Monthly Archives: April, 2016

እነ ኦኬሎ ኦኳይ ጥፋተኛ ተባሉ

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ መጋቢት 28ቀን 2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት የቀድሞው የጋምቤላ ርዕሰ መስተዳድር ኦኬሎ ኦኳይ እና አብረዋቸው የተከሰሱት ስድስት ተከሳሾች ጥፋተኛ ናቸው ብሎ ውሳኔ አስተላለፈ።ፍርድ ቤቱ የቅጣት አስተያየት ለመስማት ሚያዚያ 17 ቀጠሮ ስጥቷል፡፡

Okello Akuay

በሰኔ ወር 2006ዓ.ም የሽብር ክስ ተመሰርቶባቸው ክሳቸው እየታየላቸው የሚገኙት እነ ኦኬሎ ኦኳይ በየካቲት 28 ቀን 2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውሳኔ ለማስተላለፍ ለዛሬ ለሶስተኛ ጊዜ ተቀጥረው ነበር፡፡ በዚህም መሰረት ዛሬ በችሎት ከተሰየሙት ሶስት ዳኞች መካካል የቀኝ ዳኛ የሆኑት አቶ ሳሙኤል ታደሰ የፍርድቤቱን ውሳኔ በንባብ አሰምተዋል፡፡

ዳኛ ሣሙኤል ታደሰ ወደ አንድ ስዓት በቆየው የፍርድ ውሳኔ ንባባቸው እንዳመለከቱት አቶ ኦኬሎና ስድስቱ ተከሳሾች የጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል በመሆን እና የጋምቤላ ክልልን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ተንቀሳቅሰዋል፡፡ ከአሜሪካ ገንዘብ በማሰባሰብ እና የሽብር ቡድን ማስተባበራቸውን በንባባቸው ጠቅሰዋል፡፡

አቃቤ ህግ በነኦኬሎ ላይ ከዘረዘራቸው ክሶች መካከል ከኤርትራ መንግስት ጋር የሽብር ድርድር በማድረግ እና ከኦነግ እና ግንቦት 7 አመራሮች ጋር በተለይ ከሞት ፍርደኛው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ጋር መገናኘት እንደሚገኙበት ዳኛ ሳሙኤል አስታውሰዋል፡፡ከዚህም በተጨማሪ ወጣቶችን ለሽብር ተግባር መመልመል፣ ወታደራዊ ስልጠና መስጠት በክሳቸው ላይ መጠቀሱን ዳኛው ተናግረዋል፡፡

ከክስ ንባብ መስማት በኃላ ወደ ሁለት አመት ያህል ፍርድቤት የተመላለሱት እነ ኦኬሎ አኳይ የክስ መቃወሚያ ካቀረቡበት ጊዜ አንስቶ ለውሳኔ እስከተቀጠሩበት ጊዜ ያለው ሂደት በዳኛው ተብራርቶ ቀርቧል፡፡
የእነ ኦኬሎ የክስ መቃወሚያ በፍርድ ቤቱ ሙሉ ለሙሉ ውድቅ መደረጉን እና የተከሰሱበትን ክስ ክደው መከራከራቸውን ያስታወሱት ዳኛ ሳሙኤል በመቀጠል አቃቤህግ ምስክሮቹን አቅርቦ ማሰማቱን አስረደተዋል፡፡
ለወራት ከዘለቀው የምስክሮች መሰማት ሂደት በኃላ ፍርድቤቱ ተከሳሾቹን እንዲከላከሉ መወሰኑን ዳኛው ጠቅሰዋል፡፡ ተከሳሾቹ በምርመራ ወቅት በከፍተኛ ጫና እና ድብደባ ውስጥ እንዳለፉ ማስመዝገባቸውን ዳኛው ጠቁመዋል፡፡

የግራና የቀኙን ክርክር ያዳመጠው እና የቀረቡለትን ማስረጃዎች የመረመረው ፍርድ ቤት በሁሉም ተከሳሾች ላይ የጥፋተኛ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

አንደኛ ተከሳሽ ኦኬሎ አኳይ በሰው እና መማስረጃ የጋምቤላን ክልል ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር በመሆን የአመራር ሰጪ ውሳኔዎችን ሲመራ በመቆየቱ አቃቤህግ በሰው እና በማስረጃ ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዳ ዳኛው በውሳኔው አመልክተዋል፡፡ተከሳሹ በበኩሉ የተከሳሽነት ቃል ከማሰማት በስተቀር መከላከያ ምስክሮችም ይሁን ሰነዶችን አቅርቦ በበቂ ሁኔታ እንዳልተከላከለ ዳኛው ገልፀዋል፡፡
ቀሪዎቹም ተከሳሾች በምርመራ ወቅት ለፖሊስ ቃላቸውን ተገደው ስለመስጠታቸው ያሰረዱ እንጂ የቀረበባቸውን ክስ የሰው ምስክር እና የሰነድ ማስረጃ አቅርበው እንዳልተከላከሉ በዳኛው ተገልጿል፡፡
“[ተከሳሾቹ] ምስክሮቻቸው ማዕከላዊ አብረዋቸው የነበሩ፣ በሌላ ወንጀል ተጠርጥረው ያሉ እና ተዓማኒነታቸው ጥርጣሬ ውስጥ የሚገባ ከመሆኑ በተጨማሪ ከዋናው ክስ እና የክስ ማስረጃ ጋር የማይገናኙ በመሆናቸው ክሳቸውን በደንብ አልተከላከሉም” ሲሉ ዳኛው ገልፀዋል፡፡

ክሱ መታየት ያለበት በፀረ ሽብር አዋጁ ነው ወይስ አይደለም የሚለውን ፍርድቤቱ መርምሮ በአንደኛ ተከሳሽ የተመሰረተው ጋህነን፣ የጋምቤላ ህዝብን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ከተለያዩ የሽብር ቡድኖች ጋር የስልጠና ትብብር መጠየቃቸው በአቃቤ ህግ የተረጋገጠ ነው ብለዋል ዳኛው፡፡ ሆኖም ድርጊቱ የአገሪቷን አንድነት የማፈራረስ ሙከራን የሚያቋቁም እንደሆነ የገለፁት ዳኛው በዚህም መሰረት ተከሳሾቹ በፀረ ሽብር አዋጁ ሳይሆን የወንጀል ህጉን 241 በመተላለፋቸው በወንጀለኛ መቅጫ ስነስርአት ህግ 149(1) የጥፋተኝነት ውሳኔ ማስተላለፉን ተናግረዋል፡፡

መጋቢት 28/2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት የጥፋተኝነት የፍርድ ውሳኔ የተላለፈባቸው ሰባት ሰዎች ሲሆኑ፣ እነዚህም ኦኬሎ አኩዋይ፣ ዴቪድ ኦጅሉ፣ ኡቻል አፒዮ፣ ኡማን ኒኮዮ፣ ኡጅሉ ቻም፣ ኡታካ ኡዋር እና ኡባንግ ኡቡንግ ናቸው፡፡

ምንጭ፡- EHRP

የዜጎች የመንቀሳቀስ መብት ይከበር!

ዞን 9

Zelalem Kibret

የዜጎች ከሀገር ሀገር የመንቀሳቀስ መብት በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥትም ሆነ ኢትዮጵያ አባል ሆና በፈረመቻቸው አህጉር አቀፍ እና ዓለማቀፍ ድንጋጌዎች የተጠበቀ ነው፡፡ በሕገ መንግሥቱ በአንቀጽ 32/1 ላይ “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ . . . ከሀገር የመውጣት ነጻነት አለው” በማለት ተደንግጓል፡፡ ኢትዮጵያ ፈራሚ አባል የሆነችበት ‘ዓለም አቀፉ የሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች ቃልኪዳን’ በበኩሉ ማንኛውም ግለሰብ ሕጋዊ ማዕቀብ ካልተጣለበት በስተቀር ወደፈለገው ቦታ የመንቀሳቀስ ከሀገር መውጣትን የሚጨምር መብት እንዳለው ይደነግጋል፡፡ በኢትዮጵያ ህግም ብቸኛ ገደብ የሚያስቀምጠው የኢምግሬሽን አዋጅ ቁጥር 354/2003 በአንቀጽ 7 ላይ “ማንኛውም ሰው ከኢትዮጵያ እንዳይወጣ ሊታገድ የሚችለው በሕግ መሠረት በፍርድ ቤት ሲታዘዝ ብቻ ነው” በማለት የመንቀሳቀስ መብት ገደብን በማያሻማ መልኩ ያስቀምጠዋል፡፡

