Category Archives: News

የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች የክስ መቃወሚያ ውድቅ ተደረገ

prisoners

በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት እየታየ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮችና ሌሎች በተመሳሳይ መዝገብ የተከሰሱት ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ ላይ ያቀረቡት መቃወሚያ ውድቅ ተደረገባቸው፡፡ አመራሮቹ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም ችሎት ቀርበዋል፡፡

በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የተከሰሱት የአንድነት፣ የሰማያዊና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች የሆኑት አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዳንኤል ሺበሽ እና ሌሎች ስድስት ተከሳሾች መቃወሚያቸው በፍርድ ቤቱ ውድቅ ተደርጓል፡፡

ተከሳሾች በጠበቆቻቸው አማካኝነት የቀረቡባቸው የተለያዩ የክስ ይዘቶች ላይ መቃወሚያቸውን አቅርበው የነበር ቢሆንም ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ የተከሳሽ መቃወሚያ ውድቅ እንዲደረግለት የጠየቀውን በመቀበል ‹‹በመቃወሚያው ላይ የተነሱት ነጥቦች በአብዛኛው ማስረጃ በማሰማት ሂደት ወቅት ሊረጋገጡ የሚችሉ ስለሆኑ›› በሚል መቃወሚያቸው ውድቅ ተደርጓል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤት በቀረበው ክስ አግባብ የክስ ሂደቱ እንዲቀጥል ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

በሌላ በኩል ተከሳሾች በእስር ላይ በሚገኙበት ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ላይ ‹‹የመብት ጥሰት እየተፈጸመብን ነው›› በሚል አቤቱታ አቅርበው የነበር ሲሆን በአቤቱታው ላይ እስካሁን ከማረሚያ ቤቱ መልስ አለመሰጠቱ ታውቋል፡፡ አቤቱታው በጽሑፍ ተገልብጦ ለማረሚያ ቤቱ መላኩን የገለጸው ፍርድ ቤቱ፣ ለአቤቱታው መልስ ከማረሚያ ቤቱ እየተጠበቀ እንደሆነ ተገልጹዋል፡፡

በመሆኑም ይህንኑ የማረሚያ ቤቱን መልስ ለመስማትና የክሱን ሂደት ለመቀጠል ፍርድ ቤቱ ለየካቲት 11 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ምንጭ፡-ነገረ-ኢትዮጵያ

“የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና ምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!” በምርጫ ቦርድ የፈረሰው አንድነት

በቅርቡ በ”ኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ” ፈርሶ ዋና ጽህፈት ቤቱ በፖሊስና በደህንነት ቁጥጥር ስር ከዋለ በኋላ ፤ የፓርቲው ጽህፈትም “ምርጫ ቦርድ” መርጫቸዋለሁ ላላቸው አካላት ከተላለፈ በኋላ አባላቱና አመራሩ ትግላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል፡፡ ፓርቲው የአንድነት ዓላማዎችና እሴቶች በገዥው ፓርቲ እና ምርቻ ቦርድ ህገ-ወጥ ሴራ እንደማይጠፋ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ሙሉ መግለጫውን ከታች ይመልከቱ፡-

udj

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)

UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)

ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የተሠጠ መግለጫ
********************************************************************************

የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና በምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!
***********************************************************************************
ገዢው ፓርቲ ለጻፋቸው ህጎችም ሆነ ይህን እንዲተገብሩ ኃላፊነት የወሰዱትን ሰዎች ክብር በሚያዋርድ መንገድ፤ በየደረጃው ያሉ ምርጫ ቦርድ ኃላፊዎችም ለመዋረድ ፈቃደኛ ሆነው በአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) አባላት አንድ ድምፅ ለማግኘት ለተቸገረ፤ ነገር ግን ለገዢው ፓርቲ ለመላላክ ቁርጠኛ ለሆነ ግለሰብ ዕውቅና ሰጥቻለሁ ማለቱ የሚታወስ ነው፡፡ ይሁን እንጂ አንድነት ፓርቲ የተቋቋመበት መሰረት የምርጫ ቦርድ ዕውቅና ሳይሆን በእያንዳንዱ አባላት ዘንድ የሚቀጣጠለው የነፃነት ስሜት እና ኢትዮጵያዊነት ነው፡፡ የአንድነት ፓርቲን መንፈስ፣ አላማዎቸና እሴቶች በዚህ ዓይነት እኩይ ደባ ከአባላትና ደጋፊ አዕምሮ ማውጣት አይቻለም፡፡

