Tag Archives: Ethiopian press freedom

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በተመሰረተበት ክስ 3 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈረደበት

የቀድሞ የፍትህ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅና መስራች፣ የአዲስ ታየምስ መፅሔት፣ የልዕልና ጋዜጣ በመጨረሻም የፋክት መፅሔት ባልደረባና አዘጋጅ የሆነው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በተመሰረተበትና ጥፋተኛ በተባለበት 3 ክሶች መካከል በአንዱ ክስ ብቻ የ3 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈረደበት፡፡ጋዜጠኛው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቃቤ ህግ በመሰረተበት ክስ ጥፋተኛ የሚል ብይን ከሰጠ በኋላ ቅጣት የተጣለበት በ2004 ዓ.ም. በፍትህ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በነበረበት ወቅት በፃፋቸው ፅሑፎችን መሰረት አድርጎ መሆኑ ታውቋል፡፡

temesegen dጋዜጠኛው የተፈረበት፤ዛሬ ጥቅምት 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በዋለው ችሎትም ጋዜጠኛው ጥፋተኛ ከተባለበት 3 ክሶች መካከል በአንዱ ክስ ብቻ የ3 ዓመት ፅኑ እስራት ቅጣት ተጥሎበታል፡፡ በዚህም መሰረት ጋዜጠኛ ተመስገን በፀጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ስር እንደሆነ፤ወደ አቃቂ ቂሊንጦ ወደሚገኘው ወህኒ ቤት ተወስዷል፡፡

የጋዜጠኛው ተከላካይ ጠበቃ አቶ አምሃ መኮንን ቅጣቱን እና ፍርዱን በሚመለከት ይግባኝ እንደሚጠይቁ የተገለፀ ሲሆን፤ በቅጣት ፍርዱ አቃቤ ህጉም ሆኑ ተከላካይ ጠበቃው የቅጣት ማክበጃም ሆነ ማቅለያ አለመጠየቃቸው ተጠቅሟል፡፡ በኢትዮጵያ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝን ጨምሮ የታሰሩት ጋዜጠኞች እና ብሎገሮች ቁጥር 18 መድረሱ ታውቋል፡፡

ኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት በፃፉት ፅሑፍ የተከሰሱ፣የታሰሩም ሆነ የተፈረደባቸው ጋዜጠኞችም የሉም የሚል ተደጋጋሚ ማስተባበያ ቢሰጥም፤ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ጨምሮ ከታሰሩት 18 ጋዜጠኞችና ብሎገሮች መካከል 15ቱ ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞችና ብሎገሮች የቀረበባቸው ክስናም ሆነ ፍርድ ከስራቸው ጋር በተያያዘ በፃፉትና በተናገሩት መሆኑ የተመሰረተባቸው ክስ ያመለክታል፡፡

በቅርቡ የተሰደደው ጋዜጠኛ ሚሊዮን ሹሩቤ ህይወቱ አለፈ

 

milion shurbieየማራኪ መፅሔት ባለቤት እና ማኔጂንግ ዳይሬክተር የነበረው ጋዜጠኛ ሚሊዮን ሹሩቤ በስደት በሚገኝበት ናይሮቢ ኬኒያ ጥቅምት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. በድንገት ህይወቱ ማለፉን ከማኀበራዊ ገፆች የተገኙ መረጃች እና ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት በጅምላ ያደረገውን የመፅሔቶች እና ጋዜጣ ክስ እና የበርካታ ጋዜጠኞችን እና ብሎገሮችን እስርን ፍርሃት ተከትሎ በቅርቡ ከተሰደዱ ጋዜጠኞች መካከል ጋዜጠኛ ሚሊዮን ሹሩቤ አንዱ ነበር፡፡

ጋዜጠኛው በስደት ኬኒያ ከሚገኝበት አንድ ናይሮቢ ሆስፒታል በህክምና ሲረዳ ቢቆይም ህይወቱን ማትረፍ እንዳልተቻለ ታውቋል፡፡ ጋዜጠኛው ከኢትዮጵያ ከተሰደደ ገና ሁለት ወር እንኳ እንዳልሞላው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ጋዜጠኛው ህይወቱ እስካለፈበት ድረስ በኢትዮጵያ ነፃ ፕሬስ ውስጥ ከ12 ዓመታት በላይ  እንዳገለገለና የድርሰት ስራም እንዳለው ተጠቁሟል፡፡