እንደሚታወሰው የዚህ የጡመራ መድረክ አባል የሆነው ዘላለም ክብረት በወንጀል ተጠርጥሮ ታስሮ የነበረ ቢሆንም ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ በራሱ ተነሳሽነት ክሱ እንዲቋረጥ በማድረጉ ከማሕሌት ፋንታሁን፣ ከአስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ፣ ከኤዶም ካሳዬና ከተስፋለም ወልደየስ ጋር ሐምሌ 01/2007 ከእስር ተፈትቷል፡፡ ከላይ በተጠቀሰው የሕግ አግባብ መሠረት ከሀገር እንዳይወጣ የሚያደርግ ምንም ዓይነት ሕጋዊ ክልከላም የለበትም፡፡ ይሁንና ሕዳር 05/2008 ዘላለም ለቡድኑ የተበረከተ ሽልማትን ለመቀበል ወደ ፈረንሳይ፣ ፓሪስ ለማቅናት ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ቢገኝም የጉዞ ሰነዱ (ፓስፖርቱ) ተነጥቆ ከሀገር እንዳይወጣ ተከልክሏል፡፡ በተለያዩ የመገናኛ አውታሮች እንደተገለጸው ጦማሪው የጉዞ ሰነዱ እንዲመለስ እና የመንቀሳቀስ መብቱ እንዲከበር ያደረገው ሙከራ ከመጉላላት በቀር ምንም መፍትሔን አላስገኘም፡፡ እንዲያውም በአግባቡ ምላሽ የሚሰጥ መንግሥታዊ አካል መጥፋቱን ለመታዘብ ችለናል፡፡ በዚህም ምክንያት የተለያዩ ዕድሎችን ተጠቅሞ መማርም ሆነ መሥራት እንዳይችል ሁኗል፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽንም ይህንን የመብት ጥሰት ‹ጉዳዩ ከአቅሜ በላይ ነው› በሚል ምክንያት ሊያስቆም አልቻለም፡፡

በሌላ በኩል ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ በታኅሣሥ 01/2008 ዓ.ም. ለትምህርት ወደ አሜሪካ ለመሔድ በሞከረችበት ወቅት የጉዞ ሰነዷን ተቀምታ ከሐገር መውጣት እንደማትችል የተነገራት ሲሆን፤ ለምን የጉዞ ሰነዷን እንደተነጠቀች በተደጋጋሚ ለኢሚግሬሽን እና ዜግነት መምሪያ ጥያቄ ብታቀርብም እስከ አሁን ድረስ ምላሽ ማግኘት አልቻለችም፡፡

እንዲሁም ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በጥር 11/2008 ዓ.ም. ወደ ጀርመን ሃገር ለስድስት ሳምንታት የጋዜጠኝነት ልምድ ለመቅሰም ያገኘውን አጋጣሚ ለመጠቀም ያደረገው ሙከራም በተመሳሳይ የጉዞ ሰነዱን ያለምንም ሕጋዊ ምክንያት በመነጠቁ ምክንያት ሳይሳካ ቀርቷል፡፡

ይባስ ብሎም ጋዜጠኛ አስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ ለስድስት ሳምንታት ወደ ጀርመን ሃገር በመሔድ በጀርመኑ የመንግስት ቴሌቪዥን ጣቢያ የቀረበለት የልምድ ልውውጥ ላይ ተሳትፎ ወደ ሃገሩ ሲመለስ በየካቲት 26/2008 ዓ.ም. በተመለሰበት ወቅት ‹ከሃገር እንዴት ልትወጣ ቻልክ› ከሚል ከባድ ዛቻና ማስፈራሪያ ጋር የጉዞ ሰነዱን ሊነጠቅ ችሏል፡፡

ይህንን ሕገ ወጥ ድርጊት ለማረም ሁሉንም ሕጋዊ መንገዶች አሟጠን የምንጠቀም ሲሆን፤ ሕግ አስፈጻሚው አካል ግን ይህንን ስህተቱን ማረም የሚጀምርበት ተጨማሪ ዕድል አግኝቷል፡፡ ዘላለም ክብረት የዘንድሮው The Nelson Mandela Fellowship ወይም በቀድሞው አጠራር Young African Leaders initiative (YALI) አሸናፊ ሆኗል፡፡ የኔልሰን ማንዴላ ፌሎውሽፕ የአሜሪካው ፕሬዝዳነት ባራክ ኦባማ ወጣት አፍሪካውያን አህጉራቸውን የሚጠቅሙ መሪዎች እንዲሆኑ የሚያግዛቸውን ክህሎት እንዲጨብጡ በማሰብ እ.ኤ.አ. 2010 ይፋ ያደረጉት መርሐ-ግብር ሲሆን፤ በዚህ ስድስት ሳምንታት በሚፈጀው መርሐ-ግብር በየዓመቱ በርካታ አፍሪካውያን ለራሳቸውም ለአህጉራቸውም ጠቃሚ የሆነ ዕውቀት ገብይተው ተመልሰዋል፡፡ የዘንድሮው ውድድር አሸናፊ የሆኑት ሌሎች ኢትዮጵያውያን እና ዘላለም ክብረት በመጋቢት እና ሚያዝያ ወር ቅድመ ሁኔታዎችን አሟልተው በሰኔ አጋማሽ ወደ አሜሪካ እንደሚያቀኑ የመርሐ-ግብሩ የጊዜ ሰሌዳ ያሳያል፡፡

እኛም ከጊዜ ወደ ጊዜ ጉዳዩ ሕጋዊ መልክ ይይዛልና ይሻሻላል ብለን ተስፋ ብናደርግም ነገሮች ግን እየተባባሱ እና የመብት ጥሰቱም እየጨመረ መጥቷል፡፡ ይሄም ድርጊት ዜጎች በሃገራቸው ሕግን አምነው ለመኖር አለመቻላቸው ማሳያም ነው፡፡ በመሆኑም የሚመለከተው የአስፈጻሚ አካል ያለምንም የሕግ አግባብ የጉዞ ሰነዳቸውን ተቀምተው የሚገኙ ጦማሪዎችና ጋዜጠኞች መብታቸው ተከብሮላቸው የጉዞ ሰነዶቻቸው ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲመለሱላቸው እንዲያደርግ እና የመንቀሳቀስ መብታቸውን እንዲያከብር እንጠይቃለን፡፡

ሕገ መንግሥቱ ይከበር!

