Daily Archives: March 31st, 2015

በየመን ጦርነት 45 ኢትዮጵያዊያን ሲገደሉ ከ60 በላይ ቆስለዋል

ግሩም ተ/ኃይማኖት

ሰሞኑን ያለማቋረጥ የመን ላይ እየተወሰደ ባለው የአየር ጥቃት ምክንያት ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በከፍተኛ ችግርና ጭንቀት ውስጥ ናቸው፡፡ ዛሬ በተደረገ የአየር ድብደባ ምክንያት ካምፕ ውስጥ የነበሩ 45 ኢትዮጵያዊን ሲገደሉ ከ60 በላይ ቆስለዋል፡፡

Yeman war

በIOM ካምፕ ላይ በስህተት የተወሰደ እርምጃ ነው በተባለው በዚህ ጥቃት፤የስደተኞች መጠለያ ካምፕ ውስጥ የነበሩት የምስራቅ አፍሪካ ስደተኞች ናቸው የሞቱት የሚል መግለጫ IOM ቢያወጣም፤ በዛ ካምፕ ውስጥ የሚጠቀሙት ኢትዮጵያዊን መሆናቸው ግን የታወቀ ነው፡፡ በተደጋጋሚ ሄጄ ካምፑን እንዳየሁት እኔም የማውቀው በጅቡቲ በኩል ወደ የመን የሚገቡ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ብቻ እንደሚያርፉበት ነው፡፡ የሞቱትን ነፍስ ይማር!!!! የተቀሩት ኢትዮጵያዊያንስ እጣ ፋንታ ምን ይሆን?

የመድረክ ከፍተኛ አመራርና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህሩ አቶ በቀለ ገርባ ከእስር ተለቀቁ

አቶ በቀለ ገርባ

አቶ በቀለ ገርባ

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርና የቀድሞው የኦሮሞ ፌደራሊስት ንቅናቄ፣ የአሁኑ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ/መድረክ ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት አቶ በቀለ ገርባ ከነሐሴ 2003 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ከቆዩ በኋላ መጋቢት 21 ቀን 2007 ዓ.ም. ተለቀዋል፡፡ አቶ በቀለ ገርባ መንግሥት በዜጎች ላይ በፈፀማቸውና እየፈፀማቸው ባሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ጉዳይ ከአምንስቲ ኢንተርናል ጋር ቃለ መጠይቅ ካደረጉ በኋላ የኦነግ አባል ናቸው በሚል በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ ወንጀል ችሎት 8 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸው ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ተከላካይ ጠበቆቻቸውና አቶ በቀለ የታሰሩት ያለምንም ወንጀል እንደሆነ፣መንግሥት የኦነግ አባል ብሎ የመሰረተባቸው ክስ እንደማይመለከታቸው፣ እሳቸው በወቅቱ በሀገር ውስጥ በሰላማዊ መንገድ እየታገለ ያለው የኦፌዲን/መድረክ አመራር መሆናቸውን በማስረጃ ቢከራከሩም ፍርድ ቤቱ ሳይቀበለው በመቅረቱ ለፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ መጠየቃቸው ይታወሳል፡፡

እነ አቶ በቀለ ገርባ የከፍተኛው ፍርድ ቤት ውሳኔ በመቃወም ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ካሉ በኋላ የ8 ዓመቱ ፅኑ እስራት ወደ 3 ዓመት ከ7 ወር የተቀነሰ ሲሆን፤ ይሄንንም ይግባኝ ብለው ወደ ፌደራሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ቢሄዱም የ3 ዓመት ከ7 ወር ፍርድ በመፅናቱ በእስር ቆይተዋል፡፡ አቶ በቀለ ገርባ በህጉ መሰረት በአመክሮ ከእስር መፈታት የነበረባቸው ከአንድ ዓመት በፊት ጥር 2006 ዓ.ም. ቢሆንም፤ ዝዋይ የሚገኘውም ሆነ አቃቂ ቂሊንጦ የሚገኘው ወህኒ ቤት ፈቃደኛ ባለመሆናቸው 4ኛ ዓመት ድረስ በእስር ሊቆዩ ችለዋል፡፡ መረጃዎች እንደጠቆሙት ከሆነ አቶ በቀለ ገርባ የተለቀቁት ከነበሩበት እስር ቤት ከተለቀቁ በኋላ ከባለቤታቸው ወ/ሮ ሐና ጋር እየተጓዙ ከእስር ቤቱ ብዙም ሳይርቁ፤ በወህኒ ቤቱ ጠባቂዎች ቆይ ሌላ የሚጣራ ጉዳይ አለ በሚል ተመልሰው እስር ቤት ካስገቧቸው በኋላ በጭለማ ሞጆ ከተማ አካባቢ ተወስደው መለቀቃቸው ተጠቁሟል፡፡ አቶ በቀለ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ከማስተማራቸው በተጨማሪ የዶክተሬት ዲግሪ ማጠናቀቂያቸው ላይ መታሰራቸው አይዘነጋም፡፡ በአሁን ወቅት የኦፌኮ/መድረክ አመራር አቶ ኦልባና ሊሊሳን፣ የአድነት ከፍተኛ አመራር አቶ አንዱዓለም አራጌ እና ጋዜጠኛ እስንክንድር ነጋን ጨምሮ በርካታ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮችና አክቲቪስቶች በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡

%d bloggers like this: