ የትግርኛ ቅላፄ መኖሩ ያጎናፀፈው ዕድል ነው። በጊቢው ውስጥ ካሉ ጥበቃዎች ውስጥ በጣም ቁጡ የሚባሉት የትግራይ ተወላጆች መሆናቸው አነጋጋሪ ነበር። እነሱ ዲያቆን ዳዊት ላይ ቁጣቸው ይበርዳል። እኛ ክፍል ከነበረው ሌላኛው ዳዊት ጋር ስናወራ “የነሱ ክፋት የግላቸው እንጂ የወጡበት ማኅበረሰብ በውክልና የሰጣቸው ስላልሆነ የነርሱን ለነርሱ እንተወዋለን” እንባባል ነበር። ለምሳሌ ኃይሌ የሚባለው የኛ ክፍል ኃላፊ የአዲስ አበባዎቹ ‘ሠልጣኞች’ ከሔድን በኋላ መምታት በኮማንድ ፖስቱ ልዑካን ቡድን በመከልከሉ የተቆጨ ይመስላል። የውይይት ተሐድሶው የሚለውጠን ስላልመሰለው ማታ ማታ እየመጣ ይቆጣንና ይመክረን ነበር። አንዴ እንዲያውም፣ ዘላችሁ ዘላችሁ ያው የምታርፉት መሬት ነው ለማለት የእንግሊዝኛ ተረት ተርቶ በሳቅ ገድሎናል፤ “ራቢት ጃምፒያ ጃምፒያ ቱ ኧርዝ” ነበር ያለን ቃል በቃል። የእነ ኢያስጴድ ክፍል ኃላፊ ደግሞ አብርሃም ነበር። ኃይሌም አብርሃምም በጣም ከሌሎቹ ጠባቂዎች ሁሉ በጥላቻ እና በክፋት ነበር የሚያዩን።
አንድ ቀን ማታ ሜዳ ላይ ተኮልኩለን ቲቪ ስናይ ጥቂቶች ወንበር እያመጡ ሲቀመጡ እኔም ወንበር አምጥቼ ተቀመጥኩ። ሌሎቹ ምንም አይሉም፤ አብርሃም ግን “ወንበሩን መልሱ” እያለ መጥቶ አንዴ ዠለጠኝ። በጣም ተናድጄ ቻልኩት። ስመለስ ዲያቆን ዳዊት እና ሌላ አንድ ተመሳሳይ ሰው ከወንበራቸው አልተነሱም። የባሰ ተናደድኩ እና የማይገባ ቃል ተናገርኩ። ዲያቆን ዳዊት “ወንበሩን ካልለቀቅኩልህ” አለኝ፤ እምቢ አልኩት። በማግስቱ መጥቶ ሲያናግረኝ፣ በቋንቋ ላይ ተመሥርቶ አብርሃም እንደበደለኝ ነገርኩት። “የምርቃታችን” ዕለት አብርሃም ጠራኝና ይቅርታ ጠየቀኝ። ነገሩን ያደረገው “በሆነ ብስጭት” ተነሳስቶ እንደሆነና “ቂም ይዤ እንዳልሔድ” ጠየቀኝ። ይቅርታ መጠ‘የቅ ደስ ይላል። ቂም ይዤበት ነበር ለማለት ግን ይከብዳል። ነገር ግን ክፉው አብርሃም ይቅርታን ኬት አመጣው ብዬ ዳዊትን ጠየቅኩት። “አናግሬው ነበር” አለኝ። “የሠራው ሥራ ጥፋት እንደሆነ ይቅርታ መጠየቅ እንዳለበት አሳምኜዋለሁ” አለኝ። አሪፍ ነው።
ዳዊት ወደትግራይ ሊወስደኝ ቃል የገባው የሕዝቡን ድህነት እና ሰው ወዳድነት ሊያሳየኝ ፈልጎ ነው። እኔም ይሄንን አልክድም። ምናልባት እሱ ያልገባው፣ እሱ በአነጋገር ዘዬው ብቻ ያገኘውን ተቃራኒው ለኔ መሰሎቹ እየተሰጠን እንደሆነ ነው። እሱ እንደልቡ ጊቢው ውስጥ መንቀሳቀስ ሲፈቀድለት የኔብጤዎቹ ለምነንም ማግኘት አልቻልንም ነበር። እሱም እዚያ የነበረው በግፍ ነው። ይሁን እንጂ ሌሎቻችንም በተመሳሳይ ሁኔታ ከመያዛችን አንፃር እሱ ቢያንስ ግቢው ውስጥ ሲኖር በፍርሐት ተሸማቆ አልነበረም። ይሄን ችሮታ (entitlement) ዲያቆን ዳዊት ከነበፍቃዱ ተነጥቆ ይሰጠኝ አላለም፤ ነገር ግን ለሱ ችግር ስላልነበር አልታየውም። በተጨማሪም ይሄን መሰል አድሎ የትግራይ ሕዝብ ባርኮ አላፀደቀውም። ነገር ግን ተመልካች ይሄን ያመዛዝናል? የማመዛዘን ግዴታስ አለበት?