ጋዜጠኛ ሚሊዮን በተወለደ በ33 ዓመቱ በስደት ናይሮቢ ኬንያታ ናሽናል ሆስፒታል ቢያርፍም፤የቀብር ስነስርዓቱ እሁድ ጥቅምት 9 ቀን 2007 ዓ.ም. በትውልድ አካባቢው ይርጋ ጨፌ ከተማ ቅድስት ኪዳነ ምህረት ቤተ ክርስቲያን ተፈፅሟል፡፡ ጋዜጠኛው የአንድ ወንድ ልጅ አባት ነበር፡፡

አዲስ ሚዲያም በጋዜጠኛው ሞት የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን እየገለፀ፤ ለጋዜጠኛ ሚሊዮን ፈጣሪ ነፍሱን በገነት እንዲያኖር፤ ለቤተሰቦቹ፣ለወዳጅ ዘመዶቹና አድናቂዎቹ መፅናናትን ይመኛል፡፡

maraki magazine

የኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በአምስት ሺህ ብር ዋስ መለቀቁ ተሰማ

 

ቀደም ሲል መስከረም 23 ቀን 2007 ዓ.ም. ለምሳ ሲወጡ ቢሯቸው ታሽጎ ሰኞ መስከረም 26 ቀን 2007 ዓ.ም. የተከፈተው እና ለሰባት ሳምንታት ህትመቷ የተቋረጠው የኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጌታቸው ወርቁ በፌደራል የወንጀል ምርመራ ማዕከል ማዕከላዊ ፖሊስ ቃሉን እንዲሰጥ በተደረገለት ጥሪ መሰረት ማክሰኞ መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ማዕከላዊ መቅረቡ ታውቋል፡፡ ጋዜጠኛው ማዕከላዊ የተጠራው የቀድሞው መኢአድ አመራር የነበረው አቶ ማሙሸት አማረ ክስ መሰረት ቃሉን እንዲሰጥ የነበረ ቢሆንም፤ ማዕከላዊ ምርመራ ክፍልም የጋዜጠኛውን ቃል ከተቀበለ በኋላ ጉዳዩ አስፈላጊ ሲሆን እንደሚቀርብ በመጠቆም በ5,000.00 (አምስት ሺህ ) ብር ዋስ መለቀቁ ተጠቁሟል፡፡

Getachew workuኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ መንግስት በጋዜጠኞች፣ በመፅሔቶች እና ጋዜጦች ላይ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የሚወነጅል ዘጋቢ ፊልም በተደጋጋሚ መስራቱን ተከትሎ አታሚ ቤቶች የነፃ ጋዜጦችን እና መፅሔቶችን እንዳያትሙ በተለያዩ የመንግስት አካላት ጫና በማሳደሩ ለ7 ሳምንታት ከህትመት መቋረጧን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የጋዜጣው አዘጋጆች በተደጋጋሚ ስራውን አጠናቀው ቀድም ሲል የሚያትምላቸው አታሚ ድርጅትና ሌሎች አታሚዎች ጋር በተደጋጋሚ ቢኬድም እስካሁን ለማተም ፈቃደኛ እንዳልሆኑ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ መንግስት የነፃ መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞችን፣ ጋዜጦችን እና መፅሔቶችን በተደጋጋሚ መወንጀሉ እና መክሰሱን ተከትሎ የተለያዩ በርካታ ነፃ ጋዜጦችና መፅሔቶች ከህትምት እና አንባቢ ውጭ እንዲሆኑ መደረጉ ይታወቃል፡፡ ይህንንም ተከትሎ ከሚያዝያ 2006 ዓ.ም.  እስከ ነሐሴ 2006 ዓ.ም. መጨረሻ ድረስ ከ25 ያላነሱ የነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞች የግፍ እስርና ስቃዩን በመሸሽ መሰደዳቸው ይታወቃል፡፡ በአሁን ወቅት ኢትዮጵያ ውስጥ 3 የውጭ ዜጎችን ጨምሮ ከ17 ያላነሱ ጋዜጠኞች እና ብሎገሮች በግፍ ታስረው ይገኛሉ፡፡

