ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና አቶ አንዱዓለም አራጌ 5 ዓመት እስር እንደዋዛ
ጋዜጠኛና ጦማሪ እስክንድር ነጋ እና የሰላማዊ ትግል አቀንቃኝ ፖለቲከኛ አቶ አንዱአለም አራጌ በሽብር እና በሃገር ክህደት ወንጀል ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸው እስር ቤት ከገቡ መስከረም 3 ቀን 2009 ዓ.ም ድፍን አምስት ዓመት ሆናቸው፡
እስክንድር “ንፁህ ስለሆንኩኝ፣ የቀረበብኝ ማስረጃ የሌለ በመሆኑ እንዲሁም ፍርድቤቶችን የሚያህሉ የተከበሩ ተቋማት የበቀል የአፈናና የጭቆና መድረክ መሆን ስለሌለባቸው በነፃ እንድለቀቅ የተከበረውን ፍርድቤት እጠይቃለሁ” ብሎ በፌደራል ጠቅላይ ፍርድቤት ይግባኙን በነሐሴ 2004 ዓ.ም ያቀረበ ቢሆንም የከፍተኛው ፍርድቤት የፈረደበትን የአስራ ስምንት ዓመት ፅኑ እስራት እና አምስት አመታት ህዝባዊ መብቶች እግድ ጠቅላይ ፍርድቤቱም አፅንቶበት የፍርዱን ሩብ አመታት በእስራት አሳልፏል፡፡
በፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር አዲስ አበባ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት አምስት አመታትን በእስር ሲያሳልፍ ዘንድሮ የ48 አመት ጎልማሳ የሚሆነው ጦማሪው እስክንድር ነጋ በየኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራያዊ ግንባር /ኢህአዴግ/ መንግስት ለሰባተኛ ጊዜ ሲታሰር በበርካታ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብተ ተሟጋች ድርጅቶች እስራቱ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደሆን ደምፃቸውን ከፍ አድርገው አምስቱንም አመታት ለኢትዮጵያ መንግስት ውትወታቸውን አስምተዋል፡፡
ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የፍርድቤት የችሎት ሂደቱን በመከታተል ላይ እያለ በግንቦት ወር 2004ዓ.ም ፔን አሜሪካ ከተባለ አለማቀፍ ድርጅት በአደገኛ የመገናኛ ብዙሐን ድባብ ውስጥ ሆኖ በመፃፍ ላደረገው አስታዋፅኦዖ “የመፃፍ ነፃነት ሽልማትን” አግኝቷል፡፡ በዚሁ አመት አለማቀፉ የሰብዓዊ መብት ተማጋች ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል እስክንድር ነጋ የህሊና እስረኛ ስለመሆኑ አውጇል፡፡
ለሰባተኛ ጊዜ ለእስር በተዳረገ በአንድ አመት ከአራት ወራት ጊዜ ውስጥ በታህሳስ 2005ዓ.ም ደግሞ የሂውማን ራይትስ ዎች የነፃ ንግግር ሽልማት አሸናፊ ከመሆኑ በተጨማሪ በ36ተኛው አለማቀፍ የፀሃፊዎች ፌስቲቫል ላይ እስክንድር ነጋ የፔን ካናዳ “የአንድ ስብዓዊነት ሽልማት” አሸናፊ ሆኗል፡፡
በጋዜጠኝነት ሙያው በሚሰራው ስራ የኢትዮጵያ የፀረ ሽብር አዋጅ ቀደምት ሰለባ የሆነው ጋዜጠኛ እስክንድር በ1997 ዓ.ም የተደረገውን አገር አቀፍ ምርጫ ተከትሎ መንግስት በአገር ክህደት፣ አመፅ በመቀስቀስ፣ህገ መንግስት እና ህግ መንግስታዊ ስርዓቱን በሃይል በመናድ ወንጀል ተከሶ ፍርድ ቤት የፈረደበት ቢሆንም አንድ አመት ከአምስት ወራት እሰራት በኃላ ክሱ ተቋርጦ መለቀቁ ይታወሳል፡፡
የኢንተርናሽናል ወመንስ ሚዲያ አሶሴሽን “የብርቱ ጋዜጠኛ” ሽልማት አሸናፊ የጋዜጠኛ እስክንድር ባለቤት ጋዜጠኛ ሰርክዓለም ፋሲልም የ1997 ዓ.ም ምርጫን ተከትሎ ከባለቤቷ ጋር በተመሳሳይ ክስ በአንድነት ታስራ በቃሊቲ እስር ቤት ሳለች የመጀመሪያ እና ብቸኛ ልጃቸውን ናፍቆት እስክንድርን ተገላገላለች፡፡
የያኔው ስድስተ አመት ህፃን ልጁን ከትምህርትቤት ወደ ቤት እያመጣ ሳለ በድንገት ያለምንም ማስጠንቀቂያ በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋለው እስክንድር ነጋ እነሆ ዛሬ አብረውት ከተከሰሱት 23 አባሪዎቹ ጋር አምስት አመትን ሲደፍን የቀደሞ የአንድነት ፓርቲ ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበርና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አንዷለም አራጌም የእድሜ ልክ እስራቱን በቃሊቲ ማረሚቤት እየገፋ ይገኛል፡፡