ሕወሓት/ኢሕአዴግ እታደሳለሁ ካለ መጀመሪያ ይህን ዓመሉን ይሻር እና በአዲስ የተሻለ አመል ይተካው። መልካም አስተዳደር ለማግኘት የአነጋገር ዘዬ የሚያደርገው ያልተጻፈ አዎንታዊም አሉታዊ አስተዋፅዖ ይቀረፍ።
በዝዋይ ወህኒ ቤት እስር ላይ የነበረው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ አሁን የት እንዳለ አለመታወቁን ቤተሰቦቹ አስታወቁ
(አዲስ ሚዲያ) የፍትህ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ እና መስራች የነበረው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ባለፈው ህዳር 2007 ዓ.ም. በመንግሥት በተመሰረተበት ክስ የ3 ዓመት ፅኑ እስር ተፈርዶበት ዝዋይ ወህኒ ቤት የነበረ ቢሆንም፤ ከፋለፈው ማክሰኞ ህዳር 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ የነበረበት ዘዋይ ወህኒ ቤትን ጨምሮ ቃሊቲ፣ የአቃቂ ቂሊንጦ እና ሸዋ ሮቢት ወህኒ ቤት ጥበቃ ሰራተኞችና ኃላፊዎች፤ ጋዜጠኛ ተመስገን የት እንዳለ ከቤተሰቦቹ ለቀረበላቸው ጥያቄ በተጠቀሱት ወህኒ ቤቶች እንደሌለ በመግለፅ በአሁን ወቅት የት እንዳለ ግን እንደማያውቁ መናገራቸውን የጋዜጠኛው ቤተሰቦች ይፋ አድርገዋል፡፡

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፤ ፎቶ ከማኀበራዊ ገፅ
አዛውንቱ ወላጅ እናቱን ጨምሮ ሌሎች የጋዤተኛው ቤተሰቦችና ወዳጆች ቀደም ሲል ታስሮ የነበረበትን እና በፌደራል ደረጃ የሚታወቁ ወህኒ ቤቶች በሙሉ በመሄድ ያለበትን ሁኔታ ለማረጋገጥ ሙከራ ቢያደርጉም ሊያገኙት እንዳልቻሉ የተገለፀ ሲሆን፤ በተለይ በዕድሜ የገፉ አዛውንት ወላጅ እናቱ ወ/ሮ ፋንታዬ እርዳቸው በከፍተኛ ስጋትና ጭንቀት ላይ መሆናቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ ጋዜጠኛው ቀደም ሲል በእስር ላይ እያለ በደረሰበት ህመም ምክንያት የህክምና ዕርዳታ ለማግኘት ጠይቆ በተደጋጋሚ መከልከሉ አይዘነጋም፡፡
የፌደራል አቃቤ ህግ ጋዜጠኛ ተመስገን በፍትህ ጋዜጣ ላይ በፃፋቸው ፅሑፎችን ዋቢ በማድረግ በመሰረተበት ክስ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት 3 ዓመት ፅኑ እስራት እና የፍትህ ጋዜጣ አሳታሚ ማስተዋል ህትመትና ማስታወቂያ ድርጅትደግሞ 10 ሺህ ብር እንዲቀጣ መበየኑ ይታወሳል፡፡ጋዜጠኛ ተመስገን ከመታሰሩ በፊት መንግሥት ይፈፅማል ያላቸው የመብት ረገጣዎችና ብልሹ አሰራሮችን በግልፅ በመተቸት ይታወቃል፡፡
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝን ጨምሮ በገዥው የኢህአዴግ መንግሥት 11 ጋዜጠኞችና 1 ብሎገር ኢትዮጵያውያን እንዲሁም 3 የውጭ ዜጋ ጋዜጠኖች በአጠቃላይ 15 ጋዜጠኞችና ብሎገር በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ በተለይ በእስር ከሚገኙ ጋዜጠኞች መካከል ኢትዮጵያውያኑ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ ውብሸት ታዬ፣ ተመስገን ደሳለኝ፣ ጌታቸው ሽፈራው፣ ፈቃዱ ምርከና፣ጌታቸው ወርቁ፣ አናኒያ ሶሪ፣ ኤልያስ ገብሩ፣ በፈቃዱ ኃይሉ፣ ከድር መሐመድ፣ ዳርሰማ ሶሪ እና የደ ብርሃን ብሎገር ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ ተጠቃሾች ናቸው፡፡
