Tag Archives: TPLF/EPRDF Ethiopia

አብዮት የሚናፍቀው የኢትዮጵያ መሬት

ብስራት ወልደሚካኤል
afrosonb@gmail.com

መሬት ለኢትዮጵያውያን የሕልውና ጉዳይ ነው። አገሪቱ ከመንግሥት ስርዓት ጋር ከተዋወቅችበት ከክ.ል.በ. 2545 ጀምሮ ለነገሥታቱም ይሁን ለቀሪው ዜጋ መሬት የመኖርና ያለመኖር ጉዳይ ነበር። የመሬቶቹ ባለቤትነትም ከመደበኛው ከነዋሪው ይልቅ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የገዥው መደብ አባላት እና አጋሮቻቸው እንጂ የአራሹ ሆኖ አያውቅም ነበር። ይህ መሬት ለየአካባቢው የጭፍራ አለቆችም ሆነ ለመኳንንቱ የርስበርስ መቃቃርና ግጭት ዋነኛ ምክንያት ነበር። ይህ ሁሉ ታሪክ በሀገሪቱ ዘመናዊ የመንግሥት ስርዓት መሥራች በነበሩት ዳግማዊ ዐፄ ቴዎድሮስ አማካኝነት በተወሰነ ደረጃ ለውጥ የታየበት ቢሆንም፤ ሕጋዊና ሁሉንዐቀፍ አልነበረም።

በተለይ በዘመናዊ የኢትዮጵያ ታሪክ ከመኳንንቱ በተጨማሪ በርካታ ሰዎች መሬትን ለማግኘት ከቤተክርስቲያን ይጠጉም ነበር። ይሁን እንጂ ይህ ሁሉ ሲወርድ ሲወራረድ የመጣው ኋላ ቀር የመሬት ይዞታ ፊውዳላዊ ስርዓት በዐፄ ቴዎድሮስ ስላልተወደደ፣ በዜጎች መካከል ከመሬት ጋር በተያያዘ የነበረው የገዥና ተገዥ ስሜት ያበቃ ዘንድ የመኳንንቱን እና በክሕነት ሥም በየቤተክርስቲያኑ ተጠግተው በርካታ መሬቶችን በመያዝ ገበሬውን ያንገላቱ የነበሩ ባላባቶች ሁሉ አብዛኛው መሬቶቻቸው እየተወሰደ መሬት ለሌለውና ሲያርስ ለነበረው እንዲከፋፈል፤ በቤተከርስቲያንም የሚያገለግሉ ካሕናት ቁጥር ውስን እንዲሆን እና ቀሪዎቹ ወደ ግብርና ሥራ እንዲገቡ አዘዙ። ይህ ሁሉ የነበረው በዛው በጎንደርና አቅራቢ አጎራባች አካባቢ በነበሩት ወሎ፣ ጎጃምና ትግራይ እንጂ በሌላ የአገሪቱ አካባቢ በገዥ ሥም ባሉ የጎበዝ አለቆች የተለመደው የመሬት ብዝበዛ ሲያከናወን ነበር። የተጠቀሱ ቦታዎችም ቢሆኑ የተሳካ ወጥ የመሬት ክፍፍልና አዋጅ ተፈፃሚ አልሆነም፤ ምክንያቱም የነበረው ስርዓት የተረጋጋና በሰነድ የታገዘ አልነበረም።

በመጨረሻም በዐፄ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት በ1966 ዓ.ም. በነበረው የተማሪዎች እንቅስቃሴ የዜጎች በተለይም የገበሬዎች የመሬት ባለቤትነት መብት ይረጋገጥ ዘንድ በይፋ ጥያቄ መቅረብ ጀመረ። ከዓመት በኋላም ለዓመታት የሕዝቡ ጥያቄ የነበረው የመሬት ባለቤትነት መብት ከዘውዳዊ ስርዓት ስንብት ጋር አብሮ ተበሰረ። ይህ የመሬት ባለቤትነት መብት በተለይም የ“መሬት ላራሹ” መብት ጥያቄ የካቲት 25 ቀን 1967 በዘመነ ደርግ ምላሽ አገኘ። ያ ወቅት ለኢትዮጵያ አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ ከፋች ነበር። ምክንያቱም ለረጅም ዘመናት መሬት የኢትዮጵያውን የመብትም የሕልውና ጥያቄ ነበርና። ያ አዋጅም ሆነ የተማሪዎች ጥያቄ ትኩረት የእርሻ መሬት ላይ እንጂ ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሱ በነጻነት በእንሰሳት እርባታ የሚተዳደሩትን በተመለከተ ነበር ለማለት አያስደፍርም። ምክንያቱም ከቦታ ቦታ በመንቀሳቀስ በእንስሳት እርባታ ይተዳደሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያን መሬታቸውን ማንም ከልካይና የሚቀማ ወይም የባለቤት መብት የነፈጋቸው አካል አልነበረም። በተለይ አርብቶ አደሮች የመሬት እና የውኃ ሀብትን በሚመለከት በአነስተኛ ደረጃ እርስበርስ ከሚኖራቸው አለመግባባት በስተቀር የሚንቀሳቀሱበት ቦታ ሁሉ በነጻነት የሚጠቀሙና የባለቤትነት መብቱም ቢሆን ቢበዛ በጎሳ ይሆን እንጂ እንደ እርሻው መሬት በመኳንንቱና በመንደር የጎበዝ አለቆች ባለቤትነት የሚተዳደር አልነበረም።

ዛሬ ግን ሁሉም ነገር ተቀይሯል። የካቲት 25 ቀን 1967 የታወጀው የመሬት ላራሹም ሆነ የመሬት ባለቤተነት መብት ከሕዳር 1987 ጀምሮ በዘመነ ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ ተሽሯል። የመሬት ባለቤትነት በእርሻ፣ በእንስሳ እርባታ እና በከተማ ኑሮ የሚተዳደረውን ሁሉ መብት ነው የቀማው። ምክንያቱም የግለሰብ የመሬት ባለቤትነት መብት መነጠቁን 4ኛው እንደሆነ በሚነገርለት የአገሪቱ ሕገ መንግሥት አንቀፅ በግልጽ አረጋግጧል። በዚህ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 40 ‹የንብረት መብት› በሚለው ሥር ንዑስ አንቀፅ 3 “የገጠርም ሆነ የከተማ መሬት እና የተፈጥሮ ሀብት ባለቤትነት መብት የመንግሥትና የሕዝብ ብቻ ነው። መሬት የማይሸጥ የማይለወጥ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የጋራ ንብረት ነው” ይላል።

እዚሁ አንቀፅ ላይ በንዑስ አንቀፅ 6 የመሬት ባለቤትነት የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ መንግሥት ‹ለግል ባለሀብቶች በሕግ በሚወሰን ክፍያ በመሬት የመጠቀም መብታቸውን ያስከብርላቸዋል› ይላል። በንዑስ አንቀፅ 4-5 “የኢትዮጵያ አርሶ አደሮች መሬት በነጻ የማግኘትና ከመሬታቸው ያለመነቀል መብታቸው የተከበረ ነው። የኢትዮጵያ ዘላኖች ለግጦሽም ሆነ ለእርሻ የሚጠቀሙበት መሬት በነጻ የማግኘት፣ የመጠቀምና ከመሬታቸው ያለመፈናቀል መብት አላቸው። ዝርዝር አፈፃፀሙ በሕግ ይወሰናል” ይላል።
በመጀመሪያ ደረጃ ሕገ መንግሥቱም ሆነ ሕጉን ያወጡት እና ያፀደቁት እንዲሁም አገሪቱን እየመሩ ያሉ አካላት ሊመልሱት ያልቻሉት፤ ነገር ግን ሊመልሱ የሚገባቸው በርካታ ጥያቄዎችን ማንሳት ይቻላል። ከነዚህም መካከል፦

