Category Archives: Human Rights

በአማራ ክልል በአገዛዙ ወታደሮችና በነፃነት አርበኞች መካከል ውጊያ እየተካሄደ ሲሆን፤ ከሁለቱም ወገን ጉዳት መድረሱ ተገለፀ

(አዲስ ሚዲያ)በአማራ ክልል በተለይም በሰሜንና ደቡብ ጎንደር ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች የገዥው ስርዓት በደል እና ጭቆናን የተቃወሙ የአማራ ተጋድሎ አርበኞች እና የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ ድርጅት የነፃነት ኃይሎች ከመንግሥት ወታደሮች ውጊያ ማካሄዳቸው ተገለጠ፡፡ በተለይ ካለፈው ሐሙስ ህዳር 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ በዋናነት በሰሜን ጎንደር ምዕራብ እና ላይ አራማጭሆ፣ ሳንጃ፣ ደንብያ፣ ጃን አሞራ፣ ዳባት፣ ደባርቅ እና ወገራ ወረዳዎች፤ እንዲሁም በወልቃይት አካባቢ ቃፍታ ሑመራ እና ጠገዴ ተከታታይ ውጊያ መደረጉን እና አሁንም በተጠቀሱ አካባቢዎች ውጊያዎቹ የቀጠሉ መሆናቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

kefagn-amhara-resistance

የአማራ ተጋድሎ መብት አራማጆችም በተለያዩ የሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች የተጋድሎው አርበኞች ከአገዛዙ ወታደራዊ ኃይሎች ጋር ውጊያ መግጠማቸውን እና ከ70 ያላነሱ የአገዛዙ መንግሥት ወታደሮች ሲገደሉ ከአማራ ተጋድሎ በኩል 2 ያህል አርበኞች መገደላቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ አገዛዙን ስርዓት ለመጣል በይፋ ሁለገብ ትግል እያደረገ የሚገኘውና በፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የሚመራው የአርበኞች ግንቦት 7 ለፍትህና ለነፃነት ንቅናቄ በተለያዩ የሰሜን ጎንደር ዞን ወረዳዎች አውደ ውጊያዎች በአገዛዙ ወታደራዊ ኃይሎች ላይም ተደጋጋሚ ጥቃት በመክፈት ድል መቀዳጀቱን በመግለፅ ከንቅናቄው ወገን በወቅቱ አዛዥ የነበሩት ሻለቃ መሳፍንት ጥጋቡን (ገብርዬ) ጨምሮ የተወሰኑ ታጋዮቹ እንደተሰዉ ይፋ አድርጓል፡፡ በነበረው ውጊያም ንቅናቄው በርካታ የአገዛዙ ወታደሮችን መግደሉን፣ ማቁሰሉን እና መማረኩንም ይፋ አድርጓል፡፡

ገዥው መንግሥት በበኩሉ በሰሜን ጎንደር ዞን እና በምዕራብ ትግራይ ዞን የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ ኃይሎች ጋ ውጊያ መኖሩን እና በወቅቱ የንቅናቄው መሪ የነበሩት ሻለቃ መሳፍንት ጥጋቡን ገድሎ 70 ያህል የንቅናቄው ወታደሮችን መማረኩን በስሩ በሚቆጣጠረው የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ይፋ አድርጓል፡፡ ይሁን እንጂ ከአገዛዙ በኩል ስለደረሰ ጉዳት የጠቀሰው ነገር የለም፡፡ እንደ አካባቢው የዓይን እማኞች በበኩላቸው አገዛዙ ተጨማሪ በርካታ ወታደሮችን ከነ ሙሉ ትጥቃቸው ወደ ስፍራው ማንቀሳቀሱን እንደተመለከቱ ይናገራሉ፡፡ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በርካታ የአገዛዙ ወታደራዊ ተሸከርካሪዎች ጎንደር ከተማን ጨምሮ በተለያዩ የክልሉ የዞን እና የወረዳ ከተሞች እንደሚታዩ ተጠቁሟል፡፡

tplf-soldiers-logistic

አገዛዙ ተግባራዊ ያደረገውን የ6 ወር አስቸኳይ አዋጅ ተከትሎ ከአማራ ክልል ብቻ ከ 19 ሺህ ያላነሱ ሰላማዊ ዜጎችን በተለያዩ የክልሉና የፌደራል እስር ቤቶች በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስቱ መታሰራቸውን የአማራ ተጋድሎ የመብት አራማጆች እና የአካባቢው የፖሊስ መረጃ ምንጮች የጠቆሙ ሲሆን፤ የተጠቀሰው አሀዝ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፊት በነበሩ ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ ወቅት የታሰሩትን ቁጥር ሳይጨምር እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ የአገዛዙ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የአንድ ወር የወሰደውን ርምጃን ይፋ ባደረገበት ወቅት በአጠቃላይ 11,706 ያህል ዜጎች መታሰራቸውን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡

እንደ መረጃ ምንጮች ጥቆማ ከሆነ፤ በአማራ ክልል ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. የወልቃይት ጠገዴ ሁመራ የአማራ ማንነት የመብት ጥያቄ መነሻ አድርጎ በነበረው ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ ተቃውሞ ተከትሎ በአገዛዙ በርካታ ሰላማዊ ዜጎች መገደላቸው፣ መታሰራቸውና ለከፋ ስቃይ መዳረጋቸው ያስቆጣቸው የአማራ ማኀበረሰብ አባላት መካከል በርካታ ሰዎች ራሳቸውን ” ከፋኝ” በሚል በየአካባቢው የጎበዝ አለቃ በሚመራ የአማራ ተጋድሎ ራሳቸውን አደራጅተው በአገዛዙ ላይ የአፀፋ እርምጃ መውሰድ እንደጀመሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ የአንድ ዓመት እስር እና 1,500 ብር ቅጣት ተፈረደበት

ኢትዮ ምህዳር ጋዜጣም 10ሺህ ብር ቅጣት ተፈረደበት

getachew-worku

(አዲስ ሚዲያ) ዛሬ ህዳር 6 ቀን 2009 ዓ.ም.  የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 6ኛ ወንጀል በዋለው ችሎት የኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ መስራች እና ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ አንድ ዓመት እስራትና 1,500 ብር ቅጣት ተፈረደበት፡፡ ከጋዜጠኛው በተጨማሪ ድርጅቱ ኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣም የ10 ሺህ ብር ቅጣት ተፈርዶበታል፡፡

ጋዜጠኛው እና ጋዜጣው ላይ የዛሬ ፍርድ ውሳኔ የተላለፈው አዲስ አበባ መንበረ ጵጵስና ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ውስጥ ተፈፀመ የተባለውን ሙስና የሚያጋልጥ ዜና በጋዜጣው መሰራጨቱን ተከትሎ፤ የደብሩ እና የቤተክህነቱ ኃላፊዎች ”በጋዜጣው ስማችን ጠፍቷል” በሚል በመሰረቱት ክስለ መሆኑ ታውቋል፡፡
ከፍርድ ቤቱ ቅጣት ውሳኔ በኋላም ጋዜጠኛው በፀጥታ ኃይሎች ተይዞ አዲስ አበባ አቃቂ ቃሊቲ በሚገኘው ቂሊንጦ ወህኒ ቤት የእስር ቅጣቱ ተፈፃሚ እንዲሆን ፍርድ ቤቱ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት በፀጥታ ኃይሎች ተይዞ መታሰሩ ታውቋል፡፡ በችሎቱ ላይ ከወዳጆቹ እና ጋዜጠኞች በተጨማሪ ከሳሾቹ ካህናት እና የደብሩ ኃላፊዎች ተገኝተው እንደነበር የተጠቆመ ሲሆን፤ ጋዜጠኛውም በመጨረሻ ”እውነት ትመነምናለች እንጂ አትጠፋም፤እውነቱ አንድ ቀን ይወጣል፡፡ ይህ ፍርድ የተፈረደብኝ ጋዜጣውን ለመዝጋት ታቅዶ ነው፡፡” ማለቱ ተሰምቷል፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ ቀደም ሲል ሐዋሳ ዩኒቨርስቲን ጨምሮ የተለያዩ ተቋማት ላይ የተፈፀሙ የሙስና መረጃዎችን በጋዜጣው ለህዝብ በማድረሱ ተከሶ ከፍተኛ መጉላላት፣ እስርና እንግልት እንዲሁም በባልደረባው ጋዜጠኛ ኤፍሬም በየነ ላይ ከፍተኛ የአካል ጉዳት ደርሶ እንደነበር አይዘነጋም፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው በአዲስ አበባ መንበረ ጵጵስና ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተፈፀመ ሙስና የሚያጋልጥ ዜና በቂ መረጃ እንዳለው ለፍርድ ቤቱ በተደጋጋሚ ቢያሳውቅም፤ ፍርድ ቤቱ ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡ ጋዜጠኛው ለቀጣይ አንድ ዓመት በእስር ቅጣት እንዲያሳልፍ በመወሰኑ ላለፉት አምስት ተከታታይ ዓመታት ለንባብ ይበቃ የነበረው ኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ህትመትም እንደማይቀጥል መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ ከኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅነት በተጨማሪ በመንግሥት እውቅና የተነፈገውና በ2004 ዓ.ም. ለኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መብትና ጥቅም እንዲሁም በፕሬስ ነፃነት ዙሪያ ለመስራት የተቋቋመው የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ ጠቅላላ ጉባኤ ምክትል ሰብሳቢ እንደነበርም ይታወቃል፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ በአንድ ወር ብቻ 11,700 በላይ ዜጎችን ማሰሩን አስታወቀ

(አዲስ ሚዲያ)ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በኦሮሚያ፣ በአማራ እና በደቡብ ክልል ኮንሶ የነበረውን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ በተፈጠረው ህዝባዊ ቁጣ ለማረጋጋት በሚል ባለፈው መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ተግባራዊ በሆነው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ን ተከትሎ 11,607 ዜጎች መታሰራቸውን ገዥው መንግሥት አስታውቋል፡፡

ከታሰሩት መካከል ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ የመብት አራማጆች፣ተማሪዎች፣ መምህራን፣ ገበሬዎች፣ ሴቶች እንዲሁም በርካታ ወጣቶች እንደሚገኙበት ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዕድሜ የገፉ አዛውንትም የታሰሩ እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡ ይሁን እንጂ አዋጁን ተከትሎ በአንድ ወር ውስጥ ብቻ መታሰራቸው ይፋ የተደረገው የታሳሪዎች ቁጥር ከዚህ ቀደም በህዝባዊ ተቃውሞው ወቅት በ10 ሺህዎች የሚገመቱ የታሰሩትን እንደማያካትት ተጠቁሟል፡፡

ገዥው መንግሥት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ህዝባዊ ተቃውሞውን ለማረጋጋት ቢሞክርም፤ አሁንም በተለይ በአማራ ክልል ሰሜን እና ደቡብ ጎንደር እንዲሁም ምዕራብ ጎጃም ተቃውሞ እና የመንግሥት ወታደራዊ የኃይል ርምጅ በተለይም ግድያ እና የአካል ማጉደል ርምጃዎች መቀጠላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በኦሮሚያም ክልል በተለይም ምዕራብ እና ደቡብ ምዕራብ ሸዋ እና አርሲ አካባቢ ተቃውሞች እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡

በተለይ አዋጁን ተከትሎ የፀጥታ ኃይሎች በወንጀል የጠረጠሩት ሰው ላይ ያለምንም ፍርድ ቤት ትዕዛዝ እርምጃ እንዲወስዱ ስልጣን መስጠቱ ቢታወቅም፤ ከተጠቀሰው የ11706 እስረኞች በስተቀር ስለተፈፀመው እርምጃና ስለተጎጂዎች የተሰጠ ዝርዝር ማብራሪያም ሆነ መረጃ የለም፡፡

እነ በቀለ ገርባ ላይ የአቃቤ ህግ ምስክሮች አልተሰሙም፤ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ተጠርጣሪዎችን አሟልቶ አላቀረበም

‹‹እሰነጥቅሃለሁ ተብያለሁ›› አቶ በቀለ ገርባ

bekele-gerba-et-al

በኢትዮጵያ ኦሮሚያ ክልል ውስጥ የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ለእስር ተዳርገው የሽብር ክስ የቀረበባቸው የኦፌኮ ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ከሦስት ወራት በኋላ እንደገና ወደ ችሎት ሲመለሱ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ቀጠሮ በመያዝ የነበር ቢሆንም፣ በእስር የሚገኙበት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ተጠርጣሪዎችን አሟልቶ ባለማቅረቡ ምክንያት ምስክሮቹ ሳይሰሙ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ ህዳር 2 ቀን 2009 ዓ.ም በዋለው ችሎት ላይ እንደተመለከተው በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ ከተካተቱት ተጠርጣሪዎች (22 ሰዎች) መካከል 5ቱን ማረሚያ ቤቱ አላቀረባቸውም፡፡ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ህዳር 2 ቀን 2009 ዓ.ም ለፍርድ ቤቱ በጻፈው ደብዳቤ እንደገለጸው ‹4ቱ ተጠርጣሪዎች በቂሊንጦ የደረሰውን የእሳት ቃጠሎ አደጋ ተከትሎ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደው ስላልተመለሱ› ማቅረብ አልቻለም፡፡ ማረሚያ ቤቱ ሸዋሮቢት እንደሚገኙ ያመለከታቸው ተጠርጣሪዎች ገላና ነጋሪ፣ ገመቹ ሻንቆ፣ ደረጀ መርጋ እና ቶምሳ አብዲሳ ናቸው፡፡