እንደ ሀገር ውስጥ የሰብዓዊና የፕሬስ ነፃነት መብት ተሟጋቾች እና እንደ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች መረጃ ከሆነ፣ ኢትዮጵያ በአሁን ወቅት የፕሬስ ነፃናት ከሌለባቸው የዓለም ሀገራት ተርታ በቀዳሚነት ከሚጠቀሱት አንዷ ስትሆን፤ በርካታ ጋዜጠኞችን በማሰር በአፍሪካ ከጎረቤት ኤርትራ ቀጥሎ በሁለተኛ ደረጃ ላይ የምትገኝ ሀገር ነች፡፡
እውቁ ፖለቲከኛ እና የኦፌኮ/መድረክ ከፍተኛ አመራር ዶ/ር መረራ ጉዲና ታሰሩ
(አዲስ ሚዲያ)የኦሮሞ ፌደራሊስት ሊቀመንበር እና የኢትዮጵ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንደነግ ግንባር (መድረክ) ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና ታሰሩ፡፡ ዶ/ር መረራ የታሰሩት በቤልጂየም ብራሰልስ የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ በተጋበዙት መሰረት ንግግር አድርገው ረቡዕ ህዳር 21 ቀን 2009 ዓ.ም. ወደ ሀገር ቤት ሲመለሱ አዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ሲደርሱ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መታሰራቸው ታውቋል፡፡ ዶ/ር መረራ የታሰሩት አብረዋቸው ከነበሩ ከሁለት የቅርብ ቤተሰቦቻቸው ጋር እንደነበርም ታውቋል፡፡

ገዥው የህወሓት/ኢህአዴግ መንግሥት በበኩሉ ዶክተር መረራ የታሰሩት “በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መመሪያ ቁጥር አንድ አንቀጽ 2 ላይ የተመለከተውን መመሪያ ተላልፈው በመገኘታቸው እና ከአርበኞች ግንቦት 7 መሪ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ጋር ተገናኝተው መግለጫ ሰጥተዋል“ በሚል መሆኑን በልሳኑ ፋና ብሮድካሲቲንግ ኮርፖሬት ዘገባ ይፋ አድርጓል፡፡
መንግሥት ባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. የተቀሰቀሰውን የኦሮሚያ ክልል የፀረ አገዛዝ ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ፤ በተመሳሳይ መልኩ ሐምሌ 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በአማራ ክልል እና በደቡብብ ክልል ኮንሶ የተዛመተውን ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ተከትሎ ከ1400 በላይ ዜጎች ሲገደሉ ከአንድ ሺህ ያላነሱ በፀጥታ ኃይሎች ወታደራዊ ርምጃ የቆሰሉ ሲሆን፤ ከ50 ሺህ ያላነሱ ዜጎች በእስር ላይ እንደሚገኙ የፖሊስ መረጃዎችና የሰብዓዊ መብት አራማጆች መረጃ አመልክቷል፡፡የህወሓት/ኢህአዴግ ደጋፊዎችም ዶ/ር መረራ በአውሮፓ ፓርላማ ንግግር ማድረጋቸውን ተከትሎ እንደሚታሰሩ የሚያመለክት ቅስቀሳ ሲያደሩ እንደነበረም መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በተለይ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀውን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞውን ተከትሎ ገዥው መንግሥት መስከረም 28 ቀን 2009 ኣ.