‹መንግሥት እና ሕዝብ የሚባለው ማነው የሚለው ግልጽ አይደለም። ሌላው ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የሚል የቃላት ክምር ልዩነታቸውና አንድነታቸው (ካለ) ምንድነው? እነሱስ እነማን ናቸው? በማንስ ይወከላሉ፣ መብቶቻቸውና ግዴታቸውስ? የሚሉ ጥያቄች እስካሁን በየትኛውም ሕዝባዊ መድረክም ሆነ የመንግሥት ሕጋዊ መዝገበ ቃላት ፍቺም ሆነ ትርጉም ያልተሰጣቸው፤ ግን ደግሞ መልስ የሚያሻቸው ናቸው። ምክንያቱም በድፍኑ የቃላት ድርደራ ከመሆን በዘለለ ለሕዝቡ በሚገባ መልኩ በግልጽ የተቀመጠ ትርጉም የለውም።
ሌላው መሬት የማይሸጥ የማይለወጥ… የጋራ ንብረት ነው ይልና ወረድ ብሎ ደግሞ መንግሥት ለግል ባለሀብቶች በሕግ በሚወሰን ክፍያ በመሬት የመጠቀም መብታቸውን ያስከብርላቸዋል ይላል። ይህ የሚያሳየው የማይሸጥ የማይለወጥ የተባለው መሬት መንግሥት መሬት ቸርቻሪ እንዲሆን መብት ሰጥቶታል። አሁን ባለው በሀገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ መንግሥት የሚለውም ትርጉም የሚያስፈልገው ዐብይ ጉዳይ ነው። በአንቀፅ 40 (7-8) ላይ ደግሞ ዜጎች የግል ንብረት ባለቤትነት መብት ያላቸው በመሬቱ ላይ በሚገነቡትና በቋሚነት ለሚያሻሽሉት ቁስ እንጂ መሬቱ ላይ የባለቤትነት መብት እንደሌላቸው ያመለክታል። ይህም ከቦታው በግድ የሚፈናቀል ሰው ካሳ እንኳ ቢያስፈልገው፤ በመሬቱ ሳይሆን መሬቱ ላይ ባለው የተጠቃሚነት መብት ባፈራው ንብረት ብቻ መሆኑን ያመለክታል።

የመሬት ባለቤትነት መብት ያለመኖር ያስከተለው ችግር

በርግጥ ሕገ መንግሥቱ ሥራ ላይ ባያውላቸውም በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ዓለም አቀፍ የዴሞክራሲና ሰብኣዊ መብት ድንጋጌዎችን ያካተተ ቢሆን ግልጽ ያልሆኑ፣ ጥያቄ የሚያስነሱ በርካታ ግግር ጉዳዮችንም ይዟል። ይበልጥ ግን የገዥውን ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. በተለይም የሕ.ወ.ሓ.ት.ን የፖለቲካ ፕሮግራምና ፍላጎት በስፋት ይገኝበታል። ለዚህም ይመስላል፤ ሕገ መንግሥቱ ከተወሰኑ አንቀፆች (ላለፉት 21 ዓመታት ሥራ ላይ ያልዋሉ) ዓለምዐቀፍ ድንጋጌዎች በስተቀር የሕ.ወ.ሓ.ት./ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. የፖለቲካ ፕሮግራምና ፍላጎት የሰፈረበት ሰነድ ነው የሚል ጥያቄ የሚነሳው። በተደጋጋሚ ከሚነሱ ጥቄዎችና ቅሬታዎች መካከል የመሬት ጉዳይ ዋነኛው ነው።

በተለይ ሕ.ወ.ሓ.ት. መሬትን በተመለከተ የሚከተለው የፖለቲካ ፕሮግራም (ፖሊሲ) እና ሕገ መንግሥቱ ላይ የሰፈረው አንድ ነው። ከሕ.ወ.ሓ.ት. ውጭ ያሉ ሌሎቹ የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. አባላት (ብ.አ.ዴ.ን.፣ ኦ.ሕ.ዴ.ድ. እና ደ.ኢ.ሕ.ዴ.ን.) የተሰጣቸውን ከማስፈፀም በቀር የፖለቲካ ፕሮግራማቸውን ተመሳሳይ ከማድረግ ውጭ ሥልጣኑም ሆነ ሞራሉ ያላቸው አይመስልም። አጋር ድርጅቶች የተባሉት የጋምቤላ፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ ሶማሌ፣ አፋር እና ሐረሪ ክልል ፓርቲዎች ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ.ን. ከማጀብና የሚለውን ከመቀበል ውጭ በየትኛውም አገራዊ ጉዳይ ላይ የመወሰን፣ የመጠየቅም ሆነ ላሉበት ማኅበረሰብ መብትና ጥቅም የመቆም ሕልውናም ሆነ አቅም የላቸውም። ምክንያቱም አጋር እንጂ የገዥው ኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. አባል ስላልሆኑ የተሰጣቸውን ሥራ ከማከናወን ባለፈ በፖሊሲም ሆነ በፖለቲካ ፕሮግራማቸው የተለየና የራሳቸውን ነገር ይዘው መቅረብ አይችሉም። በዚህም ምክንያት ከመሬት ባለቤትነት መብት ጋር በተያያዘ ዋነኛ ገፈት ቀማሽ መሆናቸው አልቀረም።

በገጠሪቱ ኢትዮጵያ በፌደራሉ መንግሥት ፍላጎትና ሥልጣን ሰፋፊ ለም የእርሻ መሬቶች ከገበሬዎቹ በግድ ተነጥቀው ለባለሀብቶች እንዲተላለፉ ተደርገዋል። ከባለሀብቱ በተጨማሪ ስርዓቱ ለሚከተለው መንግሥታዊ ባለሀብትነት (state capitalism) ትግበራ ሰፋፊ የእርሻ መሬቶችን ከገበሬዎች ነጥቋል። ይሁን እንጂ ከገበሬዎች ያለምንም አካባቢያዊና ማኅበራዊ ተፅዕኖ ግምገማ (Environmental and social impact assessment) ሰፋፊ ለም መሬታቸው ወደ መንግሥታዊና ግል ባለሀብቶች በመተላለፉ አንዳቸውም ፕሮጀክቶች ውጤታማ አልሆኑም። ይልቁንም ያለበቂ ምክክር፣ ካሣና ምትክ ቦታ የተፈናቀሉ በርካታ ገበሬዎች ዛሬም ድረስ ሕይወታቸውን በጉስቁልና እንዲመሩ አስገድዷቸዋል። ከገበሬዎች ማኅበራዊ ችግር በተጨማሪ በአካባቢያዊ የአየር ጠባይ እና የአየር ንብረት ላይ የሚኖረው ጉዳት አገሪቱ በቀላሉ የምታካክሰው አይደለም። ይህ ሁሉ በሕገ መንግሥቱ የሰፈረው የመሬት ባለቤትነት መብትና ስርዓቱ የሚከተለው የመሬት ፖሊስ ምክንያት የተፈጠረ ችግር ነው።

Ethiopian land grabbing sample

በሰንጠረዡ ላይ እንደሚታየው በደቡብ ክልል ደቡብ ኦሞ እና ቤንች ማጂ ዞን አካባቢ ለስኳር ፕሮጀክት መንግሥት የወሰደውን 335,000 ሔክታር መሬት፣ የወልቃይት፣ የከሰም፣ የተንዳሆ ሰፋፊ እርሻዎችን፣ 2,000 ሔክታር እና ከዛ በታች ስርዓቱ የኔ ለሚላቸው ሰዎች የሰጠውን ሳያካትት ነው። መሬቱ ለግል ባለሀብቶች የተላለፈው ከ30-50 ዓመት በሚቆይ ኪራይ ነው። በዚህም ምክንያት በአንድ ሔክታር በዓመት ከ14-135 ብር የሊዝ ኪራይ የተላለፉና መንግሥት በነጻ የወሰዳቸው መሬቶች ላይ የኖሩ ዜጎች ያለ በቂ ምክክር፣ ካሣና ምትክ ቦታ ተፈናቅለዋል። በተለይ በጋምቤላ ክልል ብቻ 225 ሺሕ ዜጎች ሲፈናቀሉ፣ ከ8-10 ሺሕ የሚሆኑ ተፈናቃዮች ደግሞ አገር ጥለው ሲሰደዱ፤ ከ424 ያላነሱ ተገድለዋል። በተመሳሳይ በደቡብ ክልል በሚገኘው ደቡብ ኦሞ ዞን 200 ሺሕ ያህል ዜጎች ተፈናቅለዋል።