ሆኖም ግን ማረሚያ ቤቱ በስም ጠቅሶ ሸዋሮቢት ስለሆኑ ማቅረብ አለመቻሉን ከጠቀሰው ሌላ አንድ ተጠርጣሪ ችሎት አለመገኘቱን በማጣራት ፍርድ ቤቱ ተጠርጣሪውን ለምን እንዳላቀረበ የማርሚያ ቤቱን ተወካይ ጠይቋል፡፡ ሆኖም የዕለቱ ጉዳይ አስፈጻሚ ምክትል ሰርጀንት ዘውዱ ወልደማርያም ተጠርጣሪው በእርግጥ የት እንደሚገኝ እንደማያውቁ ተናግረዋል፡፡ ይህ የት እንዳለ ያልታወቀው ተጠርጣሪ ጭምሳ አብዲሳ ይባላል፡፡

በዛሬው የችሎት ውሎ ተጠርጣሪዎች ብቻ ሳይሆኑ ጠበቆችም ተሟልተው አለመቅረባቸው ታውቋል፡፡ የብዙዎቹ ተጠርጣሪዎች ጠበቃ የሆኑት አቶ ወንድሙ ኢብሳ አልቀረቡም፡፡ ተከሳሾችም ጠበቃቸው ከቀጠሮ በፊት ደንበኞቻቸውን ለማነጋገር ወደቂሊንጦ ሄደው ማግኘት እንደማይችሉ ተነገሯቸው መመለሳቸውን ከማወቃቸው ውጭ በዛሬው ችሎት ለምን እንዳልቀረቡ እንደማያውቁ ለችሎቱ ተናግረዋል፡፡ በችሎት የቀረቡት ሌሎች ጠበቆችም ቢሆን ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ደንበኞቻቸውን በነጻነት ስለጉዳያቸው ለማነጋገር እንዳይችሉ እንቅፋት እየፈጠረባቸው መሆኑን አመልክተዋል፡፡

ችሎቱ ዛሬ የተሰየመው የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት መሆኑን በመጥቀስ አቃቤ ህግ ከአጠቃላይ 42 ምስክሮቹ መካከል አምስቱ መቅረባቸውን በመግለጽ ምስክሮቹ ቀርበው እንዲሰሙለት ጠይቋል፡፡ ሆኖም ግን ተከሳሾቹ ሁሉም ተሟልተው ባልተገኙበት ሁኔታ ምስክር ሊሰማ እንደማይገባ ጠቅሰው ተቃውመዋል፡፡ ተከሳሾቹ በክሱ ላይ በጋራ የቀረበባቸው ፍሬ ነገር ስላለ በተናጠል ምስክሮች ቢደመጡ መብታችንን ይነካል በሚል በጠበቆቻቸው አማካኝነት አስረድተዋል፡፡

በሌላ በኩል አቶ በቀለ ገርባ አሁን ጉዳያቸውን እየየ የሚገኘው ችሎት በክስ መቃወሚያቸው ላይ ጉዳያቸው በፌደራል ፍርድ ቤት ሳይሆን በኦሮሚያ ክልል ፍርድ ቤቶች ሊታይ ይገባል በሚል ያነሱትን ህገ-መንግስታዊ የመብት ጥያቄ በጣሰ መልኩ ሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም መቃወሚያቸውን ውድቅ ማድረጉን በማስታወስ፣ በፍርድ ቤቱ ገለልተኝነት ላይ ጥያቄ ስላላቸው ችሎት ቀርበው ክርክር ለማድረግ እንደማይፈልጉ ቀደም ብለውም ገልተጸው እንደነበር ጠቅሰው በዛሬው ችሎት ላይም ፖሊስ በጉልበት እየደበደበ እንዳቀረባቸው አስረድተዋል፡፡

አቶ በቀለ ሌሎችንም ተከሳሾች በመወከል እንዳስረዱት ከዚህም በኋላ ችሎት የሚቀርቡ ከሆነ ተገደው እየቀረቡ እንዳሉ ችሎቱ እንዲያውቅላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ውድቅ ያደረገባቸውንና በክስ መቃወሚያ የጠቀሱትን ይህንኑ የህገ-መንግስት ጉዳይ ከጠበቆቻቸው ጋር ተመካክረው ወደ ፌደሬሽን ምርድ ቤት የመውሰድ ሀሳብ እንዳላቸውም ጠቅሰዋል፡፡