የምርጫ ቦርድ ተብዬው ተቋም በገዢው ፓርቲ ደህንነት የተደራጁ የፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔ አባላት ያልሆኑ ሰዎች ያካሄዱትን ህገወጥ ስብሰባ ጉባዔ ነው በማለት እውቅና ሰጥቻለሁ ሲል፤ የተሰበሰቡት ሰዎች የአንድነት አባላት መሆናቸውን እና የጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ መሆናቸውን አረጋግጣችኃል ወይ? ለሚል ቀላል የጋዜጠኛ ጥያቄ መልስ መስጠት አልቻሉም፡፡ ዕቅዱም አንድነትን እንደተቋም ማፍረስ ስለነበር ይህን ሊያስፈፅም ለሚችል ተላላኪ መስጠታቸውን በይፋ ከተናገሩ በኋላ በማግስቱም የፓርቲውን ፅ/ቤት በጠብመንጃ አፈሙዝ አስወርረው ለህገወጥ ቡድን በህገወጥ መንገድ አስረክበዋል፡፡

የአንድነት ፓርቲ በዚህ ዓይነት ህገወጥ ድርጊት የሚፈርስ አይደለም፡፡ የአንድነት አባላት በየትም ቦታ የምትገኙ ሁሉ ይህን ህገወጥ እርምጃ በፅኑ እየተቃወማችሁ ለነፃነትና ለኢትዮጵያዊነት የሚከፈለውን መስዋዕትነት ለመከፍል ዝግጁ መሆን ይኖርባቸኋል፡፡ አንድነት ፓርቲ በሰላማዊ ትግል ስልት የሚያምን በመሆኑ ይህን ትግል በላቀ ደረጃ ለማስቀጠል አበክሮ ይስራል፡፡ እያንዳንዱ አባልም አሁን በተፈጠረው ሁኔታ ሳይደናገጥ ለሰላማዊ ትግል ያለውን ፅናት እንደሚያስቀጥል እምነታችን ነው። በአንድነት ስራ አስፈፃሚ እምነት አሁን ባለው ሁኔታ የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ ተቀበረዋል የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሰናል።

በመሆኑም ስርዓቱ ለመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ የሚመች የአስተሳሰብ ለውጥ እሰካላመጣ ድረስ ምርጫን በየአምሰት ዓመት የሚደረግ ክብረ በዓል አድርጎ ለማድመቅ እና የህዝብ ሀብት ለማባከን በሚደረግ ሂደት ተሳተፊ ለመሆን አዲስ ፓርቲ መመስረትም ሆኖ አሁን ካሉት ፓርቲዎች ጋር ተቀላቅሎ መታገል የሚያመጣው ለውጥ የለም፡፡ ምክንያቱም እነርሱም ልከ በአንድነት ላይ እንደተደረገው በሀይል እንዲፈርሱ የማይደረጉበት ምንም ዓይነት ዋስትና አለ ብለን ስለማናምን ነው። ከዚህ በኋላ በመድብለ ፓርቲ ሰርዓት ስልጣን ይያዛል ብሎ ማመን ህዝቡን ማታለል ነው የሚል ፅኑ እምነት አለን፡፡ ነገር ግን አሁንም የፓርቲ ፖለቲካ አላበቃም ብለው የሚያምኑ የአንድነት አባላት ካሉ በራሳቸው ነፃ ውሳኔ ወደ ፈለጉት ፓርቲ ተቀላቅለው የመታግል መብታቸው የተጠበቀ ነው።

