ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ “ስለ ኦሮሞና አማራ ትክክለኛ የዘር ምንጭ” ያብራራሉ!!
ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ “ስለ ኦሮሞና አማራ ትክክለኛ የዘር ምንጭ” ያብራራሉ!!
• ሁሉም የኢትዮጵያ ብሔር፣ የአንድ አባትና እናት ልጆች ነው
• አዳም የተፈጠረው ጎጃም፤ ኖህ መርከቡን ያሳረፈው አራራት ተራራ ላይ ነው
• ስለ ኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ አጥንቼ አለሁ ይላሉ …

ኑሮአቸውን በአሜሪካ ያደረጉት ታዋቂው የሥነፅሁፍ ምሁር ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሣ፤ የፃፉት‹‹የኦሮሞና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ›› የተሰኘ አዲስ አነጋጋሪ የታሪክ መፅሐፍ ዛሬ ለገበያ ይቀርባል፡፡ የኦሮሞና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ ማን እንደሆነ በጥናት ደርሼበታለሁ የሚሉት ፕሮፌሰሩ፤ እስከ ዛሬ የተለያዩ የታሪክ ምሁራን ከተናገሩት ፍፁም የተለየና አዲስ የጥናት ውጤት ማግኘታቸውን ይናገራሉ፡፡ የሁለቱ ቋንቋዎች አመጣጥም በጥናቱ ተካቷል ብለዋል፡፡ በሊንከን ዩኒቨርሲቲ በሂዩማኒቲስ የትምህርት ዘርፍ የሚያስተምሩት ፍቅሬ ቶሎሳ ፤ከዚህ ቀደም ‹‹Heaven to Eden›› እና ‹‹The Hidden and untold History of the Jewish People and Ethiopians›› የሚሉ መጽሐፍትን በእንግሊዝኛ ቋንቋ ያሳተሙ ሲሆን ሁለቱም በኢንተርኔት
“አማዞን” በተባለ የመፅሃፍ ሽያጭ ድረገፅ ላይ ከተፈላጊ መፃህፍት ተርታ ተሰልፈዋል፡፡ በሙያቸው
ፀሃፌ-ተውኔትና የሥነ ፅሁፍ ምሁር ሲሆኑ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ጥልቅ ጥናትና ምርምሮችን
በማድረግም ይታወቃሉ፡፡
አንጋፋው ምሁር ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም በቅርቡ ለንባብ ባበቁት
“አዳፍኔ” የተሰኘ መፅሃፋቸው ላይ፤“የኦሮሞን ታሪክ ሙሉ አደርጎ ሊፅፍ የሚችለው ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ ብቻ ነው” ሲሉ ለብቃታቸው ምስክርነትና ዕውቅና መስጠታቸው አይዘነጋም፡፡ ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሣ በርካታ ቲያትሮችን ለደረክ ያበቁ ሲሆን ከእነዚህም መካከል “ጓደኛሞቹ”፣ “ፍቅር በአሜሪካ” እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡ በቅርቡም ‹‹ላሟ›› የተሰኘ ባለ ሁለት ገቢር ቲያትር ፅፈው ማጠናቀቃቸውንም ተናግረዋል፡፡ ፕሮፌሠሩ ለአጭር ጊዜ ዕረፍት ወደ ኢትዮጵያ መጥተው የነበረ ሲሆን ወደ አሜሪካ ከመመለሳቸው በፊት ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር በታሪክ ጥናቶቻቸው ዙሪያ ቃለ ምልልስ አድርገዋል፡
በእንግሊዝኛ ቋንቋ ያሳተሟቸው “Heaven to Eden” እና “The Hidden and untold History of the Jewish People and Ethiopians›› የሚሉት መፃህፍት በአለማቀፍ ደረጃ ሰፊ ተቀባይነት ያገኙበት ሚስጥር ምንድነው? በምን ርዕሰ ጉዳይ ላይ ነው የሚያተኩሩት?
የመፅሐፍቱ ይዘት ነው ወሳኙ፡፡ ተቀባይነት ያገኙት በቋንቋ አጠቃቀም ለአንባቢያን ምቹ ስለሆኑ ይመስለኛል፡፡
በአይሁዶች ታሪክ ላይ የሚያተኩረው መፅሐፍ፤በጉዳዩ ላይ ከተጻፉ ሌሎች መጻህፍትና በተለምዶ ስለ አይሁዶች ከሚታወቀው ምን የተለየ ነገር ይዟል?
ብዙ ጊዜ ስለ አይሁዳውያን ሲወራ፣ቀዳማዊ ሚኒልክ የዛሬ 3ሺህ ዓመት፣ 40ሺህ አይሁዳውያንን ይዞ መጣ የሚለውን ነው የምናውቀው፡፡ ከመጡት መካከል 12ሺህ ያህሉ ንፁህ እስራኤላውያን ናቸው። 28ሺህ ያህሉ እነሱን በሥራ ያገለግሉ የነበሩ ኢያቡሳውያን የሚባሉ ነገዶች ናቸው፡፡ ቀዳማዊ ሚኒልክ ለ12 ሺህዎቹ ልዩ ቦታ ሰጥቷቸው፣ በሀገሪቷ ላይ ካህናት አድርጎ ታቦት እያስቀረፀ፣ ኢትዮጵያ ላይ በዚህ መልክ ሾሟቸው ነበር፡፡ ኢያቡሳውያን ደግሞ ንጉሱን በእጅ ስራና በውትድርና ያገለግሉት ነበር፡፡ ይሄ እንግዲህ አይሁዳውያን ወደ ኢትዮጵያ ያደረጉት ሁለተኛው ፍልሰት ነው፡፡
የመጀመሪያውና ብዙም የማይነገረው የአይሁዳውያን ፍልሰት፣ የእስራኤላውያኑ መሪ ሙሴ በህይወት እያለ አባ ብሄር የሚባል ልኡል ነበር። የሙሴ አማች ነው፡፡ አባ ብሄር የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ሊሆን ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ፣አይሁዳውያን ተከትለውት መጥተው ነበር፡፡ ምክንያቱም አባ ብሄር ያገባት ልጅ የሙሴ እህት ነበረች፡፡ ሙሴ በወቅቱ ለአባ ብሄር ፅላት ቀርፆ እንዲሁም ቀይ ባህርን የከፈለባትን በትር ሰጥቶት፣ወደ ሳባ ከተማ መጥቶ ነግሷል፡፡ በወቅቱ ብዙ አይሁዳውያንም ተከትለውት መጥተው ነበር፡፡
ሶስተኛው ፍልሰት የምንለው፣የኢራቁ ናቡከደነፆር አሸንፏቸው በሚያሳድዳቸው ጊዜ፤ “ኢትዮጵያ ውስጥ አይሁዳውያን ወገኖች አሉን” ብለው ወደ ኢትዮጵያ መጥተዋል፡፡ አይሁዳውያን በነዚህ መንገዶች ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጡት፡፡
ትክክለኛዎቹ አይሁዳውያን በኢትዮጵያ ያሉት ናቸው የሚሉ ወገኖች አሉ…?