ፖሊስ በጉልበት መኪና ውስጥ ካስገባን በኋላ ‹‹እሰነጥቅሃለሁ›› የሚል ዛቻ እንደደረሰባቸው፣ ይህን የተናገረውን ፖሊስ ችሎት ፊት ጠቁመው በማሳየት ጭምር ገልጸዋል፡፡ ሆኖም ግን ይህን ዛቻ ያደረሰውን ፖሊስ ችሎቱ አንድም ጥያቄ ሳያቀርብለት አልፎታል፡፡

በመጨረሻም ፍርድ ቤቱ በዛሬው ውሎ ያልቀረቡ ተከሳሾችን ማረሚያ ቤት እንዲያቀርብ፣ 7ኛ ተከሳሽ ጭምሳ አብዲሳን ማረሚያ ቤት ለምን እንዳላቀረባቸው ምክንያት እንዲያስረዳ እንዲሁም የኦሮምኛና ስዋህሊ ቋንቋዎች አስተርጓሚዎች እንዲመደቡ ትዕዛዝ በመስጠት ተከሳሾቹ ተሟልተው ሲቀርቡ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት ለህዳር 6 ፍርድ 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ፍርድ ቤት ማንኛውም ተከሳሽ በቀጠሮው ዕለት የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ አክብሮ መገኘት እንዳለበትም ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡

በዛሬው የችሎት ውሎ የኦሮምኛ ቋንቋ አስተርጓሚ ችሎቱ ባለማቅረቡ ከተከሳሾች መካከል አቶ በቀለ ገርባ በአጋዥነት ሲያስተረጉሙ ውለዋል፡፡ የዛሬውን ችሎት ከተከሳሽ ቤተሰቦች በተጨማሪ የዲፕሎማቲክ ኮሚኒቲ ተወካዮችና ጋዜጠኞች ተከታትለውታል፡፡
ምንጭ፡- EHRP.

ጋዜጠኛ እና ጦማሪ በፍቃዱ ኃይሉ በድጋሚ ታሰረ

“ኮማንድ ፖስቱ ሊያናግርህ ይፈልጋል”

befekadu-hailu

ከተለያዩ አለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተቆርቋሪ ድርጅቶች ከዞን፱ ጦማሪያን ስብስብ ጋር በመሆን ሽልማቶችን ያገኘው ጋዜጠኛ እና ጦማሪ በፍቃዱ ኃይሉ ህዳር 02 ቀን 2009ዓ.ም ጠዋት ከቤቱ በፀጥታ ኃይሎች ወደ ፖሊስ ጣብያ ተወስዷል።

ጋዜጠኛ እና ጦማሪ በፈቃዱ ሚያዝያ 17 ቀን በ2006ዓ.ም ከሌሎች የዞን፱ ጦማሪያን እና ሶስት ጋዜጠኖች ጋር በመሆን በሽብር ወንጀል ተጠርጥሮ የተያዘ ሲሆን ከአንድ አመት ከስድስት ወር የእስር ቆይታ በኋላ የፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት የተከሰሰበትን የሽብር ወንጀል ወደ አመፅ ማነሳሳት ቀይሮ በ20ሺ ብር ዋስ እንዲወጣ ፈቅዶለት ነበር። በፍርድ ቤቱ ውሳኔ ያልተደሰተው አቃቤ ህግ በበፍቃዱ ላይና ሌሎች ፍርድ በቤቱ ነፃ የለቀቃቸው የዞን፱ ጦማሪያን (ሶልያና ሽመልስ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ አጥናፉ ብርሃኔና አቤል ዋበላ) ላይ ይግባኝ የጠየቀ ሲሆን የፊታችን ማክሰኞ ህዳር 06 ቀን 2009 ጠቅላይ ፍርድ ቤት አቃቤ ህግ በጠየቀው ይጋባኝ ላይ ውሳኔ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል።

በፈቃዱ ኃይሉ ከእስር ከተፈታ አንድ አመት በኋላ ዛሬ ጠዋት ላይ በመኖሪያ ቤቱ እያለ “ኮማንድ ፖስቱ ሊያናግርህ ይፈልጋል” በሚል በፀጥታ ሀይሎች ሊወሰድ ችሏል።

ጋዜጠኛ እና ጦማሪ እና የሰብአዊ መብት ተሟጋች በፍቃዱ ኃይሉ ከእስር ከተፈታ በኋላ በአጭር ጊዜ ተወዳጅ በሆነችውና ከ10 እትም በኋላ ከገበያ በወጣችው ውይይት መፅሄት ላይ በዋና አዘጋጅነት ይሰራ እንደነበር ይታወቃል።
ምንጭ፡- EHRP.