የኢትዮጵያ ህዝብ አሁን ካለበት አምባገነናዊ ስርዓት ተላቆ ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲሸጋገር ለማድረግ ህዝቡ የትግሉ ባለቤት ሆኖ የስርዓት ለውጥ እንዲመጣ እኛም የበኩላችንን ሀገራዊ ግዴታችንን ለመወጣት ቁርጠኞች ነን፡፡

ድል የህዝብ ነው!!!

አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)

ጥር 26 ቀን 2007

ብሎገሮቹና ጋዜጠኞቹ ሰብሳቢ ዳኛው ከችሎት እንዲነሱ ጠየቁ

ከቀኝ ወደ ግራ የዞን 9 ብሎገር ማህሌት ፋንታሁን እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ ከችሎት ሲወጡ

ከቀኝ ወደ ግራ የዞን 9 ብሎገር ማህሌት ፋንታሁን እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ ከችሎት ሲወጡ

በእነ ሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው የዞን ዘጠኝ ብሎገሮችና ጋዜጠኞች፤ ሰብሳቢ ዳኛው ከችሎት እንዲነሱ ጠየቁ፡፡
ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም ለ17ኛ ጊዜ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 1ልደታ ምድብ 9ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት ብሎገሮቹና ጋዜጠኞቹ የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ የሆኑት አቶ ሸለመ በቀለ “የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብታችንን አላስከበሩልንም” በሚል ከችሎት እንዲነሱ በጽሑፍ አቤቱታ አቅርበዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የተሰየመው ተሻሽሎ ቀርቧል በተባለው የአቃቤ ህግ ክስ ላይ የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል ለመስማት እንደነበር ዳኞቹ ቢናገሩም፣ ተከሳሾች አቤቱታ እንዳላቸው በመግለጽ የእምነት ክህደት ቃል ለመስጠት ዝግጁዎች አለመሆናቸውን ለችሎቱ ማስረዳት ችለዋል፡፡
ተከሳሾች ‹‹እኛ በሰብሳቢ ዳኛው ላይ አቤቱታ አለን፤ ፍርድ ቤቱ የራሱን ውሳኔ እንኳ አላከበረም፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሆነን የእምነት ክህደት ቃላችንን ለመስጠት ዝግጁዎች አይደለንም›› በሚል ፍርድ ቤቱ አቤቱታቸውን እንዲቀበል ጠይቀዋል፡፡

ዳኛ ሸለመ በቀለ “ፍርድ ቤቱ ቃሉን አላከበረም›› በሚለው ጉዳይ ላይ መልስ ሲሰጡ ‹‹የእኛን ውሳኔ የማትቀበሉ ከሆነ ጉዳዩን በይግባኝ እንዲታይ ማድረግ ይቻላል” ብለዋል፡፡
“ላለፉት ስድስት ወራት በነበረው የክርክሩ ሂደት የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ ሂደቱን በአግባቡ በመምራት የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብታችንን አላስጠበቁልንም፡፡ በተለያየ ጊዜም ሐሳባችን ለመግለጽ ስንሞክር ክልከላ አድርገውብናል፡፡ አሁን ደግሞ ችሎቱ ራሱ የሰጠውን ትዕዛዝ ራሱ ሽሮ ፈጽሞ ልንረዳው በማንችለውና የመከላከል መብታችንን በሚያጣብብ የክስ ሁኔታ ክርክሩን እንድንቀጥል ሲበየንብን የችሎቱ ሰብሳቢ ወሳኝ ሚና ነበራቸው” ሲሉ ተከሳሾች በሰብሳቢ ዳኛው ላይ ቅሬታቸውን በአቤቱታቸው ገልፀዋል፡፡
ፍርድ ቤቱም የችሎቱ ሰብሳቢ ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ ከችሎት እንዲነሱ የሚጠይቀውን አቤቱታ አይቶ ነገ ብይን ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል ሲል ነገረ-ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡

በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉት “ፀረ- ሰላም ህፃናት”

ጌታቸው ሽፈራው

ጌታቸው ሽፈራው

ጌታቸው ሽፈራው

አቶ ቀኖ የሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት ውስጥ በጥበቃነት ይሰራሉ፡፡ አቶ ቀኖና ጎረቤቶቻቸው ሰብሰብ ሲሉ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ በተለይ ኢህአዴግ ስለሚወስዳቸው ህገ ወጥ እርምጃዎች፣ ስለተቃዋሚዎች ጥንካሬና ድክመት… የመሳሰሉት ጉዳዮች ላይ ያወራሉ፣ ይወያያሉ፣ በሚያከራክሯቸው ነገሮችም ይከራከራሉ፡፡ ይህ የእነ አቶ ቀኖ ሰፈር ሰዎች የውይይት መድረክ በእነሱ ብቻ ተወስኖ አልቀረም፡፡ ጉዳዩ በመደጋገሙ ህፃናት ልጆቻቸው ሳይቀር ‹‹ሰማያዊ፣ አንድነት፣ መድረክ፣ ኢህአዴግ…..›› እያሉ የአቅማቸውንና የገባቸውን ያህል ያወራሉ፡፡ ቤተሰቦቻቸው ሲከራከሩና ሲያወሩ ከሰሙት! በዚህ አቋማቸውም ህፃናቱ ‹‹ፀረ ሰላም›› ተብለው ታስረውበታል፣ ተደብድበውና ይቅርታ ጠይቀውም ተለቀዋል፡፡

ማክሰኞ ጥር 19 ቀን 2007 ዓ.ም ነው፡፡ ከቀኑ 11፡30 አካባቢ አራዳ ክፍለ ከተማ የሚገኘው መስከረም 2 ት/ቤት ተማሪዎች የሆኑት 14 ያህል ህጻናት ወደ ቤታቸው እየተመለሱ ነው፡፡ ህፃናቱ እንደወትሯቸው ከት/ቤተ መልስ እየተጨዋወቱ፣ እየተቀላለዱ፣ እየተሯሯጡ ወደ ቤታቸው በመመለስ ላይ ናቸው፡፡ መሃል ላይ ግን ቤተሰቦቻቸው በተደጋጋሚ የሚያነሱትን ጉዳይ አንስተው መከራከር ጀምረዋል፡፡ የ13 አመት እድሜ ያለውና የ6ኛ ክፍል ተማሪ የሆነው የአቶ ቀኖ ልጅ ‹‹ኢህአዴግኮ ፈሪ ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲን ይፈራዋል›› ይላል፡፡ ጓደኛው ደግሞ ‹‹ኢህአዴግማ የሚፈራው አንድነትን ነው፡፡›› ይላል፡፡ ሌላኛው ደግሞ ‹‹መድረክ የሚባል ፓርቲምኮ አለ፡፡ እሱንም ይፈራዋል፡፡ ኢህአዴግ ፈሪ ነው!›› ይላል፡፡ ሌሎቹም ቤተሰቦቻቸው ውሃ፣ መብራትና ኔትዎርክ ሲጠፋ፣ ኑሮ ሲወደድ፣ ሙስና ሲያስመርራቸው በስርዓቱ ላይ ከሚያሰሙት ሮሮ መካከል የሚያስታውሱትን እየጠቀሱ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ይከራከራሉ፣ ያወራሉ፡፡ ይቀልዳሉ!

