የሰኔ 15 ቀን ጥቃት ሰለባ አመራሮች የቀብር ስነ ሥርዓት ተፈፀም

(ዳጉሚዲያ) ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በባህርዳር እና አዲስ አበባ በተፈፀሙ ጥቃቶች ሰለባ የሆኑ ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች መካከል የአማራ ክልል ፕሬዘዳንት ዶ/ር አምባቸው መኮንን፥ የክልሉ አደረጃጀት ዘርፍ አማካሪ አቶ እዘዝ ዋሴ እንዲሁም በአዲሴ አበባ የመከላከያ ሰራዊት ጠቅላይ ኢታማዡር ሹም የነበሩት ጀነራል ሰዓረ መኮንን እና ከአንድ ዓመት በፊት በጡረታ የተሰናበቱት ሜጀር ጀነራል ገዛዒ አበራ በዕለቱ ተገድለዋል። በዕለቱ በአማራ ክልል በደረሰው ጥቃት ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸው የነበሩት የክልሉ ጠቅላይ አቃቤ ህግ የነበሩት አቶ ምግባሩ ከበደ የህክምና ዕርዳታ ቢደረግላቸውም ሰኔ 17 ቀን 2011 ዓ.ም. ህይወታቸው ያለፈ ሲሆን፤ በጥቃቱ መንግሥት ጠርጥሬያቸዋለሁ ያላቸው የክልሉ የሰላምና ደህንነት ጉዳይ ኃላፊ የሆኑት ብርጋዴየር ጀነራል አሳምነው ጽጌ በፌደራል ፖሊስና መከላከያ በተወሰደባቸው ወታደራዊ ጥቃት ሰኔ 17 ቀን 2011 ዓ.ም. መገደላቸውን መንግሥት አስታውቋል።

Amhara regiona victim leaders
ዶ/ር አምባቸው መኮንን፥ ብጀነራል አሳምነው ጽጌ፥ አቶ ምግባሩ ከበደ እና አቶ እዘዝ ዋሴ (ፎቶ፡ ከማኀበራዊ ሚዲያ)

ይህ በእንዲህ እንዳለ መንግሥት በአዲስ አበባ በጄነራል ሰዓረ መኮንን እና ሜጀር ጀነራል ገዛዒ አበራ ግድያ ግድያ ተጠርጣሪው የጀነራል ሰዓረ መኮንን የግል ጠባቂ የአስር አለቃ መሳፍንት ጥጋቡ ነው ሲል ይፋ አድርጓል። ይሁን እንጂ ተፈፀሙ ለተባሉ ጥቃቶች መንግሥት “መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ነው” በሚል ለዓለም ይፋ ቢያደርግም የጥቃት አድራሾችን፥ ጥቃቱን እና ምክንያቱን በተመለከተ ርስ በርሱ የተጣረሰ የአንድ ወገን መረጃ ብቻ በመሆኑ ይህ እስከተጠናቀረበት ድረስ ሁኔታውን በተመለከተ ከጥቃቱ ተርፈናል ከሚል አራት የአማራ ክልል አመራሮች በስተቀር ከተጠርጣሪዎችም ሆነ ከገለልተኛ አካል የተሰጠ ምላሽም ሆነ ማረጋገጫ የለም። ጥቃቱን ተከትሎ ከከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች ግድያ በተጨማሪ ቁጥራቸው ያልተገለፀ ሌሎችም በርካታ ዜጎች መገደላቸውንም የአማራ ክልል የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰማኽኝ አስረስ ለሮይተርስ ገልፀዋል።

በጥቃቱ ህይወታቸው ያለፈ አመራሮች ዶ/ር አምባቸው መኮንን፥ አቶ ምግባሩ ከበደ እና አቶ እዘዝ ዋሴ ሰኔ 19 ቀን 2011 ዓ ም በባህርዳር ከተማ አባይ ማዶ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የቀብር ሥነ ሥርዓታቸው የተፈፀመ ሲሆን፤ የብርጋዴየር ጀነራል አሳምነው ጽጌ በትውልድ ከተማቸው በላሊበላ አብያተ ቤተክርሥቲያናት በቤተ ጊዮርጊስ የቀብር ስፍራ ተፈፅሟል። በተመሳሳይም ጥር 20 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀን የጀነራል ሰዓረ መኮንን እና ሜጀር ጀነራ ገዛዒ አበራ የቀብር ሥነሥርዓት በመቀሌ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ተፈፅሟል።
General Seare and M.General Gezae
ጀነራል ሰዓረ መኮንን እና ሜ/ጀነራል ገዛዒ አበራ (ፎቶ፡ ከማኅበራዊ ሚዲያ)

የአመራሮችን ግድያ እና የቀብር ሥነ ሥርዓት ቢያሳውቅም፤ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ የወታደራዊ የኃይል ርምጃ የተገደሉ በርካታ ዜጎች ቢኖሩም መንግሥት እስካሁን ቁጥራቸውንም ሆነ ማንነታቸውን አልገለፀም። መንግሥት ቀደም ሲል ጥቃቱን “መፈንቅለ መንግሥት ነው፥ የአዲስ አበባው ከባህርዳሩ ጥቃት ጋር የተያያዘ ነው” በሚል በጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ቃል አቀባይ ኃላፊዎች እና በፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነሩ የተገለፀ ቢሆንም፤ ዛሬ ሰኔ 21 ቀን 2011 ዓ ም የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቃል አቀባይ ቢልለኔ በበኩላቸው “የአዲስ አበባው ከባህር ዳሩ ጥቃት ጋር ስለመያያዙ ገና ይጣራል።” ሲሉ ገልፀዋል። በተለይ የባህርዳሩን እና የአዲስ አበባውን የባላሥልጣናት ግድያ በተመለከተ ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ቃል አቀባይ ኃላፊዎች እና ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነሩ የሰጡት መግለጫዎች ርስ-በርስ የሚጣረሱ በመሆናቸው፤ መንግሥት እየሰጠ ያለው መረጃ ተዓማኒነት ላይ በርካቶች ጥርጣሬ እንዳላቸው እየገለፁ ይገኛሉ።

በሌላ በኩል ፤ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በበኩሉ በመተከል ዞን ሰኔ 16 ቀን 2011 ዓ ም ከ 30 በላይ ሰላማዊ ዜጎች ባልታወቁ ታጣቂዎች መገደላቸውን ይፋ አድርገዋል።

መንግሥት ባህርዳሩን እና የአዲስ አበባውን ጥቃት ተከትሎ በርካታ ዜጎችን እያሰረ ሲሆን፤ ከነዚህ መካከል የአማራ ክልል የፀጥታ ዘርፍ አመራሮች፥ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) አመራሮች እና አባላት፥ በጋዜጠኛ እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች እስክንድር ነጋ የሚመራው የአዲስ አበባ ባላደራ ምክር ቤት (ባልደራስ) አመራር አባላት፥ ጋዜጠኞች እና የፀጥታ ዘርፍ አባላት እና ሰኣላማዊ ጄጎች በጅምላ መታሰራቸው ታውቋል። እስካሁን ባለው መረጃ ከ300 በላይ ዜጎች በጅምላ እንደታሰሩ መረጃዎች ቢጠቁሙም፤ ሌሎች ምንጮች ደግሞ የእስካሁኑ የጅምላ እስር በሺህዎች የሚቆጠር እንደሚሆን ይገምታሉ። ይህንንም ተከትሎ በርካታ ሰዎች በማኀበራዊ ሚዲያ ላይ መንግሥት የአማራ ማኅበረሰብ ልሂቃን ላይ ያነጣጠረ የጅምላ እስር እየተፈፀመ ነው ሲሉ የኮነኑት ሲሆን መንግሥትም በግፍ በጅምላ ያሰራቸውን ዜጎች እንዲፈታ፥ ያለውን እውነታም ለህዝብ ግልፅ እንዲያደርግ ተጠይቋል።

በኢትዮጵያ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ተገደሉ

(ዳጉ ሚዲያ) ቅዳሜ ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በባህርዳር ከተማ በስብሰባ ላይ የነበሩ የአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ላይ በተፈጸመ ጥቃት የክልሉ ፕሬዘዳንት ዶ/ር አምባቸው መኮንን እና የማኀበራዊ ዘርፍ አማካሪያቸው አቶ እዘዝ ዋሴን ጨምሮ ቁጥራቸው ያልተገለጸ ጠባቂዎቻቸውም ሲገደሉ የክልሉ ጠቅላይ አቃቤ ህግ የሆኑት አቶ ምግባሩ ከበደ የመቁሰል አደጋ እንደደረሰባቸው ለማወቅ ተችሏል::

ዶ/ር አምባቸው መኮንን (ፎቶ፡ ከአማራ ቴቪ)

በተመሳሳይም በአዲስ አበባ

አቶ እዘዝ ዋሴ (ፎቶ፡ ከአማራ መገናኛ ብዙኃን)

የሀገር መከላከያ ሰራዊት ጠቅላይ ኢታማዡር ጀነራል ሰዓረ መኮንን እና በጡረታ ላይ የነበሩት የቀድሞ የስራ ባልደረባቸውና የሰራዊት የሎጀስቲክ ዘርፍ ኃላፊ የነበሩት ሜጀር ጀነራል ገዛዒ አበራ
በጀነራል ሰዓረ መኖሪያ ቤት እያሉ በኢታማዡሩ ጠባቂ መገደላቸውን መንግሥት አረጋግጧል:: ድርጊቱን ያወገዙት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ(ዶ/ር) በተለይ የባህር ዳሩን የባለሥልጣናት ግድያ ጥቃት “በአማራ ክልል የተፈጸመ መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ መሆኑና መክሸፋን” ገልፀዋል::

 

ነገር ግን እስካሁን ለጥቃቱ ኃላፊነት የወሰደ አካል ባይኖርም መንግሥት በበኩሉ “ጥቃቱን የመሩትና ያቀናበሩት የአማራ ክልል የሰላምና ደህንነት ጉዳዮች ኃላፊ ብርጋዴየር ጀነራል አሳምነው ጽጌ ናቸው::” ቢልም ከገለልተኛ አካልም ሆነ በስም የተጠቀሱት ተጠርጣሪ ብርጋዴየር ጀነራል አሳምነው የተሰጠ ማረጋገጫም የለም:: ከጥቃቶቹ ጋር በተያያዘ በአዲስ አበባ ከመከላከያ ሰራዊት ሹማምንት ግድያ ጋር በተያያዘ የጀነራል ሰዓረ መኮንን ታማኝ የግል ጠባቂያቸውና ሌሎች የመከላከያ ሰራዊት ተጠርጣሪ የጦር መኮንኖች በቁጥጥር ስር ውለዋል::

ጀነራል ሰዓረ መኮንን (ፎቶ፡ ከኢቴቪ)

ከአማራ ክልል አመራሮችና ጠባቂዎቻቸው ግድያ ጋር በተያያዘ የክልሉ የፀጥታ ዘርፍ ኃላፊ ብርጋዴር ጀነራል ተፈራ ማሞ እና የፖሊስ ኮሚሽኑ ኮምሽነር አበረ አዳሙ ተጠርጥረው በፌደራል ፖሊስ እና በመከላከያ ሰራዊት ቁጥጥር ስር መዋላቸው የተሰማ ሲሆን በቀዳሚነት ተጠርጥረው ስማቸው የተነሳው ብርጋዴየር ጀነራል አሳምነው ጽጌ ይህ እስከተጠናቀረበት ድረስ በቁጥጥር ስር እንዳልዋሉና ያሉበትም እንዳልታወቀ ተጠቁሟል::

ሜጀር ጀነራ ገዛዒ አበራ (ፎቶ፡ ከኢቴቪ) 

የተለያዩ የመንግሥት ኃላፊዎችም ጥቃቶቹን በመኮንንና በማውገዝ ህዝቡ እንዲረጋጋ እንዲሁም በጋራ አንድነቱን እና ሰላሙን እንዲያስጠብቅ ጥሪ አቅርበዋል:

በኢትዮጵያ የለውጥ ተስፋ እና ስጋቶች

ብስራት ወልደሚካኤል
afrosonb@gmail.com

ጥንታዊ እና ቀዳሚ ከነበሩ ሀገሮች መካከል አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያ በተለይ በቅርቡ ከአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) በዓለ ሲመት ከተደረገበት መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም. አካባቢ የተስፋ አድማሶች ጎልተው ይታዩ ነበር። ዛሬም በርካታ ፈተናዎች ተደቅነውባታል። ህዝቡም ዛሬም ቅን መሪና የዴሞክራሲ ሥርዓትን ይናፍቃል። ምንም እንኳ የተፈጥሮ ሃብትን የተቸረች ቢሆንም፤ ዛሬም ድረስ ለዜጎቿ ንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት፥ የምግብ ዋስትና አለመረጋገጥ፥ የመብራት አቅርቦት እና አገልግሎት መጓል፥ ጥራቱን የጠበቀ በቂ የትምህርት እና የጤና ሽፋን በበቂ ሁኔታ አለመዳረስ ተጠቃሽ ችግሮች ናቸው።

