Monthly Archives: March, 2018

አቶ አበበ ካሴ በእስር ቤት ስለደረሰበት ግፍ ተናገረ

ዳንኤል ተስፋዬ

~ “በግብረሰዶም ወንጀል ከተፈረደባቸው እና ከአህምሮ እመምተኞች ጋር ከአንድ አመት በላይ አንድ ላይ አንድታሰር ተደርጌያለሁ”

~ በደረሰብኝ ኢ-ሰባዊ ድርጊት ኩላሊቴ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶበታል። ሽንቴንም መቆጣጠር አልችልም…”

~”ከወልቃይት ማንነት ጋር በተያያዘ አሁንም በማረሚያ ቤት ሀላፊዎች ድብደባ እየፈፀሙብኝ ነው…”

በግንቦት 7 ስም ተከሶ 7 ዓመት ተፈርዶበት አዲስ አበባ ማረሚያ ቤት ቃሊቲ የሚገኘው የአበበ ካሴ በእስር ቤት በደል እየተፈፀመበት እንደሚገኝ ገልፆአል።

ከ2006 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ የሚገኘው አበበ ካሴ በቃሊቲ ማ /ቤት ከፍተኛ ስቃይና ድብደባ እንደደረሰበት ተናገረ። ከዝዋይ ማረሚያ ቤት ወደ ቃሊቲ ከተዛወረ ከ2009 ዓ.ም ጀምሮ በፖለቲካ አመለካከቱ ምክንያት ሱፐር ገብረ ህይወት፣ ኦፌሰር መካሻ፣ ኦፌሰር ጥላሁን እና ሌሎችም የማረሚያ ቤቱ አመራሮች ከፍተኛ ድብደባ እንደፈፀሙበት ገልፆአል።

ስነ ልቦና እና አካላዊ ጉዳት እንዲደርስበት ግበረ ሰዶም ተከሰው ከተፈረደባቸው እና የአህምሮ ህመምተኞች ለብቻቸው ከሚተሰሩበት ማቆያ እንዳሰሩትም ተናግሯል። “ከወልቃይት ማንነት ጋር በተያያዘ እዚህ ሆነህ ወጣቶች እንዲደራጁ፣ እንዲያምፁ፣ በወልቃይት ጉዳይ ህዝብ አቋም እንዲይዝ መልህክት አስተላልፈሃል” በሚል ድብደባ ተፈፅሞብኛል ብሏል።

“እስር ቤት ውስጥ በደረሰበት ድብደባ ኩላሊቴ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶብኛል። ሽንቴንም መቆጣጠር አልችልም” ብሏል። ይህን መረጃ ያጠናቀረው ዳንኤል ተስፋየ አበበ ከፍተኛ የሆነ የወገብ ህመም እና ድካም እንዳለበት መታዘብ ችሏል።

በሌላ ክስ 20 አመት ተፋርዶበት ከአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፍርድ ቤት ቅጣቱ ተፈፃሚ እንዲሆን ትህዛዝ ለቃሊቲ ማረሚያ ቤት መሰጠቱን አበበ ገልጿል። አቶ አበበ ካሴ በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ በደረሰበት ድብደባ እና ስቃይ 20 የእግሩ እና የእጁ ጥፍሮቹ ሙሉ በሙሉ መነቀላቸው፣ ብልቱ መኮላሸቱ፣ በኤሌክትሪክ ንዝረት በተፈፀመበት ግርፋት ለ11 ወራት ያህል አንድ ጎኑ ደንዝዞ እንደነበር በዚህም ምክንያት የእግሩ ጡንቻዎች መሸማቀቃቸው መግለፁ ይታወሳል።

የዋልድባ ገዳም መነኮሳት አባ ገብረ-ሥላሴ ስና አባ ገብረ-ኢየሱስ የፍርድ ቤት ውሎ

ሀብታሙ ምናለ

የፌደራሉ ከፍተና ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት፤ የካቲት 30 ቀን 2010 ዓ. ም. በዋለው ችሎት የዋልድባ መነከሳት ባቀረቡት “የሰብዓዊ ጥሰት በማረሚያ ቤቱ ተፈፅሞብናል ፍርድ ቤቱ ተትዕዛዝ ይስጥልን!” ብለው ያቀረቡትን አቤቱታ ሰምቶ የማረሚያ ቤቱን ምላሽ ለመስማት ሲኾን ማረሚያ ቤቱም ምላሽ የሚለውን በደብዳቤ ለፍርድ ቤቱ አቅርቧል፡፡