ምንጭ፡ https://www.facebook.com/Zone9ers/?fref=nf

በኦሮሚያ ለግጭት ምክንያት የነበረው የከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች ተሰረዙ

በውድነህ ዘነበ

Fekadu Tesema,Oromia PR

በኦሮሚያ ክልል ሕዝባዊ ጥያቄ የተነሳበት የከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች ተሰረዙ፡፡ እነዚህ አወዛጋቢ የተባሉ አንቀጾች ከተሰረዙ በኋላ ባለፈው ሳምንት የተሰበሰበው ጨፌ ኦሮሚያ አዋጁን አፅድቋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ተነስቶ ለነበረው ረብሻ የአዲስ አበባና ዙሪያዋ ኦሮሚያ ልዩ ዞን የጋራ ማስተር ፕላንና የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ ምክንያት እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የማስተር ፕላኑን ተግባራዊነት ማቆሙን በወቅቱ በይፋ የገለጸ ሲሆን፣ ለውዝግቡ መባባስ ምክንያት የነበሩ የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ ሦስት አንቀጾች እንዲሰረዙ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

የተሰረዙት ሦስት አንቀጾች ከተሞችን መቀላቀል፣ የተቀላቀሉ ከተሞች ስያሜና ራዲዮ ፖሊ (የክልሉን ትልልቅ ከተሞች በተመለከተ) የሚያትቱ ናቸው፡፡ የኦሮሚያ ከተሞች አዋጅ አንድ የክልሉ ከተማ በዙሪያው ካሉት አነስተኛ ከተሞችን (ሳተላይት) በመያዝ እንደ አዲስ ይደራጃል ይላል፡፡
ለፀጥታ መደፍረስ ምክንያት የሆነው የኦሮሚያ ልዩ ዞን ውስጥ ያሉ ከተሞችን ከአዲስ አበባ (ፊንፊኔ) ጋር ለመቀላቀል ነው የሚሉ ግምቶችን ከተለያዩ ወገኖች በመስጠቱ ነው ተብሏል፡፡

በሌላ በኩል የክልሉ ከተሞች ሲቀላቀሉ አንድ ስም የግድ ይመርጣሉ፡፡ ይህ ሁኔታ የክልሉን ታሪክና ባህል ያጠፋል፣ ልዩ ዞኑን ከአዲስ አበባ ጋር ለመቀላቀል ያለመ ነው የሚል ትንታኔ አሁንም በመስጠቱ ለችግሩ መንስዔ ነው ተብሏል፡፡

በሦስተኛ ደረጃ የተቀመጠው የራዲዮ ፖሊ ትንታኔ ነው፡፡ የአገሪቱ መዲና አዲስ አበባ የፌዴራል መንግሥት ከተማ ነች፡፡ የክልል ከተሞች ባህር ዳር፣ መቐለ፣ ሐዋሳ፣ ጅማ፣ አዳማና የመሳሰሉት ከተሞች በራዲዮ ፖሊ ምድብ ይገኛሉ፡፡
የፌዴራል መንግሥት ባወጣው የከተሞች ፖሊሲ ራዲዮ ፖሊ ከተሞች ከፌዴራል መንግሥት ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ታቅዷል፡፡

የኦሮሚያ ክልል በከተሞች አዋጅ ላይ ስለ ከተሞቹ የገለጸ ሲሆን፣ ለዚህ ጉዳይ ከተለያዩ ወገኖች የተሰጠው ምላሽ ግን የኦሮሚያ ከተሞች በፌዴራል ሥር ሊገቡ ነው የሚል ነው፡፡ እነዚህ ሦስት ጉዳዮች በኦሮሚያ ተከስቶ ለነበረው ደም አፋሳሽ ግጭት መንስዔ እንደነበሩ ተገልጿል፡፡

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊና የካቢኔ አባል አቶ ፈቃዱ ተሰማ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በእነዚህ ጉዳዮች ላይ ሕዝብ ጥያቄ በማንሳቱና የኦሮሚያ መንግሥት ሕዝብ የማይስማማበትን አንቀጾቹን ከአዋጁ ውስጥ ፍቆታል፡፡