መንግሥት ለስኳር ልማት፣ ለማዳበሪያ ፋብሪካና ተያያዥ ግንባታዎች ልማት በሚል የወሰዳቸው ሰፋፊ ለም የእርሻ መሬቶችና ለግል ባለሀብቶች ከተላለፉት ውስጥ ለአገሪቱም ሆነ ለዜጎች ያመጡት ጥቅም የለም። ከጥቅማቸው ይልቅ በተለይ በምዕራብና ደቡብ ኢትዮጵያ ለዘመናት የቆዩ ደኖችና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብቶች ከጥቅም ውጭ ሆነዋል። ይህም ማኅበራዊ ሕይወት ላይ ካስከተለው ችግር በተጨማሪ የአገሪቱ ኢኮኖሚ እና አካባቢ ጥበቃ ላይ ያስከተለው ጉዳት ቀላል የሚባል አይደለም። እዚህ ላይ በቅርቡ የገባበት ያልታወቀውን 77 ቢሊዮን ብር የስኳር ልማት ፕሮጀክት ገንዘብ እና የኢሉ አባቦራ ያዩ ማዳበሪያ ፋብሪካ የደን ጭፍጨፋን በምሳሌነት ማንሳት ይቻላል።

ሌላው ችግር ባለሀብቶች ውጤታማ መሆን ባልቻሉበት መሬት ላይ የተጠቀሟቸው ኬሚካሎች በተፈጥሮ ሀብት ላይ በተለይም በአፈሩ፣ በውሃውና በአካባቢው አየር ላይ የሚኖረው አሉታዊ ተፅዕኖ እንደቀላል የሚታይ አይደለም። ገበሬው መሬቱን በሚመለከት ለሚያቀርባቸው ጥያቄዎችም ሆኑ ቅሬታዎች ከመንግሥት ወገን የሚሰጠው መልስ “መሬት የመንግሥት ነው፤ ወደህ ሳይሆን ተገደህ ትነሳለህ” የሚል ሲሆን፤ ያለበቂ ካሳና ምትክ ቦታ ከቀዬያቸው መፈናቀላቸውን የተቃወሙ ደግሞ የእስርና ግድያ ሰለባ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል። ይሄ በገጠሪቱ ኢትዮጵያ የመሬት ሕጉና ፖሊሲው ካስከተሏቸው ችግሮች መካከል ጥቂቶቹ ናቸው።

በከተማው ያለው የመሬት ችግር ከገጠሩ እጅጉን የባሰ ሲሆን፣ ሕዝቡ በኢኮኖሚው፣ በማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የስርዓቱ ጥገኛ እንዲሆን ካስገደዱት ነገሮች መካከል የመሬት ሕጉና ፖሊሲው ዋነኞቹ ናቸው።

‹መሬት አይሸጥም አይለወጥም›፣ ‹የመሬት ፖሊሲው የሚቀየረው በኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. መቃብር ላይ ነው›… የሚሉ የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. መፈክሮች ይበልጥ የሚሰሙት በከተማ ነው። ምንም እንኳ መሬት አይሸጥም አይለወጥም ቢባልም የአገሪቱን የከተማ መሬቶች እንደጉሊት ንግድ በአደባባይ የሚቸረችረው ደግሞ ራሱ መንግሥት መሆኑን ላስተዋለ፣ መሬትን በተመለከተ በሕገ መንግሥቱ ላይ የተቀመጠውና የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. ፖሊሲ እርስበርስ ሲጋጭ ይታየዋል። ከዛም አልፎ የሕጉና የፖሊሲው ዓላማ እንዲሁ በቀላሉ እንደተራ ነገር በትዝብት የሚያልፍ ጉዳይ አይደለም። ምክንያቱም መሬት ለኢትዮጵያውን መነሻ ካፒታል ብቻ ሳይሆን፣ የሕልውና ጉዳይም ነው። ነገር ግን አሁን የመሬት ጉዳይ ሌላ አብዮት የሚናፍቅ ጉዳይ የሆነ ይመስላል። አለበለዚያ በተለይ ሰፋፊ ለም የእርሻ መሬት ያለባቸው አካባቢዎች፣ በከተማ የሚኖሩ ዝቅተኛና መካከለኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች እንደሰው የመቆጠራቸውም ጉዳይ ጥያቄ የሚገባ ይመስላል። ምክንያቱም በከተሞች ያለው የመሬት የሊዝ ጨረታ ዋጋ እንኳን በወር ደመወዝ በተቋማት ተቀጥሮ የሚተዳደር ቀርቶ በቂ ገንዘብ አለው የሚባለውን ነጋዴውንም ቢሆን እጅግ የሚፈታተን ጉዳይ ሆኗል። ይህ ታቅዶ፣ ዓላማና ግብ ኖሮት የሚፈፀም ያልተጻፈ ፖሊሲ አካል እንጂ በድንገት እየተከናወነ ያለ የሚመስለው ካለ ተሳስቷል።

ከሊዝ ጨረታ ውጭ አዲሱ ትውልድም ሆነ ከዚህ በፊት የራሳቸው መኖሪያ ቤት የሌላቸው ዜጎች የከተማ መኖሪያ ቤት መሥሪያ ቦታ የማግኘት ዕድላቸው ሙሉ ለሙሉ ከስሟል። በዚህ ምትክ መንግሥት ለፖለቲካ ፍጆታ የሚጠቀምበትን ኮንዶሚኒየም ቤት ደስ ባለው ሰዐትና ራሱ በተመነው ዋጋ ለዓመታት በተስፋ በመጠበቅ የከተሜው ነዋሪ ግዴታ መሆን ከጀመረ እነሆ 10 ዓመት አልፎታል።
በተለይ ከሊዝ አዋጅ በተያያዘ የከተማ ቦታን በሊዝ ስለመያዝ የወጣ አዋጅ 721/2004 መሠረት አይደለም መሬት በሊዝ ጨረታ መግዛት በውርስ ያገኘው የቤተሰብ ንብረትም ሆነ በቀድሞ ስርዓት ሠርቶ የቤት ባለቤት የነበረ ሰው መንግሥት በፈለገው ጊዜ እንደሚያስነሳው፣ ካሣውን የሚተምነው ለተሠራው ቤት ጣሪያና ግድግዳ እንጂ ለመሬቱ እንዳልሆነ በግልጽ አስቀምጦታል።

በተለይ ከከተማ ቦታ ይዞታ ጋር በተያያዘ ቤት ያለአግባብ የፈረሰበት ወይም መብቱን የተነጠቀ ማንኛውም ግለሰብ በከተማ አስተዳደሮቹ ውሳኔ ቅር ቢሰኝ እንኳ ወደፍርድ ቤት ሄዶ አቤቱታ ማቅረብ አይችልም። ምክንያቱም የከተማን ቦታ በሊዝ ስለመያዝ የወጣው አዋጅ 721/2004 መሠረት፤ ከተማ አስተዳደሩ 5 አባላት ያሉት ራሱ ፖለቲከኛው የመረጠውና የሾመው የጉባዔ አባላት አቋቁሞ እንዲፈርድ ሥልጣን ሰጥቶታል። ለዚህም በአንቀፅ 30 (8-9) “ጉባዔው ሥራውን በሚያከናውንበት ጊዜ በመደበኛው የፍትሐብሔር ሥነ ስርዓት ሕግ አይመራም። ሆኖም በክልሉ ወይም በከተማ አስተዳደሩ በሚወሰን የተቀላጠፈ ሥነ ስርዓት ይመራል። የጉባዔው አባላት የሥራ ዘመን በክልሉ ወይም በከተማ አስተዳደሩ ይወሰናል” በሚል ያስቀመጠውን መረዳት ይቻላል።

በዚህ የሊዝ አዋጅ መሠረት፤ አንድ የከተማ አስተዳደር አካል የሆነና በፖለቲካ የተሾመ ሰው ከመሬት ይዞታ መፈናቀልና መብት ጋር በተያያዘ የትኛውንም በደል ወይም ጥፋት ቢፈፅም፤ ጉዳዩን የሚያየው ጥፋት የፈፀመው የአስተዳደር አካል የሾመው ሌላ የባለሥልጣናት ስብስብ “ጉባዔ” መሆኑ ችግሩን የበለጠ ውስብስብ ያደርገዋል። ይህም መሬት የስርዓቱ የፖለቲካ መቆመሪያ መሣሪያ መሆኑን በግልጽ ያሳያል። ምናልባት ቤት ንብረት ኖሯቸው መንግሥት በፈለገው ሰዐት ለፈለገው ግለሰብ በስጦታም ይሁን በሊዝ ጨረታ መስጠት ቢፈልግ፤ ከይዞታዬ አልነሳም፣ የካሣ ክፍያውም ሆነ የተሰጠኝ ምትክ ቦታ (ዕድለኛ ሆኖ ከተሰጠው) በቂ አይደለም ቢል፣ አስተዳደሩ የፈለገውን ቤት በፖሊስ ኃይል እንዲፈርስ ማድረግ እንዲችል ሥልጣን ሰጥቶታል።