‹ምርጫ 97ን›› ተከትሎ ወህኒ ከወረደው የቅንጅት አመራር አንዱ የነበረው የያኔው ወጣት የአሁኑ ጎልማሳ፣ በብዙዋች ዘንድ የሰላማዊ ትግል አርበኛ ተበሎ የሚወደሰውአንዷለም አራጌ የቅጥት ማቅለያ እንዲያቀርብ በፍርድቤት ሲጠየቅ አንዷለም አራጌ እንዲህ ብሎ ነበር ማቅለያውን ያቀረበው፡፡ “እኔም ለልጆቼ፣ ለወገኖቼ፣ ለአገሬ እና ለራሴ በመረጥኩት ሰላማዊ ትግል ስታገል ቆይቻለሁ፡፡ የበደልኩት ህዝብ አለ ብዬ አላምንም፡፡ ወንጀል ሰርቻለሁ ብዬ አላሰብም፡፡ ውስጤ ፍፁም ሠላማዊ ነው ከሳሾቼ የሚስጡኝን የግፍ ፅዋ ለመጠጣት ዝግጁ ነኝ፡፡”
አቶ አንዷለም አራጌ “ያልተሄደበት መንገድ” የሚል የመጀመሪያ መጸሐፉን በእስር ላይ ሆኖ ከቃሊቲ ማረሚያ ቤት ለአንባቢያን አደርሷል፡፡ በ2007 ዓ.ም ሰኔ ወር ደግሞ “የሀገር ፍቅር እዳ” የተሰኘው ሁለተኛ መጽሐፋ ዳግም ለህትመት በቅቷል፡፡
እስካሁንም ድረስ በእስር ላይ የሚገኙት እነዚህ የሰላማዊ ትግል አርበኞ አዲሱን አመት 2009 ዓ.ም የተቀበሉት አምስተኛ አመታቸውን በማሰብ ነው፡፡
እስክንድር ነጋ እና አንዷዓለም አራጌ በፍትህ እጦት አመታትን በእስር እንዲያሳልፉ ሲገደዱ እስራቸው አገሪቷ በዓለም አቀፍ ህግ መደረክ ተገዢ እሆናለሁ ብላ ቃል የገባችባቸውን የቃልኪዳን ሰነዶች ሁሉ የናደ ሰለመሆኑ የሰበዓዊ መብት ተሟጋቾች በተደጋጋሚ ሲሞግቱ አምስት አመታት አልፈዋል፡፡
ዛሬም አስራቸው ህገ መንግስቱን የጣሰ፣ አላግባብ፣ ኢፍታዊ እና የሰብዓዊ መብቶቻቸውን ያላከበረ ነው ፡፡ አንዱአለም በተለምዶው ቅጣት ቤት ተብሎ የሚጠራው ከፍተኛ ጥበቃ የሚደረግበት ክፍል ውስጥ ታስሮ ሲገኝ እስክንድር በቃሊቲ የተለያዩ ዞኖች ታስሯል፡፡ ሁለቱም እስረኞች ከቅርብ ቤተሰብ ውጪ ማንም እንዳይጠይቃቸው የተከለከሉ ሲሆን ከእስራቸው እስከ አያያዛቸው ኢሰብአዊነትን እያስተናገዱ አምስት አመት አስቆጥረዋል፡፡
ምንጭ፡- EHRP
በአዲስ አበባ አቃቂ በሚገኘው ቂሊንጦ ወህኒ ቤት በደረሰ የእሳት አደጋ ከ25 ያላነሱ እስረኞች ህይወት አለፈ
(አዲስ ሚዲያ)ዛሬ ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. አዲስ አበባ አቃቂ በሚገኘው ቂሊንጦ ወህኒ ቤት በደረሰ የእሳት ቃጠሎ ከ25 ያላነሱ እስረኞች መሞታቸው ተጠቆመ፡፡ በጥበቃ ላይ የነበሩ ወታደሮችም ከእሳቱ ለማለጥ የሞከሩ እስረኞች ላይ ሲተኩሱ እንደነበር ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
ከቃጠሎው በፊት በነበረው ተኩስ ምን ያህል እስረኞች ላይ ጉዳት እንደደረሰ እስካሁን ማረጋገጥ ባይቻልም፤ በነጋታው ጠዋት በነበረው የእሳት አደጋ ከ25 ያላነሱ ሰዎች መሞታቸውን ከቅዱስ ጳውሎስ፣ ሜክሲኮ በሚገኘው ፖሊስ ፣ ጥሩነሽ ቤጂንግ እና የካቲት 12 ሆስፒታል ምንጮች ለማወቅ ተችሏል፡፡ በቃጠሎው ጉዳት የደረሰባቸውና በህይወት የተረፉትም አብዛኞቹ ፖሊስ ሆስፒታልና የካቲት 12 ሆስፒታል በጥበቃ ስር ሆነው ህክምና እየተደረገላቸው እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡

በወህኒ ቤቱ ታስረው ከሚገኙት መካከል ስመጥር እና ህዝባዊ ተቀባይነት ያላቸው በርካታ የፖለቲካ እስረኞች ያሉበት ሲሆን በተለይም፤ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ ፖለቲከኞች፣ የመብት አራማጆች እና ጋዜጠኞች እንደሚገኙበት ይታወቃል፡፡
በያዝነው 2008 ዓ.ም. ብቻ ከአዲስ አበባ አቃቂ ከሚገኘው ቂሊንጦ ወህኒ ቤት በተጨማሪ በርካታ የፖለቲካ እስረኞች የሚገኙባቸው ጎንደር፣ አምቦና ደብረ ታቦር ወህኒ ቤት በተመሳሳይ መልኩ የእሳት አደጋ ሰለባ መሆናቸው አይዘነጋም፡፡ በነበሩ አደጋዎች መንስኤ እና ጉዳትን በተመለከተ የሚመለከተው የመንግሥት አካልም ከመግለፅ መቆጠቡ ይታወቃል፡፡
በተለይ የአቃቂ ቂሊንጦውን እሳት ቃጠሎ ተከትሎ በርካታ የታሳሪ ቤተሰቦች፣ ወዳጆች እና ደጋፊዎች ስጋት እንዳደረባቸው በተለያየ መድረክ ከመግለፅ በተጨማሪ በአዲስ አበባና አጎራባች አካባቢ ያሉ ሰዎች የቤተሰቦቻቸውን ደህንነት ለማጣራት ሙከራ ቢያደርጉም በወህኒ ቤቱ አስተዳደር እንዳልተፈቀደ ተረጋግጧል፡፡ በወህኒ ቤቱ የታሰሩ ቤተሰቦቻቸውን ለመጠየቅ ከተለያዩ የክልል ከተሞች የመጡ ሰዎችም ወደ እስር ቤቱ ግቢም ሆነ ከግቢ ውጭ በቅርብ ርቀት እንዳይጠጉ በመከልከላቸው ወደየመጡበት መመለሳቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
በአደጋው የደረሰውን ጉዳትና ምክንያት በተመለከተ የወህኒ ቤቱ አስተዳደርም ሆነ መንግሥት እስካሁን የሰጡት መረጃ የለም፡፡ ይሁን እንጂ የተለያዩ ሰዎች አደጋው በመንግሥት ሆን ተብሎ የተቀነባበረና የፖለቲካ እስረኞችን ለመጉዳት የታሰበ የገዥው ስርዓት የተለመደ ስልት እንደሆነ የሚገልፁ ቢኖሩም፤ ስለ አደጋውና አጠቃላይ መረጃ ከገለልተኛ አካልም ሆነ ከመንግሥት ለማወቅ አልተቻለም፡፡
በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ አድማሱን እያሰፋ ቀጥሏል፤ በኦሮሚያ ኢኮኖሚ ተኮር ተቃውሞ እንደሚጀመር ይፋ ተደረገ
ብስራት ወልደሚካኤል
(አዲስ ሚዲያ)የወልቃይት የአማራ ማንነት መብት ጥያቄን መነሻ አድርጎ በጎንደር ፋሲል ከተማ የተጀመረው ህዝባዊ ተቃውሞ፤ የተለያዩ የሰሜን እና ደቡብ ጎንደር ወረዳና ከተሞችን ጨምሮ ወደ ምስራቅና ምዕራብ ጎጃም እንዲሁም ወደ ሰሜን ወሎ መቄት እና ሸዋ ሮቢት መስፋፋቱን እማኞች ለአዲስ ሚዲያ ተናግረዋል፡፡
በተለይ ነሐሴ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ጎጃም ፍኖተ ሰላም ከተማ፣ ነሐሴ 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ቡሬ ወምበራ ወረዳ ቡሬ ከተማ የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች ተካሂደዋል፡፡ በሰሜን ጎንደር በተለያዩ ወረዳዎች እና ከተሞች ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ተቃውሞዎች እና የመንግሥት የኃይል ርምጃዎችም የቀጠሉ መሆናቸው ተረጋግጧል፡፡
በጎንደር፣ ባህርዳር እና ደብረማርቆስ ከተሞች ከቤት ያለመውጣት ተከታታይ ህዝባዊ ተቃውሞች የተደረጉ ሲሆን ከነሐሴ 22-25 ቀን 2008 ዓ.ም. ደግሞ በተመሳሳይ ምልኩ በደቡብ ጎንደር ደብረ ታቦር ከተማ ከቤት ያለመውጣት ተቃውሞ እንደሚደረግ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በአማራ ክልል ባሉ ሰሞንኛ ተቃውሞች በተለይ በማክሰኝት፡በገደብዬ፡በእንፍራንዝ፣ በአብደራፊ፣ በአርማጭሆ፣ በፍኖተ ሰላም፡ቡሬ፡ ጅጋ እና ማንኩሳ በተባሉ ወረዳዎች ህዝባዊ ተቃውሞዎች የበረቱባቸው መሆኑን ያገኘነው መረጃ አመልክቷል፡፡ በነኚህ ስፍራዎች የነበሩ ተቃውሞች መካከልም የተወሰኑ በማኀበራዊ ሚዲያዎች ሲሰራጩ መዋላቸውን ለመታዘብ ተችሏል፡፡
በነበሩ የአማራ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞች ሁለት ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት መገደላቸው የተጠቆሙ ሲሆን፤ በተለይ በሰሜን ጎንደር ዞን ባሉ ወረዳዎች በነበሩ ተቃውሞች ጉዳት የደረሰባቸው ዜጎች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ተገምቷል፡፡
በኦሮሚያ ክልልም ህዝባዊ የፀረ አገዛዝ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተቃውሞች የቀጠሉ ሲሆን፤ በዚህም በምዕራብ ሐረርጌ መሰላ ወረዳ በሚገኙ ዋልተሲስ እና ጎሮ በተባሉ መንደሮች በነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ አራት ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት በተወሰደ የኃይል ርምጃ መገደላቸው ታውቋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በሀገሪቱ ያለውን የመንግሥትን ግድያ፣ እስርና እና አፋና በመቃወማቸው በአዲስ አበባ ቂሊንጦ ወህኒ ቤት ለእስር የተዳረጉ የፖለቲካ እስረኞች በተለይም እነ አቶ በቀለ ገርባ በሀገሪቱ ከነሐሴ 19-21 ቀን 2008 ዓ.ም. ብሔራዊ የሀዘን ቀን በሚል ታስቦ እንዲውል ያደረጉት ጥሪ ከወዲሁ በተለያዩ ደጋፊዎቻቸው ተግባራዊ መደረግ መጀመሩ ታውቋል፡፡