አቶ ፈቃዱ ‹‹እነዚህ አንቀጾች ጉዳት ኖሯቸው ሳይሆን ፅንፈኞች በአሉታዊ መንገድ ጉዳዩን እጅግ ያስተጋቡት በመሆኑና እኛ ደግሞ በተገቢው መንገድ ግልጽነት ስላልፈጠርን የተፈጠረው ብዥታ ከፍተኛ ነበር፤›› ብለዋል፡፡

‹‹እነዚህ ጉዳዮች የሕዝቡን ጥቅም የሚጎዱ ሆነው አይደለም፤›› በማለት ክልሉ ሐሳቡ የሕዝብ እስከሆነ ድረስ የሕዝብን ጥያቄ እንደሚቀበለው አቶ ፈቃዱ ገልጸዋል፡፡

እነዚህ አንቀጾች ከመሰረዛቸው በተጨማሪ በሌሎች ሁለት ጉዳዮች ላይ ማሻሻያ መደረጉን አቶ ፈቃዱ ገልጸዋል፡፡ ፀድቆ በነበረው የከተሞች አዋጅ የክልሉ ከተሞች የሚሰበስቡትን ፋይናንስ ለራሳቸው ይጠቀማሉ የሚል አንቀጽ ነበር፡፡ ነገር ግን ገቢ የማመንጨት አቅም የሌላቸውን ከተሞች ስለሚጎዳ፣ በማዕከል ደረጃ በጀት ቢከፋፈል የተሻለ መሆኑ ስለታመነበት ማሻሻያ ተደርጓል፡፡

ቀደም ሲል በክልሉ ከተሞች በላይኛው የአስተዳደር እርከንና በቀበሌ መካከል ራሱን የቻለ የመንግሥት መዋቅር አልነበረም፡፡ ቀደም ብሎ ፀድቆ በነበረው አዋጅ የወረዳ መዋቅር እንዲከፈት ተደንግጎ ነበር፡፡ ነገር ግን ከወረዳ ይልቅ ክፍለ ከተማ የተሻለ መዋቅር ነው ተብሎ ማሻሻያ መደረጉን አቶ ፈቃዱ ገልጸው፣ ትልልቅ ከተሞች የክፍለ ከተማ መዋቅር እንዲመሠርቱ በአዲሱ አዋጅ ማሻሻያ ተደርጓል፡፡

ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ

COINTELPRO: ተቃዋሚዎችን የመከፋፈያ ቀላል ዘዴ (ከአሜሪካ የተኮረጀ)

Befekadu Hailu

በፈቃዱ ኃይሉ

ይህንን ባለፈው በእንግሊዝኛ ጽፌው «በአማርኛ እና በኦሮምኛ ብትተረጉመው ጥሩ ነው» ተብዬ ነበር። በአማርኛ ይኸው፤ አፋን ኦሮሞ የምትችሉ ተርጉሙት።

ጋዜጠኛ ‪#‎እስክንድር_ነጋ‬ ነበር የዛሬ ሁለት ዓመት ገደማ ልጠይቀው ቃሊቲ እስር ቤት ስሄድ ኮኢንቴልፕሮ (COINTELPRO) ስለሚባለው ነገር መጀመሪያ የነገረኝ። ቃሉ የአሜሪካ ፌዴራል ምርመራ ቢሮ (ኤፍቢአይ) ካውንተር ኢንተሊጀንስ ፕሮግራም ባጭሩ ሲጻፍ የተፈጠረ ነው። ፕሮግራሙ ድብቅ፣ አንዳንዴ ሕገ ወጥ፣ የአገር ውስጥ የፖለቲካ ድርጅቶችን የመሰለል፣ ውስጣቸው ሰርጎ የመግባት፣ ተአማኒነት የማሳጣት እና የማስተጓጎል ተከታታይ ፕሮግራም ነው። ይህንን ጉዳይ አሁን ማንሳት ያስፈለገኝ ሰማያዊ ፓርቲ፣ እንደብዙዎቹ ከጨዋታ ውጪ እንደተደረጉ ፓርቲዎች በፈተና ውስጥ እያለፈ በመሆኑና ይህም የተቀናጀ ሴራ ውጤት ሊሆን ይችላል ብዬ መጠርጠሬ ነው።

«ማጋለጥ፣ ማስተጓጎል፣ ተአማኒነት ማሳጣት፣ ዝም ማሰኘት አሊያም ማጥፋት» ~ በወቅቱ የኤፍቢአይ ዳይሬክተር – ኤድጋር ሁቨር ለአንድ የኤፍቢአይ ኤጀንት የተሰጠ ትዕዛዝ ነው።
በዚህ መንገድ፣ ኤፍቢአይ በከፊልም ቢሆን የጥቁሮች የዕኩል መብት ጥያቄን፣ የፀረ-ቪየትናም ጦርነት እንቅስቃሴን እና ፀረ-ቅኝ ግዛት ድርጅቶችን አዳክሟል። በማልኮም ኤክስ እና በኤልያስ መሐመድ መካከል ያለውን አለመግባባት ኤፍቢአይ ማልኮም እንዲገደል በማድረግ ፕሮግራሙን ተጠቅሞበታል የሚሉ አሉ፤ ባይጠቀምበት እንኳ መረጃው እየደረሰው ዝም ብሏል።