ፍርድ ቤቱ ማረሚያ ቤቱ የሰጠውን ምላሽ እንደተመለከተው እና ውሳኔ እንደሚሰጥ አሳውቋል፡፡ አባ ገብረ ኢየሱስ ኪዳነ ማርያም “የተከሰስነውም የታሰርነው አንድ ላይ ቢኾነም እኔን ያለምንም ምክንያት ወደ ዞን አምስት በተለምዶ ጨለማ ወይም ቅጣት ቤት ወደሚባለው አዘዋውረውኛል፡፡ ተቀጥቼ ከኾነ ጥፋቴ ተነግሮኝ፤ ቅጣቴ ምን ያህል ቀን እንደኾነ አውቄ ቅጣቴን ልቀበል፤ ያለምንም ጥፋት ዝም ብዬ ነው፡፡ እየተሰቃየኹ ያለኹት ብዙ በደል ደርሶብናል፡፡ ከአመት በላይ ልብስ ሳንቀይር ቆይተን በቅርብ ቀን አንድ ምዕመን ልብስ አምጥቶልኝ እኔ ለመቀየር ችያለሁ፡፡

ነገር ግን አባ ገብረሥላሴ ከተያዙ ጀምሮ ምንም ልብስ ቀይረው አያውቁም። ሰዎች ልብስ ሲያመጡ ማስገባት አይቻልም፡፡ እያሉ እያስመለሱ ከአንድ ዓመት በላይ በአንድ ልብስ ብቻ ሳናወልቅ ቆይተናል፡፡ ኹለታችንም አብረን በአንድ ዞን የነበርነው ያለምክንያት በታትነውናል፡፡ ሰዎች ሊጠይቁን ሲመጡ የተለያየ ዞን በመኾናችን ጠያቂዎቻችን እክል እየገጠማቸው ነው፡፡ ወደነበርኩበት ዞን ልመለስ” ብለው ጠይቀዋል፡፡

ዳኞቹም፡- “ልብስ ለምን አይገባም?” ብለው የማረሚያ ቤቱ ኃላፊዎች ሲጠይቁ መልስ መስጠት ባለመቻላቻው “ልብስ ማነው የሚያመጣላችሁ?” ብለው ዳኞች ሲጠይቁ ችሎቱን ሲከታተሉ ከነበሩት ወጣቶች መካከል ለአንዳቸው የሚኾን የምንኩስና ልብስ ገዝተው ይዘው ነበር፡፡ ልብሱን ሲያቀርቡ ዳኞቹ፡- “ጠባቂዎቹን ፈትሹና ስጧቸው!” ቢልም ፍቃደኛ አለመኾናቸውን ሲያሳዩ ዳኞቹ በቁጣ “ተቀበሉና ፈትሻችሁ ስጡ!” በማለት ሲያዙ የማረሚያ ቤቱ ኃላፊ ወታደራዊ ሰላምታ በመስጠት ወደ ዳኞቹ ተጠግቶ ሊናገር ሲል ዳኞቹ፡- “የተባልከውን ብቻ አድርግ! ምንም ሌላ አያስፈልግም!” በማለት ልብሱ ተፈትሾ ለአባ ገ/ሥላሴ ተሰጥቷቸዋል፡፡

ፍርድ ቤቱም ያቀረቡትን አቤቱታ እና የተሰጠውን መልስ አይተው ውሳኔ ለመስጠት ለመጋቢት 5 ቀን 2010ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡ መጋቢት 18 መደበኛ የክስ የሚቀጥል እና ምስክር እንደሚሰማባቸው ይታወቃል፡፡

የአምቦ ዩኒቨርስቲ መምህር፥ የመብት ተሟጋች እና ጦማሪ ስዩም ተሾመ በማዕከላዊ እስር ቤት የመብት ጥሰት ተፈፀመበት

(ዳጉ ሚዲያ) የአምቦ ዩኒቨርስቲ መምህር፥ የመብት ተሟጋች፥ የኢትዮ ቲንክታንክ እና ማኀበራዊ ገፅ ጦማሪ ስዩም ተሾመ ከሚኖርበትና ይሰራበት ከነበረው ወሊሶ ከትማ በፀጥታ ኃይሎች ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ በዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እስር ቤት ከፍተኛ ስቃይና እንግልት እንደተፈፀመበት ተጠቆመ።