የመንግሥት የኃይል ርምጅና ግፍ በመቃወም በሚደረግ ብሔራዊ የሀዘን ቀንም ፀጉር መላጨት፣ ጥቁር ልብስ መልበስ፣ ጥቁር ባንድራ(ጨርቅ) ማውለብለብ፣ ሻማ ማብራት፣ በተቃውሞ ትግሉ የተገደሉ ሰላማዊ ዜጎች ቤተሰቦችን መጎብኘት እና ተሰብስቦ ህዝባዊ ውይይት በማካሄድ እንዲተገበር ጥሪ ማስተላለፋቸውን ተከትሎ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ ባሉ ዜጎች ከወዲሁ ተግባራዊ መደሩ የሚያመለክቱ የተለያዩ ምስሎች በማኀበራዊ ሚዲያዎች ላይ መሰራጨታቸውን ማየት ተችሏል፡፡
በኦሮሚያ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ ካለው የፖለቲካና ማኀበራዊ ጉዳዮች በተጨማሪ ከጳጉሜ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞችም እንደሚተገበሩ የኦሮሞ ተቃውሞ አስተባባሪዎች እና የመብት አራማጆች ይፋ አድርገዋል፡፡ ይሁን እንጂ የአኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞው ምን ላይ እንደሚያተኩር በዝርዝር የተቀመጠ ነገር ባይኖርም፤ ወደፊት ይፋ እንደሚደረግ የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡
በታቀደው መሰረት በኦሮሚያ የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞ ተግባራዊ የሚደረግ ከሆነ መንግሥት በክፍተኛ ደረጃ የውጭ ምንዛሪ እጥረትና አደጋ ላይ እንደሚወድቅ ይጠበቃል፡፡ በተለይም መንግሥት ከክልሉ በከፍተኛ ደረጃ የውጭ ምንዛሪና የሀገሪቱ ዋነኛ የገቢ ምንጭ የሆኑት እንደ ቡና፣ የጫት፣ የአበባ፣ የቁም እንሰሳትና፣ የቆዳና ሌጦ እንዲሁም የምግብ ነክ የሆኑ የብግርና ምርቶች እንዲሁም ወርቅና የመሳሰሉ የማዕድን ሃብቶች ከክልሉ እንዳይወጡና ወደ ማዕከላዊም ሆነ የክልሉ ገበያ ንግድ ላይ የማይውሉ ከሆነ ምን አልባትም በሀገሪቱ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ ከባድ ፈተና በመንግሥት ላይ ሊደርስ እንደሚችል ይጠበቃል፡፡
የኢኮኖሚ ተኮር ህዝባዊ ተቃውሞ በቀጣይ ወደሌሎች ክልሎች በተለይም አማራ እና ደቡብ ክልል የሚዛመት ከሆነ ደግሞ የመንግሥት 90% የገቢ ምንጭ በማድረቅ ስርዓቱን ሙሉ ለሙሉ አደጋ ላይ እንደሚጥለው ይገመታል፡፡ በተለይ ኦሮሚያ እና አማራ ክልል ብቻ የሀገሪቱን 54% የሆነውን ህዝብ ቁጥር እንደሚሸፍኑ እና ከ65% የሀገሪቱ የውጭ ምንዛሪና የገቢ ምንጭም መሆናቸው ይታወቃል፡፡
ከባለፈው ህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ የተቀጣጠለው የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞ መላው ኦሮሚያ ክልልን በማዳረስ፤ ከሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ አማራ ክልል ተዛምቷል፡፡ በሁለቱም ክልሎች ዘገባው እስከተጠናቀረበት ድረስ ህዝባዊ ተቃውሞዎቹ በተለያዩ ወረዳዎችና ከተሞች ቀጥሏል፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ በሁለቱም ክልሎች ባሉ የተለያዩ ቦታዎች መደበኛ የመንግሥት ስራን ጨምሮ የተለያዩ ፖለቲካዊ፣ ማኀበራዊና ኢኮኖሚያዊ አለመረጋጋቶች እየታዩ ነው፡፡