የሃይማኖታቸውን ስርአት፣ መፅሃፍትና ህግጋት ከመጠበቃቸው አንፃር ከሌላ ህዝብ ጋር ስላልተደባለቁ ትክክለኛው ያለው እነሱ ጋ ነው፡፡ ሌሎቹ ወደ አውሮፓ፣ እስያ፣ አሜሪካ የተሰደዱት እነዚህን ነገሮች በተለያዩ ጫናዎች የተነሳ ሙሉ ለሙሉ ጠብቀው አላቆዩትም፡፡ ወደዚህ የመጡት ግን በግድ ባህላችሁን ሃይማኖታችሁን ለውጡ ተብለው በኢትዮጵያውያን አልተረበሹም፤ነፃነት ነበራቸው፡፡ መሬትና ሁሉ ነገር የተመቻቸላቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ነበር፡፡ ሌላ አገር ላይ ቦታ እንዳይኖራቸው ተደርገው በየጊዜው ይሰደዱ ነበር፡፡ እንደውም በሩሲያ ውስጥ በድንገት አይሁዳውያንን የመግደል ድርጊት ይፈፀም ነበር። ሩሲያውያኑ ተሰባስበው፤“ዛሬ አይሁዳውያንን ገድለን እንምጣ” እያሉ ይዘምቱባቸው ነበር፡፡ ወደ መንደራቸው ሄደው አውድመዋቸው ይመለሳሉ፡፡ ማንም ስለማይበቀልላቸው ደማቸው ደመ ከልብ ሆኖ ነበር የሚቀረው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን ከተሰጣቸው ክብር የተነሳ በትንንሽ ንጉስነት ጭምር ይሾሙ ነበር፡፡ በርካቶቹም ካህናትና ሊቀ-ካህናት ተደርገው ለአይሁድ እምነት ተሹመል፡፡ ቀጥሎ ደግሞ የሰለሞን ዘር ነን በሚሉት ውስጥም ገብተው፣ ስርወ መንግስት እስከ መመስረት የደረሱ ነበሩ፡፡ በዓለም ላይ አይሁዳውያን ደልቷቸው የኖሩት ኢትዮጵያ ላይ ብቻ ነው፡፡ በጠቅላላው በኢትዮጵያ ሀገራት ማለትም፡- በግብፅ፣ የመን፣ ኑቢያ—ኢትዮጵያ ባስተዳደረቻቸው አካባቢዎች በሙሉ በክብር ተይዘው ነው የኖሩት፡፡ ትልቁ ማስረጃ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ፣ እናቱ ማርያምና ቅዱስ ዮሴፍ በስደቱ ዘመኑ እኛ ጋ ብቻ ነው ጥገኝነት ያገኙት። በወቅቱ ግብፅ ለሁለት ተከፍሎ ነበር፡፡ አንዱ ክፍል በሮማውያን ቁጥጥር ስር ነበር፡፡ ሁለተኛው የኢትዮጵያ ክፍል ነው፡፡ ኢየሱስ ከመወለዱ ከ880 ዓመት በፊት አማራዎች፤ አማሩላ ደልታ ወደሚባል ቦታ ሄደው፣ አክሱማይት የተባለውን ህፃን ልጅ ዙፋን በመጠበቅ ያገለግሉ ነበር፡፡ በኋላ በ800 ዓመታት ውስጥ አማሩላ ደልታ የሚባል መንደር መስርተው ነበር፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ጋርና ከቅዱስ ዮሴፍ ጋር ሲሸሹ፣ እዚያ ነው ማረፊያ ያገኙት፡፡ ይሄ መፅሃፍ ቅዱስ ውስጥ የለም፤እኛ ግን ከተለያዩ መዛግብት እናገኘዋለን፡፡ በወቅቱ የአካባቢው ንጉስ አማናቱ ተትናይ ይባላሉ፡፡ ከጎጃም ከጣና አካባቢ ነው ወደዚያ የሄደው፡፡ ሌላው አይሁዳውያኑ መፅሐፍ ቅዱሳቸው ሲጠፋባቸው ከኛ ነው የወሰዱት፡፡ አፄ ደንቀዝ የተባለው ንጉሰ ነገስት ነው ከግዕዝ ወደ እብራይስጥ አስተርጉሞ የሰጣቸው፡፡
ትክክለኛውን የአይሁድ ባህልና እምነት በመጠበቅ በኢትዮጵያ ያሉት አይሁዳውያን ብቸኞቹ ናቸው ማለት ይቻላል?
አዎ! ኦሪትን ይዘዋል፡፡ ግን በደማቸው ከኛ ተደባልቀዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ነው ሃበሻ የተባሉት። ሃበሻ ማለት የተደባለቀ ነው፡፡ “አበሳ” ያለበት ወይም እንከን ያለበት ማለት ነው፤ ሃበሻ ማለት፡፡ በቀዳማዊ ሚኒልክ ጊዜ የመጡት ከኛ ጋር ተደባልቀው 560 ዓመት ከቆዩ በኋላ በባቢሎን ስደት ጊዜ ሶስተኛዎቹ ሲመጡ፣ነባሮችን ሲያዩአቸው በመልካቸው አይሁዳውያንን አልመስል አሏቸው። ስለዚህ፤“እናንተማ ክልስ ናችሁ፤አበሳ አለባችሁ” ብለው ይሰድቧቸዋል፡፡ ነባሮቹ አይሁዶች ደግሞ፤ “እናንተ ፈላሾች፤እኛ ሀገር አለን” እያሉ ይሰድቧቸው ነበር፡፡ በዚህም “አበሻ” እና “ፈላሻ” የሚለው መጠሪያቸው ሆነ፡፡ “ሀበሻ” የሚለው ቃል እኛን አይወክለንም የምለው ለዚህ ነው፤ሀበሻ አይሁዳውያኑን ነው የሚወክለው፡፡ እኛ የኢትዮጰያ ልጆች ነን፤ ኢትዮጵያውያን ነን፡፡
“በሃበሻነቴ እኮራለሁ” ስንል የከረምነውስ—–ቀለጠ ማለት ነው?
አዎ! እኔ ኢትዮጵያዊ እንጂ ሀበሻ አይደለሁም። ሀበሻ የሚለው ቃል የስድብ ቃል ነው፡፡ እኛን አይወክለንም፡፡ አይሁዳዊ ካልሆነ በስተቀር አንድ ሰው ራሱን “ሀበሻ ነኝ” ብሎ ሊጠራ አይገባውም። ስድብ አያኮራም፡፡ ብዙ ሰው ስለማያውቅ ነው በሀበሻነቴ እኮራለሁ የሚለው፡፡ በአረብኛም ብናየው “የተደባለቀ”፤ “ንፁህ ያልሆነ” ማለት ነው። ይሄ መልካም ቃል አይደለም፡፡ ግን ሀበሻ የሚለው “አበሳ” ከሚለው እንጂ ከአረብኛ የመጣ አይደለም። ሁለቱ አይሁዳውያን መሃል ያለ የመሰዳደቢያ ቃል ነው እንጂ እኛ ኢትዮጵያውያንን አይመለከተንም፡፡
‹‹ኢትዮጵያ›› የሚለውስ ከየት የመጣ ነው?