በሀገሪቱ ስር የሰደደ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እና የመልካም አስተዳደር ዕጦት ሌላው የዜጎች ትልቁ ፈተና ነው። በተለይ ከሀገሪቱ ኢኮኖሚ ጋር ያልተመጣጠነ የህዝብ ብዛት፥ የወጣቶች ሥራ አጥነት፥ የህግ የበላይነት አለመረጋገጥ እንዳለ ሆኖ፤ ልቅ የሆነው የሙስና ሰንሰለት ሀገሪቱ ከውጭ በዕርዳታ፥ ብድርና ንግድ ከምታገኘው ዓመታዊ የውጭ ምንዛሪ ይልቅ በተደራጀ ፖለቲካዊ መዋቅር ተደግፎ ከሀገር የሚሸሸው የዶላር መጠን እና አድሏዊነት የተፀናወተው ሥርዓት አልባው የንግድ ሥርዓት የዜጎችን ሰላምና ህይወት ሲፈታተን ቆይቷል።

PM_Abiy_Ahmed_Ali
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ (ፎቶ፡ ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት የተወሰደ)

በርግጥ በኮሎኔል መግሥቱ ኃይለማርያም ይመራ ከነበረው የኢሕዴሪ መንግሥታዊ ሥርዓት መገርሰስ በኋላ ግንቦት 1983 ዓ.ም. በምዕራባዊያን እና አረብ ሀገራት ድጋፍ ወደ ሥልጣን የመጣው የቀድሞው የጫካ አማጺ የትግራይ ነፃ አውጭ ድርጅት (ህወሓት) ኢህአዴግ በሚል ካባ በአምሳሉ ከፈጠራቸው የፖለቲካ ድርጅት (ብአዴን/አዴፓ፥ ኦህዴድ/ኦዴፓ እና ደኢህዴግ/ደኢህዴን) ድርጅቶች ጋር ኢህአዴግ በሚል ግንባር ወደ ሥልጣን ሲመጣ ብዙ ተስፋ ተጥሎበት ነበር። ይሁን እንጂ በነበረበት ያለፉት 27 ዓመታት የማዕከላዊ መንግሥት ሥልጣን ቆይታው ለሀገሪቱም ሆነ ለዜጎችም በበርካታ ጉዳዮች እጅግ ፈተና የበዛበት የግፍ አገዛዝ ነበር። በአገዛዙም በርካታ ዜጎች በግፍ ታስረዋል፥ ተገድለዋል፥ ከሀገር ተሰደዋል። የሰብዓዊና የዴሞክራሲያዊ መብት ጥሰትም ከሀገር አልፎ በዓለም አቀፍ ደረጃ መነጋገሪያ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው። በርካታ ሰነዶችና ጥናቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ የህዝቡን ብቻ ሳይሆን ብሔራዊ የሀገሪቱን ጥቅም በማሳጣትም በሀገሪቱ ታሪክ ከነበሩ አገዛዞች በተለየ በጥቁር መዝገብ እንዲሰፍር ተደርጓል።

ከሶስት ዓመታት ተከታታይ ህዝባዊ አመፅ በኋላ መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ ም የሀገሪቱ 15ኛው ጠቅላይ ሚኒስትር በመሆን ወደ ሥልጣን የመጡት አብይ አህመድ (ዶ/ር) በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ፊት ቃለ መሐላ በመፈፀም ከወትሮ የኢህአዴግ አሰልቺ የቃላት ጋጋት እጅጉን የራቀና በዜጎች የተወደደላቸውን ንግግር በተሰማበት ወቅት ሀገሪቱ በብሩህ ተስፋ ተሞልታ ነበር። በተለይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተከታታይ በወሰዷቸው መልካም ርምጃዎች፤ በተለይም የታሰሩ የነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞችን እና ጦማሪዎችን ጨምሮ የፖለቲካ እስረኞችን መፍታት፥ መንግሥት በዜጎች ላይ ለፈፀመው ጥፋት በይፋ ይቅርታ መጠየቅ፥ ብረት ያነሱ ተቀናቃኝ አማጺያንን ጨምሮ በውጭ ያሉ ተቀናቃኝ የፖለቲካ ኃይሎች በሰላም ወደ ሀገር ገብተው ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ እንዲያካሂዱ ጥሪና ድጋፍ ማድረግ ተጠቃሽ በጎ ርምጃዎች ናቸው።

ለረጅም ጊዜ “ሞት አልባ” ጦርነት የነበረው የኢትዮጵፃ እና የኤርትራ መፋጠጥ በሰላም እንዲቋጭ ማድረጋቸው እና ብሔራዊ አንድነትና መግባባትን በአደባባይ ከማቀንቀን አልፈው ለተግባራዊነት መንቀሳቀሳቸው ከህዝቡ ባልተለመደ መልኩ በርካታ ድጋፍና አጋርነት አስገኝቶላቸዋል። እንዲሁም ለበርካታ ዓመታት ህዝቡ ያለገዥው ህወሓት/ኢህአዴግ ፍላጎት ውጭ ናቸው የተባሉና ታግተው የነበረው የሳተላይትና የመረጃ መረብ ሚዲያዎች ክፍት እንዲሆኑና ለህቡም አማራጭ ሆነው እንዲያገለግሉ መፍቀዳቸው፤ በተለይ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ እና የፕሬስ ነፃነት አቀንቃኞችና ተሟጋቾች ሳይቀር ይበል የሚያሰኙ በርካታ ውዳሴዎችን እንዲያገኙ አስችሏቸዋል።

በሀገር ውስጥ በተለያዩ ከተሞች ጉብኝትና ምክክር ከማድረጋቸው በተጨማሪ በውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ጋር ያደረጉት ምክክርና መቀራረብም ያልተለመደና የተወደሰ አዲስ የለውጥ ክስተት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። በህዝባዊ አመፅ ተዳክሞ የነበረውን እና የተራቆተውን የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለማሻሻሉ እየወሰዱ ያሉት በጎ ርምጃም ከሚወደስላቸው ተግባራት መካከል አንዱ ነው። በተጨማሪም ላለፉት 27 ዓመታት በፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት ለሁለት ተከፍሎ የነበረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ወደ አንድነት እንዲመጡ የተደረገው ድጋፍና አስተዋፅዖ ፤ እንዲሁም በተመሳሳይ መልኩ የኢትዮጵያ ሙስሊም መጅልስ ተቋም ላይ በተደረ ፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት የነበረው መለያየት ወደ አንድነት እንዲመጣ መደረጉ በበጎ የሚወሱ ተግባራት ናቸው። እነኚህ በጎ ተግባራት የህዝቡን አንድነትና ህብረት ከማጠናቀር በተጨማር በሀገሪቱ ሰላም፥ ዕድገትና ብልፅግና ላይ ዜጎች ብሩህ ተስፋን እንዲሰንቁ አስችሏቸዋል።

ነገር-ግን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ያ ሁሉ የነበረው ተስፋና ድጋፍ ግን ከአንድ ዓመታ በላይ መዝለቅ የቻለ አይመስልም። ለአንድ ዓመት ያህል የመብት ተሟጋቾችና ጋዜጠኞች ሳይታሰሩ የመቆየታቸው በጎ ተስፋ አሁን አሁን ስጋት እየታየበት ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ የለውጥ መሪውና ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይወክሉታል በሚባለው ኦሮሚያ ክልልን ጨምሮ በርካታ ዜጎች የደህንነት ዋስትና ማጣት እየተለመደ መጥቷል። በአማራ ክልል፥ በደቡብ እና ቤኒሻንጉል ክልልም የተለያዩ አካባቢዎች ተመሳሳይ የፀጥታና ደህንነት ስጋቶች ይስተዋላሉ።

በጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ ከሚነሱ ነቀፌታዎች መካከል ይሰሩልኛል ብለው የነበረውን ህግ ወደ ጎን በመተው የራሳቸውን ሰው ከህግ አግባብ ውጭ የሾሟቸው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አካላት ሹመት፥ የሥራ ስምሪት እና የተለያዩ ከፍተኛ የመንግሥት ሥልጣን እና ሹመት ከብቃትና አካታችነት ይልቅ ከዚህ ቀደም ይወገዝና ተቃውሞ ይቀርብበት የነበረውን የሟቹ አቶ መለስ ዜናዊ እና የድርጅታቸው ህወሓት አገዛዝን ተመሳሳይ መንገድ እየተከተሉ ነው በሚል በርካታ ደጋፊዎቻቸው ሳይቀር ነቀፌታ ማቅረባቸውን ቀጥለዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ሥልጣን ከመምጣታቸው በፊት በዋናነት ሶማሊና ኦሮሚያ ክልል አካባቢ ወደ አንድ ሚሊዮን ዜጎች ከመደበኛ መኖሪያቸው የተፈናቀሉ ቢሆንም፤ በአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር የአንድ ዓመት አስተዳደር ጊዜ ውስጥ ግን ወደ ሁለት ሚሊዮን ዜጎች በኃይል ተፈናቅለዋል፥ በርካቶችም በርስ በርስ ግጭት ተገድለዋል፥ ቆስለዋል።

አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ብቻ የአዲስ አበባ ወጣቶችን ከአንዴም ሁለት ጊዜ ያለምንም ህጋዊ መሰረትና ምክንያት በጅምላ ሰብስቦ ማሰርና ማንገላታት በቀዳሚነት ይደግፏችው የነበሩ ወጣቶች አዲሱን አስተዳደር በጥርጣሬ እንዲያዩት ምክንያት ሆኗል። በተለያዩ መንግሥታዊ አስተዳድር ጉዳዮች እና አገልግሎት አሰጣጥ ላይም ሁሉንም በእኩል ከማየት ይልቅ ፖለቲካዊ ወገንተኝነትን የተላበሰ አድሏዊነት እየተንፀባረቀ ነው በሚልም የነበረውን ተስፋ በሂደት ወደ ስጋት እየተለወጠ መጥቷል። በተለይም በኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ አቅራቢያ ቡራዩ፥ ለገዳዲና ለገጣፎ ከተሞች፥ ምዕራብ ወለጋ፥ ቄለም ወለጋ፥ ሆሮ ጉድሩ ወለጋ፥ ምሥራቅ ወለጋ፥ ምዕራብ እና ምሥራቅ ጉጂ ዞን፤ በአማራ ክልል፥ ሰሜን ጎንደርና ምዕራብ ጎንደር፤ በደቡብ ክልል ጉራጌ ዞን፥ ጉጂ ዞን፥ ቡርጂ ጌዲዮ፥ አማሮ፥ ከፋ ዞን እና ደራሼ አካባቢን መጥቀስ ይቻላል። ይህ ዘገባ በሚጠናከርበት ጊዜም መንግሥት ባመነው መረጃ እንኳ ወደ ሶስት ሚሊዮን ዜጎች ከመደበኛ ኑሯቸውና ቀዬያቸው ተፈናቅለዋል። በርግጥ የተወሰኑት ወደ ቀድሞ መኖሪያቸው እንዲመለሱ ጥረት እየተደረ መሆኑ እንዳለ ሆኖ፤ አሁንም ድረስ ዜጎች ተረጋግተው የመኖር ተስፋቸው ላይ ስጋትን ጭሯል።

በኦሮሚያ ክልል ለሰላማዊ ትግል በሚል ስምምነት ወደ ሀገር ውስጥ ጥሪ ተደርጎለት ከኤርትራ አስመራ ወደ ሀገር የገባውና በአቶ ዳውድ ኢብሳ የሚመራው ሸኔ የሚባለውና የኦነግ ክንፍ
በአራቱም የወለጋ ዞኖች በሚገኙ የተለያዩ 19 ያህል የንግድ ባንኮች ዘረፋ መፈፀሙ ቢገለፅም በጉዳዩ ዙሪያ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ አዲስ አበባ የሚገኙት የድርጅቱ መሪም ሆኑ ሌሎች የሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ዝምታን መምረጣቸው የህግ የበላይነት መላላትና የዜጎች ደህንነት ከዕለት ወደ ዕለት አደጋ ውስጥ መውደቁ ሌላኛው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ድክመት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። የሀገሪቱ ፀጥታና ደህንነት ጉዳይ ከወዲሁ ትኩረት ካልተሰጠው፥ ተጠያቂነትና የህግ የበላይነት በሁሉም ዜጎች ላይ በእኩል የማይሰራ ከሆነ ወደ አላስፈላጊ ረብሻና ሥርዓት አልበኝነት እንዳያመራ ስጋት አለ። የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ከመጠበቅ አኳያ በመንግሥት በኩል እየተወሰደ ያለው የእርምትም ይሁን የጥንቃቄ ርምጃ እጅጉን ደካማ ነው።