ም ጀምሮ ለ6 ወራት ተግባረዊ የሚደረግ የአስቸኳይ ዚጌ አዋጅ አውጥቷል፡፡ አዋጁ ተግባራዊ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ ጋዜጠኞች፣ የተለያዩ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት፣ የመብት አራማጆችንና ሲቭል ማኀበረሰቡን ጨምሮ በአንድ ወር ብቻ ከ11,706 ማሰሩን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡
ዶ/ር መረራ ጉዲና በቅርቡ በጡረታ እንዲሰናበቱ ከመደረጋቸው በፊት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህርነት ለ28 ዓመታት ያገለገሉና የፓርላማ አባል የነበሩ ሲሆን፤ ላለፉት 20 ዓመታትም በሀገሪቱ ፖለቲካ ባላቸው ተሳትፎ በበርካታ ኢትዮጵያውያን ዘንድ የሚታወቁና ከፍተኛ ተቀባይነት እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ ቀደም ሲል የፓርቲያቸው ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ፣ ዋና ፀሐፊያቸው አቶ ደጀኔ ጣፋ፣ የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ አቶ ደስታ ዲንቃን ጨምሮ በርካታ አመራሮችና አባሎቻቸው ከአንድ ዓመት በፊት መታሰራቸው ይታወቃል፡፡
አቶ ዮናታን ተስፋዬ የቀረበበትን ክስ ለመከላከል ታዋቂና በከፍተኛ ኃላፊነት ላይ ያሉ ሰዎች በምስክርነት ተጠርተዋል
*አቶ በቀለ ገርባና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ከማረሚያ ቤት ቀርበዋል፤ ጦማሪና ጋዜጠኛ በፍቃዱ ኃይሉን ያሰረው አካል ሳያቀርበው ቀርቷል፡፡

የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበረውና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ አቶ ዮናታን ተስፋዬ በፌደራል አቃቤ ህግ የቀረበበትን ሽብር ክስ እንዲከላከል የተወሰነበትን ክስ ለመከላከል የኦፌኮ ፕሬዚደንትና ምክትል ፕሬዚደንትን ጨምሮ ከፍተኛ ኃላፊነት ያላቸውና ታዋቂ ሰዎች በምስክርነት ተጠርተዋል፡፡
አቶ ዮናታን ተስፋዬ ዛሬ ህዳር 19 ቀን 2009 ዓ.ም መከላከያ ምስክሮችን ለማስደመጥ በተያዘለት ቀጠሮ መሰረት የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ቀርቧል፡፡ አቶ ዮናታን በጠበቃው አማካኝነት የምስክሮችን ዝርዝር ለፍርድ ቤት ያስረዳ ሲሆን፣ ከምስክሮቹ መካከል አብዛኞቹ ሲገኙ ሦስቱ ብቻ ሳይቀርቡ ቀርተዋል፡፡