ኢትዮጵያ የሚለው ‹‹ኢትዮጵ›› ከተባለው ሰው የመጣ ነው፡፡ ኢትዮጵ ማን ነው ካልን፣ በመፅሐፍ ቅዱስ ላይ የተጠቀሰው መልከፀዴቅ የሚባል የሳሌም ንጉሰ ነገስትና ሊቀካህን ነበር፡፡ ይህ ሰው ሃገር ያስተዳድራልም፤ሃይማኖትም ይመራል፡፡ እሱም የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነበር፡፡ ይሄ እንዴት ይሆናል ከተባለ፣ኢየሱስ በምፅአት ቀን ሲመጣ፣ የንጉስ ንጉስ፣ የካህን ካህን ሆኖ ነው፤መልከፀዴቅም የዚህ ምሳሌ ነው፡፡ ኢትዮጵያን ከዚሁ ጋር ምን ያገናኛታል ሊባል ይችላል፡፡ በጣም የሚያኮራ ግንኙነት አለው፡፡ የመልከፀድቅ ልጅ ኢትኤል ይባል ነበር፡፡ እግዚአብሔር ኢትኤልን ካለህበት የሳሌም ምድር ለቀህ ጣና ላይ ስፈር አለው፡፡ ‹‹ከዚያም ያንተ የልጅ ልጆች፣ እኔ ከ2000 አመታት በኋላ በምወለድበት ጊዜ በኢትዮጵያ ግዛት ላይ ስለ መወለዴ ኮከብ አሳይሃለሁ” ይለዋል (እንደኔ ምርምር፤ይሄ ኮከብ የተባለው መልአኩ ገብርኤል ነው) በዚህ ሁኔታ ኢትኤል አሁን ወዳለችው ኢትዮጵያ ሲደርስ እግዚአብሔር፤‹‹ኢትዮጵ›› ተብለህ ተጠራ አለው፡፡ ‹‹ኢት›› – ስጦታ ማለት ነው፡፡ ‹‹ዮጵ” – ማለት ደግሞ ቢጫ ወርቅ ነው፡፡ ስለዚህ “ቢጫ ወርቅ ስጦታ” ተባለ፡፡ በኋላ ሃገሪቷን ኢትዮጵያ አሠኛት፡፡
በመፅሐፍ ቅዱስ በተደጋጋሚ ኢትዮጵያ ተብሎ የሚጠቀሰው ስም የትኛዋን ኢትዮጵያ ነው የሚወክለው?
እሱ አሁን ያለችውን ኢትዮጵያን ነው የሚወክለው፡፡ ግን ኢትዮጵያ የሚለው መጠሪያ እስከ 13ኛው ክ/ዘመን ድረስ ለመላዋ አፍሪካ መጠሪያ ሆኖ ሲያገለግል ቆይቷል፡፡ በኋላም የመጣው አፍሪካ የሚለው ስም ከዚሁ ከኢትዮጵያ የተገኘ ነው፡፡ ከአፋሮች ነው አፍሪካ መጠሪያዋን ያገኘችው፡፡ በመፅሃፈ እዝራ ምዕራፍ ስድስት ላይ፤‹‹አፍሪካንሳውያን›› ይላል፡፡ ይሄ አፋሮችን ነው የሚወክለው፡፡ በመርከብ ስራ በቀይ ባህር ላይ የተራቀቁ ሰዎች ነበሩ፡፡ የዛሬ 3ሺህ አመት ንጉስ ሰለሞን ቤተመቅደሱን ሲሰራ፤ልዩ እንጨት፣ እጣን፣ ወርቅ (ኦፊር የተባለ ታዋቂ ወርቅ- በነሱ የተሰየመ) ጭምር ይነግዱና ለንጉሡ ያቀርቡ ስለነበር፣ስማቸው የገነነ ሆኖ አፍሪካንሳውያን የተባሉት፡፡ በሳይንሱም አፋር የሰው ዘር መገኛ እያልን ነው፡፡ ኢስያውያንም ስያሜያቸውን ያገኙት ከሣባ ቀድሞ ከነገሰው ‹‹ኢስአኤል›› ከተባለው ንጉስ ነው፡፡ ምድሪቱን ያስተዳድር ስለነበር ኢስያ ተባለች፡፡ ‹‹አፄ” የሚለውም ከዚህ የመጣ ነው፡፡
ኢትዮጵያ የሚለው ከግሪክ ቃል የመጣ ነው የሚለውስ —?
ኢትዮጵያ የሚለው ከግሪክ ቃል የመጣ ነው የሚለው ውሸት ነው፡፡ ይሄን አጣርቻለሁ፡፡ በነሱ መዝገበ ቃላት ውስጥ ይሄ ቃል የለም፡፡ ‹‹ፊቱ የተቃጠለ›› የሚለው ቃል በግሪክ ቋንቋ ኢትዮጵያ የሚለውን ሳይሆን ሌላ ትርጉም ነው የሚኖረው፡፡ ግሪኮቹ ከኛው ሰምተው ነው መልሠው ኢትዮጵያ ያሉን፡፡ እኛ ከነሱ በፊት ነበርን እንጂ እነሱ ከኛ በፊት አልነበሩም፤ ስማችንን ሊያወጡልን አይችሉም፡፡
በምርምርዎ አዳምና ሄዋን የተፈጠሩበት ቦታ የት ሆኖ አገኙት?
ኢትዮጵያ ውስጥ ነው፡፡ ጎጃም፤ ዳሞትና ጣና አካባቢ ያለ ቦታ ነው፡፡
ለዚህ ድምዳሜ ማስረጃዎ ምንድን ነው?