ሐሳብን ከመግለፅና ከፕሬስ ነፃነት ጋር በተያያዘ ያለው ተስፋ በቅርቡ በአንዳንድ ጋዜጠኞችና ጦማሪዎች ላይ ስጋቶች እንደ አዲስ ተደቅኖባቸዋል። በተለይ የካቲት 23 ቀን 2011 ዓ.ም. በአዲስ አበባ አቅራቢያ ባሉ የኦሮሚያ ክልል ለገዳዲና ለገጣፎ ከተሞች በመንግሥት አስተዳድር በግልፅ ውሳኔና ርምጃ የተፈናቀሉ ዜጎችን አስመልክቶ ለዘገባ የተጓዙ የ”መረጃ ቲቪ” ዘጋቢ ጋዜጠኛ ፋሲል አረጋይ እና የፎቶ ጋዜጠኛው ሀብታሙ ኦዳ በከተማው ፖሊስ ጣቢያ ፊትለፊት የአካል ጥቃት ተፈፅሞባቸዋል። ጋዜጠኛ ፋሲልም በደረሰበት ጥቃት አዲስ አበባ ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል የህክምና ርዳታ ተደርጎለታል። በቅርቡም የአሃዱ ቴቪ ጣቢያ ከሰንዳፋ ከተማ ጋር በተያያዝ በተላለፍ ዘገባ ጋር በሚል ግንቦት 16 ቀን 2011ዓ.ም. ጋዜጠኛ ታምራት አበራ ከሚሰራበት አሃዱ ቴልቪዥን እና ሬዲዮ ጣቢያ በኦሮሚያ ፖሊስ ተወስዶ መታሰሩና፤ በዕለቱ የታሰረውን ጋዜጠኛ ሊጎበኘው የሄደው የኢትዮ-ኦንላየን ሚዲያ ጋዜጠኛ ጌጥዬ ያለው መታሰሩ በነፃው ፕሬስ ጫና ጅማሮ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። እንደ ምንጮች ከሆነ በአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ አስተዳደር እየተፈፀሙ ያሉ ብልሹና አድሏዊ አሰራሮችን የሚያጋልጡ የኢንተርኔት መረጃ አምደኛ ጋዜጠኞች፥ ጦማሪዎችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች የጦማሮቻቸው እና የግል የይለፍ ቃል በኢትዮጵያ የመረጃ መረብ ደህንነት ኤጀንሲ (INSA) ብርበራና የይለፍ ቃል ነጠቃ እየተሞከረ እንደሆነ ይነገራል። እነኚህ ሁሉ የነበሩ የለውጥ ብሩ ተስፋዎች ላይ የስጋት ደመና ጋርደዋል።

ሌላው ከዚህ ቀደም በህወሓት/ኢህአዴግ የመንግሥት አስተዳደር ወቅት የአመራር አካልና የወጣት አደረጃጀት አባላት የነበሩና ተከታዮቻቸው በአዲሱ የአብይ አህመድ ኦዴፓ/ኢህአዴግ አመራር ላይ የተለያየ ጫና ለመፍጠር ሲጥሩ ይስተዋላል። ለአብነትም የቀድሞ የኦህዴድ/ኦዴፓ የታችኛው አንዳንድ አመራር አካላት፥ የህወሃት አመራሮች፥ የቀድሞ ብአዴን/አዴፓ እና የደኢህዴን አመራሮች በየአካባቢያቸው ከሚያደርጉት እንቅስቃሴ በተጨማሪ በማኀበራዊ ሚዲያ ሳይቀር አንዳንዶቹ ከአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር መምጣት በኋላ ከኢህአዴግ አካል የነበሩት አዳዲስ የፖለቲካ ድርጅት በመፍጠር ጭምር የሚያደርጉት እንቅስቃሴ በአንዳንድ አካባቢዎች ጥርጣሬ፥ ግጭትና ስጋት መፍጠራቸው አልቀረም። በአንፃሩ ከኦነግ ታጣቂ በስተቅር አብዛኛው ከውጭ የመጡትም ሆነ በሀገር ውስጥ ያሉ የገዥው ኢህአዴግ ተቀናቃኝ የፖለቲካ ድርጅቶች ከአዲሱ አስተዳደር ጋር የተሻለ መከባበርና መቀራረብ ይታይባቸዋል። ይሄ ለሰላምና መረጋጋቱ ተስፋ ሰጭ ቢሆንም፤ በአንዳንድ ሚዲያ ላይ የሚታዩ የጋዜጠኝነት የሙያ ስነ ምግባር ጋር የሚቃረኑ የሚዲያ አጠቃቀም ክፍተቶች፥ ተጠያቂነትና ኃላፊነትን ተላብሶ እንዲሰራ ሊረዳ የሚችል ነፃና ገለልተኛ የጋዜጠኞች የሙያ ማኀበር አለመኖርም እንደ አንድ ስጋት የሚታይ ነው።

በተለያ በማኀበራዊ ሚዲያ አጠቃቀም ረገድ በርካታ የማኀበራዊ የግል ገፆች ትክክለኛ ባልሆነ ስም፥ አንዳንዱ ደግሞ በህይወት ባለም ሆነ በሌለ ስመ ጥር ግለሰቦች ስም ገፅ በመክፈት የሚሰራጩ ሐሰተኛ መረጃ ስርጭት እና የጥላቻ ንግግሮች ሌላው የለውጡ ፈተና ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። በተለይ ሐሰተኛ መረጃና የጥላቻ ንግግርን የሚያሰራጩ ግለሰቦች እየተበራከተ ከሄደ መንግሥና አስተዳደር ላይ ብቻ ሳይሆን የዜጎች ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትና የፕሬስ ነፃነት ላይ አሉታዊ ጫና ያሳድራል። ምናልባትም ችግሩ ተባብሱ በዜጎች መካከል ግጭት እና ቅራኔ መፍጠር ሲባባስ መንግሥት የራሱን አስተዳደራዊ ርምጃ እንዲወስድ ሊጋብዝ ይችላል። ይሄ ደግሞ በሌላ በኩል በዜጎች ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትና የፕሬስ ነፃነት ላይ የራሱ የሆነ አሉታዊ ሚና ይኖረዋል። ስለዚህ ብሩህ ተስፋን ሰንቆ የነበረው ለውጥ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በመንግሥትና በአንዳንዴ ዜጎች መካከል ጥርጣሬና ስጋትን እየታየ ይገኛል።

በጌዲዖ ማኀበረሰብ ላይ የተፈፀመው የዘረኝነት ጥቃት እና ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣት

ብስራት ወልደሚካኤል

በዶ/ር አብይ አህመድ እና አቶ ለማ መገርሳ የሥልጣን ዘመን በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የዘረኝነት ጥቃት ሰለባ ከደረሰባቸው ወገኖች መካከል የጌዲዖ ማኀበረሰብ ላይ የደረሰው ከፍተኛው ነው። ነገር ግን በተፈናቃይ የጌዲዖ ማኀበረሰብ ላይ የተፈፀሙ ጥቃቶችና በደሎች አቶ ለማ መገርሳም ሆኑ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዶ/ር አብይ አህመድ ጠንቅንቀው ያውቃሉ። ባለፈው ክረምት የተፈፀመው በደል በኦነግ እንደሆነ ብዙ ሸፋፍኖ ለማለፍ ተሞክሮ ነበር። ግን አልነበረም። መጀመሪያ ላይ የተፈፀመው ማፈናቀልና አካላዊ ጥቃት በምሥራቅ እና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች ባሉ የኦህዴድ/ኦዴፓ ከፍተኛ እና የወረዳ አመራሮች ራሳቸውን “ቄሮ” ብለው የሚጠሩ ወጣቶችን በማስተባበር ጭምር እንደተሳተፉ የጥቃቱ ሰለባዎችና ድርጊቱን የተቃወሙ የጉጂ ዞን ሌሎቹ አመራሮች አጋልጠው ከኦሮሚያ ክልል ሪፖርት አድርገው ነበር። ይሄንንም የክልሉ ፕሬዘዳንት አቶ ለማ መገርሳ እና ምክትላቸው ወ/ሮ ጠይባ ሐሰን ያውቃሉ። ለዚህም ነው አቶ ለማ መገርሳ ተፈናቃዮቹ ያሉበት ጉጂ ዞን በአካል ሄዶ የጎበኘውና ድርጊቱን ኮንኖ ሀዘኑን የገለፀው። ይህም ብቻ አይደለም በድርጊቱ የተሳተፉና መረጃ የተገኘባቸው ናቸው ያየተባሉት ላይ ወዲያውኑ ከሥራ ማገድ እስከ እስር ርምጃ መውሰዳቸውን ያሳወቁት። በወቅቱ የነበረውን የዘረኝነት ቅስቀሳና ማፈናቀሉን የተቃወሙ አመራሮችና የሀገር ሽማግሌዎች ቢኖሩም አደጋውን ከመቀነስ ባለፈ ማስቆም አልቻሉም ነበር። ምክንያቱም ጥቃቱ በመሳሪያ የታገዘ ስለነበር። ድርጊቱ ከዚህ ቀደም ሱማሌ ክልልና ወሰን አካባቢ በአብዲ ኢሌ እና አጋዦቹ በምስኪኑ ኦሮሞ ላይ ከተፈፀመው ጋር ተመሳሳይ ነው። ያንን አውግዘን እና ኮንነን ይሄን መሸፋፈን አይቻልም። ወንጀል የትም በማንም ላይ ይፈፀም ያው ወንጀል ነው።

ድርጊቱ የተፈፀመው በፖለቲካ መሪዎችና የፀጥታ ኃይሉ እንጂ በህዝቡ አለነበረም። ታዲያ በአብዲ ኢሌ የተፈፀመውን ኮንነን እና አውግዘን ስናብቃ ምስኪኑ የጌዲዖ ማኅበረሰብ መፈናቀልን እና የፖለቲካዊ የርሃብ ጥቃት መሸፋፈን ለምን አስፈለገ? የጌዲዖ መፈናል እና ሰብዓዊ ርዳታ ልክ ኦሮሞ በክፉ ሥራው የተጋለጠ ለማስምሰል ሌላ ጥፋት ነው። አንድም የግለሰቦችን ወንጀል ለምስኪኑ ኦሮሞ ማላከክ አሊያም ኦሮሞ ላይ የተፈፀመ ስም ማጥፋት አስመስሎ ማስፈራራት እና ወንጀሉን ለመሸፋፈን የመሞከር ወንጀል። ይሄ ጊዜ ያለፈበት ነው። ልክ የሶማሌ ማኅበረሰብ ኦሮሞ ከአስተዳደር ክልላቸው የኦሮሞ ማኅበረስብ እንዲፈናቀል ለእነ አብዲ ኢሌ ትዕዛዝ እና ድጋፍ እንዳላደረገ ሁሉ በምስኪን የጌዲዖ ማኅበረሰብ ከጉጂ ዞኖች መፈናቀል የኦሮሞ ማኅበረስብ ትዕዛዝ ሰጥቶ ድጋፍ አድርጓል ብሎ የሚያምን የለም። የአካባቢው የኦህዴድ/ኦዴፓ ፅንፈኞችና ዘረኛ አመራሮች ግን አድርገውታል። ይሄን መካድ አይቻልም። ለዚህም በሁለት ዙር በግፍ የተፈናቀሉ የጌዲዖ ማኀበረሰብን ሰቆቃ በአካል ሄዶ ማየት በቂ ነው። ይሄ ደግሞ ከህግም፥ ከሞራልም ሆነ ከሰብዓዊነት አንፃር መጋለጥና መወገዝ ያለበት ወንጀል ነው። ያውም “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥቃት። ያኔ በህወሓት እና አብዲ ኢሌ ፖለቲካዊ ወንጀል የኦሮሞ ማኅበረሰብ ከሶማሌ ክልል በግፍ ሲፈነቀል ከሀገሩ ሊፍናቀል አይገባም ብለን በጋራ እንደተቃወምነው ሁሉ የጌዲዖ ማኀበረሰብ በግፍ መፈናቀልንም ልናወግዝ ይገባል እንጂ ጉዳዩ ተጋለጠ ብሎ በርሃብና ሞት እንዲቀጡ መሸፋፈን ትክክል አይደለም። ይሄ ጭካኔ የተሞላበት ኢ- ሰብዓዊነት ነው።
Gedeo crises
ከኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በማንነታቸው የተፈናቀሉ የጌዲዮ ማኅበረሰብ በከፊል (ፎቶ፡ የጌዲዮ ዞን ኮሚኒኬሽን ጽህፈት ቤት)
በተለይ አቶ ለማ መገርሳ ከፌደራል የደኢህዴን አመራሮች መካከል ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል እና ከደቡብ ክልል ደግሞ አቶ ሚሊዮን ማቴዎስ እንዲሁም በችግሩ ቅርበት ያለው የጌዲዖ ዞን አመራሮች የጥቃቱ ሰለባዎች የሚገኙበት ጊዜያዊ መጠለያ ቦታ ድረስ በመሄድ አረጋግጠው፤ ጉዳዩ በሽምግልና እንዲፈታ፥ የተፈፀመባቸው ጥቃትም ወደ አደባባይ እንዳይወጣ ብዙ ሞክረው ነበር። ጉዳዩን አለዝቦ “በጉጂ ኦሮሞ እና በጌዲዖ ማኀበረሰብ ተከስቶ የነበረው ግጭት በሀገር ሽማግሌዎች ርቀሰላም ተፈቷል” በሚል ለዘብ ያለ የዜና ሽፋን ሁሉ ተሰጥቶት ነበር። ያውም ከቪዲዮ ምስል ጋ ተያይዞ። እንደ ጥቃቱ ሰለባዎች ገለፃ ከሆነ ግጭቱ የተቀሰቀስውም ሆነ የተቀነባበረው በጉጂ ኦሮሞ ማኀበረሰብና ብጌዲዖ ማኀበረብ መካከል ሳይሆን በምሥራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞን በሥልጣን ላይ ባሉ አካላትና የ“ብሔር” እና ጥላቻ ቅስቀሳ ሲያደርጉ በነበሩና ራሳቸውን “ቄሮ” ብለው በሚጠሩ ወጣቶች እና የማኀበራዊ ሚዲያ “አክቲቪስቶች” ነበር። በተለይ ከአካባቢው ጋር በተያያዘ በማኀበራዊ ሚዲያ ጭምር በኦሮሚኛ “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥላቻ ቅስቅሰሳ ይደርግ ሁሉ እንደነበር አስታውሰዋል።

በወቅቱ የጌዲዖ ማኅበረሰብ አባላት የደረሰባቸው የዘረኝነት ጥቃት መካከል፡-

1ኛ. በርካቶች ቤቶቻቸው እየተመረጠ ተቃጥሎባችዋል።
2ኛ. የእርሻ ማሳ ላይ ያለ ቡና እና ሰብሎችን ጨምሮ ንብረቶቻቸው ተዘርፈዋል፥ መሬቶቻቸውም በአካባቢው ባለሥልጣናትና ራሳቸውን “ቄሮ” ብለው በሚጠሩ ወጣቶች የተነጠቁም ይገኙበታል።
3ኛ. እናቶችን ጨምሮ ወጣት ሴቶች ተደፍረዋል።
4ኛ. በዚህ ወቅት ሊታሰብ የማይችል አሰቃቂ ግድያ ተፈፅሞባቸዋል። ከሞት የተረፉትም በዲላ እና ይርጋለም ሆስፒታሎች ሳይቀር ህክምና ርዳታ ያገኙ ነበሩ። በወቅቱም የኦሮሚያና የደቡብ ክልል ባለሥልጣናትም እንደተጎበኙ መረጃው አለ። ለውጡ እንዳይደናቀፍ በሚል ችላ ከተባለ በኋላ ዘግይቶ ጥቃቱ ግን በኦነግ ላይ ብቻ ተሳቦ ተሸፋፍኖ ታልፏል። ይሁን እንጂ የኦሮሚያ ክልልም ሆነ የደቡብ ክልል ባለሥልጣናት እውነታውን በደንብ ያውቁት ነበር። ከዚያም አቶ ለማ መገርሳ በጥቃቱን የተሳተፉ የምስራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞን አመራሮችን ከሥልጣን በማንሳት እንዲታሰሩና በህግ እንዲጠየቁ ማድረጋቸውን በአደባባይ በዕርቀ ሰላሙ ወቅት ተናግረው ነበር። ጥቃቱ የደረሰባቸው ምሥራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች ውስጥ በተጨማሪ አጎራባች የደቡብ ክልል ጌዲዖ ዞን ወረዳዎች የነበሩ ምስኪን ገበሬዎችም ጥቃት ደርሶባቸው ተፈናቅለዋል። በተለይ አጎራባች በጌዲዖ ዞን ትምህርት ቤቶች ሁሉ በጥቃቱ ወድመዋል። ከዛም በመንግሥት ግፊት፥ በሀገር ሽማግሌዎችና አባገዳዎች ድርድር አማካኝነት ነሐሴ 30 ቀን 2010 ዓ. ም. ወደ 359 ሺህ የሚሆኑ ተፈናቃዮች ወደ ቀድሞ ቀዬያቸው እንዲመለሱ ተደርጎም ነበር።

ነገር ግን የመንግሥትን እና የሀገር ሽማግሌዎችን ጥሪ ተቀብለው ወደ ቀዬያቸው ሲመለሱ የተዘረፉና ንብረቶቻቸውን እና የተወረሱ መሬቶቻቸውን ተከልክለው ድጋሚ ሌላ ጥቃት ደርሶባቸዋል። በዚህም ወደ 175 ሺህ ያህ የጌዲዖ ማኅበረሰብ አባላት በድጋሚ እንዲፈናቀሉ ተደርጓል። የሁለተኛው መፈናቀል ላይ ከኦህዴድ/ኦዴፓ የአካባቢው አመራሮች በተጨማሪ የኦነግ ታጣቂዎችም እንደተሳተፉ የተገለፀ ሲሆን፤ ድርጊቱን አውግዘው የተቃወሙ የጉጂ የሀገር ሽማግሌዎች በጥቃት አድራሽ የአካባቢው አመራሮች፥ ወጣቶችና ታጣቂዎች ማስፈራሪያና ዛቻ እንደደረሰባቸው ለኦሮሚያ ባለሥልጣናት ጭምር አሳውቀዋል። ይሄን በደል ያጋለጡ እና ለኦሮሚያ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ሪፖርት ያደረጉ አካላት አሁንም አሉ። ይሁን እንጂ ተፈናቃዮቹ ከኦሮሚያ ክልል ባለሥልጣናትም ሆነ የሚመለከተው የፌደራል መንግሥት ተገቢውን የሰብዓዊ እና የህግ ከለላ ድጋፍ ካለማግኘታቸው በተጨማሪ ፥ የተዘረፉና የተወረሱባቸው ንብረቶች እና የእርሻ ማሳዎች ሳይመለሱ ለረጅም ጊዜ በታፈነ አነስተኛ ጊዜያዊ የሸራ መጠለያ እንዲቆዩ መደረጉንም ያስታውሳሉ።

ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ ያለሰብዓዊ ድጋፍ በመጠለያ እያሉ የህግ ከለላና ድጋፍ ባለማግኘታቸው በተወስኑ ተመላሾች ላይ በፅንፈኞቹ ተደጋጋሚ የዘረኝነት ጥቃት ሲደርስባቸው በድጋሚ ከጉጂ ዞን ጊዜያዊ መጠለያዎቻቸውም ተፈናቅለው ወደ ጌዲዖ ዞን በተለይም ገደብ፥ ይርጋጭፌ እና ወናጎ ባሉ ወረዳዎች ተሰደው በአብያተ ክርስቲያናት አዳራሽ መኝታ አልባ ወለል ላይ እንዲሁም በሸራ በተወጠረ ጊዜያዊ መጠለያ ውስጥ ተፋፍገው ይገኛሉ። ከርሃቡ በተጨማሪም ለተለያየ ተላላፊ በሽታም የተጋለጡ ይገኝበታል። በድጋሚ ከተሰደዱትና በከፍተኛ ደረጃ ለርሃብ ከተጋለጡት መካክለ ከ45 ሺህ በላይ የሚሆኑት በጌዲዖ ዞን ገደብ ወረዳ ባሉ ቤተክርስቲያኖችና ትምህርት ቤቶች የተጠለሉ ቢሆንም በድጋሚ ወደ ቀዬያችሁ ካልተመለሳችሁ በሚል በፌደራል፥ በደቡብ እና ኦሮሚያ ክልል ባለሥልጣናት ግፊት ሰብዓዊ ድጋፍ እንዳይደረግላቸው መደረጉን መረጃዎች ይፋ ከሆኑ ሁለተኛ ሳምንቱን ይዟል። በዚህም በአማካይ በቀን ከ2 እስከ 3 ሰዎች በርሃብ እየሞቱ እነደሆነ፥ ቀሪዎቹ ለከፍተኛ ርሃብ በመጋለጣቸው አስቸኳይ የምግብ፥ የጤና እና መሰል የሰብዓዊ ድጋፍ ካላገኙ በአጭር ጊዜ ውስጥ በሺህዎች የሚቆጠሩ ተፈናቃይ የጌዲዖ ማኀበረሰብ አባላት ለሞት እንደሚጋለጡ የገደብ ወረዳ አመራሮች፥ የአካባቢው የመካነ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጉዳዩን አጋልጠዋል።
Gedeo
ከኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ጉጂ ዞን ከተፈናቀሉና የፖለቲካዊ ርሃብ ቅጣት ሰለባ ከሆኑ እናቶች መካከል አንዷ ናቸው።(ፎቶ፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ድርጊቱን ያጋለጡ የዲላ ዩኒቨርስቲ በጎ ፈቃደኞች እና ከአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ የተወሰደ)

መረጃው የደረሳቸው የዲላ እና ይርጋጨፌ ከተማ ነዋሪዎች እንዲሁም የተወሰኑ የዲላ ዩኒቨርስቲ ማኅበረሰብ አባላት ፈጥነው በመድረስ የተቻላቸውን ሰብዓዊ ድጋፍ በማድረግ ጉዳዩን ለቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲደርስና አስቸኳይ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው ከምስል ጋር ይፋ አድርገዋል። ይሁን እንጂ የደቡብ ክልል፥ የጌዲዖ ዞን፥ የኦሮሚያ ክልል እና የፌደራል ከፍተኛ አመራሮች በተለይም የሰላም ሚኒስቴር እና የፌደራል አደጋ መከላከል ዝግጁነት አመራሮች ጉዳዩን እያወቁ ለማስተባበል ሞከረው የነበረ ቢሆንም፤ በድጋሚ በቪዲዮ ማስረጃ ጭምር ከተጋለጠ በኋላ የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያ ካሚልና የደቡብ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ልክ ጉዳዩን እንደማያውቅ በመምሰል ተፈናቃይ ተጎጂዎችን በአካል ጎብኝተዋል።

በተለይ የጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ እና የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል በከፍተኛ ርሃብ የተጋለጡ ከ45 ሺህ በላይ ተፈናቃዮች ያሉበትን ገደብ ወረዳ መካከል ኮቲት ቀበሌን ብቻ ጎብኝተው በመመለስ የገጎጂዎቹን ቁጥር 13 ሺህ ናቸው በሚል ዝቅ ለማድረግና አደጋውንም ለማሳነስ ሞክረዋል። ይሄ የቀዳማዊ አጽ ኃይለሥላሴ ዘመን የትግራይና ወሎ ርሃብ እንዲሁም የደርግ ዘመን የ1977ቱ ርሃብ መደበቅ ጋር ተመሳሳይ ተግባር መሆኑ ነው። የጌዲዖ ርሃብ የሚለው ርሃቡ በተፈጥሮ ድርቅ ምክንያት የተከሰተ ሳይሆን በአመራሮች እና ጽንፍ የያዙ ዘረኞች የተቀናጀ ቅጣት መሆኑ ነው። ርሃቡን ለመሰበቅ ብቻ ሳይሆን ለማስተባበልም በሶስት ቀን ውስጥ ብቻ የተለያየ ይሐሰት ማስተባበያ መረጃ ለማሰራጨት ተሞክሯል። ግን ለምን? ሰው እንዴት በወገኑ ላይ ይህን ያህል ይጨክናል? ይባስ ብሎ ራሳቸው የኦሮሞ “ጠበቃ” ያደረጉ እና ዘረኝነት በተደጋጋሚ ሲያቀነቅኑ የነበሩ አካላት የመፈናቀሉና ርሃቡ መጋለጡ ለምን አስቆጣቸው? ምናልባት የማፈናቀሉና የርሃቡ ቅጣት ላይ ተባባሪ ነበሩ ወይስ በምስኪን ህፃናትና ሞት የሚገኝ ሌላ ትርፍ ፍለጋ? ያሳዝናል።

የጌዲዖ ማኅበረሰብ “ብሔር” ተኮር ዘረኝነት ላይ መሰረት አድርጎ የተፈፀመው መፈናቀል እና የአመራሮች የተቀናጀ የርሃብ ቅጣት በዝምታ መታለፍ የለበትም። ጉዳዩ በገለልተኛ አካል ምርመራ ተደርጎበት ተሳታፊዎችና ጉዳዩን ለመሸፋፈን የሞከሩ የሚመለከታቸው አካላት በህግ ሊጠየቁ ይገባል። ይሄ በዋናነት የምሥራቅ ጉጂ፥ ምዕራብ ጉጂ እና ጌዲዖ ዞኖች፥ የደቡብ ክልል እንዲሁም የኦሮሚያ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ ለማ መገርሳ እና ካቢኔያቸው፥ የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፥ የፌደራል፥ የኦሮሚያ እና የደቡብ ክልል አደጋ መከላከልና ዝግጁነት ቋቋሚያ) አመራሮች እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን በህግ ሊጠየቁና መልስ ሊሰጡ ይገባል። ምክንያቱን ጉዳዩን በደንብ ያውቁ ነበርና። ከጠቅላይ ሚኒስትሩ በስተቅር የተጠቀሱ አካላት እና አመራሮች ከዚህ ቀደም ችግሩን በአካል ድረስ ሄደው አይተዋልና። ስለዚህ ለተጎጂው የሚደረገውን የሰብዓዊ ድጋፍና ርዳታ ለማጣታልና ከኦሮሞ ህዝብ ጋራ ማያዝ ተገቢ አይደለም። ይሄ የባሰውኑ የለየለት ዘረኝነትና ጥላቻ ነው። ቢያንስ ሰብዓዊነት ተሰምቶን ለተጎጂዎች ቀና ትብብር ማድረግ ቢያቅተን እንኳ ደጋግና ቅን ሰዎች ድጋፍ ሲያደርጉ ከ”ኦሮሞ ብሔር” ስም አስታከን ለምን ተጋለጠ በሚል ግብዝነት ዓይናችን ሊቀላ አይገባም። ስለሆነም ተጎጂዎቹ የጌዴዖ ማኀበረሰብ አባላት በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥቃት ሰለባ ብቻ ሳይሆን የፖለቲካዊ ርሃብ ቅጣት ሰላባም ጭምር መሆናቸው ሊታወቅ ይገባል።

