Category Archives: News

ጋዜጠኞቹ እና የዞን 9 ብሎገሮቹ ለጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ተጠየቀባቸው

  • ኤዶምና ማህሌት የመብት ጥሰት እንደተፈጸመባቸው ቅሬታ አቅርበዋል

የዞን 9 ብሎገሮቹና ሶስቱ ጋዜጠኞች ያቀረቡት መቃወሚያ ‹‹ተቀባይነት የለውም›› ተብሎ ለጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ተቀጠረባቸው፡፡ ጦማሪያኑና ጋዜጠኞቹ የተከፈተባቸው ክስ አግባብ አለመሆኑን የሚገልጽ ስምንት ገጽ የክስ መቃወሚያ አቅርበው የነበረ ቢሆንም አቃቢ ህግ ‹‹ክሱ ምንም ችግር የለበትም፣ የሚሻሻል ነገር የለውም፡፡›› በሚል መቃወሚያውን ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡

zone9 & journalismቃሊቲ እስር ቤት ታስረው የሚገኙት ኤዶም ካሳዬና ማህሌት ፋንታሁን ማረሚያ ቤቱ ውስጥ የመብት ጥሰት እንደሚፈጸምባቸው ቅሬታቸውን አቅርበዋል፡፡ ሁለቱ ታሳሪዎች በፍርድ ሂደት ላይ ያሉ ቢሆንም እስር ቤቱ ውስጥ ‹‹አሸባሪ›› የሚል ስም እንደሚሰጣቸው ቅሬታ ያቀረቡ ሲሆን ከዚህም በተጨማሪ ‹‹ቤተሰብ ብቻ ነው የሚጠይቀን፡፡ ከቤተሰብ ውስጥም የምንጠየቅው ስማቸውን ባስመዘገቡት ብቻ ነው፡፡ ያም ሆኖ የምንጠየቀው ለ10 ደቂቃ ነው፡፡ ለመጠየቅ የሚመጡ ቤተሰቦቻችንም ድብደባ ይፈጸምባቸዋል፡፡›› በሚል ቅሬታቸውን አቅርበዋል፡፡

ባለፈው ችሎቱ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ኃላፊ ታሳሪዎቹ ይደርስብናል በሚሉት በደል ዙሪያ ለዛሬ ቀርበው እንዲያስረዱ ተጠይቀው የነበር ቢሆንም ሳይቀርቡ ቀርተዋል፡፡ ዛሬ ያልተገኙት የማረሚያ ቤቱ ኃላፊ ለጥቅምት 25/2007 ዓ.ም ቀርበው ያስረዳሉ ተብሎ የነበር ቢሆንም ኤዶምና ማህሌት ‹‹ይህ የመብት ጉዳይ ስለሆነ አጭር ቀጠሮ ሊሰጥልን ይገባል፡፡›› በማለታቸው ማረሚያ ቤቱ ውስጥ እየተፈጸመብን ነው ያሉትን በደል ብቻ ለማየት ጥቅምት 11 ቀን 2007 ዓ.ም.ቀነ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡ የማረሚያ ቤት ኃላፊው ቀርበው ያስረዳሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ኤዶምና ማህሌት ለዋናው ክስም ጥቅምት 25 ደግመው ይቀርባሉ፡፡

በዛሬው ችሎት የታሰሪዎቹ ቤተሰቦች፣ የአገር ውስጥና የውጭ ጋዜጠኞች፣ የኤምባሲና የተቋማት ተወካዮችን ጨምሮ በርከት ያለ ታደሚ ተገኝቶ ተከታትሏል፡፡ ጥቅምት 25 ቀን 2007 ዓ.ም አቃቢ ህግ ያቀረበው ክስና ጦማሪያኑና ጋዜጠኞቹ ያቀረቡት የክስ መቃወሚያ ላይ ምርመራ ተደርጎ ሌላ የፍርድ ሂደት ይጀመራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ምንጭ፡- ነገረ-ኢትዮጵያ ጋዜጣ