አንደኛ ኤደንን ከሚያጠጡ አራት ወንዞች ውስጥ አባይ የምንለው ነው ኤፌሶን የሚባለው። በኦፌር ወርቅ ዙሪያ የሚዞር መሆኑ ተፅፏል፡፡ በኔ ድምዳሜ፣የኤፌሶን ወንዝ የአሁኑ ዋቢ ሸበሌ ነው። ጤግሮስና ኤፈራጥስ ደግሞ ጊዮን ራሱ ጥንት ሜዲትራኒያን ባህር ይገባ ነበር፡፡ ድሮ ሜድትራኒያን “ኪቲ” ይባል ነበር፡፡ ጥንት ጊዮን ወንዝ ሜድትራኒያን ሲደርስ ተራራ ስለነበር ተጋጭቶ ይመለስ ነበር፡፡ ከዚያ ነው መሬት ተነቃንቆ፣ቦታው ተቆራርጦ አሁን ወዳለበት ኢራቅ የሄደው እንጂ አካባቢው እዚሁ ነበር፡፡
አዳም የት ተፈጠረ ለሚለው በመፅሃፈ ሄኖክ ላይ “ኤልዳ” በሚባል ቦታ ተፈጠረ ይላል፡፡ ኤልዳ ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ ነው ያለው፡፡ ምክንያቱም አስሌዳውያን ወይም ኤልዳውያን የሚባሉ አሁንም ድረስ ጎጃም ውስጥ አሉ፡፡ ሄኖክ በመፅሃፉ ኤልዳ ነው የተፈጠረው ይላል፡፡ ከዚያ ወስዶ ነው እግዚአብሄር በ40 ቀኑ ወደ ኤደን ገነት የከተተው ይላል፡፡ ሄዋንን ደግሞ ከአዳም ጎን አውጥቷት ነው በ80 ቀኗ ወደ ኤደን ገነት የከተታት፡፡ ከዚህ ተነስቶ ነው ወንድ በ40፣ ሴት በ80 ቀን ክርስትና የሚነሱት። ይሄ አይነቱ ስርአት በዓለም ላይ የትም የለም፤እና ይሄ በሄኖክ መፅሃፍ የተፃፈውና አሁን ያለው እውነታ ይገኛል፡፡
ሌላው ኮሬብ የሚባል ዋሻ ውስጥ አዳም ተቀበረ ይላል፡፡ በእርግጥ በሲናይ በረሃ አካባቢ ኮሬብ የሚባል ቦታ አለ፤ ግን በተመሳሳይ ይህ ቦታ ኢትዮጵያ ውስጥም አለ፡፡ ሌላው ኖህ መርከቡን ያሳረፈው አራራት ተራራ ላይ ነው ይላል፡፡ አራራት ተራራን ለመፈለግ ወደ ቦታው ሄጄ ነበር፤ በታንኳ ጣናን አቋርጬ፡፡ አራራት ተራራ የሚባለውን ሳገኘውና አቀማመጡን ሳጠናው፣ ለመርከብ ማሳረፊያነት በአናቱ ላይ ምቹ ሜዳ አለው፡፡ ኖህ ወይን ጠጅ ጠጥቶ ሰክሮ ነበር ይላል፤መፅሃፍ ቅዱስ፡፡ በእርግጥም ቦታው የወይን ጠጅ ፍሬ ለማብቀል ተስማሚ ነው፡፡ አሁንም አትክልቶችና ጌሾ ይበቅልበታል፡፡ ከዚሁ ማስረጃ ሳልወጣ፣አዲስ አመትን አበቦች አብበው አከበረ፤የእንጨት መስዋዕትም አደረገ ይላል፡፡ ይሄ እንግዲህ ዛሬ በመላ ኢትዮጵያ ያለው የአዲስ ዓመት መቀበያ ስርአት፣ ከየት መጣነትን ሊያስረዳ ይችላል። በኋላ ወደ ክርስትናው የመስቀል በዓል ደመራነት ተለወጠ እንጂ በፊት ደመራ የሚነደው በአዲስ ዓመት መጀመሪያ ላይ ነው፡፡ ለዚህ ማስረጃው አሁንም ድረስ ክርስቲያን ያልሆኑ የሀገራችን ሰዎች የደመራ ስርአት አላቸው። ይሄ የአባታቸው የኖህ ትዝታ (ማስታወሻ) ነው ሲወረስ ሲዋረስ የመጣው፡፡ በዚህና በኖህ ጉዳይ ሰፊ ጥናት እያደረግሁ ነው፤ወደፊት ይፋ ይሆናል፡፡ አንድ እዚህ ላይ ልጠቅሰው የምፈልገው፣ሌላ አራራት የሚባል ተራራ አርመን ውስጥ አለ፡፡ ተራራው ግን በረዶ ያለበት፣ ገደላገደል፣ እንኳን መርከብ ሊያሳርፍ ለሰው ልጅ የማይመችና የማያብብ ቦታ ነው፤ ስለዚህ ያ ሊሆን አይችልም፡፡
በሰንደቅ አላማው ላይም የተለየ መከራከሪያ ያቀርባሉ፡፡ ለኢትዮጵያ የተሰጠ ስጦታ ነው ሲሉ ምን ማለትዎ ነው?
ሰንደቅ አላማው ለኖህ ከተሰጠው ምልክት የመጣ ነው፡፡ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ የጎሉበት ቀለማት ሰማይ ላይ ታይተዋል፡፡ እነዚያ ቀለማት ናቸው ዛሬ ያሉት፡፡ ከንግስት ሳባ በፊት የነገሰው አፄ ኢሲአኤል ነው ሰንደቅ አላማ እንዲውለበለብ ያደረገው፡፡ ሰንደቅ አላማ የሚለው የመጣው የኢስአኤል መንግስት “ሰንደቅ አለማ” ከሚለው ነው፡፡ ከዚያ የመጣ ነው። እሱ በወቅቱ የመረጠው፡- አረንጓዴ ቢጫ፣ቀይና ሰማያዊ ቀለማት ነበር፡፡ ለሰንደቅ አላማው ያልተገዛና ያላውለበለበ ይቀጣል ብሎ ለመጀመሪያ ጊዜ አስገዳጅ ህግ ያወጣውም እሱ ነበር፡፡ በሰንደቋ አናት ላይ ኮከብ ነበር የሚቀመጠው፡፡ ኢየሱስ ሲወለድ የሚጠቁመውን ኮከብ ለማስታወስ ይጠቀም ነበር፡፡ በዓለም ላይ ሰንደቅ አላማን የፈለሰፈ የመጀመሪያው ሰውም ሊሆን ይችላል፡፡
የኢትዮጵ የልጅ ልጅ የሆነው ኢስአኤል ከፈለሰፈው ሰንደቅ አላማ ነው፣ዛሬ ያሉት የሰንደቅ አላማ ቀለማት የመጡት፡፡ ስለዚህ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በሰንደቅ አላማው ላይ ከዚህ ተነስቶ አንድ አይነት አቋም ቢይዝ መልካም ነው፡፡ ኢስአኤል ለኦሮሞውም፣ ለአማራውም፣ ለትግሬውም፣ለአፋሩም ለሌላውም ብሄረሰብ ሁሉ አባት ነው፡፡ ከአባቶቻችን የወረደ ሰንደቅ አላማ እንጂ ከባዕድ የመጣ አይደለም፡፡
ሰውየው እጅግ ጠቢብ ነበር፤ልእለ ሰብዕ (superman) ነበር፡፡ 150 አንበሳ መግደሉን ለማስታወስ ጭምር አፄ ኢስአኤል የሰብዕ እና የአውሬዎች ንጉሰ ነገስት ብሎ ነበር ራሱን የሚጠራው፡፡ ሰውየው እጅግ ጠቢብ ከመሆኑ የተነሳ የጀነቲክ ኢንጅነሪንግን የፈለሰፈውም እሱ ነው፡፡ እንስሳን ከእንስሳ፣ ዘርን ከዘር እየቀላቀለ የፈለሰፈ የመጀመሪያው የጀነቲክ ኢንጅነር ነበር። በቅሎን የፈጠረውም እሱ ነው፡፡ አህያንና ፈረስን አዳቅሎ፡፡ ይህ ሰው የሁሉም ኢትዮጵያውን አባት ነው፡፡ የኢትዮጵ ልጅ ነው፡፡ የኢትዮጵ 10 ወንዶች ልጆች ናቸው፤ አሁን የምናያቸውን የኢትዮጵያውያን ጎሳዎች ሁሉ የፈጠሩት፡፡
ሰሞኑን ለአንባቢያን የሚቀርብ መፅሃፍ እንዳዘጋጁም ሰምቼአለሁ፡፡ የመፅሐፉን ይዘት በአጭሩ ሊነግሩኝ ይችላሉ?