ይህኔ ነው አስገራሚው ነገር የተከሰተው፡፡ ፖሊስ 14ቱንም ህፃናት በ‹‹ፀረ ሰላም›› እንቅስቃሴያቸው ከእነ ሙሉ የትምህርት መሳሪያቸው በቁጥጥር ስራ ካዋላቸው በኋላ በጥፊና በእርግጫ እያለ ወደ ወረዳ 7 ፖሊስ ጣቢያ ይወስዳቸዋል፡፡ ፖሊስ ጣቢያ ከደረሱ በኋላም ‹‹ተንበርከክ!›› ተብለው ‹‹ማን ነው ሰማያዊ፣ አንድነት፣ መድረክ እያለ ሲያወራ የነበረው?›› እየተባሉ ህፃናት ላይ ይፈፀማል ተብሎ የማይታሰብ ድብድባ ይፈፀምባቸዋል፡፡ ህፃናቱ ‹‹ፀረ ሰላም›› ለተባለው እንቅስቃሴያቸው ቅጣትና ማስፈራሪያ ከተደረገባቸው በኋላ ‹‹ከአሁን በኋላ አይደግመንም›› ብለው ይቅርታ ጠይቀው በ‹‹ፖሊስ ሆደ ሰፊነት›› ከምሽቱ 1 ሰዓት አካባቢ ከእስር ተለቀዋል፡፡

እነዚህ ህጻናት ‹‹ዳግመኛ አይለምደንም!›› ብለው ይቅርታ ባይጠይቁ ኖሮ ታስረው ሊያድሩም ይችሉ ነበር፡፡ ምን አልባትም ፖሊስ ‹‹ያልተፈቀደ ቅስቀሳ አድርገዋል፣ ህገ መንግስቱን ለመናድ ጥረዋል፣ ህዝብን ለማናወፅና አመጽ ለመቀስቀስ ተደራጅተው ተንቀሳቅሰዋል፣ ምርጫው ሰላማዊ እንዳይሆን እየሰሩ ነው….›› የሚል ክስ እንደማይመሰርት እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ እስካሁን ፖሊስ ሲያቀርባቸው ካየናቸው አስቂኝ የቀጠሮ ማራዘሚያ ‹‹ምክንያቶች›› አንጻር ‹‹አብረዋቸው የሚማሩት ሌሎች ግብረ አበሮቻቸው አልተያዙም፣ ቢወጡ አሁንም ተመሳሳይ ‹ፀረ ሰላም› ተግባር ይፈፅማሉ፣ መረጃ ይደብቁብኛል›› በሚል ተጨማሪ ቀን ይሰጠኝ ላለማለቱ እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡

ስርዓቱን ለመከላከል ሲባል እስሩ እዚህ ደርሷል!

የአንድነት ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት በፖሊስ ቁጥጥር ስር ዋለ

የአዲስ አበባ ፖሊስ የአንድነት ፓርቲ ዋና ጽ/ቤትን ሲቆጣጠር የሚያሳይ

የአዲስ አበባ ፖሊስ የአንድነት ፓርቲ ዋና ጽ/ቤትን ሲቆጣጠር የሚያሳይ

አዲስ አበባ ቀበና የሚገኘው የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዋና ጽህፈት ቤት በፖሊስ እና ደህንነቶች ቁጥጥር ስር ዋለ፡፡ የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት በቁጥጥር ስራ የዋለው ምርቻ ቦርድ ለእኔ ይታዘዘኛል በሚል የፓርቲውን ስምና ህልውና ለነ አቶ ትዕግስቱ አወሉ ማስረከቡን ተከትሎ ነው፡፡ ፖሊስ አርብ ጥር 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ጽህፈት ቤቱን ከመቆጣጠሩ በፊት የፓርቲው ስራ አስፈፃሚዎች ስብሰባ ተቀምጠው እንደነበርና በዕለቱ ከሰዓት በኋላ የፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት በምርጫ ቦርድ ውሳኔ ጉዳይ ለመምከር ወደ ጽህፈት ቤቱ ሲያመሩ በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉ ተረጋግጣል፡፡ በዕለቱ ጠዋት ስራ አስፈፃሚው በጉዳዩ ዙሪያ ከመከረና ከተወያየ በኋላ ለምሳ ወጥተው ለምክር ቤቱ ስብሰባ ሲመለሱ ወደ ቢሮው መግባት የተከለከሉ ሲሆን፤ ቢሮው በፖለስ ቁጥጥር ስር በመዋሉ ቀጠሮ የተያዘለት የፓርቲው ምክር ቤት ስብሰባም ሳይካሄድ መቅረቱ ታውቋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የፓርቲው ስራ አስፈፃሚዎች ለምሳ ሲወጡ ትተዋቸው የሄዷቸውን ተሸከርካሪም ሆነ ማንኛውንም ወረቀት ይዘው እንዳይወጡ ከታገዱ በኋላ ፖሊሶቹ በስልክ በተሰጣቸው ትዕዛዝ ስራ አስፈፃሚዎቹ መኪናቸው ብቻ ተፈትሾ እንዲወጣ መደረጉን የፓርቲው ምክትል ፕሬዘዳንት አቶ ግርማ ሰይፉ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ተናግረዋል፡፡ ፖሊስ ቢሮውን ሲቆጣጠር ከስራ አስፈፃሚው ውጭ በቢሮ ያሉ የፅህፈት ቤት ሰራተኞችና ሌሎች የፓርቲው አባላትና አመራሮች ላልተወሰነ ጊዜ ከቢሮ እንዳይወጡ፣ከግቢ ውጭ የነበሩትም እንዳይገቡ መደረጉን የአይን እማኞች ለአዲስ ሚዲያ ገልፀዋል፡፡ ፖሊስ ቢሮውን በኃይል ሲቆጣጠር ምንም ዓይነት የፍርድ ቤት ትዕዛዝ አለመያዙ ታውቋል፡፡ የአንድነት ፓርቲ ዋና ፅህፈት ቤት በምርጫ ቦርድ እነ ትዕግስቱ አወሉ ከተመረጡ በኋላ አሁንም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ይገኛል፡፡

በተመሳሳይ ዜና አዲስ አበባ ቸርችል ጎዳና አካባቢ የሚገኘው የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ዋና ጽህፈት ቤትም በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉ ተጠቁሟል፡፡ ፖሊስ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ የፓርቲዎቹን ዋና ጽህፈት ቤት ለምን እንደተቆጣጠረ እስካሁን የተገለፀ ነገር የለም፡፡ የአዲስ ሚዲያ ፖሊስ ምንጮች እንዳረጋገጡት ከሆነ፤ፖሊሶችም የፓርቲዎቹን ቢሮዎች ተቆጣጠሩ የሚል ትዕዛዝ ከመሰጠቱ በስተቀር ለምን እንደተቆጣጠሩ ራሳቸውም ምክንያቱን እንደማያውቁ ተጠቁሟል፡፡ ምርጫ ቦርድ መጪውን ምርጫ 2007 ዓ.ም. ሂደትን ተክትሎ በዋዜማው ሁለት አንድነት እና መኢአድ ፓርቲዎችን በማፍረስ ሌላ አዲስ ታሪክ አስመዝግቧል፡፡ ቀደም ሲል “የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ” ከህወሓት/ኢህአዴግ የተሰጠውን ትዕዛዝ ከማስፈፀም ውጭ ነፃና ገለልተኛ አይደለም፣ቦርዱን የሚመሩት ስራ አስፈፃሚዎችም ተቋሙን ለመምራት የሚያስችል አቅምና ቁርጠኝነት ስለሌላቸው ለተቋሙ አይመጥኑም፣..በሚል በተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተደጋጋሚ ትችት ይቀርብበት እንደነበር አይዘነጋም፡፡

አሁን ያለው የቦርዱ እንቅስቃሴ በቀጣይ ቀናትም ከምርጫው ዋዜማ እስከ ድህረ ምርጫ አዳዲስ ውሳኔዎችን እና እንቅስቃሴዎችን ሊያሳይ እንደሚችል ይጠበቃል፡፡