የጌዲዮ ማኀበረስብ የአረንጓዴ ወርቅ “ቡና” የበለፀጉ ታታሪ ገበሬና ነጋዴዎች ናቸው። በድርቅ ምክንያት በርሃብ የሚጎዱ የአካባቢውን ወገን ከመርዳት ባለፈ በርሃብ ምክንያት ለልመና እጅ የሚሰጡም አይደሉም። በዛ ላይ በዓለም ላይ ውድ የሆነውን እና የኢትዮጵያ ቡና (ኮፊ አረቢካ) ልዩ ተፈጥሯዊ ጣዕም የይርጋጨፌ ቡና ብራንድ ብቸኛ አምራችም ናቸው። ጥራት ያለው ተፈጥሯዊ ልዩ የይርጋጭፌ ቡና ወደዓለም አቀፍ ገበያ በመላክምለሀገራችን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ከማስገኘት በተጨማሪ የተፈጥሮ አካባቢ ጥበቃም የተካኑና የተመሰገኑ ታታሪዎች ናቸው። ዛሬ ቀን ጎድሎና በዘረኝነት የፖለቲካ ጥቃት ሰለባ ሆነው ለርሃብ ሲጋለጡ ቢያንስ በሰብዓዊነት ልናዝንላችውና ልንደርስላቸው ይገባል እንጂ ለምን ጥቃታችውና ርሃባቸው ተጋለጠ፥ ለምን ተረዱ በሚል ቡራ ከረዩ ማለት ያስገምታል። ቢያንስ እኮ የክፉ ቀን ደራሽ ባለፀጎች እንጂ በሥንፍና ደኽይተው ለርሃብ የተጋለጡ አልነበሩም። የደረሰባቸው “ብሔር” ተኮር ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣት እንጂ። ይሄ በኢትዮጵያ ያልነበረ አዲስ አስቀያሚና ልዩ ታሪክ ነው። ምንም እንኳን ዴሞክራሲያዊና በህዝብ የተመረጠ መሪ ኖሮን ባያውቅም፤ በሀገራችን የነበሩ ርሃቦች በተፈጥሮ የድርቅ አደጋ ተከስተው መሪዎች ለግል ፖለቲካ ስብዕናቸው ሲሉ (አጼ ኃይለሥላሴና መንግሥቱ) ደብቀዋል እንጂ “ብሔር” ተኮር የዘረኝነት ጥቃት ደርሱ ዜጎች ተፈናቅለው ፖለቲካዊ ርሃብ ጥቃት ደርሶ አያውቅም።

የተፈፀመባቸው እኮ የዘረኝነት ጥቃት ብቻ ሳይሆን ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣትም ጭምር ነው። በዚህ ልናፍርና ሊሰማን ይገባ ነበር። ጉዳዩ ለታሪክም መመዝገብ አለበት። ህዝብን ማፈናቀልና በርሃብ መቅጣት ወንጀል። ይሄ ወንጀል የተፈፀመው በምስኪኑ ኦሮሞ ህዝብ ድጋፍና ይሁንታ አይደለም፤ በአመራሮቹና በደጋፊዎቻቸው እንጂ። ይሄ ደግሞ በ”ኦሮሞ” ስም ራሳቸውን “የመብት” አራማጅና ወኪል አድርገው የሚቆጥሩ “አክቲቪስቶች” ሚና ቀላል አልነበረም። ለዚህም በተለይ ከ2008 ዓ. ም. ጀምሮ የአቶ ጃዋርን፥ አውስትራሊያ ሜልቦርን የሚገኘው አቶ ፀጋዬ አራርሳ፥ ኖርዌይ ኦስሎ የነበረው አቶ ግርማ ጉተማ፥ ሀገር ውስጥ ያለው አቶ አየለ ደጋጋ ፥ አሜሪካ ያለው ኢታና ሀብቴ እንዲሁም አንዳንድ በ #OMN_TV እና #ONN_OnlineTV ላይ በተለያየ ጊዜ “ብሔር” ተኮር ጥላቻ አዘል ንግግሮች እና ውይይት ላይ ሲሳተፉ የነበሩት ተጠቃሾችን ማኀበራዊ ገፅና ቪዶዮ መመልከት ይቻላል። ይሁን እንጂ እስካሁን ድረስ ግለሰቦች አሊያም የፖለቲካ ድርጅቶች በ”አሮሞ” ስምና ሰቆቃ ከመነገድ እና ራስን የህዝብ “እንደራሴ” አድርጎ ከማቅረብ ባለፈ ማንም ጥላቻና ዘረኝነት እንዲሰብክም ሆነ ዜጎችን እንዲያፈናቅል ሥልጣን አሊያም ውክል የሰጠው ኦሮሞም ሆነ ሌላ ብሔር የለም።
Gedeo displacement
ከኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን ተፈናቅለው በጌዲዮ ዞን ገደብ ወረዳ መጠለያ ካሉ የጌዲዮ ተጎጂዎች በከፊል (ፎቶ፡ የጉጂ ዞን ኮሚኒኬሽን)
በአጠቃላይ በሀገርም ሆነ በብሔር ወይም በፖለቲካ ፓርቲ ወይም ድርጅት ከአቻዎቹ ጋር ተወዳድሮና አማራጭ ሐሳብ አቅርቦ በህዝብ ተመርጦ የተወከለ ማንም የለም። ለደረሱትም ሆነ እየደረሱ ላሉ ጥፋቶች ተጠያቂዎች የበደሉ ፈፃሚዎችና ተባባሪዎቻቸው እንጂ ህዝብ አይደለም። ምክንያቱም ህዝብ እንደ ህዝብ አይበድልም፤ በህዝብ የተወከለም የለምና። የበደል ውክልናም ሆነ ውርስ የለም። ስለዚህ በየትኛውም ቦታ ከክፉዎች ጋር አትተባበር።

እውነታው ከላይ የተጠቀሰው ሆኖ ሳለ ራሳቸውን የ”ኦሮሞ” ማኅበረሰብ ተወካይ ወኪል አድርገው የሾሙና ራሳቸውን የመብት አራማጅ አድርገው የሚቆጥሩ አካላት ፤ የጌዲዖ ማኀበረሰብ ፖለቲካዊ ርሃብና ጥቃቱ መጋለጥ ለምን አስቆጣቸው? የምስኪኖች ርሃብና ስቃይ ከኦሮሞ ህዝብ ጋር ምን ያገናኘዋል? ርግጥ ነው። የተፈናቀሉትም ሆነ በደል የደረሰባቸው በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ እና ምዕራብ ጉጂ ዞኖች ውስጥ ነው። በደሉ የተፈፀመባቸው ደግሞ በኦህዴድ/ኦዴፓ ፥ በዘረኝነት ጥላቻ የተገፋፉ ወጣቶች እና በኋላም በአካባቢው በነበሩ የኦነግ ታጣቂዎች ነው። እዚህ ላይ የደቡብ ክልልና፥ በተለይ ለርካሽ ጊዜያዊ ሥልጣናቸው ሲሉ በግፍ ተፈናቃይ ህዝብ ላይ በተፈፀመው ፖለቲካዊ የርሃብ ቅጣት ላይ የደቡብ ክልልና የጌዲዖ ዞን አመራሮች እንዲሁም የተወሰኑ የፌደራል ባለሥልጣናት እጅ አለበት። በተለይም በርሃብ መቅጣትና መሸፋፈኑ ላይ የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን ጉዳዩን በደንብ ያውቁ ነበርና ህግ ካለ ሊጠየቁ ይገባል። ይሄን መካድ አይቻልም።

ሌላው አስቂኝ ነገር መልካም ነገር ሲሆን “እኔ ይህን አድርጌ፥ እገሌ ይህን አድርጎ” ይሉናል፥ ሲወደሱም ምስጋናው እና ውዳሴውን ለግላቸው ጠራርገው ይወስዱና ስንት ዋጋ የከፈለውን እና አስተዋፅዖ ያበረከቱትን ስም ቅርጫት ውስጥ ይጥሉታል። ያው ባለሥልጣን ወይም “አክቲቪስት” ሲበድልና ግፍ ስፈፅም ልክ ኦሮሞን አማክረውና አስፈቅደው ያደረጉ ይመስል፤ በደሉንም ውግዘቱንም ኦሮሞ ላይ የተፈፀመ በማስመስል ለማስፈራራት ይሞክራሉ። ወዴት ወዴት!? ይሄ ግብዝነት ብቻ ሳይሆን ድንቁርናም ነው። የቀድሞው ጭካኙ አቶ ጌታቸው አሰፋ በወንጀል ሲጠየቅ ተመሳሳይ የህወሓት ደናቁርት አቶ ጌታቸውን ከምስኪኑ የትግራይ ህዝብ ጋር አያይዘው “ የትግራይ ህዝብ ላይ የተቃጣ ጥቃት” አስመስለው ካድሬዎቻቸው ህዝቡን አስገድደውና አታለው ሰልፍ አስወጥተው ነበር። ይሄንንም ራሳቸውን ተረኛ ባለሥልጣንባለጊዜ አድርገው የሚያቀርቡልን ድኩማን የኦህዴድኦዴፓ ካድሬዎችን ጭምሮ ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሲኮንኑ ነበር። በዛ እኔም እስማማለሁ። ምክንያቱም አቶ ጌታቸውም ሆነ የህወሓት አመራሮች እንደዛ አረመኔና ጨካኝ እንዲሆኑ የትግራይ ህዝብ ውክልናም ሆነ ድጋፍ አልሰጣቸውምና። ቀድሞንስ የተበደለ ካልሆነ ማን ያውቅና? ህዝቡ ሚኒገረው ልክ እንደዛርው እንደነ ጠቅላይ ሚኒስር ዶ/ር አብይና ካድሬዎቻቸው የምናቧን ኢትዮጵያ አልነበር? የህወሓት አመራሮችን በተለይም የነ መለስ ዜናዊ እና ጌታቸው አሰፋ የፈፀሙትን በደል ከትግራይ ህዝብ እንደለያችሁት ሁሉ በጉጂዎች የተፈፀመውንም በደል ከኦሮሞ ጋር አታገናኙት። በደለኛው ራሱ ይጠየቅ፥ ሥራው ያውጣው።

ጠቅላይ ሚኒስትሩም ሆነ አቶ ለማ መገርሳም ቢሆኑ ሰዎች እንጂ መላዕክት አይደሉም። አንዳንዱም ፈጣሪ አድርጎ ሊስላቸው ሚዳዳው ሁሉ አለ። ይቅር በለን እንጂ። ትናንት ጅልጣን ላይ የነበሩም ሆነ ዛሬ በህዝብ ማዕበል ተገፍተውና ተደግፈው ወደ ሥልጣን የመጡት እነ አብይ፥ ደመቀ፥ ለማ፥ ገዱ ያው ኢህአዴግ ናቸው፤ እንደየ ድርሻቸው የተለያየ ወንጀልብደል ላይም ተሳትፎ የነበራቸው ናቸው። ይሄን እነሱም ሚክዱት አይመስለኝም። ያው ከነበረው የ27 ዓመታት ሰቆቃ ወደ ለውጥ መግባታችን ጥሩ፥ “የሚታየውን ብሩህ ለውጥ” ማጨለምና እንቅፋት መሆን ጥሩ አይደለም በሚል እንጂ እያንዳንዱ ዶሲው ከቢሮው መደርደሪያ ቢፀዳም ከያንዳንዱ የጥቃት ሰለባ ወገን እና ተባባሪዎቻቸው ህሊና ሊጠፋ አይችልምና ድጋፉንም ቢሆን በልክ እናድርገው። በየትኛውም ቦታና ጊዜ በደልን እንፀየፍ። መልካም ነገሮችን እናበረታታ። ከዛ ውጭ የሚፈፀሙ በደሎችን ደብቁልን እያሉ ከምስኪኑ ህዝብ ጋር ለማገናኘት መጋጋጥ የትም አያደርስም። የህወሓትም ሰዎችም ቢሆኑ ይህንንም ነበር ያደረጉት። ግን አልጠቀማቸውም። እና ያንን የቆሸሸ መንገድ መልሶ መድገም ጭፍኑ እና ላሞኛችሁ” ዓይነት የጅል ጨወታ ስልሆነ ጉድፍና ቆሻሻን ነገር ከ”ብሔር” ጋር ማያያዝ ተውትይቅርባችሁ። በ”ኦሮሞ” ስም ራሳቸውን ባጩ “ልሂቃን” እና “አክቲቪስቶች” በስሙ፥ በአስከሬኑ እና ሰቆቃው እየተነገደ ለነበረው ኦሮሞ ማኅበረሰብ ልክ ለፖለቲካ መቆመሪያ የያ ርካሽ ትውልድ እንዳደረገው ዛሬም የልቅሶና የበታችኘት፥ የማስፈራሪያና ዛቻ ስሜት ቅስቀሳን ፖለቲካ አይመጥነውም።