መፅሐፉ፤“የኦሮሞና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ” የሚል ነው፡፡ አሁን ያሉት ኢትዮጵያውያን በሞላ የኢትዮጵ ልጆች መሆናቸውን ከላይ አስረድቻለሁ፡፡
አሁን እንደምናው በሁላችንም ላይ የማንነት ቀውስ አለ፡፡ የማንነት ቀውሱ የመጣውም እኛ ማን እንደሆንን በትክክል ባለማወቃችን ነው፡፡ ስለዚህ ይህ መፅሐፍ እኛ ማን እንደሆንን፣በርካታ ታሪካዊ ማስረጃዎችና ሰነዶችን አስደግፎ፣ግልጥልጥ አድርጎ ያስረዳናል፡፡ ይህ የማንነት ቀውሳችን ከተስተካከለና ራሳችንን ካወቅን፣ በመካከላችን ግጭቶች ሊኖሩ አይችሉም፡፡ መፅሐፉ፤ፍቅር፣ ሰላምና ህብር ሊፈጥር ይችላል የሚል እምነት አለኝ፡፡ እኛ የትልቅ ሰው ዘር ነን የሚለውን በማስረጃ የሚያሳየን ነው፡፡ የሰው ዘር ምንጭ ናሙናዎች መሆናችን ይተነትናል፡፡ ማንነታችንን በትክክል ተረድተን፣ አንድ ላይ ለመጓዝ ያስችለናል ብዬ አስባለሁ – ይህ ብዙ የተደከመበት የምርምር ውጤት፡፡
የኦሮሞና የአማራ የዘር ሀረግ አንድ ነው የሚለውን ነው መፅሃፉ የሚያስረዳው?
አማራና ኦሮሞ ብቻ ሳይሆን ሁሉም በኢትዮጵያ ግዛት ያለው ብሄር፣ ጎሳ ከ10ሩ የኢትዮጵ ልጆች ነው የመጣው፡፡ ዝቅ ሲል ደግሞ የኢትዮጵ የልጅ ልጅ የሆነ፣ ጎጃም ላይ አዳምና ሄዋን ተፈጥረዋል ብዬ ባልኩት አካባቢ አንድ ጠቢብ ሰው ነበር፡፡ “ደሴት” ወይም “ደሸት” ይባላል፡፡ እሱ ነው የኦሮሞና የአማራ አባት፡፡ የዛሬ 3600 ዓመት 4 ወንዶች ልጆች ወለደ፡- መንዲ፣ መደባይ፣ ማጂ፣ ጅማ የሚባሉ፡፡ እነዚህ 4ቱም አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ የሀገር መጠሪያ ሆነዋል። ማጂ ደግሞ ማራ እና ጀማን ይወልዳል። ዛሬ አማራ የምንለው ማራ ነው፡፡ “ማራ” ማለት “እውነተኛ ብርሃን” ማለት ነው፡፡ አማራ ያሉት አጋዚያን ወይም የግዕዝ ቋንቋ ተናጋሪዎች ናቸው፡፡ ማጂ ማራን ወለደ ካልን፤ ጀማ እና ማራ ወንድማማቾ ናቸው፡፡ ሁለቱ ወንድማማቾች በአካባቢው ካሉት ጋፋቶች ጋር መዋጋት ሰልችቷቸው፣ ሃገር ለቀው ወደ ሸዋ ሲመጡ አንድ ወንዝ ያገኛሉ፡፡ ወንዙን ጀማ አሉት። አሁን የጀማ ወይም የ“ዠማ” ወንዝ ማለት ነው። ከአካባቢው እየራቁ ሲሄዱ የጥንት አባቶቻቸውን ቋንቋ “ሱባ”ን ትተዉ አማርኛን መፈልሰፍ ጀመሩ፡፡ መደባይ፣ ጅማና መንዲ ደግሞ ግማሾቹ ጎጃም ላይ ቀሩ፤ ግማሾቹ ወለጋ ሄዱ፤ሌሎቹም እየራቁ በምስራቅ አፍሪካ ተሰራጩ፡፡ ኦሮሚኛ ቋንቋ የሚባለውንም ፈጠሩ፡፡ በዚህ ሁኔታ ነው ዛሬ ያሉት ኦሮሞና አማራ የመጡት፡፡ ዘረ ደሸት ይባላሉ፡፡ የደሸት ልጆች ናቸው። የዘር ሀረጋቸው አንድ ነው፡፡ ቋንቋቸው የተለያየ የሆነው በሂደት ነው፡፡
ኦሮሞው የኩሽቲክ፣ አማራው የሰሜቲክ ዘር ናቸው፤ የመጡትም ከውጭ ነው የሚለው ለዘመናት የዘለቀ ታሪክስ …?
እሱ ፈፅሞ ውሸት ነው፡፡ ሁለቱም ከውጭ አልመጡም፡፡ እንዳስረዳሁት እዚሁ የበቀሉ ናቸው። የአማራም የኦሮሞም አባት ደሸትም ሆነ ታላቁ አባት ኢትዮጵ ኩሽ ነው፡፡ መልከፀዴቅም ኩሽ ነው። ኦሮሞና አማራ ሁለቱም ኩሽ ናቸው፡፡ አማራ ሴም አይደለም፤ ኩሽ ነው፡፡
እስከ ዛሬ ሲነገር የነበረው ውሸት ነው። ምናልባት የአማርኛ ቋንቋ ከሌሎች ጋር ሲደበላለቅ ሴሜቲክ ቤተሰብ ውስጥ ተገኝቶ ሊሆን ይችላል። ሁሉም ኢትዮጵያውያን የኩሽ ዘሮች ናቸው። በዚሁ መፅሐፌ ላይ ስለ ቋንቋም አስረድቻለሁ፡፡ በእብራይስጥም ሆነ በአረቢክ የሌሉ እንደ ጨ፣ቀ፣ፀ ያሉ ድምጾች በአማርኛና በኦሮሚኛ ቋንቋ ውስጥ አሉ። ይሄን በዝርዝር በመፅሐፉ አስቀምጫለሁ፡፡
ኦሮሞና አማራ አንድ ነው የሚለው አመለካከት በተለይ በኦሮሞ ምሁራን ዘንድ እምብዛም ተቀባይነት ያገኘ አይመስልም፡፡ በግድ ኦሮሞን አማራ ለማድረግ ነው በሚል ወቀሳ የሚሰነዝሩ አሉ …
እንዲህ የሚሉት ሁሉም ከኢትዮጵ ዘር የመጣው የደሸት ልጆች መሆናቸውን ባለማወቃቸው ነው። ይሄ መረጃ ስለሌላቸው ራሳቸውን እንደ ባዕድ አግልለው ስለሚያዩ ነው እንጂ አሁን ይሄ እኔ ያቀረብኩትን ማስረጃ በቅን ልቦና አገናዝበው ለመረዳት ከሞከሩ፣ የትልቁ ሰው የኢትዮጵ፣ የጠቢቡና የሊቀካህናቱ የደሸት ልጅ እንደሆኑ በሚያውቁ ጊዜ፣ እነሱ እንደተሳሳቱ ተገንዝበው ወደ ማንነታቸው ላይ አተኩረው ይኮሩበታል ብዬ አስባለሁ፡፡ የመጣነው ከትልቅ ዘር ነው፡፡ ኦሮሞውም አማራውም የመጣው ከዚህ ትልቅ ሰው ነው፡፡ በዚህ ሁላችንም ልንኮራ ይገባናል፡፡
የአሁኗ እና የቀድሞዋ ኢትዮጵያ ልዩነታቸውና አንድነታቸው ምንድን ነው?
በግዛት ከሄድን ጥንት መላው አፍሪካ ኢትዮጵያ ነው የሚባለው፡፡ ከየመን አልፎ ሁሉ ይሄዳል፡፡ ግብፅ ውስጥ ፈርኦኖች የሚባሉት ኢትዮጵያውያን ነበሩ፡፡ ኢትዮጵያውያን ከአባይ ላይ ከመርከብ ወርደው ሜዳ አግኝተው የሰፈሩበት ቦታ ነው፤ ግብፅ፡፡ የአፍሪካ ሁሉ ነገር ከኛ አይወጣም፡፡
የኢትዮጵያ ታሪክ የ3ሺህ ዘመን ነው ይባላል፡፡ እርሶ የደረሱበት የጥናት ውጤት ምን ይላል?-
አዎ፤ በተለምዶ 3ሺህ አመት ይባላል እንጂ ከ7ሺ በላይ ነው፤ የኢትዮጵያ ታሪክ፡፡ ኖህ ኢትዮጵያ ላይ ነግሷል፤ ከዚያ ጀምሮ 7ሺህ አመት ነው፡፡
እስካሁን በነገሩን ታሪክ ውስጥ መፅሐፍ ቅዱስ ብቻ ነው በማስረጃነት የሚጠቅሱት፡፡ መፅሐፍ ቅዱስን ብቻ የታሪክ ምንጭ ማድረግ ይቻላል?
መፅሐፍ ቅዱስ ብቻ አይደለም፡፡ 42 ሰነዶችን አሁን በሚወጣው መፅሐፌ ላይ በግልፅ አስቀምጫለሁ። እነዚህ ሰነዶች በተለያዩ ሰዎች በጥንት ጊዜ የተፃፉ ናቸው፡፡ ኑቢያ ውስጥ ጀበል ኑባ በተባለ ቦታ ተቀብረው የቀሩ፣በጥንት ፍርስራሽ የኢትዮጵያ ቤተ-ክርስቲያን (ከእስልምና በፊት የነበረ) ድንጋይ ሳጥን ውስጥ ተቀብረው የነበሩ የብራና ሰነዶች አግኝቻለሁ፡፡ በዚያ ላይም የተመሰረተ ነው። ከመፅሐፍ ቅዱስ ውጪ 42 ተጨማሪ የታሪክ ሰነዶችን ተጠቅሜያለሁ፤ይሄን መፅሐፍ ሳዘጋጅ፡፡
ቀጣይዋ ኢትዮጵያ ምን መምሰል አለባት ይላሉ?
አሁን ማንነታችንን አውቀን፣ የማንነት ቀውሳችንን ፈትተን፣ሁላችንም የኢትዮጵያ ዘር፣ የአንድ አባትና እናት ልጆች—–መሆናችንን ተገንዝበን፤ በፍቅር፣ በሰላም፣ በመከባበር፣ በእኩልነት መኖር አለብን ብዬ አስባለሁ፡፡ ሁላችንንም ኢትዮጵ ያገናኘናል፡፡
ምንጭ፡- አዲስ አድማስ
ሁለት ኢትዮጵያውያን ካይሮ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን በራፍ ራሳቸውን አቃጠሉ
ሁለት ኢትዮጵያውያን ካይሮ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን በራፍ ራሳቸውን አቃጠሉ። በቅርቡ ኦሮሚያ ከተካሄደው መጠነ ሰፊ ግድያና እስራት ሸሽተው ግብጽ መድረሳቸው የተገለጸው እነዚህ ሁለት የኦሮሞ ተወላጅ የሆኑ ኢትዮጵያውያን፣ ራሳቸውን ያቃጠሉት በተቃውሞ መሆኑን ተመልክቷል።

ሁለቱ ኢትዮጵያውያን ራሳቸውን በማቃጠል ተቃውሟቸውን የገለጹት የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን የካይሮ ቢሮ የስደተኝነት ጥያቄያቸው ውድቅ በማድረጉ እንደሆነም መረዳት ተችሏል። በግብፅ ካይሮ የሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን (UNHCR) በርካታ ኢትዮጵያውያን የጥገኝነት ጥያቄ ውድቅ በማድረጉ ብዙዎች በባህር ወደ አውሮፓ ለመሻገር በሚያደርጉት ጉዞ ህይወታቸው ማለፉ ይታወቃል።
ለጊዜው ስማቸው ያልታወቀው ኢትዮጵያውያን መቃጠላቸውን ተከትሎ ፖሊስ በስፍራው መድረሱን እና ራሳቸውን ካቃጠሉት ኢትዮጵያውያን አንዱ ቆዳው ጉዳት መታየቱን ተጠቁሟል፡፡ የሁለቱም ጤንነት አሁን በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ እስካሁን ለማወቅ አልተቻለም።
የእነ ኦሞት አግዋ ላይ ዛሬም የአቃቤ ህግ ምስክር ሳይሰማ ተቀጠረ
ከመጋቢት 2007 ዓ.ም ጀምሮ የዋስ መብት በፍርድቤት ተከልክለው በእስር የሚገኙት እነ ኦሞት አግዋ ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. የህግ አማካሪና ጠበቃቸው አመሃ መኮንን በህመም ምክንያት ችሎት ባለመገኘታቸው መዘገቡ የአቃቤ ህግ ምስክር ለመስማት ብቻ ለዘጠነኛ ጊዜ ተቀጥሯል፡፡

አንደኛ ተከሳሽ ኦሞት አግዋ ጠበቃችን አመሃ መኮንን ታመው ሆስፒታል የተኙ ስለሆነ ያለእርሳቸው ውክልና ምስክር እንዳይሰማብን ፍርድቤቱ አጭር ቀጠሮ ይስጠን ሲሉ ሶስቱንም ተከሳሾች ወክለው ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡
በዕለቱ ችሎት አቃቤ ህግ አሉኝ ካላቸው ሰባት ምስክሮች መካከል ሶስቱ በችሎቱ ምስክርነታቸውን ለመስጠት ቀርበው ነበር፡፡
ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለአቃቤ ህግ ምስክር ለመሆን የመጡት ቄስ ሽብሩ ኦጅራ በተደጋጋሚ መጥተው ሳይመሰክሩ ተመልሰውብኛል ስለዚህ እንዲመሰክሩ ይደረግልኝ ብሎ ለተከራከረው አቃቤህግ፣ ዳኛ ታረቀኝ አማረ የስነስርዓት ህጉ ተከሳሾች ያለጠበቃቸው ውክልና እንዲከራከሩ አይፈቅድም በሚል ጥያቄውን ውድቅ አድርገውታል፡፡
የአቃቤ ህግ ምስክር ቄስ ሽብሩ ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለምስክርነት ለመጡበት የሁለት ቀን ትራንስፖርት እና አበል እንዲከፈላቸው እንዲሁም ዛሬ የቀረቡ ምስክሮች ያለምንም የፍርድቤት መጥሪያ ሌሎች ተጨማሪ የአቃቤህግ ምስክሮች በጠቅላላ በቀጣይ ቀጠሮ ነሐሴ 9 ቀን 2008 ዓ.ም እንዲቀርቡ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ወንጀል ክስ ቀርቦባቸው ክሳቸው ከነሐሴ 29 ቀን 2007 ዓ. ም ጀምሮ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት አየታየ የሚገኛው የእነ ኦሞት አግዋ ሶስት ተከሳሾች ያሉበት(ኦሞት አጉዋ፣ አሽኔ አስቲን እና ጀማል ኡመር ) የክስ መዘገብ ላይ አቃቤ ህግ ምስክሮችን ማሰማት የጀመረው መጋቢት 6 ቀን 2008 ዓ.ም ነው፡፡