የመሬት ባለቤትነት መብት ችግር መፍትሔ

የመሬትና የመኖሪያ ቤት ችግርን ለመፍታት የተለያዩ መፍትሔዎችን ማንሳት ይቻላል።
ሕገመንግሥቱ አንቀፅ 40 ላይ የዜጎችን የመሬት ንብረት ባለቤትነት መብትን የሚነጥቁ ድንጋጌዎች መሻሻል አለባቸው። የሚሻሻሉት ድንጋጌዎችም በማያሻማ መልኩ በግልጽ መቀመጥ አለባቸው። በተለይም መንግሥት፣ ሕዝብ፣ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የሚሉ የቃላት ድርድሮች ልዩነታቸውና አንድነታቸው (ካላቸው) በግልጽ መቀመጥና መለየት አላስፈላጊ ድግግሞሽ ወይም የትርጉም አቻ ያላቸው ቃላት መወገድ አለባቸው። በመቀጠልም መሬት በነዋሪዎች ይዞታ ሥር ያለ የከተማም ሆነ የገጠር መሬት የንብረት ባለቤትነቱ ለራሱ ለግለሰቡ መሰጠት አለበት። መንግሥትም ሆነ የግል ባለሀብቶች የነዋሪዎቹን መሬት ለተለያየ ፕሮጀክቶች ቢፈልጉ በወቅቱ የመሬትና ተያያዥ የንብረት ዋጋ በቀጥታ ከግለሰቡ ጋር ተደራድረው መግዛት አለባቸው። በዚህም ነዋሪው መሬቱን እንደካፒታል በመጠቀም ይንከባከባል፣ ያለማል፣ ቢሸጥ እንኳ ምትክ ቦታ ገዝቶ ቀሪውን ገንዘብ እንደችሎታው የፈለገውን መጠነኛም ሆነ ዝቅተኛ ኢንቨስትመንት ማካሄድ ይችላል። ለዚህ ደግሞ በንብረቱ ላይ ራሱ እንዲወስን ሙሉ ሥልጣኑ ሊኖረው ይገባል።

በሕዝብ የተያዙ የገጠርም ሆነ የከተማ መሬቶች የንብረት ባለቤትነቱ የአካባቢው ነዋሪ ሕዝብ መሆን አለበት። የአካባቢው ነዋሪ ሕዝብ ሲፈልግ ለልጆቹ መዝናኛ አሊያም ለግጦሽም ሆነ ለሚፈልገው የልማት ፕሮጀክት ማዋል ይችላል። ምናልባት የአካባቢውን ክፍት መሬት መንግሥት ወይም የግል ባለሀብት የሚፈልገው ከሆነ በወቅቱ የመሬት ገበያ ዋጋ ከአካባቢው ነዋሪ ማኅበረሰብ ጋር ተደርድሮ መግዛት ይችላል። መሬቱን የሸጠው የአካባቢው ማኅበረሰብም ገንዘቡን ወደሌላ የገቢ ምንጭ እንዲቀይሩ መንግሥት በነጻ የማማከርና የሙያ ድጋፍ ማድረግ ይችላል፤ ካልሆነ ራሱ ማኅበረሰብ በባለሙያ አስጠንቶ የመረጠውን ሥራ ማከናወን እንዲችል መደረግ አለበት።

በግለሰብም ሆነ በማኅበረሰብ ያልተያዙ መሬቶች የንብረት ባለቤትነት መብቱ ለመንግሥት ቢሆን፤ መንግሥት ለግል ባለሀብቶችም ሆነ ለተለያዩ ማኅበራዊ ተቋማት ግንባታ ወይም ለመንግሥት የልማት ፕሮጀክቶች ማዋል ከፈለገ ተጠያቂነት ባለበት ሁኔታ ለሕዝብ ይፋ ተደርጎ ጥቅም ላይ መዋል አለበት። ነገር ግን ጥቅም ላይ የሚውሉ መሬቶች መጪውን ትውልድ ደኅንነትና የተሻለ ሕይወት ከግምት ያስገባ ሆኖ፣ ከፖለቲካ ተፅዕኖ ነጻ በሆነ መልኩ ባለሙያዎች የአካባቢ ጥበቃና ማኅበራዊ ተፅዕኖ ግምገማ ጥናትና ምክር ቢያደርጉ፣ ሕዝቡ በሥራው ላይ በዕውቀት፣ በገንዘብም ሆነ በጉልበት ተሳታፊ እንዲሆን፤ ካልሆነ የሞራል ድጋፍ እንዲሰጥ መመቻቸት አለበት።

የከተማ ቦታን በሊዝ ስለመያዝ የወጣው አዋጅ መሻር ወይም መሻሻል አለበት። ምክንያቱም አዋጁ የግለሰብ የመሬት ንብረት ባለቤትነትን መብት ከመንጠቁ በተጨማሪ መንግሥት ከመደበኛው ሥራው ውጭ የመሬት ቸርቻሪ፣ ካድሬዎችን የሥልጣን መባለጊያ እና የሙስና ምንጭ፣ ለስርዓቱ የመጨቆኛ መሣሪያ፣ ሕዝቡን ደግሞ የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ጥገኛ እንዲሆን አስችሎታልና።

ሰፋፊ ለም የእርሻ መሬቶችን በርካሽ ዋጋ ለውጭ ባለሀብት መስጠት የሚያስከትለውን የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ (የአገር ውስጥ የባንክ ብድር ወስደው ስለማይከፍሉ)፣ የማኅበራዊ እና የአካባቢ ጥበቃ ችግር ለመቅረፍ የአገሪቱ የሰው ሀብት ልማት ላይ ትኩረት መደረግ አለበት። በተለይ በአገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች የሚማሩ የግብርና ሳይንስና ተያያዥ ባለሙያዎች በራሳቸው ፈቃድና ተነሳሽነት ተደራጅተው ዘመናዊ የግብርና ሥራን እንዲጀምሩ የባንክ ብድርን ጨምሮ የተለያዩ ድጋፎች ቢደረግላቸው። ምክንያቱም የአገር ውስጥ ባለሙያዎች በግብርና ምርትና ንግድ ዘርፍ ቢሰማሩ፣ የአገሪቱን የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ በተጨማሪ የሥራ ዕድል በመፍጠርም ሆነ የውጭ ምንዛሪ በማስገኘት እንዲሁም ፕሮጀክቱን በሚያከናውኗቸው አካባቢ ያሉ ማኅበረሰብን ሕይወት ለማሻሻል እጅግ የተሻሉ ናቸው።

 

የከተማ ቦታን በሚመለከት መንግሥት ከመሬት ችርቻሮ ወጥቶ የመንግሥትን ሥራ ብቻ እንዲሠራ ቢደረግ፤ የከተማ ነዋሪዎች ራሳቸው አቅማቸው በፈቀደ መጠን በሚፈልጉት የሙያ ማኅበርም ሆነ መሥሪያ ቤት ወይም ተቋም ዘመናዊ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ሠርተው እንዲኖሩ መደረግ አለበት። መሬትም ከሊዝ ነጻ ቢመቻችና የመኖሪያ ቤት ግንባታን ሊያግዝ የሚችል በረጅም ጊዜ የሚከፈል የባንክ ስርዓትና ብድር ቢመቻች፣ መንግሥት ግንባታዎቹ የከተማውን ደረጃ በጠበቀ መልኩ አካል ጉዳተኞችን እና የአደጋ ጊዜ መከላከልን ታሳቢ ያደረጉ ግንባታዎች እንዲከናወኑ ወጥነት ያለው መመሪያ ቢያዘጋጅና መሠረተ ልማቶችን በማመቻቸት ብቻ ቢሳተፍ አሁን ያለውን እና ከዚህ በኋላ የሚኖረውን የቤት ችግር ለመቅረፍ ይረዳል። ከዛ በተጨማሪ በግላቸው ቤት መሥራት ለሚፈልጉና ለሚችሉ መንግሥት የግንባታ ደረጃዎችን በማውጣትና በተመጣጣኝ ዋጋ ነጻ መሬት ቢያቀርብ፣ መንግሥት ነጻ መሬት ማቅረብ ካልቻለ፣ ግለሰቦቹ ከሌሎች ነባር ነዋሪ ከሆኑ የመሬት ባለቤቶች ራሳቸው በቀጥታ ተደራድረው ገዝተው እንዲገነቡና እንዲኖሩ ቢደረግ ሁለቱም አካላት ተጠቃሚ ይሆናሉ።