አስረኛ ወሩን ባስቀጠረው ህዝባዊ ተቃውሞ በሁለቱም ክልሎች ከ650 በላይ ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት በተወሰደ የኃይል ርምጃ ሲገደሉ፣ ከ 1,250 ያላነሱ ዜጎች ቆስለው በግምት ከ35,000 በላይ ሰዎች ለእስር ተዳርገዋል፡፡ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉ እና የቆሰሉ ሰዎች በተለያየ ጊዜ ስማቸውና ምስላቸው በሰፊው በማኀበራዊ ሚዲያ እየተገለፀ ይገኛል፡፡ በሁለቱም የኦሮሚያ እና አማራ ክልሎች ህዝባዊ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ የወጣው ህዝብ አንዱ ለሌላው በተለያዩ ጊዜና ቦታ ያሳዩት የርስ በርስ አጋርነት፤ መንግሥትን ከፍተኛ ድንጋጤ ላይ እንደጣለው ባለስልጣናቱ በስራቸው ባሉ መገናኛ ብዙኃን ሲናገሩ የተደመጡ ሲሆን፤ በዚህም ስጋት እንዳደረባቸው ባለስልጣናቱና ደጋፊዎቻቸው በይፋ የሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎችና ከሚሰነዝሯቸው አስተያየቶች መረዳት ተችሏል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ህዝባዊ ተቃውሞ ፤የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ክልል ፊንፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን ”የጋራ ልማት የተቀናጀ ማስተር ፕላን” በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ ገበሬዎች የሚያፈናቅልና ለጎዳና ህይወት የሚዳርግ ነው በሚል ቀደም ሲል የነበረውን ተቃው ከዓመት በኋላ በማገርሸት በምዕራብ ሸዋ ጊንጪ ከተማ መጀመሩ ይታወቃል፡፡ በአማራ ክልል ደግሞ የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ማንነት መብት ጥያቄ ህዝባዊ ወኪሌ ኮሚቴ አባላት ላይ መንግሥት በሌሊት በመኖሪያቸው አካባቢ የፀጥታ ኃይሎችን በመላክ የኃይል ርምጃ መውሰዱን ተከትሎ በጎንደር ከተማ መጀመሩ ይታወሳል፡፡
መንግሥት በወሰደው የኃይል ርምጃ ስለደረሱ አጠቃላይ ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳቶች በተመለከተ በመንግሥት ጉዳዩን ለመሸፋፈን ከመሞከር በዘለለ ትክክለኛውን ቁጥርና የጉዳት መጠለን ለመናገር አልደፈረም፡፡ ቀደም ሲል ሀገር በቀል በሆነው የሰብዓዊ መብት ጉባዔ (ሰመጉ) እና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች በሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች (HRW) አማካኝነት በተወሰኑ ወረዳዎችና አካባቢዎች የተደረጉ ምርመራዎች ይፋ ከመደረጋቸው በስተቀር አጠቃላይ በደረሱ የሰብዓዊ እና ቁሳዊ ጉዳቶች የተደረገ ምርመራም ሆነ ሪፖርት የለም፡፡ ይህን በተመለከተ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ምት ኮሚሽን ጉዳዩ በገለልተኛ አካል ምርመራ እንዲደረግ በይፋ ጥያቄ ቢያቀርብም በስልጣን ላይ ያለው መንግሥት በበኩሉ የመንግሥታቱን ድርጅት ጥያቄ ውድቅ በማድረግ ምላሽ መስጠቱ ይታወሳል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በነበረው ተቃውሞ ከ400 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ሂውማን ራይትስ ዎች ይፋ አደረገ
ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች የሆነው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ከህዳር ወር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በኦሮሚያ ክልል በተካሄዱ የተቃውሞ ሰልፎች የኢትዮጵያ መንግስት የጸጥታ ሀይሎች ከ400 በላይ የሚሆኑ ሰልፈኞችን የገደሉ ሲሆን ከአስር ሺህ በላይ የሚቆጠሩትን ደግሞ ማሰራቸውን አስታውቋል፡፡ የሰብዓዊ መብት ድርጅቱ “የኢትዮጵያ መንግስት የተፈጸሙ ግድያዎችን፣ እስራቶችንና ሌሎች የመብት ጥሰቶች በአስቸኳይ ተአማኒነት ያለውና ገለልተኛ የሆነ ማጣሪያ እንዲካሄድ ድጋፍ ማድረግ አለበት።” ሲል ባለ 61 ገፅ ሪፖርት ይፋ አድርጓል፡፡