 

 

 

 

 

 

 

የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት በጋዜጠኞችና ብሎገሮች ጉዳይ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጠ

የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ ሐምሌ 28 ቀን 2006 ዓ.ም. በዋለው ችሎት የፌደራሉ አቃቤ ህግ በሽብርተኝነት በሶሊያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ክስ የመሰረተባቸው ዘጠኝ ጋዜጠኞችና የኢትዮጵያ ዞን 9 ብሎገሮች ለነሐሴ 14 ቀን 2006 ዓ.ም. ከጠዋቱ 3 ሰዓት ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ሰጠ፡፡ ጋዜጠኛ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ፣ ተስፋዓለም ወልደየስ እና ኤዶም ካሳዬ እንዲሁም የኢትዮጵያ ዞን 9 ድህረ-ገፅ ብሎገሮች በፈቃዱ ኃይሉ፣ ዘለዓለም ክብረት፣ማህሌት ፋንታሁን፣ አጥናፍ ብርሃኔ፣ አቤል ዋበላ እና ናትናኤል ፈለቀ በአካል ፍርድ ቤት የቀረቡ ሲሆን፤ 1ኛ ተከሳሽ ሶሊያና ሽመልስ በአካል ልትቀርብ ስላልቻለች በኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ጋዜጣ ጥሪ እንዲደረግ የተሰጠው ትዕዛዝ አቃቤ ህጉ ማስፈፀም ባለመቻሉ ዛሬ ክሳቸው ሊታይ ባለመቻሉ ፍርድ ቤቱ ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ሰጥቷል፡:

zonይህ በእንዲህ እንዳለ ተከላካይ ጠበቆች በአቃቤ ህግ የተመሰረተው ክስ የህገ መንግስት ጉዳይ ስለሆነ ፤ለህግ መንግስት አጣሪ ጉባዔ እንዲመራ፣አቃቤ ህግ ያቀረበው ክስ የህግ ስነስርዓቱን ባለመከተሉና ግልፅ ባለመሆኑ መቃወሚያ በማቅረብ ተከሳሾች በነፃ እንዲሰናበቱ አሊያም የዋስትና መብታቸው እንዲከበር በሚል ያቀረቡት ክርክር ከፍርድ ቤቱ መቅረፀ- ድምፅ ተገልብጦ አልቀረበም በሚል ፍርድ ቤቱ ብይን ሳይሰጥ ቀርቷል፡፡

ጉዳያቸው ክስ ሳይመሰረት ከ10 ወራት በላይ እንደፈጀ የሚነገርላቸውና እስካሁን ለህዝብ ይፋ ያልተደረገ የበርካታ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ጉዳይም በዕለቱ ችሎት ውሎ ነበር፡፡ በዚህም 8ቱ ከአዲስ አበባ ወደ ወልቂጤ፣ ያለፈው ጥቅምት 2006 ዓ.ም.ለአረፋ በዓል ሲሄዱ፣8ቱ ደግሞ አዲስ አበባ እያሉ በፀጥታ ኃይሎች ተይዘው በቁጥጥር ስር የዋሉት የነ ኤልያስ ከድር የክስ መዝገብ የሚገኙ 15 ወንዶችና አንዲት ሴት በአጠቃላይ 16 ወጣቶች ጉዳይ ለነሐሴ 5 ቀን 2006 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡
በተያያዘ ወቅት እንደታሰሩ የሚነገርላቸውና ከአዳማ 4 ወንድ እና አንዲት ሴት በአጠቃላይ 5 ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች በፀጥታ ኃሎች በቁጥጥር ስር የዋሉት ለነሐሴ 12 ቀን 2006 ዓ..ም. ተለዋጭ ቀነቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡ በዚህ ጉዳይ ከተከላካይ ጠበቃ በተለይም በአንድ ወንድ እና በአንዲት ሴት ተጠርጣሪ ላይ በማረሚያ ቤቱ አያያዝ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ተፈፅሟል በሚል ቅሬታ ቢቀርብም፤ ፍርድ ቤቱ በቀጠሮ ቀን መርምሮ ውሳኔ እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡ ፍርድ ቤቱም መቼ እንደሚጀመር ባይገልፅም ከነሐሴ 14 ቀን 2006 ዓ.ም. በኋላ ዝግ እንደሚሆን አስታውቋል፡፡