መንግሥትም ከዜጎች በሚሰበስበው ግብርና በዜጎች ሥም ከሚያገኘው ብድርና ዕርዳታ የመሠረተ ልማትና ማኅበራዊ ተቋማትን በመገንባት ብቻ እንዲሳተፍ መደረግ አለበት። በግላቸውም ሆነ በማኅበር ተደራጅተው መሥራት ለማይችሉ በመንግሥት ድጎማ እንደየአቅማቸው እንዲደራጁና እንዲመዘገቡ በማድረግ ለግል የኮንስትራክሽን ኩባንያዎች በጨረታ እንዲሠሩ ቢደረግ፣ የሚሠሩ ግንባታዎች ደረጃ ላይም ጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል ቢደረግ፣ የግል የመኖሪያ ቤት ግንባታ ተቋራጭ ድርጅቶች (ሪል ኢስቴቶችም) መሬት በመጠኛ ዋጋ እንዲያገኙ መደረግ አለበት። ድርጅቶቹም በወቅቱ ተመጣጣኝ የገበያ ዋጋ ለቤት ፈላጊዎች እንዲያስተላለፉ ቢደረግ፤ ለዚህም የቤት ግንባታን ብቻ ለማገዝና ለመደጎም የሚችል የባንክ ተቋምና ስርዓት ቢመሠረት ያለውን የቤት ችግር በቶሎ መቅረፍ ይቻላል። መንግሥትም የመኖሪያ ቤት ችግርን የፖለቲካ ፍጆት ከማድረግ ያግደዋል፤ የመንግሥት ግዴታ፣ ኃላፊነትና ተጠያቂነት በግልፅ እንዲሰፍን ያግዛል የሚል እምነት አለኝ።

በአዲስ አበባ አራዳ ፒያሳን ጨምሮ ከ10 ዓመት በላይ ታጥረው ምንም ዓይነት ግንባታ ያልተከናወነባቸው በርካታ ቦታዎች እያሉ የአቅማቸውን ያህል በከተማ ጥጋጥግ ጎጆ ቀይሰው የሚኖሩ ዜጎችን ክረምት ጠብቆ ለጎዳና ሕይወት መዳረግ በየትኛውም መመዘኛ ተገቢ ሊሆን አይችልም። ቢቻል በክረምት መኖሪያ ቤት አጥተው ለጎዳና ሕይወት የሚዳረጉትን መታደግ ሲገባ፤ በአዲስ አበባ ቦሌ ቡልቡላ እና ንፋስ ስልክ ላፍቶ በሁለት ወረዳዎች ብቻ 20 እና 30 ሺሕ ነዋሪዎችን ማፈናቀል ከሰብኣዊ መብትም ሆነ ከሞራል አንፃር የሚያስኬድ አይደለም። መንግሥት እየወሰደ ያለው ኃላፊነት የጎደለውን ተግባር ቆም ብሎ ማሰብ አለበት። ቤቶቻቸው ሕገ-ወጥ እንኳ ቢሆን ያለምትክ ቦታና ካሣ እንዲሁም ክረምት ጠብቆ ማፈናቀል የተሳሳተው የመሬት ፖሊሲ ውጤት መሆኑ መታወቅ አለበት።

ስርዓቱን ብቻ አምነው የሕዝቡን የመሬት ባለቤት መብትና ጥቅም ወደጎን በመተው የመሬት ቅርምቱ ላይ የሚሳተፉ የግል ባለሀብቶች ቆም ብለው ማሰብ አለባቸው። የስርዓት ለውጥ ቢኖርም ሆነ ያለው ስርዓት ቢቀጥል የሕዝቡ መብትና ጥቅም እስካልተጠበቀ ድረስ መዋዕለ ነዋያቸውን አፍሰሰው ለሚሠሩት ኢንቨስትመንት ዋስትና እንደሌላቸው መረዳት አለባቸው። ምክንያቱም ብዙ የተገፋ ሕዝብ በአንድ ሌሊት ተነስቶ የራሱን እርምጃ የማይወስድበት ምክንያት የለም። ስለዚህ ቢቻል በቀጥታ ከነዋሪው ካልሆነ የሕዝቡ መብትና ጥቅም መረጋገጡን ሳያረጋግጡ ሕዝብ በተፈናቀለበት የገጠርም ሆነ የከተማ መሬት ላይ ገንዘባቸውን ከመበተን ይልቅ ሕዝቡን ባሳተፈ፣ አሊያም የጋራ ተጠቃሚነትን መሠረት ያደረገ ፕሮጀክት ስለመተግበራቸው ቀድመው ቢገነዘቡ ይመከራል።

መንግሥት አሁን ከሚከተለው የመንገድ የተለየ መሻሻልም ሆነ የሕዝብን መብትና ጥቅም ታሳቢ ያደረገ ለውጥ ማድረግ ካቃተው ወይንም የመንግሥትን ሚና እና ግዴታ መለየት ከተሳነው ሥልጣኑን ለሕዝብ ማስረከብ ብቸኛው አማራጭ መሆን አለበት። አለበለዚያ አሁን በሚከተለው መንገድ የሚቀጥል ከሆነ ስርዓት በሕዝባዊ ኃይል መፍረስ ብቻ ሳይሆን አገሪቱን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ በመምራት ከፍተኛ ዋጋ ሊያስከፍል እንደሚችል መታሰብ አለበት።

የመሬት ሕጉም ሆነ ፖሊሲው መሻሻል አለበት፤ ካልሆነ ግን መንግሥት ገበሬዎችንም ሆነ የከተማ ነዋሪዎችን ማፈናቀሉ ይቀጥላል። ይህ ደግሞ በአገሪቱ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ላይ አለመረጋጋትን ይፈጥራል። ለዚህ ማሳያ ደግሞ በኦሮሚያ ያለውን ሕዝባዊ ተቃውሞ፣ በአዲስ አበባ እንደክፉ ጠላት ክረምት ጠብቆ እየፈረሱ ያሉ መኖሪያ ቤቶችን ተከትሎ የሚፈጠረው ቅራኔ ምናልባት ቀኑን እንደነብይ መተንበይ ቢያስቸግርም፤ ወደሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች ተዛምቶ አዲስ የመሬት ባለቤትነት አብዮት ሊፈጠር ይችላል። ያኔ እንደዛሬው እየሳቁና እያስገደዱ፣ እንዳፈረሱና እንዳፈናቀሉ መቀጠል ላይቀል ይችላል። ምክንያቱም የመሬት ጉዳይ ለስርዓቱ የሥልጣኑ መሠረት እንደሆነ ቢታወቅም፣ ለሕዝብ ደግሞ የመኖርና ያለመኖር የኅልውና ጉዳይ ነው።

በኢትዮጵያ በሁለት ቀናት ብቻ በተቀሰቀሰው የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ 132 ዜጎች ተገደሉ

(አዲስ ሚዲያ) በኢትዮጵያ ትናንት ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. እና ዛሬ ነሐሴ 01 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ እና አማራ ክልል በተቀሰቀሰው የፀረ ጭቆና ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት የኃይል ርምጃ ህፃናት እና ሴቶችን ጨምሮ በርካታ ሰላማዊ ንፁሃን ዜጎች ተገደሉ፡፡ በተለይ እንደ መብት አራማጆች እና የአካባቢው ምንጮች መረጃ ከሆነ በሁለቱ ቀን የኦሮሚያ እና አማራ ክልል የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ 132 ንፁሃን ዜጎች መገደላቸው ተጠቁሟል፡፡

በተለይ እንደ መብት አራማጆች መረጃ ከሆነ፤መነሻውን የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን በማድረግ ወደ ጠቃላይ ሀገራዊ ይዘት የስርዓት ለውጥ ጥያቄ ያደገው የኦሮሞ ተቃውሞ ትናንት ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. አዲስ አበባን ጨምሮ በኦሮሚያ ክልል ባሉ ከተሞች አጠቃላይ በተጠራው የረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ህፃናት እና ሴቶችን ጨምሮ 67 ያህል ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ወታደራዊ ርምጃ ሲገደሉ፤ ከ500 ያላነሱ በፅኑ ቆስለው በክምና ላይ መሆናቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ትናንት በነበረው የኦሮሚያ ክልል እና የአዲስ አበባ ተቃውሞ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በርካታ ዜጎች መታሰራቸውም ተጠቁሟል፡፡

Oromo Protest, Adama

በትናንትናው ተቃውሞ በኦሮሚያ ክልል ከፍተኛ ግድያ ከተፈፀመባቸው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች መካከል በምዕራብ አርሲ አሳሳ፣ በምስራቅ ሐረርጌ አወዳይ እና ሐረማያ እንዲሁም በምስራቅ ወለቃ ነቀምት ከተሞች ዋነኛ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በነበረው የኦሮሚያ ተቃውሞም የህወሓት መንግሥት በቃን፣ የኦሮሞን ህዝብ መግደል ይቁም፣ የታሰሩ የፖለቲካ እስረኞች በአስቸኳይ ይፈቱ፣አሸባሪ አይደለንም፣ አማራ የእኛ ነው፣ የጎንደር አማራዎችን መግደል ይቁም፣ የወልቃይት ጥያቄ ሕገ መንግሥታዊ ነው፣ወያኔ ሌባ፣…የሚሉ መፈክሮች ተሰምተዋል፡፡ በነበሩ የተቃውሞ ሰልፍ ከተሞች እና አካባቢዎች በርካታ ሰዎች መሳተፋቸውን ከኦሮሚያ ሚዲያ ኔትወርክ ዘገባ፣ ማኀበራዊ ሚዲያ እና ከተለያዩ አካባቢዎች ያገኘናቸው የዓይን እማኞች መረጃ ማወቅ ተችሏል፡፡

በተመሳሳይም በአማራ ክልል በተለይም በደቡብ ጎንደር ዞን ደብረ ታቦር ሐምሌ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. በተጠራው የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ሰልፍ ላይ መንግሥት በወሰደው ወታደራዊ የኃይል ርምጃ ከ6 ያላነሱ ሰዎች ወዲያው ሲገደሉ በርካቶች በመቁሰላቸው፣ በሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ ወረዳዎች እና በደቡብ ጎንደር ጋይንት ጨምሮ የተለያዩ ወረዳቸዎች ነዋሪዎች በመቆጣት በድንገት የተቃውሞ ሰለፍ ማድረጋቸው ታውቋል፡፡ መነሻውን የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄ በማድረግ ወደ አጠቃላይ የስርዓት ለውጥ ጥያቄ ያደገው የአማራ ተቃውሞን ተከትሎ መንግሥት ከደብረ ታቦር በተጨማሪ የተቃውሞ ሰልፎች በነበሩበት ስፍራዎች ሁሉ ወታደራዊ የኃይል ርምጃ በመወሰዱ የህዝቡ ቁጣ ተባብሱ የህወሓት ደጋፊና ተባባሪ ናቸው የተባሉ የንግድ ተቋማት፣ የመንግሥት ተሸከርካሪዎች እና ተቋማት ላይ እንዲሁም በጎንደር አዘዞ የሚገኘውን የመከላከያ ወታደራዊ ካምፕ ከጥቅም ውጭ ማድረጋቸው ተሰምቷል፡፡

በሰሜን ጎንደር ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በሰሜን ጎንደር ሳንጃ፣ ቆላ ድባ፣ ዳባት፣ አርማጭሆ፣…በመሳሰሉ ቦታዎች በመንግሥት ወታደሮች እና በህዝቡ መካከል ውጊያ መኖሩን እና የመንግሥት ወታደሮችን እና ከህዝቡም በርካታ ሰዎች መሞታቸውን እና መቁሰላቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ዛሬ ነሐሴ 01 ቀን 2008 ዓ.ም. በባህርዳር ከተማ በነበረው የአማራ የፀረ ጭቆና ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ከ30 ያላነሱ ሰዎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸው ታውቋል፡፡ በአማራ ክልል ዛሬ የተገደሉ 30 ያህል እና ትናንት ደብረ ታቦር ከተገደሉ 6ቱ በተጨማሪ ሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች በተደረገ የትናንት እና የዛሬ ተቃውሞ 29 ሰዎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸው ተጠቁሟል፡፡ ህዝቡም በባህርዳር የተለያዩ ህዝባዊ ተቋማት ሰንደቅ ላይ የብአዴን እና በኢህአዴግ የፀደቀውን የፌደራሉን ሰንደቅ ዓላማ በማውረድ የቀድሞውን አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ሰንደቅ ዓላማ ሲሰቅሉ እና ሲያውለበልቡ ተስተውሏል፡፡ በአጠቃላይ በሁለቱ ቀን የአማራ ክልል ተቃውሞ 65 ያህል ዜች ሲገደሉ፤ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በርካታ ዜጎችም መቁሰላቸውን እና የህክምና ርዳታ እየተደረገላቸው መሆኑን የዓይን እማኞች አረጋግጠዋል፡፡

AmharaProtest, Bahirdar

በተለይ በደብረ ታቦር እና ባህርዳር በተደረገው የአማራ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ፤ ወልቃይት የአማራ እንጂ የትግሬ አይደለም፣ ወልቃይት አማራ ነው፣ ለሱዳን የተሸጠው መሬታችን ይመለስ፣ የታሰሩት ይፈቱ፣ በኦሮሞ ወገኖቻችን ላይ የሚደረገው ግድያ ይቁም፣ በቀለ ገርባ መሪያችን እንጂ አሸባሪ አይደለም፣ ኢትዮጵያዊነት አሸባሪነት አይደለም፣በኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ አንደራደርም፣ወያኔ ሌባ፣አንዳርጋቸው ጽጌ መሪያችን እንጂ አሸባሪ አይደለም፣ የህወሓት አገዛዝ በቃን፣ ግድያ ይቁም፣….የሚሉ መፈክሮች ተሰምተዋል፡፡

በኦሮሚያ እና አማራ ክልል እየተካሄደ ባለው የፀረ ጭቆና አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ ምክንያት የኢንተርኔት አገልግሎት በመቋረጡ በርካታ መረጃዎች በመታፈናቸው በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ ወታደረዊ የኃይል ርምጃ የተገደሉ እና የቆሰሉ ዜጎች ቁጥር ከተጠቀሰው ሊጨምር እንደሚችል ይገመታል፡፡

በኦሮሚያ እና በአማራ ክልል በነበሩ ህዝባዊ ተቃውሞዎች በጠፋው የሰው ህይወት እና በወደሙ ንብረቶች ዙሪያ እስካሁን ከገለልተኛ አካል የተጣራ ይፋ ማብራሪያም ሆነ መግለጫ የለም፡፡ ይሁን እንጂ በሁለቱም ክልሎች ባሉ በርካታ ወረዳዎችና ከተሞች ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ አለመረጋጋቱ እንደቀጠሉ ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

በአዲስ አበባ የኮሌራ በሽታ አስጊ ደረጃ ላይ መድረሱን የተባበሩት መንግሥታት የውስጥ መልዕክት ልውውጦች አጋላጡ

(አዲስ ሚዲያ) በአዲስ አበባ በንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የአካባቢ ንፁህና ጉድለት ችግር ምክንያት ከተከሰተው አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) የከተማዋ ነዋሪዎችን ጤና ማናጋት ከጀመረ ሶስተኛ ሳምንቱን አስቆጥሯል፡፡ በንፁህ የውሃ አቅርቦት እና በአካባቢ ንፁህና ጉድለት ምክንያት የሚከሰተው የኮሌራ በሽታ በከተማው መዛመት፤ ዓለም አቀፍ ተቋማት ሰራተኞችን ጨምሮ በርካታ ነዋሪዎችን ለከፋ በሽታ መዳረጉ ታውቋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ባለፈው ሰኞ ሐምሌ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በከተማዋ ለሚገኙ ለሌሎች የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሰራተኞች ባሰራጨው የውስጥ መልዕክት መሰረት፤ ሰራተኞቹ የኮሌራ ክትባት እንዲወስዱ አሳስቧል፡፡ በተለይ ኮሌራ በተበከለ ምግብና ውሃ አማካኝነት የሚዛመትና በንፁህና ጉድለት የሚከሰት በሽታ ሲሆን፤ ወዲያውኑ ተገቢውን ህክምና በጤና ተቋማት ማድረግ ካልተቻለ፤ በአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት የሰውነትን ፋሳሽ በመሳጣት ለሞት እንደሚዳርግ ይታወቃል፡፡

Addis-Ababa-Water-and-Sewerage-Authority

በሽታውን በተመለከተ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሀገር ቤት በመንግሥት ቁጥጥር ስር ለሚገኙ መገናኛ ብዙኃን በሰጠው መግለጫ፤ አተት የተከሰተው የወንዝ ውሃ በሚጠቀሙ ዜጎች ላይ እንደሆነ እና ለዚህም በወንዝ ዳር አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች የመፀዳጃ እና ፍሳሽ ማስወገጃዎቻቸውን ከወንዝ በማገናኘታቸው እንደሆነ በቃል አቀባዩ አህመድ ኢማኖ በኩል አስታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ከሆነ፤ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር የንፁህ የመጠጥ ውሃ ተገቢው ቁጥጥርና ክትትል ባለመደረጉ እና በከተማዋ በተከማቸው ቆሻሻ አማካኝነት እንደሆነ የከተማዋ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ምንጮች ማረጋገጣቸው ተነግሯል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የከተማው የንፁህ መጠጥ ውሃ ጥራት ባልተጠበቀበት ሁኔታ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የከተማው ነዋሪ በመጪው 2009 ዓ.ም. ከዚህ ቀደም ከሚከፍለው የቧንቧ ውሃ ተጨማሪ ክፍያ ማሻሻያ ሊጣልበት እንደሆነም ሪፖርተር ጋዜጣ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የአዲስ አበባ ደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃነት በ1 ቢሊዮን ወጪ በሰንዳፍ ተገንብቷል ቢባልም፤ ሰራ የተባለው ግንባታ ወጪ ከግንባተው ጋር አብሮ ሊድ እንዳይመችል የተጠቆመ ሲሆን፤ ይልቁንም በአካባቢው ያሉ የሰንዳፋ ነዋሪዎች ከአካባቢ ብክለት በሚመጡ በሽታዎች እንዲጋለጥ በማድረጉ፤ የአዲስ አበባ ቆሻሻ በከፍተኛ ወጪ ተሰራ በሚባለው ሰንዳፋ የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ እንዳይደፋ ተቃውሞና እገዳ ማድረጋቸው ታውቋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ የአዲስ አበባ አስተዳደር ለደረቅ ቆሻሻ መጣያ ባለመኖሩ መፍትሄ ባለማበጀቱ ከዚህም በኋላ አዲስ አበባን ለውሃና አየር ወለድ በሽታ ሊያጋልጥ እንደሚችል ተሰግቷል፡፡ የከተማው መስተዳደር ከሰንዳፋ ነዋሪዎች ጋር ቀደም ሲል ያለምንም ድርድርና ምክክር አለመገንባቱ ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ የጥራት ችግር ያለበት በመሆኑ ነዋሪውን ለበሽታ በማጋለጡና ተቃውሞ በመቅረቡ አስተዳደሩ ሌላ መፍትሄ እስኪያዘጋጅ የአዲስ አበባ ቆሻሻ በየመንደሩ ባለበት እንዲቆይ ተደርጓል፡፡ ይህም ከወቅቱ የክረምት ዝናብ ጋር ተዳምሮ በቀላሉ ወደተለያዩ የከተማው ወንዞችና ጉዳት ወደደረሰባቸው የንፁሃ ውሃ ማስተላለፊያ መስመሮች በመቀየጥ፤ አሁን ከተከሰተው የኮሌራ በሽታ በተጨማሪ ለተለያየ ውሃ ወደለድ በሽታ ሊያደርግ እንደሚችል የአስተዳደሩ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ባለሙያዎች ስጋታቸውን ገልፀዋል፡፡

እንደ ከተማዋ የአካባቢ ጥበቃ ባለሙያ ገለፃ ከሆነ፤ በከተማ እየሰሩ ባሉ መሰረተ ልማት እና የተለያዩ የግል ግንባታዎች ምክንያት በርካታ የንፁህ የመጠጥ ውሃ ማስተላለፊያ መስመሮች ከጥቅም ውጭ ሆነው ከከተማ ፍሳሽ ማስወገጃ ጋር በመገናኘታቸው እንደሆነ እና ችግሩንም በአጭር ጊዜ ለማስተካከል አስቸጋሪ እንደሆነ በተለይ ለአዲስ ሚዲያ አስታውቀዋል፡፡ ስለሆነም፤ ችግሩ እስኪቀረፍ የከተማው ነዋሪ አቅሙ የፈቀደ ከከተማው የባንቧ ውሃ ከመጠቀም ተቆጥቦ ሌሎች አማራጮችን አሊያም ውሃን በደንብ አፍልቶ በማቀዝቀዝ እንዲጠቀሙ አሳስበዋል፡፡ በተጨማሪም፤ አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት ምልክት የታየባቸው ሰዎች በአስችኳይ በአቅራቢያቸው ወዳለ የህክምና ጣቢያ እንዲሄዱና ተገቢውን የህክምና ክትትል እንዲያደርጉ መክረዋል፡፡

በተከሰው የኮሌራ ወረርሽን በሽታ በርካታ ህፃናትና እናቶች ሰለባ ሆነው በከተማዋ ባሉ ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች ተኝተው ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ በበሽታው ታመው የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው ከሚገኙ የከተማው ነዋሪዎች በስተቀር ህይወታቸው ያለፈ ስለመኖሩ እስካሁን የተገረጋገጠ መረጃ ማግኘት አልተቻለም፡፡ መንግሥት በስታውን እና መንስዔውን ከመገናኛ ብዙኃን ለመደበቅ ቢሞክርም፤ ዓለም ተቋማት የሚሰሩትን ጨምሮ በርካታ ነዋሪዎች የችግሩ ሰለባ በመሆናቸው በየ ህክምና ተቋሙ የሚሰጡ ውጤቶች ላይ ኮሌራ መሆኑን የሚገልፅ ማስረጃ እንዳይወጣ ያደረገው ጥረት በህክምና ባለሙያዎች ሊጋለጥ ችሏል፡፡ መንግሥት ችግሩን ለመሸፋፈን ከመሞከርና ከማስተባበል ባለፈ እየወሰደ ስላለው የማስተካከያ ርምጃ በግልፅ ያለው ነገር የለም፡፡

ዘጠነኛ ወሩን ባስቆጠረው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞ፤ የመንግሥት የግድያ ርምጃ ተጠናክሮ ቀጥሏል

(አዲስ ሚዲያ) በኦሮሚያ ክልል ዘጠነኛ ወሩን ያስቆጠረው ህዝባዊ ሰላማዊ ተቃውሞ ላይ መንግሥት እየወሰደ ያለው የግድያ ርምጃ ተጠናክሮ መቀጠሉ ታውቋል፡፡ ዛሬ ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሐረርጌ አወዳይ ከተማ በነበረው ህዝባዊ ሰላማዊ ተቃውሞ 6 ሰዎች በልዩ አልሞ ተኳሽ የፀጥታ ኃይል ሲገደሉ፤ በዊልቸር የሚንቀሳቀስ አካል ጉዳተኛን ጨምሮ 20 ያህሉ መቁሰላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በፀጥታ ኃይሉ ተኩስ የቆሰሉ ሰዎችም በሐረር እና ድሬዳዋ ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው መሆን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

Aweday rally
በተመሳሳይም በሐረማያ ህዝባዊ ተቃውሞ መቀስቀሱ የተጠቆመ ሲሆን፤ በተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ታዳሚው ላይ በመንግሥት በተወሰደ ርምጃ ጉዳት መድረሱ ቢነገርም እስካሁን በዝርዝር ለማወቅ አልተቻለም፡፡ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በህዝቡ ላይ የወሰዱትን የኃይል ርምጃ ተከትሎ በተለይ የአወዳይ ከተማ ነዋሪ ከአዲስ አበባ ሐረር እና ጅግጅጋ መንገድን ሙሉ ለሙሉ ዘግቶ እንደነበር ተጠቁሟል፡፡ በዚህ በተገባደደው ሳምንት በምዕራብ አርሲ እና ምዕራብ ሐረርጌን ጨምሮ በተለያዩ የክልሉ የወረዳ ከተሞች ጭምር የተለያዩ ህዝባዊ ተቃውሞች መደረጋቸውና ይህንንም ተከትሎ በቅርቡ ከአዳማ ዩኒቨርስቲ የተመረቀ ተማሪን ጨምሮ ሌሎች ንፁሃን ዜጎችም በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን በመግለፅ የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትወርክ ዘገባ አመልክቷል፡፡

ባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ጊኒጪ ከተማ ዳግም በተቀሰቀሰው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞ እስካሁን ከ500 በላይ ንፁሃን ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን እና በርካቶችም ቆስለው ህክምና ሲከታተሉ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ይህ ዘጠነኛ ወሩን ባስቆጠረው በዚህ ህዝባዊ ተቃውሞ ከ30 ሺህ በላይ ዜጎች እንደታሰሩ የመብት አራማጆች ያስታወቁ ሲሆን፤ አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ የተለያዩ ጋዜጠኞች እና ፖለቲከኞችም ለእስር ተዳርገዋል፡፡

አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ በቃሊቲ እና ቂሊንጦ ወህኒ ቤቶች የሚከገኙ የተለያዩ የፖለቲካ እና የህሊና እስረኞች በወህኒ ቤቱ አስተዳደርና በሌሎች የፍትህ አካላት እየተፈፀመባቸው ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት በመቃወም ላለፉት 10 ቀናት የርሃብ አድማ በመምታቸው ራሳቸውን ስተው በጉሉኮዝ እገዛ እንደነበሩ ፍርድ ቤት ከቀረባ አቤቱታ መረዳት ተችሏል፡፡

በጎንደር ታላቅ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰልፍ ተደረገ

(አዲስ ሚዲያ) ዛሬ እሁድ ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ጀምሮ መዳረሻውን በጎንደር ፋሲለደስ መስቀል አደባባይ ያደረገ ታላቅ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰልፍ ተደረገ፡፡ የተቃውሞ ሰልፉ ዋነኛ ምክንያት ባለፈው ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. የማዕከላዊ መንግሥት የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ጥያቄ አንሺ ኮሚቴ አባላት ከሚኖሩበት ጎንደር ከተማ በሌሊት አፍኖ ወስዶ በማሰሩ፣ ከኮሚቴ አባላት መካከልም ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ እቤታቸው ሊያፍኑ የሄዱትን የፀጥታ አካላት ህጋዊ ከሆናችሁ በቀን መምጣት ትችላላችሁ፣ በሌሊት ህገወጥነት በሚል በተፈጠረ አለመግባባት የ11 የፅጥታ ኃይሎች እና 3 ሲቪሎች መገደላቸው ይታወቃል፡፡ ይህንንም ተከትሎ መንግሥት የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ጥያቄ አቅራቢዎችን እና የፀጥታ ኃይሉ ላይ የአፀፋ ርምጃ የወሰዱትን ጨምሮ የመንግሥትን ርምጃ በማውገዝ እና ተቃውሞ ያቀረቡ የአካባቢውን ህዝብ ወንጀለኛ አድርጉ በሚዲያ በማቅረቡ የተቆጣው ህዝብ፤ ተቃውሞውን በአደባባይ ለማቅረብ ያቀረበው ጥያቄ ውድቅ በመደረጉ ህዝቡ በራሱ ተነሳሽነት የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ እንዲወጣ እንዳደረገው ከአስተባባሪዎቹ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Gonder 1
ከጎንደር ፋሲለደስ ከተማ በተጨማሪ በደቡብ ጎንደር በእስቴ ወረዳ መካነ ኢየሱስ ከተማ፣በምዕራብ በለሳ እና ማክሰኝት ከተማ ተመሳሳይ ጥያቄ መነሻ ያደረገ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መደረጉ ታውቋል፡፡ በተለይ በጎንደሩ ሰልፍ የተለያዩ የኃይማኖት አባቶች በተቃውሞ ሰልፉ ላይ ተገኝተው ንግግር ማድረጋቸውን የዓይን እማኞች አረጋግጠዋል፡፡

በዛሬው ተቃውሞ ሰልፍም የተለያዩ መፈክሮች የተደመጡ ሲሆን፤ በዋናነትም የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ ሕገ-መንገሥታዊ መብት ነው፣ የሻዕብያ ተላላኪ ህወሃት እንጂ ወልቃይት አይደለም፣ በግፍ የታሰሩ የወልቃይት አማራ ማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት በአስቸኳይ ይፈቱ፣…የሚሉትን ጨምሮ በርካታ መፈክሮች እንደተሰሙ ለማወቅ ተችሏል፡፡


በተቃውሞ፤ ታሪክ ምስክር ነው ወልቃይት አማራ ነው ፣ አማራ ለኢትዮጵያ የግዛት አንድነትና ሉአላዊነት የተዋደቀ ታላቅ አርበኛ ሕዝብ ነው ፣ ዘረኝነትን አጥብቀን እናወግዛለን ፣ የትግራይን ሕዝብ እናከብራለን፤የህወሓትን አፋኝ የአገዛዝ ፖሊሲ አጥብቀን እናወግዛለን፣አማራነት ይከበር፣ በኦሮሞ እህት ወንድሞቻችን ላይ የሚደርሰውን ግፍና በደል አጥብቀን እንቃወማለን፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነት ይፈልጋል፣ በኦሮሚያ የሚደረገው በወንድምና እህቶቻችን ላይ ግድያ ይቁም፣ ኢቢሲና ሌሎች መንግስታዊ ሚዲያዎች የጎንደርንና አካባቢውን ህዝብ ይቅርታ ይጠይቁ የሚሉ መሪ ቃሎች ተደምጠዋል፡፡

በተጨማሪም የወልቃይት የአማራ ማንነት ጥያቄ እስኪመለስ ድረስ ትግሉ ይቀጥላል፣አማራነት ወንጀል አይደለም፣ የትግራይ ወሰን ተከዜ ነው፣ ወልቃይት የአማራ ነው ፣ የሐብታሙ አያሌዉ ከአገር የመዉጣት እግድ በአስቸኳይ ይነሳለት፣ ዜጎችን በፖለቲካ አመለካከታቸዉ ማሰርና ማሰቃየት ይቁም፣ በፖለቲካ አመለካከታቸዉ የታሰሩ የፖለቲካና የህሊና እስረኞች በአስቸኳይ ይፈቱ እና የህወሓት የበላይነት ይቁም የሚሉ መፈክሮች ጎልተው ተሰምተዋል፡፡


ይህ ህዝባዊ ተቃውሞ ከሳምንት በፊት እውቅና ተጠይቆ በመንግሥት ተከልክሎ የነበረ ሲሆን፤ በድጋሚ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ እውቅና ለሚመለከተው የመንግሥት አካል ቢገባም፤ መንግሥት ለህዝባዊ የተቃውሞ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ እውቅና አለመስጠቱን ከማስጠንቀቂያ አዘል መልዕክት ጋር በኢቢሲ እና ኤፍቢሲ ቢያሳውቅም ህዝቡን ለተቃውሞ ከመውጣት ማገድ አልቻለም፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ መንግሥት ህዝባዊ ተቃውሞ ሰልፍ እውቅና መንፈጉን በስሩ ባለ መገናኛ ብዙኃን ከመግለፁ በተጨማሪ በጎንደር ከፍተኛ የመከላከያ፣ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ፣ የአማራ ክልል ልዩ ኃይል እና የከተማው ሚሊሻ አባላት በበብዛት በከተማው እንዲሰፍሩ መደረጉ ታውቋል፡፡

ተቃውሞ ምንም እንኳ የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄን መነሻ ያድርግ እንጂ፤ ለዓመታት በአማራ ማኀበረሰብ ላይ በመንግሥት በተለይም በህወሓት/ኢህአዴግ አማራ ክልልን  ጨምሮ በተለያየ የኢትዮጵያ ክፍል እየተፈፀመ ያለውን የሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ የመብት ጥሰት ተባብሶ መቀጠሉ አንዱ የተቃውሞ አካል መሆኑን የሰልፉ ታዳሚዎች ሲያስተጋቡ ተስተውሏል፡፡

በነበረው ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍም፤ በሰውም ሆነ በንብረት ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት ሳያስከትል በሰላም መጠናቀቁን የተሳታፊዎችን ጨምሮ ዓይን እማኞች እውቅና የነፈገው የመንግሥት አካል አስታውቀዋል፡፡ በሰልፉ ላይም በኢህአዴግ የስልጣን ዘመን በ25 ዓመታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ አረንጓዴ፣ ቢጫ ቀይ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ በብዛት ሲውለበለብ ታይቷል፡፡