ድርጅቱ ሰኔ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጣው ባለ 61 ገጽ ሪፖርት “ጭካኔ የተሞላበት አፈና’ – የግድያ እና የእስራት ምላሽ፤ ለኢትዮጵያ የኦሮሞ ተቃውሞ” የሚል ነበር፡፡ መንግሥትም በነበረው ተቃውሞ ያልተመጣጠነ ርምጃ መውሰዱን በመግለፅ ድርጊቱን አውግዟል፡፡ ሪፖርቱ በሰላማዊ ሰልፈኞች ላይ እንዲሁም ሀሳባቸውን በነጻነት በሚገልጹ ዜጎች ላይ በመንግስት የጸጥታ ሀይሎች የተወሰደውን እርምጃ አስመልክቶ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን፣ ከ125 በላይ የሚሆኑ የተቃውሞ ሰልፎች ተሳታፊዎችን፣ ጉዳዩን በአንክሮ ሲከታተሉ የቆዩ ግለሰቦችን፣ በተለያዩ ጊዜያት የመብት ጥሰት የተካሄደባቸውና ጉዳት የደረሰባቸውን ግለሰቦች ያካተተ ቃለ መጠይቅ ማድረጉንም አስታውቋል፡፡
በመንግሥት የተቋቋም የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮምሽን ይህንን የኦሮሚያ ክልል ተቋውሞ ተከትሎ በተወሰደ ርምጃ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 173 ብቻ መሆናቸውን እና በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተወሰደው ርምጃም “ተገቢና ተመጣጣኝ” ነው ሲሉ ኮሚሽነሩ ዶ/ር አዲሱ ገብረእግዚአብሔር ሰኔ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. “ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት” እና ለጋዜጠኞች ገልፀዋል፡፡ ኮሚሽነሩ ተገቢና ተመጣጣኝ ያሉት ርምጃ የተወሰደው በመከላከያ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ እና በኦሮሚያ ክልል ልዩ ኃይል መሆኑንም ለጋዜጠኞች ጠቁመዋል፡፡

መንግሥታዊ ያልሆነው ሀገር በቀል የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሆነው የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ፤ በኦሮሚያ ክልል በነበረው ተቃውሞ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተወሰደው ርምጃ ተገቢና ተመጣጣኝ እንዳልሆነ ቀደም ሲል ይፋ ባደረገው ዝርዝር ሪፖርት ማስታወቁ ይታወሳል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በነበረውን ተቃውሞ የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ፤ ሀገር በቀል የሆነው የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ሰመጉ) ባለፈው መጋቢት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. በ140ኛው የተቋሙ ሪፖርት “የኦሮሚያ ክልል በ18 ዞኖች እና በ342 ወረዳዎች የተከፋፈለ ሲሆን ሰመጉ ከ9 ዞኖች ውስጥ በ33 ወረዳዎች ብቻ ባደረገው የመስክ ምርመራ ባገኘው ውጤት መሰረት 103 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን 57 ሰዎች በጥይት የመቁሰል እና ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡” ብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተገደሉትና ከቆሰሉት በተጨማሪ በ22 ሰዎች ላይ ማሰቃየት እና ድብደባ መፈፀሙን፣ 84 ሰዎች መታሰራቸውን እንዲሁም 12 ሰዎች የደረሱበት ወይም ያሉበት አለመታወቁንም በመግለፅ ሪፖርቱን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡
ሙሉውን የሂውማን ራይትስ ዎች ሪፖርት እዚህ https://www.hrw.org/news/2016/06/15/ethiopia-protest-crackdown-killed-hundreds ያገኙታል፡፡
የዜጎች የመንቀሳቀስ መብት ይከበር!
