ዶክተር መረራ ጉዲና እና ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ክስ ተመሰረተባቸው
(አዲስ ሚዲያ) ከ3 ወር በፊት በአውሮፓ ፓርላማ ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ተጋብዘው ንግግር ያደረጉት ዶ/ር መረራ ጉዲና ወደ ሀገር ቤት ሲመለሱ ከአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ተይዘው ለ 3 ወራት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ከታሰሩ በኃላ የካቲት 16 ቀን 2009 ዓ።ም በገዥው መንግሥት ጠቅላይ አቃቤ ህግ አማካኝነት በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት ክስ ተመሰረተባቸው።

ዶክተር መረራ ጉዲና እና ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ
የቀድሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር የነበሩት እና የኦፌኮ ሊቀመንበር እንዲሁም የመድረክ ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት ዶክተር መረራ ክስ የተመሰረተባቸው፥ በአውሮፓ ህብረት በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ንግግር ለማድረግ ተጋብዘው ሲመለሱ የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራር እና ሊቀመንበር ከሆኑት ከፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ጋር ታይተዋል በሚል እንደነበር ይታወቃል።
በዶ/ር መረራ ስም የተከፈተው በዚሁ የክስ መዝገብ ፥ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ሁለተኛ ተከሳሽ ፣ አቶ ጃዋር መሃመድ ሶስተኛ ተከሳሽ በመሆን በልይሉበት ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡ ሶስቱም ተከሳሾች የተከሰሱት በወንጀለኛ መቅጫ ህጉን የተለያዩ አንቀጾች በመተላለፍ ሲሆን አራተኛ እና አምስተኛ ተከሳሽ የሆኑት የኢትዮጵያ ሳተላይ ቴሌቪዥን ( ኢሳት) እና ኦሮሞ ሚዲያ ኔትወርክ ( ኢኤም ኤን) ሲሆኑ፥ ተቋማቱ የፀረ ሽብር ህጉን በመተላለፍ ተከሰዋል፡፡
ዶ/ር መረራ ሌላ ተጨማሪ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን መተላፍ በሚል ክስ ተመስቶባቸዋል፡፡ የክሱ ጭብጥም ተከሳሾች በዋና አድራጊነት ሽብር ተግባር መፈጸማቸውን እና ለኦሮሚያ እና አማራ ክልል አመጾች ማነሳሳት እና ንብረት መውደም ተጠያቂ መሆናቸው በክሱ ላይ ተጠቅሷል።
የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤትም ክሱን ለማየት ለየካቲት 24 ቀን 2009 ዓ ም ቀነ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በተለይ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ከዚህ በፊት በሌሉበት በነ ጄነራል ተፈራ ማሞ የክስ መዝገብ የሞት ፍርድ የተፈረደባቸው ሲሆን፥ በነ አቶ አንዱዓለም አራጌ የክስ መዝገብ ደግሞ የዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት የተፈረደባቸው ሲሆን፥ የአሁኑ ከነ ዶ/ር መረራ ጉዲና ጋር የተመሰረተባቸው ክስ ለሶስተኛ ጊዜ መሆኑ ታውቋል።
መንግሥት ከህዳር 2008 ዓ ም ጀምሮ በተለይ በኦሮሚያ ፥ በአማራ ክልል እና በደቡብ ክልል ኮንሶ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀ ህዝባዊ አመፅን ተከትሎ በርካታ ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት ወታደራዊ ኃይል ሲገደሉ፥ በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ሲታሰሩ ከ15 ሺህ ያላነሱ በተለያየ ጊዜ ከእስር መልቀቁን መንግሥስት ቢያስታውቅም አሁንም ድረስ ህዝባዊ አመፁን ተከትሎ የታሰሩና ሰብዓዊ መብቶቻቸው እየተጣሰ ያሉ ዜጎች መንግሥስት ከእስር ልቅቄያቸዋለሁ ክሚለው ቁጥር እንደሚልቅ ይግመታል።
ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፊት መንግሥት በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ አማካኝነት ለህዝባዊ አምፁ ተጠያቂ ራሱ መንግሥት እና አመራሮች እንደሆኑ ቢይሳውቁም፥ ለግድያ፥ እስርና እንግልት የተዳረጉት ግን ሰላማዊ ዜጎች መሆናቸውን የሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች መግለፃቸው ይታወሳል።
እውቁ ፖለቲከኛ እና የኦፌኮ/መድረክ ከፍተኛ አመራር ዶ/ር መረራ ጉዲና ታሰሩ