በሰው በደል የሚደሰት ኦሮሞ፥ አማራ፥ ትግሬ፥ ሶማሌ፥ ጌዲዖ፥ አፋር፥ ሲዳማ፥ አኝዋክ፥ ጋሙ፥ ሀዲያ፥ ጉራጌ፥ ስልጤ፥ ሐረሬ፥ … ወዘተረፈ የለም። ህዝብ እንደህዝብ በደል የለበትም፤በጅምላ አንዱን ወገን ከሌላው በመለየት በደልም አያደርስም። ልክ ውዳሴና ሙገሳውን ለግላችሁ እንደምታደርጉት የፈፀማችሁትን በደልና ልለበደሉ ያላችሁን ተሳትፎም ኃላፊነቱን ለወንጀለኞችና ተባባሪዎች እንተው። የተጎዱ ወገኖቻችንን ግን እንታደግ። ሰብዓዊነት ዜግነትም ሆአ ብሔር የለውም። ብሔር ሰውን አልፈጠረም፤አይፈጥርም። ሰው ነው ብሔርንም፥ ባህልንም የፈጠረው። ስለዚህ ቅድሚያ ሰው እንሁን፤ ለሰብዓዊነት ይሰማን። በዛ ላይ የኦሮሞ ማኀበረሰብ እንደማንኛውም የኢትዮጵያ ማኀበረሰብ ነው። ማኅበራዊ ህይወት የሚመቸው፥ ከመንደርና ቀበሌኛ አስተሳሰብ ይልቅ ሰፋ ያለ ቦታና አድማስን የሚያስቀድም፥ ቀናዒ፥ ኃይማኖትና ሥርዓት ያለው ማኅበረሰብ ነው።

በስሙ የምትነግዱ “ሊሄቃን” እና አክቲቪስቶች” ግን በተቃራኒው ጥላቻ፥ ቀበሌኛ፥ መንደርተኛ፥ የበታችነትና ተጠቂነት ስነ ልቦና ላይ ቆሞ የቀረ ጊዜ ያለፈበት ኋላቀር አስተሳሰብ ላይ ናችሁ። በዛ ላይ ትውልዱም ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ሆኖ ከአድማስ ወዲያ አስቦና ሰርቶ፤ ራሱን፥ ቤትሰቡን፥ ማኅበረሰቡን፥ ሀገሩን፥ አህጉሩን እና ዓለምን ሊረዳ የሚችልበት ጉልበቱን፥ አእምሮና ጊዜውና በጥላቻ፥ በተጠቂነት፥ መንደርተኝነትና ቀበሌኛ ስነልቦና ውስጥ አታስቀሩት። የትናንቷ ዓለም ዛሬ የለችም። የዛሬዋ ደግሞ ነገ አትኖርም። ነገ ደግሞ ከዛሬው የበለጠ ብዙ ፈታኝ ውስብስብ የውድድር ዓለም ነው የሚጠብቀን። ከትንሽ ጊዜ በኋላ አይደለም የመንደር “ብሔር” ተኮር ቀበልኛ ኋላ ቀር አስተሳሰብ ቀርቶ ኢትዮጵያ ራሷ ትንሽዬ መንደር የምትሆንበት ጊዜ ሩቅ አይደለም። ያውም ዓለም በመሰረተ ልማትና በዲጅታል ትክኖሎጂ ከምናስበው ፍጥነት በላይ እየተሳሰረ ባለበት በዚህ ወቅት። እንኳን የስግብግብ መንደርተኛ ፖለቲካ ላይ እኝኝ ብለን ቀርቶ ምሥራቅ አፍሪካ እንኳ አንድ ላይ ብንቀናጅ እየመጣ ያለውን ፈታኝ የውድድር ህይወት መቋቋም አንችልም። ከመቼው ጊዜ በላይ የጠነከረ ህብረት፥ አንድነትና መከባበር ያስፈልጋል። ለአንዱ ሚያስፈልገው መልካም ነገር ሁሉ ለሌላውም ያስፈልገዋል። አንዱ ላይ የንፈፅመው በደልና ጥላቻ ሁሉ ይዋል ይደር እንጂ አፀፋዊ መልስ ይዞ መምጣቱ የማይቀር ነው። በዛ ላይ መቶ ዓመት ለማንኖርባት ጊዜያዊ ዓለም።

በርግጥ አውቃለሁ። በ”ኦሮሞ” ስም የሚነግዱ ኋላቀር እና የዘረኝነት ቅስቃሳና ፖለቲካ የሚያራምዱ በምቾት የሚኖሩበት የሌላ ሀገር ፓስፖርትና መኖሪያ ቤት አንዳንዶቹ በአሜሪካ፥ አውሮፓና አውስትራሊያ አላቸው። እንደ ሀገር ኢትዮጵያ ብትጎዳ፥ ወይም እንደ ህዝብ ኦሮሞ ቢጎዳ እነሱ ሌላ የምቾት መኖሪያሌላ ሀገር ስላላቸው ሳይነግሩህ በቦሌ ተሳፍረው ነው ሚሄዱት። ከዛ ባንተ አስከረንና ሰቆቃ ገንዘብ ይለቃቅማሉ። አለቀ። አንተ ሰላም ከሆንክና አተመቸንህ ግን ባንተ ስም ገቢ የላቸውም። ከዚህ የተለየ ግብ አላቸው ካልክ በስምህ ምለው ተገዝተው የሚነግዱትን ፍላጎታቸውና ዓላማቸውን እንዲሁም ምክንያታቸውን ጠይቅ። ከዛ ለምን የሌላ ሀገር ፓስፖርት ይዘው እንደሚኖሩ ጠይቅና፤ ከዛ እሱን ትተውካንተ ጋ ያለውን ተካፍለው እንዲኖሩ ጠይቃቸው። ያኔ ምላሽና ተግባራቸውን ተመልከት። በነጋታው ቻዎ እንኳን ሳይሉህ ደጋግ፥ ሥልጡን እና ሰብዓዊነት የሚሰማቸው ሰዎች ወደሰጧቸውና ወደፈቀዱላቸው የምቾት ሀገር ይመጣሉ። የሚያሳዝነኝ ምስኪኑ ወጣት ነው። አጣችም ደኽየችም ያለችው ያቺው ምስኪን አንዲት ኢትዮጵያ ናት። ተከባብሮ በአንድነት በሰላም ኖሮና ሰርቶ ፤ወጣቱ ተረጋግቶ እንዳይኖር በሰቆቃው የጉስቁልናው ህይወቱ ለሚነግዱ መቆመሪያ ማድረጉ ነው። ወዳጄ! ከሞት በኋላ ትንሳኤ ኃይማኖት ላይ እንጂ ምድርና ፖለቲካ ላይ የለም። ከሞትክ ሞትክ ነው፤ አበቃ። ስትሞትና ስትጎዳ ምታጎለው ራስህን እና ቤትሰብህን ሌላ ማንንም አይደለም። በሞትህ የሚጠቀመው ደግሞ፥ የሬሳ ሳጥን ሻጭ፥ የመቃብር ጉድጓድ ቆፋሪና በሞትህና ስቃይ ቆምሮ የሚከብር አረመኔን ብቻ ነው። ስለዚህ ነፃ ሆነህ፥ ሰልጥነህ፥ ጤናማ ደስተኛ ሆነህ ከሁሉም ጋር በፍቅር ኑር።

አንተ ላይ እንዲፈፀም የማትፈልገውን መጥፎ ነገር በሌሎች ላይ አታድርግ፤ ላንተ እንዲሆንል የምትመኘውን መልካም ነገር ሁሉ ያለምንም አድሎ ለሌሎችም አድርግ!! ምክንያቱም ሌላውም ሰው ልክ እንዳንተ መልካም ነገሮች የሚያስፈልጉት ሰው ነውና።

የለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ አስተዳደር ቤቶችን የማፍረስ ዕርምጃና የተፈናቃዮች ጩኸት

ሻሂዳ ሁሴን

በለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ ከማስተር ፕላን ውጪ ተገንብተዋል የተባሉ ከ12,000 በላይ ቤቶች እንዲፈርሱ መወሰኑና ቤቶቹም መፍረስ መጀመራቸው ውዝግብ አስነስቷል፡፡ እስካሁን በከተማው በሚገኙ ሁለት ቀበሌዎች ማለትም ቀበሌ 03 የካ ዳሌና ቀበሌ 01 አባ ኪሮስ በመባል በሚታወቁ ሥፍራዎች ከ930 በላይ የሚሆኑ ቤቶች መፍረሳቸው ተነግሯል፡፡ የአካባቢዎቹ ነዋሪዎች የተሰጣቸው የማስጠንቀቂያ ጊዜ አጭር መሆኑን፣ እየፈረሱ ያሉትም የተመረጡ ቤቶች ናቸው ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡ ካርታ ለማግኘት ተመዝግበው በመጠባበቅ ላይ የሚገኙ ነዋሪዎች ቤቶች እየፈረሱ እንደሆነ ሪፖርተር ያነጋገራቸው ገልጸዋል፡፡ ድርጊቱንም የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር አቶ ለማ መገርሳ እንዲያስቆሙ ነዋሪዎች ጠይቀዋል፡፡ የኦሮሚያ ክልል ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ አድማሱ ዳምጠው፣ ሕገወጥ ግንባታዎችን የማፍረስ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል፡፡

Legetafo_social crises 2019 በገለጣፎ ለገዳዲ ከተማ አስተዳደር እንዲፈርሱ ከተወሰነባቸው ከ12,300 በላይ ቤቶች ውስጥ አንዱ

ሪፖርተር በሥፍራው ተገኝቶ ያነጋገራቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ሜዳ ላይ መበተናቸውን ገልጸዋል፡፡ በተለይ በቀበሌ 03 የመፍረስ ዕጣ ከገጠማቸው ቤቶች የአንዱ ይህንን ይመስላል፡፡

ሦስት ክፍሎች ያለው ቤት ግድግዳው በከፊል ፈርሷል፡፡ ጣራውም ሙሉ ለሙሉ ተነስቷል፡፡ በርና መስኮትም የለውም፡፡ ሊወድቅ ቋፍ ላይ የደረሰውን የጭቃ ግድግዳ ተደግፎ ከቆመው መሰላል ውጪ ምንም አይታይም፡፡ ከወንዝ ዳርቻ የተሠራው ቤት ወደ ፍርስራሽነት የተቀየረው ዕድሜ ተጭኖት ወይም የቦምብ ፍንጣሪ መትቶት አይደለም፡፡ ሕገወጥ ግንባታ ነው ተብሎ በአፍራሽ ግብረ ኃይል በትዕዛዝ የፈረሰው ረቡዕ ረፋዱ ላይ ነበር፡፡

‹‹ጠላ ሸጬ ነው ቤቱን የሠራሁት፤›› የሚሉት ወይዘሮ ግን ቤቱ ከፈረሰ ሰዓታት ያለፉት ቢሆንም አልተፅናኑም፣ ከድንጋጤያቸውም አልተላቀቁም፡፡ ‹‹ሕገወጥ›› የተባለው ቤታቸው እንደሚፈርስና ንብረታቸውን እንዲያወጡ የሚገልጽ ደብዳቤ የደረሳቸው ቅዳሜ የካቲት 9 ቀን 2011 ዓ.ም. እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ በሰዓቱ ደብዳቤውን የተቀበለችው ኮተቤ ሜትሮፖሊታን ዩኒቨርሲቲ የምትማር ልጃቸው በድንጋጤ መታመሟን፣ እስካሁንም እንዳልተሻላትና ወደ ትምህርት ገበታዋ እንዳልተመለሰች ሲናገሩ እያነቡ ነው፡፡ ‹‹ለነገሩ ደንዳና ነኝ፤›› የሚሉት ወይዘሮዋ ቢሆኑም፣ አፍራሽ ግብረ ኃይሉ ግድግዳውን በላያቸው መናድ ሲጀምር ራሳቸውን ስተው እንደ ነበር ይናገራሉ፡፡ መናገርና መስማት አትችልም የሚሏት ትንሽ ልጃቸው ቤታቸውን እያፈረሱ የነበሩትን ሰዎች ልብስ እየጎተተች ስትለምናቸው እንደበር የሰሙትም፣ ከወደቁበት ሲነሱ ሰዎች ነግረዋቸው እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

‹ቤቱን ለቃችሁ ውጡ› የሚለው ደብዳቤ ሲደርሳቸው፣ ‹‹እውነት አልመሰለኝም ነበር፤›› ብለዋል፡፡ የተሰጣቸው የአራት ቀናት ቀነ ቀጠሮም አጭር ነበርና መፍትሔ ለማፈላለግም ሆነ ንብረታቸውን ለማውጣት በቂ ስላልነበረ፣ ከማስፈራሪያነት ያለፈ ሚና ይኖረዋል ብለው እንዳላሰቡ ተናግረዋል፡፡ ረቡዕ የካቲት 13 ቀን 2011 ዓ.ም. ረፋዱ ላይ አፍራሽ ግብረ ኃይሉ ግድግዳቸውን መናድ ሲጀምር ግን እያነቡ ከመለመን ባለፈ ንብረታቸውን ለማውጣት እንኳን ፋታ አለማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡

“ነገሮች ከአዕምሮዬ በላይ ራሴን ስቼ ወደቅኩ፤” ብለው፣ ወደ ራሳቸው ሲመለሱ ጠላ ሸጠው የገነቡት ቤት ወደ ፍርስራሽነት ተቀይሮ እንዳገኙት ተናግረዋል፡፡ የቀረላቸው ነገር ቢኖር በቆርቆሮ በር የሚዘጋው ትንሹ ኩሽናቸው ነው፡፡ በማንኛውም ሰዓት ሊያፈርሱት ይችላሉ ብለው በሚሠጉበት ኩሽናቸው ውስጥ አዳራቸውን ማድረጋቸውን፣ ከፍርስራሹ ውስጥ የወጣ ንብረታቸውን ደግሞ ቤታቸው እንደሚፈርስ ቀነ ቀጠሮ በተሰጣቸው ጎረቤቶቻቸው ቤት በታትነው ማስቀመጣቸውን አስረድተዋል፡፡