በቅርቡ የተሰደደው ጋዜጠኛ ሚሊዮን ሹሩቤ ህይወቱ አለፈ

 

milion shurbieየማራኪ መፅሔት ባለቤት እና ማኔጂንግ ዳይሬክተር የነበረው ጋዜጠኛ ሚሊዮን ሹሩቤ በስደት በሚገኝበት ናይሮቢ ኬኒያ ጥቅምት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. በድንገት ህይወቱ ማለፉን ከማኀበራዊ ገፆች የተገኙ መረጃች እና ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት በጅምላ ያደረገውን የመፅሔቶች እና ጋዜጣ ክስ እና የበርካታ ጋዜጠኞችን እና ብሎገሮችን እስርን ፍርሃት ተከትሎ በቅርቡ ከተሰደዱ ጋዜጠኞች መካከል ጋዜጠኛ ሚሊዮን ሹሩቤ አንዱ ነበር፡፡

ጋዜጠኛው በስደት ኬኒያ ከሚገኝበት አንድ ናይሮቢ ሆስፒታል በህክምና ሲረዳ ቢቆይም ህይወቱን ማትረፍ እንዳልተቻለ ታውቋል፡፡ ጋዜጠኛው ከኢትዮጵያ ከተሰደደ ገና ሁለት ወር እንኳ እንዳልሞላው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ጋዜጠኛው ህይወቱ እስካለፈበት ድረስ በኢትዮጵያ ነፃ ፕሬስ ውስጥ ከ12 ዓመታት በላይ  እንዳገለገለና የድርሰት ስራም እንዳለው ተጠቁሟል፡፡

ጋዜጠኛ ሚሊዮን በተወለደ በ33 ዓመቱ በስደት ናይሮቢ ኬንያታ ናሽናል ሆስፒታል ቢያርፍም፤የቀብር ስነስርዓቱ እሁድ ጥቅምት 9 ቀን 2007 ዓ.ም. በትውልድ አካባቢው ይርጋ ጨፌ ከተማ ቅድስት ኪዳነ ምህረት ቤተ ክርስቲያን ተፈፅሟል፡፡ ጋዜጠኛው የአንድ ወንድ ልጅ አባት ነበር፡፡

አዲስ ሚዲያም በጋዜጠኛው ሞት የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን እየገለፀ፤ ለጋዜጠኛ ሚሊዮን ፈጣሪ ነፍሱን በገነት እንዲያኖር፤ ለቤተሰቦቹ፣ለወዳጅ ዘመዶቹና አድናቂዎቹ መፅናናትን ይመኛል፡፡

maraki magazine

ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው በገዛ ፍቃዳቸው ሥልጣናቸውን ሲለቁ፤ አቶ በላይ ፍቃዱ ቀጣዩ ፕሬዘዳንት በመሆን ተመርጠዋል

gizየአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ብሔራዊ  ምክር ቤት ዛሬ ጥቅምት 2 ቀን 2007 ዓ.ም. በነበረው ስብሰባ ፕሬዚዳንቱ ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው ሪፖርት ካቀረቡ በኋላ፤ ከውስጥና ከውጭ በተፈጠሩ አንዳንድ የማያሰሩ ችግሮች፣ ካለባቸው የሥራ ጫና እና ፓርቲው ወደፊት አንድነቱን ጠብቆ ለ2007 ምርጫ አሸናፊ ሆኖ እንዲወጣ በማሰብ ስልጣናቸውን በቃዳቸው መልቀቃቸውን ይፋ ማድረጋቸው ተጠቁሟል፡፡
ምክር ቤቱም በፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ መሰረት የፕሬዘዳንቱን ጥያቄ በአድናቆት ተቀብሎ፤ ፓርቲውን በፕሬዘዳንትነት በመምራት መጪውን ምርጫ ውጤታማ ለማድረግ እንዲያስችል 1ኛ. አቶ በላይ ፈቃዱ፣2ኛ. አቶ ደረጀ ኃይሉ እና 3ኛ. አቶ ትዕግስቱ አወሉን በዕጩነት በማቅረብ፤አቶ በላይ ፈቃዱን በፕሬዘዳንት መርጧል፡፡ ምርጫውም በምስጢር ድምፅ አሰጣጥ እዛው በፓርቲው ምክር ቤት የተከናወነ ሲሆን፤በመጨረሻም አቶ በላይ ፈቃዱ በከፍተኛ ድምፅ ማሸነፋቸው መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