ዞን 9

የዜጎች ከሀገር ሀገር የመንቀሳቀስ መብት በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥትም ሆነ ኢትዮጵያ አባል ሆና በፈረመቻቸው አህጉር አቀፍ እና ዓለማቀፍ ድንጋጌዎች የተጠበቀ ነው፡፡ በሕገ መንግሥቱ በአንቀጽ 32/1 ላይ “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ . . . ከሀገር የመውጣት ነጻነት አለው” በማለት ተደንግጓል፡፡ ኢትዮጵያ ፈራሚ አባል የሆነችበት ‘ዓለም አቀፉ የሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች ቃልኪዳን’ በበኩሉ ማንኛውም ግለሰብ ሕጋዊ ማዕቀብ ካልተጣለበት በስተቀር ወደፈለገው ቦታ የመንቀሳቀስ ከሀገር መውጣትን የሚጨምር መብት እንዳለው ይደነግጋል፡፡ በኢትዮጵያ ህግም ብቸኛ ገደብ የሚያስቀምጠው የኢምግሬሽን አዋጅ ቁጥር 354/2003 በአንቀጽ 7 ላይ “ማንኛውም ሰው ከኢትዮጵያ እንዳይወጣ ሊታገድ የሚችለው በሕግ መሠረት በፍርድ ቤት ሲታዘዝ ብቻ ነው” በማለት የመንቀሳቀስ መብት ገደብን በማያሻማ መልኩ ያስቀምጠዋል፡፡
እንደሚታወሰው የዚህ የጡመራ መድረክ አባል የሆነው ዘላለም ክብረት በወንጀል ተጠርጥሮ ታስሮ የነበረ ቢሆንም ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ በራሱ ተነሳሽነት ክሱ እንዲቋረጥ በማድረጉ ከማሕሌት ፋንታሁን፣ ከአስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ፣ ከኤዶም ካሳዬና ከተስፋለም ወልደየስ ጋር ሐምሌ 01/2007 ከእስር ተፈትቷል፡፡ ከላይ በተጠቀሰው የሕግ አግባብ መሠረት ከሀገር እንዳይወጣ የሚያደርግ ምንም ዓይነት ሕጋዊ ክልከላም የለበትም፡፡ ይሁንና ሕዳር 05/2008 ዘላለም ለቡድኑ የተበረከተ ሽልማትን ለመቀበል ወደ ፈረንሳይ፣ ፓሪስ ለማቅናት ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ቢገኝም የጉዞ ሰነዱ (ፓስፖርቱ) ተነጥቆ ከሀገር እንዳይወጣ ተከልክሏል፡፡ በተለያዩ የመገናኛ አውታሮች እንደተገለጸው ጦማሪው የጉዞ ሰነዱ እንዲመለስ እና የመንቀሳቀስ መብቱ እንዲከበር ያደረገው ሙከራ ከመጉላላት በቀር ምንም መፍትሔን አላስገኘም፡፡ እንዲያውም በአግባቡ ምላሽ የሚሰጥ መንግሥታዊ አካል መጥፋቱን ለመታዘብ ችለናል፡፡ በዚህም ምክንያት የተለያዩ ዕድሎችን ተጠቅሞ መማርም ሆነ መሥራት እንዳይችል ሁኗል፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽንም ይህንን የመብት ጥሰት ‹ጉዳዩ ከአቅሜ በላይ ነው› በሚል ምክንያት ሊያስቆም አልቻለም፡፡