ምንጭ፡- EHRP
መንገድ ለመስራት የተዋዋለ የህንድ ኩባንያ ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ ይዞ ተሰወረ
በቅርቡ አንድ ቢሊዮን ብር አካባቢ የሚደርስ የመንገድ ፕሮጄክት ተሰጥቶት የነበረ አንድ የህንድ ስራ ተቋራጭ ኩባንያ የተረከበውን ስራ ሳያጠናቅቅ ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ ይዞ ከሃገር ኮበለለ።
በዚሁ ፕሮጄክት ስር ይሰሩ የነበሩ ከ200 በላይ ሰራተኞች ሊከፈላቸው የሚገባ የአንድ ወር ከግማሽ ደሞዝ ሳይከፈላቸው መቅረቱን በመግለጽ ላይ መሆናቸው ታውቋል።
የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን በበኩሉ የ958 ሚሊዮን ብር የመንገድ ፕሮጄክት ተሰጥቶት ስራውን ሳያጠናቅቅ የተሰወረው ኩባንያ ከሃገር ይዞ የወጣውን ገንዘብ ለማስመለስ ህጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቋል።

ኤስ ኢ ደብሊው (S.E.W) የተሰኘው ኩባንያ ከሶስት አመት በፊት 66 ኪሜ ርዝመት ያለው ከሃዋሳ ጭኮ የሚደርስ መንገድ እንዲሰራ ውል ተሰጥቶት የነበረ ሲሆን፣ መንገዱ በተያዘው ወር ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቅ እንደነበር ታውቋል።
ይሁንና፣ በስራው ላይ ከፍተኛ መጓተት ታይቶበታል የተባለው ኩባንያው እስካሁን ድረስ 22 ኪሎሜርት ብቻ እንደሰራ የመንገዶች ባለስልጣን ድርጅት ከሃገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ገልጿል።
ድርጅቱ የ958 ሚሊዮን ብር ፕሮጄክት ተሰጥቶት የነበረ ሲሆን፣ በሶስት አመት ውስጥ ምን ያህል ገንዘብ እንደወሰደ የተገለጸ ነገር የለም።
የህንዱ ኩባንያ በአጠቃላይ የተሰጠው ገንዘብ ከመግለፅ ተቆጥቦ የሚገኘው የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን፣ ድርጅቱ በስሩ ለሚሰሩ ሃገር በቀል ድርጅቶች መክፈል የነበረበትን ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ ከሃገር ይዞ መውጣቱን ይፋ አድርጓል።
ከአፍሪካ ልማት ባንክ በተገኘ የገንዘብ ብድር ስራውን ሲሰራ የቆየው የህንዱ ኩባንያ ከሁለት ሳምንት በፊት ፕሮጄክቱ አጓትቷል ተብሎ የተሰጠው ኮንትራትን እንዲቋረጥ ተደርጎ እንደነበር ታውቋል።
ይሁንንና፣ የኮንትራቱ መቋረጥን ተከትሎ የኩባንያው ሃላፊዎች ገንዘቡን ይዘው ከሃገር እንደወጡ የተገለጸ ሲሆን፣ ኩባንያው በአጠቃላይ ስለተከፈለው ገንዘብ ምርመራ እየተካሄደ መሆኑን ለመረዳት ተችሏል።
ከወራት በፊት በተመሳሳይ ሁኔታ በጋምቤላ ክልል በእርሻ ስራ ላይ የተሰማሩ የህንድ ባለሃብቶች የተረከቡትን ብድር ሳያወራርዱ ከሃገር መኮብለላቸውን የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ገልጾ እንደነበር ይታወሳል።
በርካታ የህንድ ኩባንያዎች በአሁኑ ወቅት በስኳር ፋብሪካ እና በመንገዶች እንዲሁም በተለያዩ የኢንቨስትመንት ስራዎች ላይ ተሰማርተው እንደሚገኙ የኢሳት ዘገባ አመልክቷል።
በእነ በቀለ ገርባ የሰብዓዊ መብት ጥሰት አቤቱታ ላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላለፈ
*ወህኒ ቤት ለአቶ በቀለ ገርባ የታዘዘውን መድሃኒት ፈልጌ ማግኘት አልቻልኩም ብሏል

በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ በሽብር ተከሰው በቂሊንጦ እስር ቤት የሚገኙት እነ በቀለ ገርባ (22 ሰዎች) የእስር ቤቱ አስተዳደር የሰብዓዊ መብት ጥሰት እያደረሰባቸው መሆኑን ሰኔ 15 ቀን 2008 ዓ.ም ለፍርድ ቤት ባቀረቡት አቤቱታ ላይ ችሎቱ ውሳኔ አሳልፏል፡፡
ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት (ጉዳያቸውን ያይ የነበረው 19ኛ ወንጀል ችሎት እንደነበር ይታወሳል 19ኛ ችሎት ለሁለት ተከፍሎ አዲስ 4ተኛ ችሎት የሽብር ጉዳዮችን ማየት ጀምሯል) በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታና በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ሰኔ ቀን 2008 ዓ.ም የሰጠውን መልስ ተመልክቶ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡
ተከሳሾች ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም ወደ ፍርድ ቤት ሲወሰዱ ድብደባ እንደደረሰባቸው፣ ልብሶቻቸው እንደተወሰዱባቸው፣ በጨለማ ቤት ስለመታሰራቸው፣ በህክምና የታዘዘን መድሃኒት እንዳያገኙ ስለመደረጋቸው፣ ቤተ መጽሐፍት እንዳልተሟላላቸው፣ በቤተሰቦቻቸው እንዳይጎበኙ ገደብ እንደተጣለባቸው፣ ገንዘብ እንደተወሰደባቸው እና ሌሎች የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እንደደረሱባቸው አቤቱታ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር በበኩሉ አቤቱታቸውን ‹‹የተቋሙን ስም ለማጥፋት›› የቀረበ ነው ሲል አጣጥሎ መልስ መስጠቱ ይታወቃል፡፡
በዚህ ላይ ፍርድ ቤቱ ዛሬ ውሳኔውን አሳውቋል፡፡ በዚህ መሰረት በሀኪም የታዘዘን መድሃኒት ማግኘት አልቻልንም በሚል ተከሳሾች ላቀረቡት አቤቱታ ፍርድ ቤቱ የእስር ቤቱ አስተዳደር ተጠርጣሪዎቹ መድሃኒቱን እንዲያገኙ እንዲፈቅድ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ ተከሳሾች ድብደባ ደርሶብናል፣ ገንዘብም ተወስዶብናል በሚል ያቀረቡት አቤቱታን በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ድርጊቱ ተፈጽሞ ከሆነ ወንጀል ስለሆነ አስፈላጊውን ማጣራት አድርገው ተከሳሾች በህግ ሊጠይቁ የሚገባቸው ስለሚሆን በዚህ የክስ መዝገብ ውሳኔ ሊሰጥበት አይችልም ብሏል፡፡
ተከሳሾች በጨለማ ክፍል መታሰራቸው ህግን ያልተከተለና የሰብዓዊ መብት ጥሰት መሆኑን በተመለከተ ያቀረቡት አቤቱታ ላይ ፍርድ ቤቱ ‹‹በማረሚያ ቤቱ በኩል ጨለማ ቤት የለም ተብሏል፤ ተከሳሾች ደግሞ ጨለማ ክፍል ታስረናል ብለዋል፡፡ ይህ ጉዳይ ማጣራትን የሚጠይቅ ስለሆነ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ጉዳዩን አጣርቶ ለሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም አስተያየቱን ይስጥበት›› የሚል ውሳኔ አስተላልፏል፡፡
የቤተ መጽሐፍትና የቴሌቪዥን አለመሟላትን እና የቤተሰብ ጥየቃ ሰዓትን በተመለከተ በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታ ፍርድ ቤቱ ‹የማረሚያ ቤቱን አስተዳደራዊ አሰራር የሚመለከት ስለሆነ ውሳኔ አንሰጥበትም› በሚል አልፎታል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ አቶ ደጀኔ ጣፋ በቤተሰብ መጎብኘት ህገ መንግስታዊ መብታችን እንጂ የአስተዳደር ጉዳይ ነው ተብሎ የሚታለፍ እንዳልነበር በመጥቀስ በውሳኔው ላይ ቅሬታቸውን ለችሎቱ አሰምተዋል፡፡
ሌላ የተሰሙ አቤቱታዎች
ፍርድ ቤቱ ቀደም ብሎ በተከሳሾች ለቀረቡት አቤቱታዎች ውሳኔ ቢያሳልፍም ዛሬም ሌሎች አቤቱታዎች ቀርበውለታል፡፡ በዋናነት አቶ በቀለ ገርባ የታዘዘላቸውን መድሃኒት አለማግኘታቸውን በተመለከተ የቀረበ አቤቱታ ሲሆን፣ አቶ በቀለ መድሃኒት ከታዘዘላቸው ሁለት ወራት ቢቆጠርም መድሃኒቱን ማግኘት አለመቻላቸውን ገልጸዋል፡፡
የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር ዋና ኦፊሰር የሆኑት ተሾመ ስዩም በጽሁፍና በቃል በሰጡት መልስ እንደተመለከተው ለአቶ በቀለ ገርባ በሀኪም የታዘዘላቸው መድሃኒት በአስተዳደሩ ባለሙያዎች በመንግስትና በከነማ መድሃኒት ቤቶች ተፈልጎ ሊገኝ አልቻለም፡፡ ‹‹መድሃኒቱ ተፈልጎ አለመገኘቱንና የሚችሉ ከሆነ በቤተሰብ በኩል እንዲሞክሩ ለአቶ በቀለ ነግሬያቸዋለሁ›› ብለዋል ዋና ኦፊሰሩ፡፡
አቶ በቀለ ገርባ በበኩላቸው በኦፊሰሩ የተሰጠው መልስ ስህተት ነው ብለዋል፡፡ ‹‹ዛሬ ፍርድ ቤት እንደምቀርብ አውቀው የተዘጋጁበት መልስ ነው፡፡ ለእኔ የነገሩኝ ነገር የለም›› ብለዋል አቶ በቀለ፡፡ ፍርድ ቤቱ ይህን በተመለከተ ማረሚያ ቤቱ በቤተሰብ በኩል መድሃኒቱ ተገዝቶ እንዲገባ እንዲፈቅድ ማሳሰቢያ በመስጠት አልፎታል፡፡
ሌላው አቶ በቀለን ከሚኖሩበት አዳማ ከተማ ተመላልሰው ከሚጠይቋቸው ቤተሰቦቻቸው መካከል ልጃቸው ቦንቱ በቀለ ባለተገለጸ ምክንያት አባቷን በእስር ቤት እንዳትጠይቅና ምግብ እንዳታደርስላቸው መከልከሏን የአቶ በቀለ ጠበቃ ለችሎት በመግለጽ፣ ልጃቸው አባቷን እንድትጠይቅና ስንቅ እንድታቀብላቸው እንዲፈቀድላት ችሎቱን ጠይቀዋል፡፡ ችሎቱ ዋና ኦፊሰር ተሾምን ስለጉዳዩ ቢጠይቅም፣ ኦፊሰሩ ‹የማውቀው ነገር የለም፣ ግን ለሚመለከታቸው አካላት አሳውቃለሁ› የሚል መልስ ሰጥተዋል፡፡
በሌላ በኩል 22ኛ ተከሳሽ የስዋህሊኛ ቋንቋ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው በተደጋጋሚ አቤቱታ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ ስዋህሊኛ አስተርጓሚ ኬንያ ኤምባሲ ጭምር ተፈልጎ ማግኘት እንዳልተቻለ ተገልጹዋል፡፡ በመሆኑም ተከሳሹ በመጠኑ እግሊዝኛ ቋንቋ ስለሚረዱ የእንግሊዝኛ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው በጠበቃቸው በኩል አሳስበዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የመቃወሚያ ብይን ለማሰማት ለሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ ይታወሳል፡፡
ምንጭ፡- EHRP