ከምርጫው ውጤት በኋላ አቶ በላይ በቀጣይ የስልጣን ጊዜያቸው ፓርቲውን ለመምራት ቃለ መሐላ የፈፀሙ መሆናቸውን የፍኖተ ነፃነት ዘገባ ያስረዳል፡፡ አቶ በላይ ጠንካራ የፖለቲካ  ልምድና ተሳትፎ ካላቸው የፓርቲው ወጣት አመራሮች መካከል በውጤታማነት ከሚጠቀሱት አንዱ እንደሆኑ የተጠቆመ ሲሆን፤የትምህርት ደረጃቸውም በስታስቲክስ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የመጀመሪያ ድግሪ (BSc) እና በኢኮኖሚ ፖሊሲ አናሊስስ የማስተርስ ድግሪ (MSc) ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ያላቸው ሲሆን፤ በስራ ልምዳቸውም በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አገልግለዋል፡፡ አቶ በላይ ወደ ፓርቲው ፕሬዘዳንትነት ከመምጣታቸው በፊት፤ በራሳቸው የጥናትና ምርምር ድርጅት በማኔጂንግ ዳይሬክተርነት ያገለግሉ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡

belayፓርቲው መጪውን 2007 ዓ.ም. ምርጫ እንዲያሸንፍ ትልቅ ሚና ይኖራቸዋል በሚል ከአባላትና ከደጋፊዎች ትልቅ ተስፋ እንደተጣለባቸውና ኃላፊነታቸውንም በስኬት ሊወጡ እንደሚችሉ ተገምቷል፡፡

 

 

የዓለም ባንክ በቅርቡ ለኢትዮጵያ የሰጠው 600 ሚሊዮን ዶላር የገባበት አልታወቀም

በቅርቡ የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ 4ኛ ዙር የሴፍቲኔት መርሃ ግብር የሚውል 600 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር የሰጠው ብድር እስካሁን የገባበት አለመታወቁ ተሰማ፡፡ በተለይ የዓለም ባንክ ቦርድ ዋና ዳይሬክተሩ እ.አ.አ. መስከረም 30 ቀን 2014 ዓ.ም. የባንኩ ዓለም አቀፍ የልማት ማኀበር (IDA) ለኢትዮጵያ መንግስት ብድሩን መስጠቱን እና ሀገሪቱም በተፈቀደው ብድር ተጠቃሚ መሆኗን አረጋግጧል፡፡ ባንኩ ብድሩን የሰጠው 4ኛው ዙር የሴፍቲኔት መርሃ ግብር ውጤታማ ለማድረግ በሚል ሲሆን፤ ይህም በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ለሚኖሩ የሴፍቲኔትን ለማዳረስ፣ድርቅን ለመቋቋም የሚደረግ ስርዓትን ለማገዝ፣ የምግብ ዋስትና ላልተረጋገጠላቸው እና የገቢ መጠናቸው አነስተኛ የሆኑ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ታስቦ መሆኑን በመግለፅ፤ ባንኩ በቅርቡ እ.አ.አ መስከረም 30 ቀን 2014 ዓ.ም. በድህረ-ገፁ ላይ አስነብቧል፡፡

worldbank agreementባንኩ የሰጠውን ብድር አስመለክቶ የዓለም ባንክ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ዧንግ ዠ ቺን ቀደም ሲል በሀገሪቱ ይተገበር የነበረው የሴፍቲ ኔት መርሃ ግብር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና ዓለም አቀፉን የሚሊኒየሙን የልማት ግብ ለማገዝ ከሚደረገው ጥረት ውጭ የተራቆተ መሬትን መልሶ ማቋቋም አብሮ ተግባራዊ አለመደረጉን ገልፀዋል፡፡ ዳይሬክተሩ አሁን የተሰጠው 600 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር 10 ሚሊዮን የሚሆኑ የገጠር ነዋሪዎችን ተደራሽ በማድረግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ጎን ለጎን የተራቆተ መሬትን መልሶ ለማቋቋምም ታሳቢ መደረጉን ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት ጠቅላይ ሚኒስቴር አቶ ኃይለማርም ደሳለኝ ባለፈው ግንቦት 20 ቀን 2006 ዓ.ም. የኢህአዴግን 23ኛ ዓመት የድል በዓል አስመልክቶ ባደረጉት ንግግር ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናዋን አረጋግጣለች ሲሉ መናገራቸው አይዘነጋም፡፡ ይሁን እንጂ በአሁን ወቅት ከ10 ሚሊዮን የማያንሱ ኢትዮጵውን የምግብ ዋስትና ችግር ስለገጠማቸው ራሱ የኢትዮጵያ መንግስት በጠየቀው መሰረት የዓለም ባንክ የምግብ ዋስትናን ችግር ለመቅረፍ እንዲያግዝ የ600 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ብድር መሰጠቱን ባንኩ ይፋ አድርጓል፡፡

ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ መንግስት ገንዘብና ብድርን የሚመለከት ስምምነቶች በቀጥታ የሚመለከተው የገንዘብ፣ ኢኮኖሚና ልማት ሚኒስቴር የዓለም ባንክ የሰጠውን ብድር አስመልክቶ ለቀረበለት ጥያቄ ፤እንደማንኛውም ሰው ከሀገር ውስጥ ከዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ከመስማት ባለፈ የዓለም ባንክ ስለሰጠው የ600 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ብድር መንግስት የሚያውቀው ነገር እንደሌለ መናገሩን ድሬ ቲዩብ አስነብቧል፡፡ ይህ እስከተዘገበ ድረስ ባለፈው ወር መስከረም መጨረሻ 2007 ዓ.ም. የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ የሰጠው 600 ሚሊዮን ዶላር ብድር እስካሁን ያለበት አልታወቅም፡፡

የኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በአምስት ሺህ ብር ዋስ መለቀቁ ተሰማ

 

ቀደም ሲል መስከረም 23 ቀን 2007 ዓ.ም. ለምሳ ሲወጡ ቢሯቸው ታሽጎ ሰኞ መስከረም 26 ቀን 2007 ዓ.ም. የተከፈተው እና ለሰባት ሳምንታት ህትመቷ የተቋረጠው የኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጌታቸው ወርቁ በፌደራል የወንጀል ምርመራ ማዕከል ማዕከላዊ ፖሊስ ቃሉን እንዲሰጥ በተደረገለት ጥሪ መሰረት ማክሰኞ መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ማዕከላዊ መቅረቡ ታውቋል፡፡ ጋዜጠኛው ማዕከላዊ የተጠራው የቀድሞው መኢአድ አመራር የነበረው አቶ ማሙሸት አማረ ክስ መሰረት ቃሉን እንዲሰጥ የነበረ ቢሆንም፤ ማዕከላዊ ምርመራ ክፍልም የጋዜጠኛውን ቃል ከተቀበለ በኋላ ጉዳዩ አስፈላጊ ሲሆን እንደሚቀርብ በመጠቆም በ5,000.00 (አምስት ሺህ ) ብር ዋስ መለቀቁ ተጠቁሟል፡፡

Getachew workuኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ መንግስት በጋዜጠኞች፣ በመፅሔቶች እና ጋዜጦች ላይ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የሚወነጅል ዘጋቢ ፊልም በተደጋጋሚ መስራቱን ተከትሎ አታሚ ቤቶች የነፃ ጋዜጦችን እና መፅሔቶችን እንዳያትሙ በተለያዩ የመንግስት አካላት ጫና በማሳደሩ ለ7 ሳምንታት ከህትመት መቋረጧን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የጋዜጣው አዘጋጆች በተደጋጋሚ ስራውን አጠናቀው ቀድም ሲል የሚያትምላቸው አታሚ ድርጅትና ሌሎች አታሚዎች ጋር በተደጋጋሚ ቢኬድም እስካሁን ለማተም ፈቃደኛ እንዳልሆኑ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ መንግስት የነፃ መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞችን፣ ጋዜጦችን እና መፅሔቶችን በተደጋጋሚ መወንጀሉ እና መክሰሱን ተከትሎ የተለያዩ በርካታ ነፃ ጋዜጦችና መፅሔቶች ከህትምት እና አንባቢ ውጭ እንዲሆኑ መደረጉ ይታወቃል፡፡ ይህንንም ተከትሎ ከሚያዝያ 2006 ዓ.ም.  እስከ ነሐሴ 2006 ዓ.ም. መጨረሻ ድረስ ከ25 ያላነሱ የነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞች የግፍ እስርና ስቃዩን በመሸሽ መሰደዳቸው ይታወቃል፡፡ በአሁን ወቅት ኢትዮጵያ ውስጥ 3 የውጭ ዜጎችን ጨምሮ ከ17 ያላነሱ ጋዜጠኞች እና ብሎገሮች በግፍ ታስረው ይገኛሉ፡፡