በሌላ በኩል ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ በታኅሣሥ 01/2008 ዓ.ም. ለትምህርት ወደ አሜሪካ ለመሔድ በሞከረችበት ወቅት የጉዞ ሰነዷን ተቀምታ ከሐገር መውጣት እንደማትችል የተነገራት ሲሆን፤ ለምን የጉዞ ሰነዷን እንደተነጠቀች በተደጋጋሚ ለኢሚግሬሽን እና ዜግነት መምሪያ ጥያቄ ብታቀርብም እስከ አሁን ድረስ ምላሽ ማግኘት አልቻለችም፡፡
እንዲሁም ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በጥር 11/2008 ዓ.ም. ወደ ጀርመን ሃገር ለስድስት ሳምንታት የጋዜጠኝነት ልምድ ለመቅሰም ያገኘውን አጋጣሚ ለመጠቀም ያደረገው ሙከራም በተመሳሳይ የጉዞ ሰነዱን ያለምንም ሕጋዊ ምክንያት በመነጠቁ ምክንያት ሳይሳካ ቀርቷል፡፡
ይባስ ብሎም ጋዜጠኛ አስማማው ኃይለ ጊዮርጊስ ለስድስት ሳምንታት ወደ ጀርመን ሃገር በመሔድ በጀርመኑ የመንግስት ቴሌቪዥን ጣቢያ የቀረበለት የልምድ ልውውጥ ላይ ተሳትፎ ወደ ሃገሩ ሲመለስ በየካቲት 26/2008 ዓ.ም. በተመለሰበት ወቅት ‹ከሃገር እንዴት ልትወጣ ቻልክ› ከሚል ከባድ ዛቻና ማስፈራሪያ ጋር የጉዞ ሰነዱን ሊነጠቅ ችሏል፡፡
ይህንን ሕገ ወጥ ድርጊት ለማረም ሁሉንም ሕጋዊ መንገዶች አሟጠን የምንጠቀም ሲሆን፤ ሕግ አስፈጻሚው አካል ግን ይህንን ስህተቱን ማረም የሚጀምርበት ተጨማሪ ዕድል አግኝቷል፡፡ ዘላለም ክብረት የዘንድሮው The Nelson Mandela Fellowship ወይም በቀድሞው አጠራር Young African Leaders initiative (YALI) አሸናፊ ሆኗል፡፡ የኔልሰን ማንዴላ ፌሎውሽፕ የአሜሪካው ፕሬዝዳነት ባራክ ኦባማ ወጣት አፍሪካውያን አህጉራቸውን የሚጠቅሙ መሪዎች እንዲሆኑ የሚያግዛቸውን ክህሎት እንዲጨብጡ በማሰብ እ.ኤ.አ. 2010 ይፋ ያደረጉት መርሐ-ግብር ሲሆን፤ በዚህ ስድስት ሳምንታት በሚፈጀው መርሐ-ግብር በየዓመቱ በርካታ አፍሪካውያን ለራሳቸውም ለአህጉራቸውም ጠቃሚ የሆነ ዕውቀት ገብይተው ተመልሰዋል፡፡ የዘንድሮው ውድድር አሸናፊ የሆኑት ሌሎች ኢትዮጵያውያን እና ዘላለም ክብረት በመጋቢት እና ሚያዝያ ወር ቅድመ ሁኔታዎችን አሟልተው በሰኔ አጋማሽ ወደ አሜሪካ እንደሚያቀኑ የመርሐ-ግብሩ የጊዜ ሰሌዳ ያሳያል፡፡
እኛም ከጊዜ ወደ ጊዜ ጉዳዩ ሕጋዊ መልክ ይይዛልና ይሻሻላል ብለን ተስፋ ብናደርግም ነገሮች ግን እየተባባሱ እና የመብት ጥሰቱም እየጨመረ መጥቷል፡፡ ይሄም ድርጊት ዜጎች በሃገራቸው ሕግን አምነው ለመኖር አለመቻላቸው ማሳያም ነው፡፡ በመሆኑም የሚመለከተው የአስፈጻሚ አካል ያለምንም የሕግ አግባብ የጉዞ ሰነዳቸውን ተቀምተው የሚገኙ ጦማሪዎችና ጋዜጠኞች መብታቸው ተከብሮላቸው የጉዞ ሰነዶቻቸው ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲመለሱላቸው እንዲያደርግ እና የመንቀሳቀስ መብታቸውን እንዲያከብር እንጠይቃለን፡፡
ሕገ መንግሥቱ ይከበር!