በተመራማሪዎች እንደተሰበሰው ከሆነ፣ ኮኢንቴልፕሮ በመንግሥት ያልተፈለጉ እንቅስቃሴዎችን እና ድርጅቶችን የሚያስተጓጉልበት የተለያዩ ተግባራት (functions) እና ቅርፆች (forms) አሉት። ዴቪድ ካኒንንግሃም የዘረዘሩትን እነሆ፣
ተግባራት፣
1) መጥፎ ገፅታ መስጠት፤
2) ውስጣዊ አደረጃጀትን መሰባበር፤
3) በቡድኖች መካከል የርስበርስ ቅራኔ መፍጠር፤
4) ቡድኑ ለእንቅስቃሴው የሚረዱት ነገሮችን እንዳያገኝ መገደብ፤
5) የመቃወም አቅምን መገደብ፤
6) የተመረጡ ግለሰቦች እንቅስቃሴውን እንዳይቀላቀሉ ማድረግ፤
7) ግጭቶችን ማስቀየስ፤ እና
8) ስለላ ናቸው።
ቅርፆች
A) ምንጫቸው ያልታወቁ ደብዳቤዎች መላክ፤
B) በውሸት ማሕተም የተፈረመባቸውን ደብዳቤዎች መላክ፤
C) መጣጥፎችን ለብዙኃን መላክ፤
D) ለባለሥልጣናት መረጃ መስጠት፤
E) የውሸት ማስረጃ መቅበር፤
F) መረጃ ሰጪዎች መመልመል፤
G) ሚዲያዎችን መጠቀም፤
H) ኤፍቢአይ ያዘጋጃቸውን መረጃዎች ማሰራጨት፤
I) ለተመረጡ ሰዎች ቃለመጠይቅ ማድረግ፤
J) የተሳሳተ መረጃ መስጠት፤
K) የውሸት የስልክ ጥሪዎችን ማድረግ፤
L) ያለማቋረጥ ክትትልና ጥቃት ማድረግ፤
M) ለተቀናቃኞቻቸው ድጋፍ መስጠት፤ እና
N) ሥም አጥፊ መረጃዎችን መላክ።

(እነዚህ ሁሉ ተቃዋሚዎችን የማስተጓጎል ሙከራዎች በኢትዮጵያ ታይተዋል።)
የዚህ አጭር ማስታወሻ ዓላማ ዴሞክራሲያዊ የሆኑት አገሮች ሳይቀሩ ምን ያህል ተቀናቃኞቻቸውን ለማጥፋት እንደሚጓዙ ማስረዳት ነው። ኮኢንቴልፕሮ ከኤፕሪል 1971 ጀምሮ፣ በተግባር 15 ዓመት ከቆየ በኋላ፣ በይፋ ተዘግቷል። ነገር ግን፣ እንደኢትዮጵያ ላሉት ጨቋኝ መንግሥታት ትምህርት ሰጥቶ አልፏል። የፖለቲካ ፓርቲዎች እና አክቲቪስቶች መንግሥታቸው እነዚህን ሴራዎች እንደሚሸርብባቸው አውቀው ግብረመልስ ካዘጋጁ [ብቻ] በትግሉ ያሸንፋሉ።

ቃና ቴሌቭዥን-በይ ደስም አላልሽኝ

ሀብታሙ ስዩም

እና ባጭሩ የምትሉኝ በሃገሪቱ የሚሰሩ ፊልሞች ጥራት እና የታሪክ ፍሰት እምብዛም ስላልሆነ የቱርክ ፊልም እያየን እንቆይ ነው? በይ ደስም አላልሽኝ አለ ሙዚቀኛው፡፡የሀገራችን ፊልሞችና ድራማዎች ጥራትና ብቃት ከፍ እንዲል ሺ ዓመት የለፋን እንመስላለን አነጋገራችን፡፡ወገኖቼ በአስር ወር የፊልም ትምህርት ቤት የተማርኩት የመጀመሪያው ነገር የኛ ሀገር ፊልም ለውዝግብ መብቃቱ ራሱ ታላቅ ስኬቱ መሆኑን ነው፡፡

Kana TV

የፊልም ዕቃዎችን ለማስገባት ያለውን ጣጣ፣ጥበቡን የሚደግፍ ሁነኛ የመንግስት አካል ዕጦት፣ የትምህርትና ስልጠና ተቋማት እጥረት ፤ታሪኮች የተገደቡ እንዲሆኑ የሚደረገው የእጅ አዙር ጫና ፣ሲኒማ ቤቶችን ከሚያስተዳድሩት ግልገል መንግስቱ ሃይለማሪያሞች ጋር ሁሌ የሚላተመው የኛ ፊልም የራሱን ተመልካቾች መፍጠሩ አፈር ህይወትን ፈጠረ እንደሚለው እሳቤ እጅግ የሚገርም ነው፡፡እንዲህ እየሆነ የብዙሃን የእንጀራ ቤት የሆነውን ዘውግ በአንድም ሆነ በሌላው የሚጓዳ አሰራርና ትግበራ ለኔ ምኑም አይስማማኝም፡፡

በዕቁብና በቤተሰብ ብድር ከተሰሩ ፊልሞች ውስጥ የሚገርሙ ተዋናያንን፣ተስፋ ያላቸው የቴክኒክ ባለሙያዎችን፣ መንገድ ላይ ስናያቸው ፈገግታችንን የሚያገዝፉ አዘጋጆች ተፈጥረው መገኘታቸው ሁሉ ለኔ እጡብ ነው፡፡በኢንተርናሽናል ደረጃም ሆነ በሀገር ቤት አምራቾች የተሰሩ ፊልሞችን አሰራርና ሂደት ለመታዘብ ዕድሉ ነበረኝ፡፡ጎበዛዝስት የፊልም ሰሪዎቻችን ሄሎሄ በታዘብክ ቁጥር ጉዳዩ እን የሚሊየን ብር ፊልምን በሁለት ብር እስኪርቢቶ( በትችት) ድራሹን አጥፍቶ ዞር በማለት የሚጠገን ነገር አላገኘሁበትም፡፡

ከዓመታት መውደቅ መነሳት በኃላ ቴሌቭዥኖቻችንም የአማረኛ ፈልሞችና ድራማዎችን ሀገራዊ ተፈላጊነት በማየት ከሰዓታቸው ሙዳ ሙዳውን ማከፈል ጀመሩ፡፡ይሄ ጅማሮ ደራሲያን ፣ተዋናያን የቴክኒክ ባለሙያዎች በገቢ የሚያድጉበትን ዕድል አስፍቶ ባልበላ ጎናቸው ያሳዩትን መፍጨርጨር በበላ ሆዳቸው አሳድገው እንደሚመጡ ተስፋ ሆኖኝ ነበር፡፡ይሄን መሰል ጥረታቸውን ተጨማሪ ዕድል በመስጠት እኒህ ወገኖች ለተጨማሪ ሰዎች የመንፈስም ሆነ የስጋ ጥግ እንዲሆኑ መጣር አስፈላጊም ነበር፡፡አሁን እንደሰማሁት ግን ለምዕታ ዐመት ተለፍቶበት እንዳልተወጠ ጉዳይ ‹‹ የሀገራችን ፊልም ጉዳይ በቅቶናል›› ተብሎ የቱርክና የቴሌሙንዶ ሀብታሞችን ግዛተ አጤ በሀገሬ ፊልመኞች ጉሮሮ ላይ መትከል በእጅጉ ያልታሰበበት የወጠጤ ነጋዴ ሀሳብ ሆኖብኛል፡፡

ፊልመኞቻችን ችግር የለባቸውም የሚል ክርክር አልወጣኝም፡፡አሁን ያለው የፊልመኞቻችን ችግር በጊዜ ውስጥ በባለሙያዎች መካከል በሚደረግ ውድድር እና የተማሩ ፊልም ሰሪዎች እየበዛ መምጣት ፤ሀገሪቱ በፊልም ስራ ዙሪያ የያዘቻቸው የእጅ አዙር ገደቦችና መሰናክሎች ሲከስሙ የሚቀረፍ ነው፡፡
እንኳን የኛ ሀገር ፊልም ይቅርና ሆሊውድ እንኳ አንዳንዴ እህል ውሃ የማይሉ ፊልሞች ይሰራሉ፡፡ነገር ግን ውሃ ስለጠማን እሳት እንሙቅ አይነት ውሳኔ በዚያ ሀገር የተለመደ አይደለም፡፡

የቱርክ ፊልሞችን ለናሙና ማየት ችግር የለውም፡፡ይሄን በሚያክል ምጥጥን ሰዐታቱን መሙላት ግን ለኔ መንስኤው ግልጽ ያልሆነ የስድ ውሳኔ ነው፡፡ደሞ እናውራ ከተባለ ፊልሞችን አስተርጉሞ የማሳየት ዕቅድ የሌሎችን ሀገራት ፊልሞች ለሀገራችን ተመልካች ከማቃመስ መልካም እሳቤ ብቻ የሚነሳ አይደለም፡፡ከሀገራቱ ኤምባሲዎች፣የሀገራቱን ልዕልና ለማጉላት ከሚሰሩ ድርጅቶች የሚገኘውን ፈንድና ጥቅማጥቅም ከመጠቅለል ፍላጎት የሚነሳ የትርፍ ጥረትም ነው፡፡