ከየካቲት 9 ቀን 2010 ዓ. ም. ጀምሮ በድጋሚ ለ6 ወራት የሚቆይ የአቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተግባራዊ በተደረገ ሳምንት ሳይሞላው ስዩም ተሾመ ከመኖሪያ ቤቱ ታፍኖ ማዕከላዊ በሚባለው የፌደራል ወንጀል ምርመራ ማዕከል ከፍተኛ ምርመራ እየተደረገበት ሲሆን፤ የአገዛዙ መርማሪዎች አካላዊ ጥቃት በመፈፀምና በማስገደድ የሚጠቀማቸውን የኮምፒዩተርና የኢንተርኔት አገልግሎት የይለፍ ቃሎች(ፓስ ወርድ) መወሰዱም ታውቋል። መርማሪ ፖሊሶችም የፍርድ ቤት ክስ በመመስረት ተጨማሪ የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜ በጠየቁት መሰረት እንደተፈቀደላቸውም ለማወቅ ተችሏል። ስዩም ተሾመን ማዕከላዊ ምርመራ በመሄድ ለመጎብኘት የሞከሩ ወዳጆቹ፥ የመብት ተሟጋቾችና የስራ ባልደረቦቹ እንዳይጎበኙት መከልከላቸውም ታውቋል።

ስዩም ባለፍው ለ10 ወራት ተግባራዊ ተደርጎ በነበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በተመሳሳይ መልኩ ከመኖሪያ ቤቱ በገዥው ስርዓት የፀጥታ ኃይሎች ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ በምርመራ ወቅት ከፍተኛ የአካል ጥቃት ተፈፅሞበት እንደነበርና ከተወሰኑ ወራት እስር በኋላ መለቀቁ ይታወሳል።

በሞያሌ 10 ያህል ሰላማዊ ዜጎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ተገደሉ

(ዳጉ ሚዲያ)ትናንት ቅዳሜ መጋቢት 1 ቀን 2010 ዓ.ም በደቡብ ኢትዮጵያ፥ቦረና ዞን የሞያሌ ከተማ በገዥው መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስት የፀጥታ አባላት 10 ሰላማዊ ዜጎች ሲገደሉ 11 ያህሉ መቁሰላቸውን የዓይን እማኞችን እና የከተማውን ከንቲባ ዋቢ በማድረግ የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘግቧል።

ግድያውን በተመለከተ በአስቸኳይ አዋጁ መሰረት የመላ ሀገሪቱን አጠቃላይ የጠጥታ እና የተፈጥሮ ሃብትን በበላይነት እየተቆጣጠረ ያለው የኮማንድ ፖስቱ ሴክሬተሪያት በበኩሉ በተፈጠረ የመረጃ ስህተት ምክንያት 9 ሰላማዊ ዜጎች በስሩ ባሉ የፀጥታ ኃይሎች 9 ሰላምዊ ዜጎች መገደላቸውን እና 12 ያህል መቁሰላቸውን አስታውቋል።

ግድያው የተፈፀመው በከተማው በተለምዶ ሸዋበር በሚባል ሰፈር ሲሆን፤ በወቅቱ በአካባቢው ምንም ዓይነት ህዝባዊ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ባልነበረበትና ዜጎች በተለመደ ሰላማዊ መደበኛ ዕለታዊ እንቅስቃሴ እያሉ ግድያው በጅምላ መፈፀሙን የከተማው ነዋሪዎች ተናግረዋል። በተለይ ጥቃቱ በሚፈፀምበት ወቅት በመዝናኛ ስፍራ የነበሩ፥ በምግብ ቤትና በሱቅ ግብይት ላይ የነበሩና መንገድ ላይ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ እንደሚገኙበት ተጠቁሟል።

በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ የካቲት 9 ቀን 2010 ዓ ም የታወጀው እና ለ6 ወራት የሚቆየው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተግባራዊ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ በተለይ በኦሮሚያ ክልል ባሉ የተለያዩ ከተሞች በርካታ ሰላማዊ ዜጎች በኮማንድ ፖስቱ የፀጥታ አባላት መገደላቸው የሚታወስ ሲሆን፤ የሞያሌው የጅምላ ግድያ ተጨማሪ ጥቃት መሆኑ ታውቋል። የጅምላ ጥቃቱን ተከትሎም በርካታ የከተማው ነዋሪዎች ወደ ጎረቤት ሀገር ኬንያ ተሰደዋል።

ቀደም ሲል የመብት ተሟጋች ኢትዮጵያውያን፥ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች፥ ዓለም አቀፍ ይሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት፥ የአሜሪካ መንግሥትና የአውሮፓ ህብረት አባላት እና የገዥው መንግሥት አካል የሆኑ በርካታ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተግባራዊ እንዳይደረግ ተቃውመውት እንደነበር አይዘነጋም። ይሁን እንጂ አዋጁን ተከትሎ በሰላማዊ ዜጎች ላይ እየተፈፀመ ያለው ግድያ እና እስር ተጠናክሮ መቀጠሉ ታውቋል።

በኢትዮጵያ የፖለቲካ ውጥረት ተባብሷል፤ መንግሥት በሰላማዊ ዜጎች ላይ እወሰደ ያለው የኃይል ርምጃም ቀጥሏል

(ዳጉ ሚዲያ) የኢትዮጵያ መንግሥት ሀገሪቱን በመደበኛው ህግ ስርዓት ፀጥታ መጠበቅም ሆነ ማስጠበቅ አልቻልኩም በማለት ከባለፈው የካቲት 9 ቀን 2010 ዓ ም ጀምሮ ለ6 ወራት የሚቆይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ህግ ተግባራዊ አድርጓል። ይሁን እንጂ አርብ የካቲት 23 ቀን 2010 ዓ ም በተደረገው ድንገተኛ የአስችኳይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስብሰባ አዋጁ በአወዛጋቢ ሁኔታ መፅደቁን ፓርላማው አስታውቋል።

አፈ ጉባዔው አቶ አባዱላ ገመዳ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ይፋ እንዳደረጉት ከሆነ 547 መቀመጫ ካሉት የፓርላማው አባላት መካከል 8ቱ በህይወት እንደሌሉ በመግለፅ፤ ቀሪዎቹ “539” የፓርላማ አባላት እንዳሉ አስታውቀዋል። ከነዚህ ውስጥ አዋጁ በህገ መንግሥቱ ድንጋጌ መሰረት እንዲፀድቅ ከፓርላማው 2/3 ኛ ድምፅ ድጋፍ ማግኘት እንዳለበት በመጠቆም፥ አዋጁን ለማፅደቅ 2/3ኛ ድምፅ 339 ድምፅ ብቻ እንደሚያስፈልግ፥ የተሰጠው የድጋፍ ድምፅ ግን 346 እንደሆነና ይህም ከሚጠበቀው በላይ ድምፅ ድጋፍ እንደተገኘ፥ በ88 ተቃውሞ እና በ7 ድምፀ ተዓቅቦ አዋጁ መፅደቁን አስታውቀው ነበር። ይሁን እንጂ አፈ ጉባዔው በርካታ የተሳሳቱ መረጃዎችን ለፓርላማ አባላቱና ለህዝቡ እንደገለፁ በዕለቱ የወጡ መረጃዎች አመልክተዋል።

በአፈ ጉባዔው ከተላለፉአት የሐሰት መረጃዎች መካከል በዕለቱ በፓርላማ የተገኙ አባላት ቁጥር 539 ሳይሆን 441 እንደሆነ የፓርላማው ህዝብ ግንኙነት ክፍል ወዲያውኑ በድህረ ገፁ በሰጠው እርማት ያጋለጠ ሲሆን፤ በዕለቱ የኦህዴድ/ኢህአዴግ ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር አብይ አህመድን ጨምሮ በርካታ የፓርላማ አባላት በዕለቱ ያልተገኙ እንደነበር፥ ከፓርላማው 2/3ኛ ድምፅ ለማግኘት ቢያንስ 365 ድምፅ ድጋፍ ማግኘት የሚገባ ሲሆን በዕለቱ የተገኘው የድጋፍ ድምፅ 346 ብቻ መሆኑ ቀድሞ በአፈጉባዔው መገለፃቸው አዋጁ በህጉ አግባብ እንዳልፀደቀ መረጃዎች አመልክተዋል። ይሄንንም የፓርላማው አባላት ከተበቱ በኋላ የነበረውን ስሀተት ለማረም የገዥው ስርዓት ደጋፊ የሆኑትን ጨምሮ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃንም ተደጋጋሚ የቁጥር መሰረዝና ማስተካከል ሲሞክሩ ተስተውሏል።