ባለትዳርና የአምስት ልጆች እናት የሆኑት ወይዘሮዋ ያለ ወትሯቸው ሜዳ ለሜዳ ይዞራሉ፡፡ አፉን ከፍቶ የቀረ ቤታቸው የሚያርፉበት ባይሆንም ቤት እንዳለው ሰው ወደ ፍርስራሹ ያመራሉ፡፡ ‹‹ከእነ ልጆቼ ሜዳ ላይ ቀርቻለሁ፤›› አሉ ትንሽ ልጃቸውን አዝለው ወደ ተቆለለው ፍርስራሽ ላይ እየወጡ፡፡ በመንደሩ ተመሳሳይ ችግር የደረሰባቸው ብዙዎች ስለሆኑ እየዞሩ ሌሎችንም ያፅናናሉ፡፡

እንደ ወይዘሮዋ ሁሉ መውደቂያ ባያጡም ጎረቤታቸው ወ/ሮ መቅደስ ተሰማ ግን እውነታውን መቀበል ተስኗቸዋል፡፡ ‹‹ሊፈርስ ነው የሚባል ነገር ከሰማሁ ቀን ጀምሮ እንዳለቀስኩ ነው፡፡ ደብዳቤው ቅዳሜ ዕለት በእጃችን ሲገባ ያልሄድንበት ቦታ የለም፡፡ ነገር ግን ማንም የደረሰልን አካል የለም፡፡ የቀን ጨለማ ነው የሆነብን፡፡ ይኼንን ቤት ለመሥራት የለፋሁትን እኔ ነኝ የማውቀው፤›› አሉ ወደ ተከመረው ፍርስራሽ በእጃቸው እያመለከቱ፡፡

በአካባቢው ይኖሩ ከነበሩ ከአንድ ግለሰብ የገዙትን ቤት አድሰውና ባለው ትርፍ ቦታም ቤት ገንብተው ኑሮ ለመጀመር ነገሮች ቀላል አልነበሩም ይላሉ፡፡ በአንድ የመንግሥት መሥሪያ ቤት ተቀጥረው እንደሚሠሩና በወር የሚያገኙትም 3,000 ብር እንደማይሞላ ይናገራሉ፡፡ ‹‹ያለው ሰው እኮ እዚህ አይኖርም፡፡ አማራጭ የሌለን ድሆች ነን እዚህ ገዝተን የምንገባው፤›› በማለት ዕንባቸውን አዘሩ፡፡

የፈረሰባቸውን መኖሪያ ቤት ለመሥራት ለዓመታት እንደተቸገሩ ይናገራሉ፡፡ ቆርቆሮ ለመምታት፣ ግድግዳ ለማቆም በወር ከሚያገኙት ላይ እየቆጠቡ ዕቁብ መጣል እንደነበረባቸው ያስታውሳሉ፡፡ የዋናው ቤት ግንባታው ባያልቅም ቀስ በቀስ ያልቃል በማለት ከአራት ዓመታት በፊት ገብተው መኖር እንደጀመሩም ያስረዳሉ፡፡ በአንዱ ዕቁብ በር፣ በሌላው ኮርኒስ እያሠሩ መደበኛ ቤት ለመሆን አንድ መስኮትና የፍሳሽ ማስወገጃ ሲቀረው፣ ሕገወጥ ግንባታ ተብሎ ረቡዕ ዕለት መፍረሱን ተናግረዋል፡፡ የቀራቸው ለተከራይ የሰጡት ሰርቪስ ቤት ቢሆንም፣ የቱ እንደሚፈርስና የቱ እንደሚቀር ስለማይታወቅ መጨረሻቸውን አላወቁም፡፡ “የዋናውን ቤት የተወሰነ ክፍል አፍርሰው ይኼ ቀርቶልሻል እጠሪው ካሉ በኋላ ነው ተመልሰው የቀረውን ሆ ብለው ያፈረሱት፡፡ አሁን ጭንቀት ሊገድለኝ ነው፡፡ የማይወለድ ልጅ ማማጥ ሆኖብኛል፤” አሉ እንደገና እያነቡ፡፡

አራት ልጆች የማሳደግ ኃላፊነት እንዳለባቸው፣ ከዘራቸውን ተደግፈው የሚቆዝሙ ወላጅ አባታቸውን የማስተዳደር ኃላፊነትም የእሳቸው መሆኑን መኖሪያ ቤታቸው በላያቸው የፈረሰባቸው ወ/ሮ መቅደስ ይናገራሉ፡፡ አንገት ማስገቢያ ጎጆ ለመቀለስ ባወጡት ወጪና ልፋት ውጤቱን ሳያዩ ስለፈረሰባቸው ሐዘን እንደሰበራቸው አክለዋል፡፡ ቤቱን ለመሥራት ከፍለው ያልጨረሱት የዕቁብ ዕዳም ዕረፍት ነስቷቸዋል፡፡ በሁኔታው ተስፋ ቆርጠው አፍራሾቹን ቆመው ሲመለከቱ እንደነበር፣ ንብረታቸውን ያወጡላቸውም ዕድርተኞቻቸው እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡ አለኝ የሚሏቸው የቤት ዕቃዎች ወደ አንድ ጎን ተከምረው አቧራ ይጠጣሉ፡፡ 276 የሚል የቤት ቁጥር የሠፈረበትን ቆርቆሮ የያዘ የብረት በር ከአንዱ ጥግ ተሸጉጧል፡፡ ወይዘሮ መቅደስ የቤት ቁጥር ከተሰጣቸው ዓመታት እንደተቆጠሩ ይናገራሉ፡፡

በራፋቸው ላይ ከተተከለው የኤሌክትሪክ ፖልም የኤሌክትሪክ ኃይል ያገኛሉ፡፡ ከዓመታት በፊት አንድ ክፍል ቤት ያለውን ግቢ የገዙት በግል ውል ነበር ይላሉ፡፡ ‹‹ማዘጋጃ ቤት በሊዝ ለባለሀብት ይሸጣል እንጂ ለምን ለእኔ ይሸጥልኛል? ባለሀብት ደግሞ እንዲህ ዓይነት ቦታ ላይ ምን ይሠራል?›› ሲሉ ለኑሮ የማይመቹ ቦታዎች ላይ ተገፍቶ የሚወጣው አማራጭ ያጣ እንደ እሳቸው ያለ ደሃ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡

ቦታው ላይ ሲኖሩ ካርታ ባያገኙም ሕጋዊ መሆናቸውን የሚያመላክቱ የልማት እንቅስቃሴዎች ውስጥ ተሳታፊ እንደነበሩ ያስረዳሉ፡፡ ‹‹የአከራይ ተከራይ ግብር ለመክፈል የሚመለከተው አካል ከቀናት በፊት አነጋግሮን ነበር፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ይኼንን እየተነጋገርን ባለንበት ሰዓት ደብዳቤው እንደ ዱብ ዕዳ ዓርብ ወጪ ተደርጎ ቅዳሜ እጃችን ላይ ገባ፡፡ በአራት ቀናት ውስጥ ምን ማድረግ እንችላለን?›› ብለው ሌላው ቢቀር እንዲወጡ የተሰጣቸው የጊዜ ገደብ ነገሮችን ያላገናዘበ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ቀረልኝ የሚሉት ተከራዮች ይኖሩበት የነበረው ቤትም እንደማይፈርስ ማረጋገጫ የለም ይላሉ፡፡ ምክንያቱም ከቀናት በፊት በእጃቸው የገባው በኦሮሚፋ የተጻፈው ደብዳቤ የቱ እንደሚፈርስና የቱ እንደሚቀርላቸው አይገልጽም፡፡

አካባቢውን በአንድ ጊዜ ወደ ፍርስራሽነት የቀየረው ዘመቻ በርካቶችን ሐዘን ላይ ጥሏል፡፡ ለገጣፎ የሚገኘው የካ ዳሌ 03 ቀበሌ ልጅ አዋቂ ሳይል ሁሉም በአንድነት የሚያነባበት መንደር ሆኖ ነበር ያረፈደው፡፡ እንደ ነገሩ ተበታትነው ከሚታዩ የቤት ዕቃዎች፣ የቆርቆሮና የፍርስራሽ ክምር ባሻገር የሚገቡበትን ያጡ በትካዜ የተዋጡ ሰዎች ብዙ ናቸው፡፡ ማረፊያ እንዳጡ ሁሉ በየመንገዱና በየጥጋጥጉ እንደቆሙ ይተክዛሉ፡፡ የደረሰባቸውን የሰሙ ዘመድ አዝማዶች ከያሉበት እየሄዱ እከሌን ዓይታችኋል እያሉ የዘመዶቻቸውን አድራሻ ሲፈልጉ ታይተዋል፡፡ ጥቂት የማይባሉ የአካባቢው ነዋሪዎች ‹ቤት ለእምቦሳ› ብለው የመረቁላቸው ቤቶች ወደ ፍርስራሽነት ተቀይረዋልና ሜዳ ላይ ቆመው ያወራሉ፡፡ ምርር ብለው የሚያለቅሱ ዘመዶቻቸውን ያፅናናሉ፡፡ ሰብሰብ ሲሉ ‹የአንተም ቤት ፈረሰ?› እየተባባሉ የቁም ቅዠት የሆነባቸው ክስተት በሌላው ላይ ደርሶ እንደሆነ ይጠያየቃሉ፡፡ ‹የእኔ ቤት እዚያ ጋ ነበር› እያሉ ነው የፈረሰባቸውን ለሰዎች የሚያሳዩት፡፡ የፈረሰባቸውን ሲያፅናኑ የቆዩ ደግሞ ተራው የእነሱ ሆኖ ቤታቸው ሲፈርስ እያዩ እንደ አዲስ ይደነግጣሉ፣ ያለቅሳሉ፡፡

“100 የሚደርሱ ሰዎች ሆ ብለው መጥተው አንድ፣ ሁለት፣ ሦስት ብለው ግድግዳ ገፍተው ሲንዱ ማየት ግራ ያጋባል፡፡ ከማልቀስ ውጪ ምንም ማድረግ አይቻልም፤” ይላሉ ወይዘሮ መቅደስ፡፡ የሚፈርሰውን ቤት መታደግ ባይቻልም ጥረው ግረው ያፈሩት ንብረት በፍርስራሽ እንዳይዋጥ ጎረቤት ተሯሩጦ ለማትረፍ ይረባረባል፡፡

ቄስ ኪሮስ ዓለምነህን ሪፖርተር ያገኛቸው ከፈረሰው ቤታቸው ውስጥ የወጣ ንብረታቸውን በጎረቤቶቻቸው ዕገዛ ወደ አንድ በኩል ሲቆልሉ ነበር፡፡ ቄሱ በሆነው ነገር ከመደንገጣቸው የተነሳ ግራ መጋባት ይታይባቸዋል፡፡ ጎረቤቶቻቸው ግቢያቸውን ሞልተው የተበተነውን ንብረታቸው ዝናብ እንዳይመታው ቆርቆሮ ይመቱላቸዋል፡፡

እናቶች በየጥጋጥጉ እንደተቀመጡ ያለቅሳሉ፡፡ ከአርሶ አደር ላይ በ250 ሺሕ ብር የገዙትን ቤት አፍርሰው በሚፈልጉት ዲዛይን ለማሠራት ብዙ ገንዘብ ማፍሰሳቸውን፣ ቤቱን የሠሩትም በ2003 ዓ.ም. እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ ቦታውን ገዝቶ ቤት ለመሥራት ከዘመድ አዝማድ ብዙ ገንዘብ መበደራቸውንና እስካሁንም ያልተከፈለ 80 ሺሕ ብር የሚሆን ውዝፍ ዕዳ እንዳለባቸው ይናገራሉ፡፡

ቄስ ኪሮስ በአካባቢው ሕጋዊ ነዋሪ መሆናቸውን የሚያሳይ የቀበሌ መታወቂያ አላቸው፡፡ ለመንገድ፣ ለውኃና ለኤሌክትሪክ የከፈሉበት ደረሰኝም አላቸው፡፡ በሌሎች ማኅበራዊ ግዴታዎች ክፍያ የፈጸሙባቸው ሕጋዊ ደረሰኞች ይዘዋል፡፡ የመኖሪያ ቤት ሽያጭ ውልም በእጃቸው ይዘዋል፡፡

‹‹ከ2003 ዓ.ም. ጀምሮ ዕዳ ላይ ነው ያለሁት፡፡ ቤቱን ለመገንባት ከ500 ሺሕ ብር ከላይ አውጥቻለሁ፤›› በማለት፣ ዕዳቸውን ከፍለው በወጉ መኖር ሳይችሉ የቤታቸው መፍረስ የተደበላለቀ ስሜት እንዳሳደረባቸው ይናገራሉ፡፡ ቤቱን በአስቸኳይ ለቀው እንዲወጡ የሚያሳስበው ደብዳቤ የተጻፈውና እጃቸው ላይ የደረሰው በአጭር ጊዜ ነው በማለት፣ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ጊዜው እጅግ አጭር እንደሆነና ነገሩን ለመረዳትም ፋታ ሳይሰጣቸው ሕይወታቸው እንዳልነበረ መሆኑን ይናገራሉ፡፡

