ፓርላማው የሕዝብና ቤቶች ቆጠራ ኮሚሽን ምክር ቤት አባላትን ሹመት አፀደቀ
• ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሰብሳቢ ሆነዋል
ዮሐንስ አንበርብር

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኔ 14 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ለሕዝብና ቤት ቆጠራ ኮሚሽን ምክር ቤት አባልነት ያቀረቧቸውን 23 ዕጩዎች ሹመት አፀደቀ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 103 ንዑስ አንቀጽ ሁለት እንዲሁም በሕዝብና ቤት ቆጠራ ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 449/97 መሠረት ዕጩ የማቅረብ ሥልጠናቸውን ተጠቅመው ነው ለምክር ቤቱ ዕጩ ተሿሚዎችን ያቀረቡት፡፡
በኮሚሽኑ ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 449 አንቀጽ ስድስት መሠረት የኮሚሽኑ አባላት ለሕዝብ ቆጠራ ጉዳይ አግባብነት ካላቸው የፌዴራል ሚኒስቴር ሚኒስትሮች፣ ከምርጫ ቦርድ፣ ከፌዴሬሽን ምክር ቤት፣ ከዘጠኙ ክልሎች፣ ከአዲስ አበባና ድሬዳዋ መስተዳድሮች የተውጣጡ ይሆናሉ፡፡
በዚህ መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሐረር ክልል ርዕሰ መስተዳድር በስተቀር ሁሉም ክልሎችና የከተማ መስተዳድሮች በምክትል ርዕሰ መስተዳድሮችና በምክትል ከንቲባዎቻቸው የኮሚሽኑ አባል እንዲሆኑ በዕጩነት አቅርበዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሕዝብና ቤት ቆጣራ ጉዳይ አግባብነት ካላቸው የፌዴራል ሚኒስቴር ሚኒስትሮች፣ ከፌዴሬሽን ምክር ቤትና ከምርጫ ቦርድ በሚለው የኮሚሽኑ ማቋቋሚያ አዋጅ መሠረት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ለኮሚሽኑ ምክር ቤት ሰብሳቢነት አጭተዋል፡፡
የተቀሩት የእርሻና የተፈጥሮ ሀብት ሚኒስትሩ አቶ ተፈራ ደርበው፣ የፌዴራልና የአርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስትሩ አቶ ካሳ ተክለብርሃን፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕዝብ ግንኙነት አማካሪ ሚኒስትር አቶ ከበደ ጫኔ፣ የብሔራዊ ፕላን ኮሚሽን አቶ ይናገር ደሴ፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ ያለው አባተ (ብአዴን) ሲሆኑ፣ የገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስትሩ አቶ አብዱላዚዝ መሐመድ፣ የትራንስፖርት ሚኒስትሩ አቶ ወርቅነህ ገበየሁ (ኦሕዴድ)፣ የትምህርት ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ፣ የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ ዶ/ር ከሰተብርሃን አድማሱ (ደኢሕዴን)፣ የመንግሥት ጉዳዮች ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው ረዳ (ሕወሓት) በዕጩነት የቀረቡ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ነጋ ዱፊሳና የማዕከላዊ ስታስቲክስ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ቢራቱ ይገዙ (በጸሐፊነት) በአባልነት ቀርበዋል፡፡
በቀረቡ ዕጩዎች ዙሪያ የመከሩት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የባለፈው የሕዝብና ቤት ቆጠራ ላይ በአማራ ክልልና በአዲስ አበባ የሕዝብ ብዛት ላይ ተፈጥሮ የነበረው ከፍተኛ ስህተት እንዳይደገም አሳስበዋል፡፡
የምክር ቤቱ ሴት ተወካዮች በበኩላቸው ከቀረቡት የኮሚሽኑ ዕጩዎች ውስጥ አንድ ሴት ብቻ በዕጩነት መቅረባቸው አስቆጥቷቸዋል፡፡
‹‹የሴቶች ስብጥር በዚህ ሹመት ላይ መታየት አለበት፡፡ መንግሥት በዚህ ላይ ቁርጠኝነቱን ማሳየት ሲገባው የታየው ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡ ይህ የድርጅታችን ባህል አይደለም፤›› ሲሉ አንድ ሴት ተወካይ ተከራክረዋል፡፡
የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትሩ አቶ አስመላሽ ወልደሥላሴ በሰጡት ምላሽ፣ መንግሥት ከስህተቱ የመማር ልምድ ስላለው በባለፈው ቆጠራ የተከሰተው ችግር እንደማይደገም፣ የሴቶች ስብጥርን በተመለከተ የመንግሥት ቁርጠኝነት እንደሚታወቅና በዚህኛው ላይ አንድ ብቻ መወከላቸው ዕጩ ምልመላው የተካሄደው አዋጁን መሠረት ያደረገ በመሆኑ ነው ብለዋል፡፡
የአቶ አስመላሽ መልስ ለምክር ቤቱ ሴት አባላት አጥጋቢ አልነበረም፡፡ የምክር ቤቱ ምክትል አፈ ጉባዔ ወ/ሮ ሽታዬ ምናለ ‹‹ሴት ብሆንም በዚህ መድረክ ላይ አቋም መያዝ አልችልም፡፡ በተጨማሪም አዋጁን ማሻሻል የሚጠይቅ በመሆኑ ወደ ድምፅ ብንሄድ፤›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ በዚህ መሠረት የኮሚሽን አባላቱ ሹመት በአንድ ተቃውሞ፣ በዘጠኝ ድምፅ ተአቅቦ ፀድቋል፡፡
ሦስተኛው ብሔራዊ የሕዝብና ቤት ቆጠራ በኅዳር ወር 2010 ዓ.ም. ይካሄዳል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ
በኢትዮጵያ የጥራት ጉድለት የተገኘባቸው 69 ሚሊየን ኮንዶሞች ተገኙ
በያዝነው 2008 ዓ.ም. ሁለተኛ አጋማሽ የጥራት ጉድለት የተገኘባቸው 69 ሚሊየን ኮንዶሞች ሊወገዱ ነው።
ከግሎባል ፈንድ በተገኘ ከ2 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር የተገዙት ኮንዶሞች፥ በኢትዮጵያ የምግብ መድሃኒትና ጤና አጠባበቅ ቁጥጥር ባለስልጣን ፍተሻ የጥራት ችግር እንዳለባቸው ተጋግጧል።

ኮንዶሞቹ ከሁለት ወራት በፊት በተደረገ ፍተሻ መያዛቸው ነው የተገለጸው። የመድሃኒት ፈንድና አቅርቦት ኤጀንሲ ዋና ዳይተሬክር አቶ መስቀሌ እንደተናገሩት፥ የኮንዶሞቹ አቅራቢ ድርጅት ለግዢ የወጣውን ገንዘብ እንዲተካ የማድረግ ስራ እየተሰራ ይገኛል።
ኮንዶሞች ለገበያ ከመቅረባቸው በፊት ጥብቅ የጥራት ፍተሻ እንደሚደረግላቸው ያነሱት ዳይሬክተሩ፥ ይህ ስራም ጥራቱ ተረጋግጦ ገበያ ላይ ከዋለ በኋላ በአያያዝ ምክንያት ሊደርስ የሚችል ችግርንም እስከ መፈተሽ ድረስ የሚከናወን ነው ብለዋል ሲል ፋናቢሲ ዘግቧል፡፡
ጥራት የጎደላቸው 69 ሚሊዮን ኮንደሞች በአንድ የህንድ ኩባንያ አማካኝነት በኢትዮጵያ መሰራጨታቸውን በተመለከተ ቀደም ሲል ዋዜማ ሬዲዮ መዘገቡ ይታወሳል፡፡
የተሰራጩት ኮንዶሞች ጫፋቸው የተቀደዱ፣ ፈሳሽ እና አየር ማሳለፍ የሚችሉ፣በላዩ ላይ ያለው ማለስለሻ ቅባት ከሰውነት ፈሳሽ ጋር ሲደባለቅ የጤና ችግር የሚፈጥር እንደሆነ በተደረገ ምርመራ መረጋገጡ ተጠቁሟል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በነበረው ተቃውሞ ከ400 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ሂውማን ራይትስ ዎች ይፋ አደረገ
ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች የሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ከህዳር ወር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በኦሮሚያ ክልል በተካሄዱ የተቃውሞ ሰልፎች የኢትዮጵያ መንግስት የጸጥታ ሀይሎች ከ400 በላይ የሚሆኑ ሰልፈኞችን የገደሉ ሲሆን ከአስር ሺህ በላይ የሚቆጠሩትን ደግሞ ማሰራቸውን አስታውቋል፡፡ የሰብዓዊ መብት ድርጅቱ “የኢትዮጵያ መንግስት የተፈጸሙ ግድያዎችን፣ እስራቶችንና ሌሎች የመብት ጥሰቶች በአስቸኳይ ተአማኒነት ያለውና ገለልተኛ የሆነ ማጣሪያ እንዲካሄድ ድጋፍ ማድረግ አለበት።” ሲል ባለ 61 ገፅ ሪፖርት ይፋ አድርጓል፡፡

ድርጅቱ ሰኔ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጣው ባለ 61 ገጽ ሪፖርት “ጭካኔ የተሞላበት አፈና’ – የግድያ እና የእስራት ምላሽ፤ ለኢትዮጵያ የኦሮሞ ተቃውሞ” የሚል ነበር፡፡ መንግሥትም በነበረው ተቃውሞ ያልተመጣጠነ ርምጃ መውሰዱን በመግለፅ ድርጊቱን አውግዟል፡፡ ሪፖርቱ በሰላማዊ ሰልፈኞች ላይ እንዲሁም ሀሳባቸውን በነጻነት በሚገልጹ ዜጎች ላይ በመንግስት የጸጥታ ሀይሎች የተወሰደውን እርምጃ አስመልክቶ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን፣ ከ125 በላይ የሚሆኑ የተቃውሞ ሰልፎች ተሳታፊዎችን፣ ጉዳዩን በአንክሮ ሲከታተሉ የቆዩ ግለሰቦችን፣ በተለያዩ ጊዜያት የመብት ጥሰት የተካሄደባቸውና ጉዳት የደረሰባቸውን ግለሰቦች ያካተተ ቃለ መጠይቅ ማድረጉንም አስታውቋል፡፡
በመንግሥት የተቋቋም የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮምሽን ይህንን የኦሮሚያ ክልል ተቋውሞ ተከትሎ በተወሰደ ርምጃ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 173 ብቻ መሆናቸውን እና በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተወሰደው ርምጃም “ተገቢና ተመጣጣኝ” ነው ሲሉ ኮሚሽነሩ ዶ/ር አዲሱ ገብረእግዚአብሔር ሰኔ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. “ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት” እና ለጋዜጠኞች ገልፀዋል፡፡ ኮሚሽነሩ ተገቢና ተመጣጣኝ ያሉት ርምጃ የተወሰደው በመከላከያ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ እና በኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል መሆኑንም ለጋዜጠኞች ጠቁመዋል፡፡

መንግሥታዊ ያልሆነው ሀገር በቀል የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሆነው የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ፤ በኦሮሚያ ክልል በነበረው ተቃውሞ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተወሰደው ርምጃ ተገቢና ተመጣጣኝ እንዳልሆነ ቀደም ሲል ይፋ ባደረገው ዝርዝር ሪፖርት ማስታወቁ ይታወሳል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በነበረውን ተቃውሞ የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ፤ ሀገር በቀል የሆነው የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ባለፈው መጋቢት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. በ140ኛው የተቋሙ ሪፖርት “የኦሮሚያ ክልል በ18 ዞኖች እና በ342 ወረዳዎች የተከፋፈለ ሲሆን ሰመጉ ከ9 ዞኖች ውስጥ በ33 ወረዳዎች ብቻ ባደረገው የመስክ ምርመራ ባገኘው ውጤት መሰረት 103 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን 57 ሰዎች በጥይት የመቁሰል እና ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡” ብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተገደሉትና ከቆሰሉት በተጨማሪ በ22 ሰዎች ላይ ማሰቃየት እና ድብደባ መፈፀሙን፣ 84 ሰዎች መታሰራቸውን እንዲሁም 12 ሰዎች የደረሱበት ወይም ያሉበት አለመታወቁንም በመግለፅ ሪፖርቱን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡
ሙሉውን የሂውማን ራይትስ ዎች ሪፖርት እዚህ https://www.hrw.org/news/2016/06/15/ethiopia-protest-crackdown-killed-hundreds ያገኙታል፡፡
የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና በድጋሚ ወደ ሐምሌ 4 ተራዘመ
(አዲስ ሚዲያ) ከሰኔ 27 እስከ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊሰጥ የታሰበው የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና በድጋሚ ተራዘመ፡፡ ትምህርት ሚኒስቴር ባለፈው ግንቦት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ሊሰጥ የነበረው ፈተና መከካከል ሁለት የትምህርት ዓይነቶች ቀድመው በማኀበራዊ ሚዲያ ከነመልሶቻቸው መለቀቃቸውን ተከትሎ እንዲቋረጥ የተደረገው ፈተና ከሰኔ 27 እስከ 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ለመስጠት ትምህርት ሚኒስቴር መርሃ ግብሩን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ከተለያዩ አካላት ቅሬታና ተቃውሞ አስከትሎ ነበር ፡፡

በተለይ ከሰኔ 27-30 ቀን 2008 ዓ.ም. መካከል የረመዳን ፆም ፍቺ በዓል ላይ የሚውል ተቃውሞ በመቅረቡ፣ ትምህርት ሚኒስቴርም ከኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ቅሬታ በመቅረቡ ፈተናው በአንድ ሳምንት ተራዝሞ ከሐምሌ 4-7 ቀን 2008 ዓ.ም. እንደሚሰጥ አስታውቋል ፡፡
ቀደም ሲል ግንቦት ሊሰጥ የታሰበውን መርሃ ግብር እንዲቀየር ያስገደዱት የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎችም ከሐምሌ 4 እስከ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. በሚሰጠው አዲሱ መርሃ ግብር ላይ ሌላ ተቃውሞ እንደማያስነሱና ከባለስልጣናቱ ጋር እልህ መጋባቱ አላስፈላጊ መሆኑን በመጥቀስ፣ ተማሪዎች ከሐምሌ 4 እስከ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. የሚሰጠውን የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና ተረጋግተው እንዲፈተኑ ጠይቀዋል፡፡
ትምህርት ሚኒስቴር እና የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች በየበኩላቸው በየአካባቢው ያሉ መምህራን፣ ወላጆች፣ አስተዳደሮች እና ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት አስፈላጊውን ድጋፍ ለተማሪዎች እንዲያደርጉላቸው የትብብር ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል ዳግም ግጭት ተከሰተ
(አዲስ ሚዲያ)እሁድ ሰኔ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. በኢትዮጵያ እና በኤርትራ ድንበር መካከል ዳግም ግጭት ተቀሰቀሰ፡፡ ግጭቱ የተቀሰቀሰው በሁለቱም ሀገራት ድንበር አካባቢ በሚገኘው ፆረና ግንባር ሲሆን፤ ዘግይተውም ቢሆን ሁለቱም ሀገራት ግጭት መኖሩን በሰጡት መግለጫ አረጋግጠዋል፡፡ ግጭቱን በተመለከተ ቀደም ብሎ መግለጫ የሰጠው የኤርትራ መንግሥት ማስታወቂያ ሚኒስቴር “የህወሓት አገዛዝ በፆረና ማዕከላዊ ግንባር ጥቃት ሰንዝሮብኛል፣ አጠቃላይ ዝርዝር መረጃውን በሚመለከት ይፋ እናደርጋለን” ሲል መግለጫ ሰጥቷል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት በበኩሉ “የኤርትራ መንግሥት በፆረና በኩል ትንኮሳ ሲጀምር የአፀፋ ርምጃ ወስደናል፣ ትንኮሳውንም ካላቆመ ተመጣጣኝ ርምጃ መውሰዱን እንቀጥላለን” ማለቱን አስታውቋል፡፡

ይህ እስከተዘገበበት ድረስ ለእሁዱ ግጭት መከሰት ዋነኛ ምክንያት እና በሁለቱም በኩል ስለደረሰ ጉዳት መንግሥታዊ ይፋ የሆነ ማብራሪም ሆነ መግለጫ የለም፡፡ ይሁን እንጂ እንደ ኤርትራ ፕሬስ ከሆነ፤ የኤርትራ ሰራዊት ሰኞ ጠዋት በወሰደው የመልሶ ማጥቃት ከባድ ውጊያ በደቡብ ፆረና ኩዱ ሃዋይ ወታየኢትዮጵን ድንበር ጥሶ በመግባት 52 ወታደሮች መማረካቸውን ዘግቧል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ በበኩላቸው በተከሰተው ግጭት የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ ወደፊት እንደሚገልፁ ለዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን አስታውቀዋል፡፡ ሚኒስትሩ በጉዳዩ ዙሪያ ዛሬ ለሀገር ውስጥ ጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ “የአገር መከላከያ ሰራዊት የወቅቱን ትንኮሳ ታሳቢ በማድረግ ባለፉት ሁለት ቀናት የኤርትራን መንግስት ለታላቅ ኪሳራ የሚዳርግና ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ ላደረገው ትንኮሳ መልስ የሚሆን እርምጃ ወስዷል” ብለዋል።
በሁለቱም ሀገራት ድንበር መካከል የተከሰተውም ግጭት ትናንት ከሰዓት በኋላ መቆሙን የኢትዮጵያ መንግሥት እንዳስታወቀ ሀገር ሸገር ኤፍ ኤም በቀትር ዜና እወጃው ዘግቧል፡፡
በተለይ በሁለቱም ሀገራት መካከል በ1990/91ዓ.ም. ከተደረገው ጦርነት ጀምሮ በድንበር አካባቢ “ሰላምና ጦርነት አልባ” ስጋት እንዳንዣበበ ይታወቃል፡፡