(አዲስ ሚዲያ)የኦሮሞ ፌደራሊስት ሊቀመንበር እና የኢትዮጵ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንደነግ ግንባር (መድረክ) ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና ታሰሩ፡፡ ዶ/ር መረራ የታሰሩት በቤልጂየም ብራሰልስ የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ በተጋበዙት መሰረት ንግግር አድርገው ረቡዕ ህዳር 21 ቀን 2009 ዓ.ም. ወደ ሀገር ቤት ሲመለሱ አዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ሲደርሱ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መታሰራቸው ታውቋል፡፡ ዶ/ር መረራ የታሰሩት አብረዋቸው ከነበሩ ከሁለት የቅርብ ቤተሰቦቻቸው ጋር እንደነበርም ታውቋል፡፡

ገዥው የህወሓት/ኢህአዴግ መንግሥት በበኩሉ ዶክተር መረራ የታሰሩት “በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መመሪያ ቁጥር አንድ አንቀጽ 2 ላይ የተመለከተውን መመሪያ ተላልፈው በመገኘታቸው እና ከአርበኞች ግንቦት 7 መሪ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ጋር ተገናኝተው መግለጫ ሰጥተዋል“ በሚል መሆኑን በልሳኑ ፋና ብሮድካሲቲንግ ኮርፖሬት ዘገባ ይፋ አድርጓል፡፡
መንግሥት ባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. የተቀሰቀሰውን የኦሮሚያ ክልል የፀረ አገዛዝ ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ፤ በተመሳሳይ መልኩ ሐምሌ 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በአማራ ክልል እና በደቡብብ ክልል ኮንሶ የተዛመተውን ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ተከትሎ ከ1400 በላይ ዜጎች ሲገደሉ ከአንድ ሺህ ያላነሱ በፀጥታ ኃይሎች ወታደራዊ ርምጃ የቆሰሉ ሲሆን፤ ከ50 ሺህ ያላነሱ ዜጎች በእስር ላይ እንደሚገኙ የፖሊስ መረጃዎችና የሰብዓዊ መብት አራማጆች መረጃ አመልክቷል፡፡የህወሓት/ኢህአዴግ ደጋፊዎችም ዶ/ር መረራ በአውሮፓ ፓርላማ ንግግር ማድረጋቸውን ተከትሎ እንደሚታሰሩ የሚያመለክት ቅስቀሳ ሲያደሩ እንደነበረም መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በተለይ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀውን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞውን ተከትሎ ገዥው መንግሥት መስከረም 28 ቀን 2009 ኣ.ም ጀምሮ ለ6 ወራት ተግባረዊ የሚደረግ የአስቸኳይ ዚጌ አዋጅ አውጥቷል፡፡ አዋጁ ተግባራዊ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ ጋዜጠኞች፣ የተለያዩ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት፣ የመብት አራማጆችንና ሲቭል ማኀበረሰቡን ጨምሮ በአንድ ወር ብቻ ከ11,706 ማሰሩን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡
ዶ/ር መረራ ጉዲና በቅርቡ በጡረታ እንዲሰናበቱ ከመደረጋቸው በፊት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህርነት ለ28 ዓመታት ያገለገሉና የፓርላማ አባል የነበሩ ሲሆን፤ ላለፉት 20 ዓመታትም በሀገሪቱ ፖለቲካ ባላቸው ተሳትፎ በበርካታ ኢትዮጵያውያን ዘንድ የሚታወቁና ከፍተኛ ተቀባይነት እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ ቀደም ሲል የፓርቲያቸው ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ፣ ዋና ፀሐፊያቸው አቶ ደጀኔ ጣፋ፣ የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ አቶ ደስታ ዲንቃን ጨምሮ በርካታ አመራሮችና አባሎቻቸው ከአንድ ዓመት በፊት መታሰራቸው ይታወቃል፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ ትምህርት ክፍል ሊቀመንበር ከኃላፊነት መልቀቃቸውን ይፋ አደረጉ
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ማኀበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሊቀመንበር ዶ/ር ካሳሁን ብርሃኑ ራሳቸውን ከኃላፊነት ማንሳታቸውን የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ይፋ አደረገ፡፡ ዶ/ር ካሳሁን ከትምህርት ክፍሉ ሊቀመንበርነት ራሳቸውን ለማንሳት የተገደዱት፤ በትምህርት ክፍሉ ከ28 ዓመታት በላይ በፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና የስራ ውል በዩኒቨርስቲው አስተዳደር መቋረጡን ተከትሎ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
ዶ/ር ካሳሁን የዶ/ር መረራ የጡረታ ጊዜ እንዲራዘም ያስገቡት ጥያቄ በዩኒቨርስቲው አስተዳደር ውድቅ መደረጉ እና ከዚያም የትምህርት ክፍሉ ስለሚፈልጋቸው በራሱ የኮንትራት ውል አስፈርሞ ለሰባት ወራት ያሰራበት ክፍያ አለመፈፀሙን ተከትሎ ከመጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ራሳቸውን ከኃላፊነት ማንሳታቸውን የሚገልፅ ደብዳቤ ለዩኒቨርስቲው አስተዳደር ማስገባታቸው ታውቋል፡፡