ፍርድ ቤቱ ባለፈው ውድቅ ያደረገውን ጉዳይ ዛሬ ያለምንም ይግባኝ ማፅደቁ ተሰማ

ዛሬ ግንቦት 24 ቀን 2006 ዓ.ም. የነበረው የፍርድ ቤት ውሎ አዲስ ክስተትን ይዞ ብቅ ማለቱ ተሰምቷል፡፡ ባለፈው ሚያዚያ 2006 ዓ.ም.ተጠርጥረው ከታሰሩ 3 ጋዜጠኞች እና 6 ብሎገሮች መካከል ዛሬ እሁድ ግንቦት 24 ቀን 2006 ዓ.ም. ቀጠሮ የነበራቸው በፍቃዱ ኃይሉ፣ አቤል ዋበላ እና ማህሌት ፋንታሁን ቀደም ሲል የማዕከላዊ ፖሊስ ጉዳዩን ወደ ፀረ-ሽብርተኝነት የክስ ጉዳይ ለመውሰድ የጠየቀው በፍርድ ቤቱ ውድቅ ተደርጎ የነበረ ቢሆንም፤ ዛሬ በሌላ ተቀያሪ ወንድ ዳኛ እዛው ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ ወንጀል ችሎት ባለፈው በነበረው ቀጠሮ ውድቅ የተደረገው በፀረ-ሽብርተኝነት ክስ ፖሊስ የጠየቀው ተጨማሪ 28 ቀናት የምርመራ ጊዜ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ በዚህም መሰረት ፍርድ ቤቱ በዛሬው ውሎ የነበፍቃዱ ፣ አቤል እና ማህሌት ሂደት ለሰኔ 22 ቀን 2006 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
FF
በጉዳዩ ላይ ጥያቄ ያቀረብንላቸው ተከላካይ ጠበቃ አቶ አምሃ መኮንን፤ ከህግ አኳያ ፖሊስ ጉዳዩን ወደ ፀረ-ሽብርተኝነት ጠይቆ ውድቅ ተደርጎበታል፣ ስለዚህ በነበረው ውሳኔ ፖሊስ ቅር ከተሰኘ ይግባኝ ማለት እንጂ በተመሳሳይ ችሎት እና ጉዳይ ላይ በፍርድ ቤቱ ውድቅ የተደረገ ጉዳይ እንደገና ቀርቦ የፖሊስ ጥያቄ ተቀባይነት ማግኘቱ እና ተጨማሪ የ28 ቀናት የምርመራ ጊዜ በሚል መፈቀዱ ከህግ አግባብ ውጭ ነው፤ ይሄንንም ለፍርድ ቤቱ ብናቀርብም ተቀባይነት አላገኘም፤ ስለዚህ የህግ አካሄድ (procedure) ስህተት ታይቶበታል ሲሉ የነበረውን ሂደት ተናግረዋል፡፡ ይህን የክስ ሂደት ፖሊስ ጉዳዩን ወደ ፀረ-ሽብርተኝነት ለመውሰድ ውድቅ ያደረገችው ዳኛ ሴት እንደነበረች አይዘነጋም፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ የነገረ-ኢትዮጵያ ጋዜጠኛ በላይ ማናየ ፖሊስ ፍርድ ቤት ያቀረባቸውን እስረኞች ሲያወጣ፤ ለተወሰነ ጊዜ በጠበቂ የፀጥታ ኃይሎች ለጊዜው ታግቶ እንዲቆይ ከተደረገ በኋላ፤ ለነገ ማዕከላዊ እንዲቀርብ ትዕዛዝ በመስጠት ተለቋል፡፡ ለተወሰነ ጊዜ የተደረገው የጋዜጠኛው እገታ ምክንያት እስካሁን አልታወቀም፡፡