ከምንም በተጀመረ ጥበብ ውስጥ ሞካሪ እስካለ ድረስ የሚሞክረውን ሰው እስትንፋስ ለማርዘም ማናቸውም ከለላዎች መደረግ አለባቸው፡፡ቢያንስ ያ ሰው ኢትዮጵያዊ ነው፡፡ያ ሰው የእኔና የአንተን ቋንቋ ተጠቅሞ በዓለም ውስጥ ትንሽም ቢሆን ዐይንና ጆሮ እንድናገኝ እየለፋ ያለ ሰው ነው፡፡ፊልም እና ሙዚቃ የእንጀራ ጉዳይ ብቻም አይደሉም ዐለምን በእጃዙር የምታማልልበትና የሀገርህን እሳቤ በሌላ ዐለም ላይ የምትጭንባቸው ህመም አልባ መሳሪያዎች ናቸው፡፡አሜሪካ የዓለምን ልብ ያስከፈተችው በኒኩሌር ይመስልሃል፡፡እኔና አንተ አሜሪካ ሳንረግጣት ያወቅናት የጠንቋይ ዘር ስለሆን ይመስልሃል? ጥበበኞቿን ይዛ አሜሪካዊነት የተጠቀጠባቸው ሁነኛ ፊልሞችን በማስንጨፍ ነው፡፡እና ለቱርክ ፊልም ይሄን ሁሉ ጊዜ መስጠት ሀሊት እና ሀዛል ሲላቀሱ ከማየት ወዲያ የማይዘል የሞራል ልዕልናን የመጫን እርሾ የሌለበት ይመስልሃል?

ለማንኛውም ፊልሞቻችን እንከነ ብዙ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡የአንዳንድ ፊልም ሰሪዎች የዕውቀት ማነስን ሰበብ አድርጎ በማንሰራራት ላይ ያለውን ጥበብ በብላሽነት መጠቅለል የማይገናኝ አመክኒዮ ነው፡፡ስላበሳጩን ሳይሆን ስላስገረሙን የፊልም ታጋዮች ክብር ውሳኔያችንን ማጤን ግድ ይላል፡፡ ምንም ይሁኑ ምንም እንድናያቸው ጉጉት የተውልን መልካም ውጥኖችም ናቸው፡፡ለመራመድ እዳለመ – ነገር ግን እንደሚወድቅ እንደሚነሳ ልጅ እየተከተልን እየደጋገፍን እራሱን ችሎ እንዲቆም ማብቃት ይኖርብናል እንጂ እንደሞተ ሁሉ ገሸሽ አድርገነው በጉዲፈቻ ሌላ ጠብደል ከእልፍኝ ማስገባቱ ዘረሰናይ ብርሃነ ማሪያምን የሚያክል የዓለም ፊልሞችና ቴሌቭዥን የጀርባ ውስጠ ባህሪ ይገባቸዋል ከሚባሉ ሰዎች የሚጠበቅ አይደለም፡፡
ቀድሞ ነገር የጣቢያው ዓላማ የሶስተኛ ዓለም ሚዲያዎች ሊኖራቸው የሚገባውን እና ህዝቡ በድህነቱና በአለማወቁ ሰበብ የገጠሙትን የኑሮ ትንቀንቆች ድል የሚያደርግበትን መላ መጠቆም አይመስልም፡፡የጣቢያው ዓላማ የየለት ኑሯችንን የሚያፈኩ ከአንጀት ጠብ የሚሉ መሰናዶዎች ማድረስ አይመስልም፡፡ተዝናኑ ነው-በባዶ ሆድ-በባዶ ጭንቅላት ተዝናኑ-አይነት ነው፡፡

አፈር ስሆን ከማብቃቴ በፊት ዘረሰናይ፡፡አንጀሊ ረድታህ የሰራኸው ፊልም ይዘቱን ታስታውሰዋለህ? እየውልህ እሱን እና እሱን መሰል ድሃውን ህዝብ በየለቱ የሚነኩ ችግሮች በተንሰራፉበት ሀገር ነው አንተ ችግሩ ሁሉ ተቀርፎለት የመዝናኛ ያለህ ብሎ እንደለመነህ ሁሉ ለዚህ ህዝብና ሀገር የቱርክና የቴሌሙንዶ ግሳንገስ ይዘህለት የመጣህ፡፡

ከጎበዝ ዳይሬክተርነት ወደ ግደቢስ ነጋዴነት –ይሄ ነው መርመጥመጥ፡፡እንኳን ወደ ማደንዘዙ ዘመቻ በሰላም ተቀላቀልክ፡፡