ይህንንም ተከትሎ አዋጁ ባለፈው ዓመት ምስከረም 2009 ዓ ም ጀምሮ ለ10 ወራት ከቆየው የአስቸኳይ አዋጅ በባሰ ህገ መንግሥቱን የሚፃረሩ፥ የዜጎችን የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የሚጥሱ አፋኝ ድንጋጌዎችን ይዟል በሚል በህዝቡ ዘንድ ተቃውሞ ቢደረግበትም፤ አዋጁ ከህግ አግባብ ውጭ በአወዛጋቢ ሁኔታ ፀድቆ ስራ ላይ መዋሉ ታውቋል። ይህንንም ተከትሎ በተለይ በምዕራብ ኢትዮጵያ የዋጁ አስፈፃሚ ተደርጎ ሙሉ ሥልጣን የተሰጠው ወታደራዊ ዕዝ “ኮማንድ ፖስት” በጥቂቱ ከ8 በላይ ሰላማዊ ዜጎች መገደላቸው ተጠቁሟል።

በተለይም በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ወለጋና ቄለም ወለጋ ዞን፥ ደንቢ ዶሎ፥ ጊንቢ፥ ሻምቡ፥ነጆ፤ ነቀምት፥ በምዕራብ ሽዋ አምቦ፥ ጊንጪ ከተገደሉት በተጨማሪ በርካታ ሰላማዊ ዜጎች በተተኮሰባቸው ጥይት መቆሰላቸውን ከስፍራው የተገኙ የዓይን እማኞች ገልፀዋል። ከተገደሉ ዜጎች መካከልም በኃይማኖት የአምልኮ ሥፍራ የነበሩ የኃይማኖት ሰባኪ “ፓስተር” እና በ80 ዎቹ የዕድሜ ክልል ያሉ አዛውንት ይገኙበታል።

መንግሥት እየወሰደ ያለውን የኃይል ርምጃ ተከትሎ ህዝባዊ ቁጣው ከምዕረብ ኢትዮጵያ ወሌሎች አካባቢዎች እየተዛመተ ይገኛል። ይህ በእንዲህ እንዳለ አዋጁን እና የመንግሥትን ወታደራዊ የኃይል ርምጃ በሚቃወሙ አካላት ከነገ ሰኞ የካቲት 26 እስከ ረቡዕ የካቲት 28 ቀን 2010 ዓ ም ከቤት ያለመውጣት፥ የንግድና የሥራ እንቅስቃሴ እቀባ መጠራቱ ታውቋል። ከነገ የካቲት 28 ቀን 2010 ዓ ም ጀምሮ ለተከታታይ 3 ቀናት በተለይ በኦሮሚያ ክልል ምንም ዓይነት መደበኛ የትራንስፖርት እና ንግድን ጨምሮ ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ እንዳይኖር፥ ህዝባዊ እቀባውን ጥሶ የሚገኝ አካልም በየ አካባቢው በሚገኙ የተቃውሞ አስተባባሪዎች ርምጃ ሊወሰድበት እንደሚችል ተጠቁሟል። ነገር ግን የጤና ተቋማትና አምቡላንሶች የተለመደ ሥራቸውን መስራት እንደሚችሉና በተቃውሞ አስተባባሪዎቹ ጥበቃ እንደሚደረግላቸው ተጠቁሟል። የአስቸኳይ አዋጁ ውድቅ እስካልተደረገ ድረስ ህዝባዊ ተቃውሞ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍል በተለያየ መንገድ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተጠቁሟል። ይሁን እንጂ በመንግሥት በኩል ግን አዋጁን በተግባር ከማስፈፀም ውጭ የተሰጠ ሌላ ምላሽ የለም። ስለሆነም ይህ እስከተዘገበበት ድረስ በሀገሪቱ ያለው የፖለቲካ ውጥረት ተባብሶ ቀጥሏል።