በተለይ እንደ አሜሪካ ድምፅ ዘገባ ከሆነ፤ ዶ/ር ካሳሁን በዩኒቨርስቲው አስተዳደር በኩል በዶ/ር መረራ ጉዲና ላይ የተወሰደውን ርምጃ ተከትሎ “ የዩኒቨርስቲው አስተዳደር ለትምህርት ክፍሉ ጥያቄና ፍላጎት ምላሽ ባለመስጠቱ፤ የትምህርት ክፍሉን እያስተባበርኩ መቀጠል ከሞራልም አኳያ ተቀባይነት እንደሌለው ይሰማኛል፡፡” በማለት ከትምህርት ክፍሉ ሊቀመንበርነት ለመልቀቅ መወሰናቸውን የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘግቧል፡፡ ዶ/ር መረራ በበኩላቸው ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንደሚወስዱት አስታውቀዋል፡፡ በአሁን ወቅት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጡረታ ጊዜያቸው እንዲራዘም ጠይቀው የተፈቀደላቸውና እየሰሩ የሚገኙ በርካታ መምህራን እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ እስካሁን በዩኒቨርስቲው አስተዳደር ባልተገለፀ ምክንያት የዶ/ር መረራ ጉዲና የስራ ጥያቄ ብቻ ተቀባይነትን ሊያገኝ አለመቻሉ ታውቋል፡፡
ዶ/ር መረራ ከዚህ ቀደም ለሙሉ ፕሮፌሰርነት የሚያበቃ በርካታ ጥናቶችን አጠናቀው ማዕረጉን ለማግኘት ያቀረቡት ማመልከቻ በሚመለከተው የመንግሥት አካል ተቀባይነት እንዳላገኘ የሚታወቅ ነው፡፡ ዶ/ር መረራ ከዚህ ቀደምም ሆነ አሁን የተወሰደባቸው እርምጃ በተቃውሞ ፖለቲካ ባላቸው ተሳትፎ እንደሆነ የተጠቆመ ሲሆን፤ በአሁን ወቅትም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርነታቸው በተጨማሪ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ ሊቀመንበር እና የአራት ፓርቲዎች ግንባር የሆነው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) ምክትል ፕሬዘዳንት እና የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡
ዶ/ር መረራ ጉዲና ስራቸውን ለመቀጠል የሚያስችል ውል መጨረሻው የሚወሰነው በዩኒቨርስቲው አስተዳደር ሲፀድቅ እንደሆነ ገለፁ
ታዋቂውና ስመ ጥር የምስራቅ አፍሪካ የፖለቲካ ሳይንቲስትና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና በመንግስት መደበኛው በስራ በቆያ ዕድሜያቸው በመጠናቀቁ ስራቸውን በሚታደስ ውል ስራቸውን እንዲቀጥሉ የትምህርት ክፍሉ ፈቃደኝነታቸውን በጠየቀው መሰረት ውል ፈርመው በስራ ገበታቸው ላይ እንደሆኑ አስታወቁ፡፡
ዶ/ር መረራ በተለይ ለአዲስ ሚዲያ እንደገለፁት ከሆነ፤ በዩኒቨርስቲው በማስተማርና በምርምር ከ25 ዓመታት በላይ እንዳገለገሉና አሁን ዕድሜያቸው 60 ዓመት ስለሞላቸው የጡረታ ጊዜያቸው በመሆኑ፤ በእሳቸውና በዩኒቨርስቲው መካከል በሚታደስ አዲስ የኮንትራት ውል ስምምነት መሰረት ስራቸውን ለመቀጠል ከዚህ ቀደም ከሚያስተምሩበት ትምህርት ክፍል እና ከዩኒቨርስቲው ማኀበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ ጋር መፈራረማቸውን እና ስራቸውንም መቀጠላቸውን አስታውቀዋል፡፡ ይሁን እንጂ በየጊዜው በኮንትራት መልክ የሚታደሰው አዲሱ የውል ስምምነት ሊፀና የሚችለው በእሳቸውና በትምህርት ክፍሉ ስራውን ለመቀጠል የሚያስችል ፈቃደኝነት ስምምነት በዩኒቨርስቲው አስተዳደር በኩል ሲፀድቅ መሆኑንም ሳይገልፁ አላለፉም፡፡
አዲስ ሚዲያም በቅርቡ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ዶ/ር መረራ ከሚሰሩበት አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተባረሩ የሚል ዜና ተሰምቷልና እውነት ነው ወይ ሲል ላቀረበላቸው ጥያቄ “እኔ እስካሁን የደረሰኝ መረጃ የለም፣ መደበኛ ስራዬን እየሰራሁ ነው፣ ነገር ግን አንዳንድ ወሬ እኔም እሰማለሁ እንጂ እሳካሁን የደረሰኝም የእግድ ደብዳቤም ሆነ መሸኛ የለም፣ አዲስ ነገር ካለ ወደፊት አብረን የምንሰማው ነው ሚሆነው” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ለዶ/ር መረራ ስራ ጋር በተያያዘ ስለተወራው ነገር ለማጣራትና ምላሽ ለማግኘት የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አስተዳደር ክፍል ተደጋጋሚ ጥረት ብናደርግም ለጊዜው አልተሳካም፡፡
ዶ/ር መረራ ጉዲና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርነታቸው በተጨማሪ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ትግል ውስጥ ጉልህ ሚና ያላቸው ሲሆን፤ በአሁን ወቅት የኦፌኮ ሊቀመንበርና በፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ የሚመራው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) የውጭ ጉዳይ ኃላፊ መሆናቸው ይታወቃል፡፡