አቶ ዮናታን ተስፋዬ ተከላከል የተባልሁበትን ክስ በመከላከያ ምስክርነት ቀርበው ያስረዱልኛል ያላቸውን 10 ምስክሮች ዘርዝሮ አቅርቧል፡፡ እነዚህም ወላጅ አባቱ ቀሲስ ተስፋዬ ረጋሳ፣ ታናሽ እህቱ ገዳምነሽ ተስፋዬ፣ የቅርብ ጓደኛው ኤፍሬም ታያቸው፣ የኦፌኮ ፕሬዚዳንት ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ አቶ በቀለ ገርባ፣ የህግ ምሁሩ ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማርያም፣ በእስር ላይ የሚገኘው ታዋቂው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ የፍልስፍና መምህሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፣ ጋዜጠኛና ጦማሪ በፍቃዱ ኃይሉ እና አቶ ሙላቱ ገመቹ ናቸው፡፡
ከእነዚህ መከላከያ ምስክሮች መካከል ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋና ጋዜጠኛና ጦማሪ በፍቃዱ ኃይሉ በዛሬው ቀጠሮ አልቀረቡም፡፡ በእስር ላይ የሚገኘው በፍቃዱ ኃይሉን ጨምሮ ዛሬ ያልቀረቡት እንዲቀርቡ፣ የቀረቡትም ተጨማሪ መጥሪያ ሳያስፈልጋቸው በቀጣይ ቀጠሮ እንዲቀርቡ ታዝዟል፡፡
ተከሳሹ በዚህ መሰረት አብዛኞቹ ምስክሮቹ መገኘታቸውን ችሎት ፊት አቅርቦ በማስረዳት፣ ምስክሮቹን አግኝቶ ስለሚመሰክሩበት ጉዳይ ለመነጋገር ጊዜ እንደሚፈልግ በመግለጽ ተለዋጭ ቀጠሮ ጠይቋል፡፡ ከምስክሮች መካከል ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ‹‹የፍርድ ቤት መጥሪያ በእጄ አልደረሰኝም፡፡ ጠዋት ትፈለጋለህ ተብዬ በጽህፈት ቤት ተጠርቼ ነው የመጣሁት፡፡ ስለምመሰክርበት ጉዳይ አሁን ገና ነው የሰማሁት፡፡ የሙያ ምስክርነት እንድሰጥ ስለተጠራሁ ትንሽ የዝግጅት ጊዜ እንዲኖረኝ በተለዋጭ ቀጠሮ ምስክርነቴን እንድሰጥ ይፈቀድልኝ›› ሲል ከተከሳሹ አቤቱታ ጋር የተጣጣመ ማሳሰቢያ ለችሎቱ አሰምቷል፡፡
አቃቤ ህግ በበኩሉ ዛሬ የቀረቡት ምስክሮች እንዲመሰክሩ እንዲደረግለት ጠይቋል፡፡ ሆኖም ፍርድ ቤቱ በተከሳሽ የቀረበውን ማሳሰቢያ በመቀበል ምስከሮቹ ተሟልተውና ስለሚመሰክሩበት ጉዳይ ተረድተው ሲቀርቡ ምስክርነታቸውን ለመስማት በሚል ለታህሳስ 26 እና 27 ቀን 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡
አቶ ዮናታን ተስፋዬ ከሰው ምስክሮች በተጨማሪ ሦስት የሰነድ ማስረጃዎችን ዘርዝሮ አቅርቧል፡፡ በዛሬው ዕለት ለምስክርነት ከቃሊቲ እስር ቤት የቀረበው የ18 ዓመት ፍርደኛ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ሙሉ ጥቁር ሱፍ ከጥቁር መነጽር ጋር ለብሶ እጆቹ በካቴና ታስረው በከፍተኛ ጥበቃ ፍርድ ቤት ሊቀርብ ችሏል፡፡ በቃሊቲም ሆነ በቂሊንጦ የሚገኙ እስረኞች የእስረኛ ዩኒፎርም ለብሰው የቀረቡ ቢሆንም እስክንድር ነጋ ብቻ በተለየ በሱፍ ልብስ መቅረቡን ለመመልከት ተችሏል፡፡ ጋዜጠኛ እስክንድር ከፍርድ ቤት ግቢ በመኪና ሊጫኑ ሲወሰዱ በካቴና የታሰሩ እጆቹን ከፍ በማድረግ በፈገግታ ታጅቦ ‹‹አይዞን እንበርታ!›› የሚል ቃል ሰላምታ ላቀረቡለት ሁሉ መናገሩን ኢጥዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት ዘገባ አመልክቷል፡፡