ሌላው ቢቀር ቀልባቸውን ሰብስበው ንብረታቸውን በመልክ መልኩ ለማሰናዳት እንኳ አልሆነላቸውም፡፡ ሕጋዊ ነዋሪ መሆናቸውን የሚመሰክሩ ሰነዶችን ቅጂ እንደያዙ ፍርስራሽ የዋጠው ቅጥር ግቢ ውስጥ ቆመዋል፡፡ ዕዳ ገብተው የሠሩት ቤት ፈራርሶ ማየታቸው በቤታቸው እንግድነት እንዲሰማቸው እንዳደረጋቸው ይናገራሉ፡፡

ከጎናቸው ሆኖ የሚያፅናናቸው የ29 ዓመቱ አቶ ቀናው በላይ ደግሞ 150 ካሬ ላይ ያረፈው ቤቱ ሙሉ ለሙሉ ፈርሶበት ሜዳ ላይ መቅረቱን ይናገራል፡፡ ደሳሳ ቤት የነበረውን ቦታ በ2004 ዓ.ም. ገዝቶ ከ300 ሺሕ ብር በላይ አውጥቶ የብሎኬት ቤት እንደሠራ፣ ባለትዳርና የልጅ አባት መሆኑን፣ በቴክኒክና ሙያ ከሰባት ዓመታት በፊት በዲፕሎማ ቢመረቅም፣ በተማረበት ሙያ ሥራ ማግኘት አለመቻሉን ያስረዳል፡፡

ቤተሰቡን የሚያስተዳድረውም ፑል ቤት ተቀጥሮ እየሠራ በሚከፈለው 1,500 ብር ቢሆንም፣ የራሱ የሚለው ቤት ስለነበረው ግን ብዙም እንደማይቸግረው፣ ዓለም የተደፋበት የመሰለው ሕገወጥ ነህ ተብሎ ቤቱ ሲፈርስበት መሆኑን ገልጿል፡፡ ‹‹ቤቴ የፈረሰው ማክሰኞ ነው፡፡ ‹‹አሁን ያለሁት አንድ ወዳጄ ዘንድ ተጠግቼ ነው፡፡ መንግሥት አካባቢውን ለማልማት ፈልጎ ከሆነ ደስ ይለናል፣ ግን እኛ የት ሄደን እንውደቅ?›› ሲል ይጠይቃል፡፡ ‹‹ከአሁን በኋላ የሚጠብቀኝ የጎዳና ሕይወት ነው፡፡ ሚስቴንም ወደ ቤተሰቦቿ እልካለሁ፡፡ ከቻሉ ሁላችንንም ወደ ትውልድ ቀዬአችን የምንመለስበትን ገንዘብ ይስጡን፤›› ይላል፡፡

ቴሌቪዥን፣ ፍሪጅ፣ ቁም ሳጥን ሳይወጣ የፈረሰባቸው፣ ፅዋ እንኳ ሳይወጣ በላያቸው የፈረሰባቸው፣ እንዲሁም ሁኔታው በፈጠረባቸው ድንጋጤ ከታመሙና ራሳቸውን ስተው ከወደቁ ባሻገር የከፋ ነገር የገጠማቸውም መኖራቸው ይሰማል፡፡

ጎረቤቶቿ ዓረብ አገር ሠርታ ባጠራቀመችው ገንዘብ ከጎናቸው ቤት ገዝታ እንደምትኖር፣ ቤቱ ላይዋ ሲፈርስ ግን ተስፋ ቆርጣ ራሷን ማጥፋቷንና አፍራሽ ግብረ ኃይሉ በአምቡላንስ እንደወሰዳት የአካባቢው ነዋሪዎች ይናገራሉ፡፡ አስከሬኗ የትና በምን ዓይነት ሁኔታ ላይ እንዳለም አይታወቅም ብለዋል፡፡ ዘመድ ይኑራት፣ አይኑራት የደረሰባትን ይስሙ፣ አይስሙ የሚያውቅ የለም ብለው ወደ ፍርስራሽነት የተቀየረው ቤቷና እሷ በአንድ አፍታ ታሪክ ሆነው መቅረታቸውን ይናገራሉ፡፡

ዱብ ዕዳ የሆነ ክስተት እንደ አቶ ጌታቸው ህያሴ ያሉ በአካባቢው ተሰሚነት ያላቸውን ሰዎች እንኳ አላለፈም፡፡ አቶ ጌታቸው ከ2000 ዓ.ም. ጀምሮ በአካባቢው እንደሚኖሩ ይናገራሉ፡፡፡ ዓምና ደግሞ የቀበሌውን ሊቀመንበር አስፈቅደው በዘመናዊ መንገድ ከብቶች ማርባት ጀምረዋል፡፡ በለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ አስተዳደር የካ ዳሌ 03 ቀበሌ አሉ የተባሉና ጠንካራ የልማት እንቅስቃሴ የሚያደርጉ እንደሆኑ ይነገርላቸዋል፡፡ ‹‹ይኼ ሁሉ ነገር ሲሠራ አብረውን ነው፡፡ ሁሉንም ነገር ያውቃሉ፡፡ ገና ሲጀመር ማስቆም ይችሉ ነበር፤›› ይላሉ፡፡ እንደ እሳቸው ገለጻ፣ ከብቶቹን ለማርባት ከ500 ሺሕ ብር በላይ ወጪ አድርገው ወደ ሥራ ሲገቡ የከለከላቸው አልነበረም፡፡ በዘመናዊ መንገድ የገነቡት የከብቶች በረት እንዲፈርስ ሲደረግ ግን ብዙ ነገር ማጣታቸውን ይናገራሉ፡፡

አቶ ጌታቸው የአካባቢው ወጣቶች የልማት ኮሚቴ አባል ናቸው፡፡ ነዋሪዎች ገንዘብ እያዋጡ መንገድና የተለያዩ የመሠረተ ልማት አውታሮች እንዲሟሉ እያስተባበሩ ከ2004 ዓ.ም. ጀምሮ ሲሠሩ መቆየታቸው ይነገርላቸዋል፡፡ ነዋሪዎች ለተለያዩ የልማት እንቅስቃሴዎች አሥር፣ አሥር ሺሕ ብር እንዲከፍሉ ተደርጎ አካባቢው መልማቱን፣ ቤታቸው ሕገወጥ ተብሎ ከፈረሰባቸው ነዋሪዎች መካከል ሪፖርተር ያነጋገራቸው አብዛኞቹ ገንዘብ አዋጥተው አካባቢውን ማልማታቸው ይነገራል፡፡ ‹‹ኮሚቴአችን በልማት አንደኛ ተብሎ የተሰጠን የምስክር ወረቀት ቤት አለኝ፤›› የሚሉት አቶ ጌታቸው፣ ‹‹ከማዘጋጃ ቤቱ ጋር ተባብረው አካባቢውን ሲያለሙ የነበሩ ነዋሪዎች ሳይቀሩ ሕገወጥ መባላቸው ግር አሰኝቶኛል፤›› ይላሉ፡፡

የአካባቢው ነዋሪዎች ይህንን ያህል ገንዘብ አውጥተው ቤት ሲገነቡና አካባቢውን ሲያለሙ ዝም ተብሎ አሁን እንዲፈርስ መደረጉ ብዙዎችን አስቆጥቷል፡፡ ግንባታውን ከጅምሩ ማስቆም ሲቻል ገንዘብ እየተቀበሉ ፈቃድ የሚሰጡ የአመራር አካላት መኖር፣ ሌሎችም እንዲገነቡ ያደፋፍር እንደነበር ነዋሪዎቹ እየተናገሩ ነው፡፡ አብዛኞቹ ቤቶች ሲገነቡ አሥር ሺሕ ብርና ከዚያ በላይ ለቀበሌው አስተዳደር አካላት ይከፈል ነበር ተብሏል፡፡

ሕጋዊ ነዋሪ እንደሆኑ የሚያሳይ የቤት ቁጥር፣ የነዋሪነት መታወቂያ፣ የኤሌክትሪክና የውኃ አገልግሎት ካገኙ በኋላ ሕገወጥ ተብለው መፈናቀላቸው ሌላ አስተዳደራዊ ችግር ቢኖር ነው ያሉም አሉ፡፡፡ በቀናት ውስጥ ቤታቸውን እንዲለቁ የሚያዘው ደብዳቤ እንደደረሳቸው በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን በኩል ድምፃቸውን ያሰሙም፣ ‹ማስፈራሪያ እየደረሰን ነው፡፡ የምንንቀሳቀሰውም ተደብቀን ነው፡፡ አብረውን ችግሩን በተመለከተ በሚዲያ የተናገሩ ሁለት ሰዎችም ተይዘዋል› ብለዋል፡፡ ቤቶቹን ሲያፈርሱም ‹እስቲ ሚዲያዎች ይድረሱላችሁ፣ እናያለን› መባላቸውን ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡

ቤቶቹን ሲያፈርሱ ከነበሩት መካከል በሦስቱ ላይ ግድግዳ ተደርምሶ ጉዳት እንደ ደረሰባቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ገልጸዋል፡፡ አንደኛው ተጎጂ ሕይወቱ ወዲያው እንዳለፈ ቢናገሩም፣ የከተማው የኮሙዩኒኬሽን ባለሙያ የሞተ እንደሌለ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ቤቶቹን የማፍረስ ኃላፊነት የተሰጠው በለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ ከንቲባ የሚመራው ገብረ ኃይል፣ አስለቃሽ ጭስና መሣሪያ በታጠቁ የፀጥታ አካላት ታጅቦ እንደነበር ነዋሪዎች ገልጸዋል፡፡

የለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ ከንቲባ ወይዘሮ ሐቢባ ሲራጅ ከቀናት በፊት በሰጡት መግለጫ፣ ቤቶቹ እንዲፈርሱ የተወሰነው ከተማዋን በማስተር ፕላን የምትመራ ለማድረግ፣ እንዲሁም ምቹና ፅዱ ቦታ ለመፍጠር ነው ብለዋል፡፡ ይፈርሳሉ የተባሉ ከ12,000 በላይ የሚሆኑ ቤቶችም የከተማውን ማስተር ፕላን በመጣስ፣ ለአረንጓዴ ልማት የተተውና የተከለከሉ የወንዞች ዳርቻዎች ላይ የተገነቡ በመሆናቸውም እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ በሕግ ከተፈቀደላቸው ቦታ ውጪ ተጨማሪ ቦታ አጥረው የያዙ ባለሀብቶችም የዚሁ አካል ናቸው ብለዋል፡፡

ዓርብ የካቲት 15 ቀን 2011 ዓ.ም. የጠቅላይ ሚኒስትር ፕሬስ ሴክሬታሪ አቶ ንጉሡ ጥላሁን፣ የክልሉ ገዥ ፓርቲ ኦዴፓ ሥራ አስፈጻሚ አባልና የገጠርና ፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ አዲሱ አረጋና ሌሎች የክልሉ ሹማምንት በለገጣፎና አካባቢው ጉብኝት አድርገው ነበሩ፡፡ ከንቲባዋ ወ/ሮ ሐቢባ በሰጡት ገለጻ መሠረት፣ ከ12,300 በላይ ካርታ የሌላቸው ቤቶች በከተማዋ ውስጥ ይገኛሉ፡፡ በአሁኑ ጊዜ እየፈረሱ ያሉ ቤቶች በመንግሥት ይዞታ ውስጥ የሚገኙ መሆናቸውን ገልጸው፣ የማፍረስ ዕርምጃ ከመወሰዱ ሁለት ወራት በፊት ደብዳቤ ለባለ ይዞታዎቹ ደርሷል ብለዋል፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ከመመሥረቱ ሦስት ዓመት በፊት ግብር የከፈሉበት ደረሰኝ ማቅረብ አለመቻላቸውን አስረድተዋል፡፡

‹‹ውኃና መብራት ማስገባት ዋስትና አይሆንም፤›› ያሉት ሪፖርተር ያነጋገራቸው የከተማው የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር ወይዘሮ ነፃነት ከበደ በበኩላቸው፣ ቤቶቹን የማፍረስ ዘመቻው በማስተር ፕላኑ መሠረት ይቀጥላል ብለዋል፡፡ ግንባታ የተከናወነባቸው አንዳንዶቹ ቦታዎች መንግሥት ለልማት የሚፈልጋቸውና ካሳ የከፈለባቸው እንደሆኑም አስረድተዋል፡፡ ከአርሶ አደሩ እየገዙ የሠፈሩም አሉ ብለዋል፡፡ አለ ለሚባለው ችግር ተጠያቂው ከዚህ በፊት የነበረው የአስተዳደር አካል እንደሆነ፣ ከእነዚህም ውስጥ በሕግ እየተጠየቁ ያሉ ሰዎች መኖራቸውንና አሁንም ተጠያቂ የሚደረጉ ሌሎች መኖራቸውን፣ ከአርሶ አደሮችም የሚጠየቁ እንደሚኖሩ አስረድተዋል፡፡

ቤት የፈረሰባቸው ነዋሪዎችን የፌዴራል ዕንባ ጠባቂ ተቋም ባለሙያዎች ዓርብ የካቲት 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በቦታው ተገኝተው እንዳነጋገሯቸው ታውቋል፡፡ ዘገባው የሪፖርተር ነው።

%d bloggers like this: