ዶክተር መረራ ጉዲና እና ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ክስ ተመሰረተባቸው
(አዲስ ሚዲያ) ከ3 ወር በፊት በአውሮፓ ፓርላማ ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ተጋብዘው ንግግር ያደረጉት ዶ/ር መረራ ጉዲና ወደ ሀገር ቤት ሲመለሱ ከአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ተይዘው ለ 3 ወራት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ከታሰሩ በኃላ የካቲት 16 ቀን 2009 ዓ።ም በገዥው መንግሥት ጠቅላይ አቃቤ ህግ አማካኝነት በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት ክስ ተመሰረተባቸው።

ዶክተር መረራ ጉዲና እና ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ
የቀድሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር የነበሩት እና የኦፌኮ ሊቀመንበር እንዲሁም የመድረክ ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት ዶክተር መረራ ክስ የተመሰረተባቸው፥ በአውሮፓ ህብረት በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ንግግር ለማድረግ ተጋብዘው ሲመለሱ የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራር እና ሊቀመንበር ከሆኑት ከፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ጋር ታይተዋል በሚል እንደነበር ይታወቃል።
በዶ/ር መረራ ስም የተከፈተው በዚሁ የክስ መዝገብ ፥ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ሁለተኛ ተከሳሽ ፣ አቶ ጃዋር መሃመድ ሶስተኛ ተከሳሽ በመሆን በልይሉበት ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡ ሶስቱም ተከሳሾች የተከሰሱት በወንጀለኛ መቅጫ ህጉን የተለያዩ አንቀጾች በመተላለፍ ሲሆን አራተኛ እና አምስተኛ ተከሳሽ የሆኑት የኢትዮጵያ ሳተላይ ቴሌቪዥን ( ኢሳት) እና ኦሮሞ ሚዲያ ኔትወርክ ( ኢኤም ኤን) ሲሆኑ፥ ተቋማቱ የፀረ ሽብር ህጉን በመተላለፍ ተከሰዋል፡፡
ዶ/ር መረራ ሌላ ተጨማሪ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን መተላፍ በሚል ክስ ተመስቶባቸዋል፡፡ የክሱ ጭብጥም ተከሳሾች በዋና አድራጊነት ሽብር ተግባር መፈጸማቸውን እና ለኦሮሚያ እና አማራ ክልል አመጾች ማነሳሳት እና ንብረት መውደም ተጠያቂ መሆናቸው በክሱ ላይ ተጠቅሷል።
የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤትም ክሱን ለማየት ለየካቲት 24 ቀን 2009 ዓ ም ቀነ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በተለይ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ከዚህ በፊት በሌሉበት በነ ጄነራል ተፈራ ማሞ የክስ መዝገብ የሞት ፍርድ የተፈረደባቸው ሲሆን፥ በነ አቶ አንዱዓለም አራጌ የክስ መዝገብ ደግሞ የዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት የተፈረደባቸው ሲሆን፥ የአሁኑ ከነ ዶ/ር መረራ ጉዲና ጋር የተመሰረተባቸው ክስ ለሶስተኛ ጊዜ መሆኑ ታውቋል።
መንግሥት ከህዳር 2008 ዓ ም ጀምሮ በተለይ በኦሮሚያ ፥ በአማራ ክልል እና በደቡብ ክልል ኮንሶ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀ ህዝባዊ አመፅን ተከትሎ በርካታ ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት ወታደራዊ ኃይል ሲገደሉ፥ በአስር ሺህዎች የሚቆጠሩ ሲታሰሩ ከ15 ሺህ ያላነሱ በተለያየ ጊዜ ከእስር መልቀቁን መንግሥስት ቢያስታውቅም አሁንም ድረስ ህዝባዊ አመፁን ተከትሎ የታሰሩና ሰብዓዊ መብቶቻቸው እየተጣሰ ያሉ ዜጎች መንግሥስት ከእስር ልቅቄያቸዋለሁ ክሚለው ቁጥር እንደሚልቅ ይግመታል።
ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፊት መንግሥት በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ አማካኝነት ለህዝባዊ አምፁ ተጠያቂ ራሱ መንግሥት እና አመራሮች እንደሆኑ ቢይሳውቁም፥ ለግድያ፥ እስርና እንግልት የተዳረጉት ግን ሰላማዊ ዜጎች መሆናቸውን የሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች መግለፃቸው ይታወሳል።
ምርጫ ቦርድ በሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ውዝግብ ላይ ውሳኔውን አሳወቀ
ታምሩ ጽጌ
– ‹‹የምርጫ ቦርድ አካሄድ የተለመደ በመሆኑ የሚያስደንቅ አይደለም›› ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት
– ‹‹በፓርቲው አባላት መካከል ምንም ዓይነት ልዩነት የለም›› አቶ የሺዋስ አሰፋ

ላለፉት አራት ወራት ‹‹የሰማያዊ ፓርቲ ሕጋዊ መሪ (ሊቀመንበር) እኔ ነኝ እኔ ነኝ›› በማለት ሲወዛገቡ በከረሙት ኢንጂነር ይልቃል ጌትነትና አቶ የሺዋስ አሰፋ ላይ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የካቲት 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ውሳኔውን አሳወቀ፡፡
ቦርዱ ውሳኔውን ያስታወቀው የሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 10(6)ን በመጥቀስ፣ እነ አቶ የሺዋስ አሰፋ መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. በፓርቲው ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን በኩል፣ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባዔ በመጥራት ምርጫ ማካሄዱንና አቶ የሺዋስን ሊቀመንበር አድርጎ መምረጡን ያሳወቀበትን ሪፖርት መርምሮ ነው፡፡
ከላይ የተጠቀሰው የፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ እንደሚያስረዳው፣ የፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የተሰጠውን ኃላፊነት በአግባቡ አልተወጣም ብሎ ካመነ፣ ብሔራዊ ምክር ቤቱ የመተማመኛ ድምፅ ሊሰጥ ይችላል፡፡ ነገር ግን ብሔራዊ ምክር ቤቱ የመተማመኛ ድምፅ ከነፈገው፣ በኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን በኩል አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባዔ በመጥራት ችግሩ እንዲፈታ ማድረግ እንደሚችል ያብራራል፡፡ በመሆኑም ቦርዱ እነ አቶ የሺዋስ ያደረጉት የምርጫ ሒደትን ሲመረምር፣ በሕጉና በፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ መሠረት መፈጸማቸውን በማረጋገጥ መስከረም 28 ቀን 2009 ዓ.ም. የተደረገው ጠቅላላ ጉባዔ፣ በቦርዱ ተቀባይነት ያገኘ መሆኑን፣ በቦርዱ ጸሐፊና የጽሕፈት ቤቱ ዋና ኃላፊ በአቶ ነጋ ዱፊሳ ፊርማ ወጪ የተደረገው ደብዳቤ ያሳያል፡፡
ምርጫ ወይም ጠቅላላ ጉባዔው የተደረገው ኮረም ሳይሟላ፣ ታዛቢዎች በሌሉበትና የፓርቲውን መተዳደሪያ ደንብ ተጥሶ መሆኑን በመጥቀስ የፓርቲው ሕጋዊ ሊቀመንበር መሆናቸውን በመግለጽ ሲከራከሩ ስለነበሩት ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ቦርዱ በውሳኔው ላይ ያለው ነገር የለም፡፡
ቦርዱ በውሳኔው እሳቸውን አስመልክቶ ምንም አለማለቱን አስመልክቶ ሪፖርተር ያነጋገራቸው ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት እንደተናገሩት፣ የምርጫ ቦርድ አካሄድ የተለመደ ነው፡፡ ‹‹አንድና ሁለት በመቶ ያህል ተስፋ ያደረግነው ሕዝቡን አስበው እውነተኛ ውሳኔ ይሰጣል የሚል ነበር፡፡ በመሆኑም የሚያስደንቅ አይደለም፡፡ እኛ የመጀመሪያ ሳንሆን በቅንጀት፣ በኦብኮ፣ በአንድነትና በመኢአድ ላይ የተፈጸመው በእኛም ላይ በመድረሱ አያስገርመንም፤›› ብለዋል፡፡
የመሠረቱት ፓርቲ እንደ ሌሎቹ ፓርቲዎች በሁለትና በሦስት አባላት መቀለጃ ሆኖ እንዳይቀጥል በሕግ ወይም ጠቅላላ ጉባዔው በሚወስነው ሁኔታ ለመታገል፣ የካቲት 11 እና 12 ቀን 2009 ዓ.ም. በሚያደርጉት ስብሰባ ለሕዝብ እንደሚያሳውቁ አስረድተዋል፡፡
የብሔራዊ ምርጫ ቦርድን ውሳኔ ተከትሎ ሰማያዊ ፓርቲ ዓርብ የካቲት 10 ቀን 2009 ዓ.ም. በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቀው፣ 15 ቀናት በማይፈጅ የውሳኔ ሐሳብ ከአራት ወራት በላይ ቦርዱ ሳያሳውቅ በመቅረቱ አላስፈላጊ ውጣ ውረዶች መከሰታቸውን አዲሱ የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ የሺዋስ ተናግረዋል፡፡ ቦርዱ ዘግይቶም ቢሆን የሰጠው ውሳኔ ሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንቡንና የፓርቲዎች የምርጫ ሕግን በማክበር የሚሠራ መሆኑን ያረጋገጠ በመሆኑ፣ ‹‹የቀድሞ አመራሮችና አንዳንድ አባላት እየፈጠሩት በነበረው ሁከት ግራ ለተጋቡ ደጋፊዎቻችን ጥሩ ምላሽ ነው፤›› ብለዋል፡፡
በፓርቲው ውስጥ መከፋፈል ስለነበር አባላትና ደጋፊዎች ግራ ተጋብተው መክረማቸውንና በፓርቲው ህልውና ላይ መተማመኛ ስለመኖሩ የተጠየቁት አቶ የሺዋስ፣ በፓርቲው ውስጥ መከፋፈል ያለ ለማስመሰል መሞከሩን አስረድተዋል፡፡ ነገር ግን አራቱም አካላት ማለትም ጠቅላላ ጉባዔው፣ ብሔራዊ ምክር ቤቱ፣ ሥራ አስፈጻሚውና የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽኑ በሙሉ እንዳሉ መሆናቸውን አክለዋል፡፡
በሁሉም ክልሎችና በአዲስ አበባ ከተማ ያሉ በፓርቲ አባላት መካከል ምንም ዓይነት ክፍተትም ሆነ ልዩነት እንደሌለ አቶ የሺዋስ ገልጸዋል፡፡
ሌላው አቶ የሺዋስ የተናገሩት በገዢው ፓርቲና 22 ተቃዋሚ ፓርቲዎች ያደረጉትን ድርድር በሚመለከት ነው፡፡
በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃንና የኅብረተሰብ ክፍሎች ‹‹ውይይትና ክርክር›› እየተደረገ እንደሆነ የሚናገሩት ስህተት መሆኑን የገለጹት አቶ የሺዋስ፣ ኢሕአዴግና ተቃዋሚ ፓርቲዎች አሁን እየተዘጋጁ ያሉት ‹‹ድርድር›› ለማድረግ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ውይይት የሚዲያ ተግባር ሲሆን፣ ክርክር ደግሞ በምርጫ ወቅት የሚደረግ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ‹‹በእርግጥ ድርድር በሁለት ወገኖች መካከል የሚደረግ ቢሆንም እኛ ግን 22 ሆነን ጀምረነዋል፤›› ብለዋል፡፡
ከ2002 ዓ.ም. ጀምሮ በገዢው ፓርቲና በተቃዋሚዎች መካከል ድርድር ተደርጎ እንደነበር ያስታወሱት አቶ የሺዋስ፣ አንድም ጊዜ የተገኘ ውጤት እንደሌለና አሁንም የተለየ ውጤት ይገኛል የሚል እምነት እንደሌላቸው ተናግረዋል፡፡
ኢሕአዴግን ሁሉም ፓርቲዎች ለድርድር ያልጠየቁበት ጊዜ እንዳልነበርና ምንም ምላሽ ሰጥቶ እንደማያውቅ ያስታወሱት አቶ የሺዋስ፣ የሕዝብ ጥያቄ አይሎ ሲነሳ ግን በሩን መክፈቱን አስረድተዋል፡፡ የመደራደርን ሐሳብ በቅድሚያ ያነሱት የአገሪቱን ሁኔታ የተመለከቱ አቅጣጫው ያስፈራቸው የውጭና የአገር ውስጥ ሽማግሌዎች ሆነው ሳለ፣ ኢሕአዴግ ግን ሐሳቡን ራሱ እንዳመነጨው በማድረግ ‹‹እንደራደር›› ማለቱ ተገቢ አለመሆኑንና ዕውቅናውን ለአገር ሽማግሌዎች መስጠት እንዳለበትም አስረድተዋል፡፡ ኢሕአዴግ እንደ አንድ ፓርቲ መደራደር እንጂ ሰብሳቢ፣ ታዛቢም ሆነ አደራዳሪ ሊሆን እንደማይችልም አክለዋል፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ እውነተኛ ድርድር ለማድረግና ሕዝቡ በድርድሩ እምነት እንዲያድርበት በቅድሚያ የፖለቲካና የህሊና እስረኞችን መፍታት፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ማንሳት፣ ድርድሩን የኢትዮጵያ ጉዳይ ያገባኛል ያሉ ወገኖች ሁሉ እንዲሳተፉ ክፍት ማድረግና ለግልም ሆነ ለሕዝብ መገናኛ ብዙኃን ክፍት መሆን እንዳለበት እምነቱ መሆኑን እንደገለጸ አቶ የሺዋስ አብራርተዋል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲን ያህል አባላት የታሰሩበት አንድም ተቃዋሚ ፓርቲ እንደሌለም ገልጸው፣ ድርድሩ ከመጀመሩ በፊት ሊፈቱ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
ሁሉም ፓርቲዎች ኢሕአዴግን ጨምሮ የሕዝብን ጥያቄ በሚመልስ መንገድ ድርድር ማድረግ እንዳለባቸው ያስታወቁት አቶ የሺዋስ ሕዝቦች ባነሱት ጥያቄ ምክንያት የሞቱ፣ የተፈናቀሉ፣ ወጥተው የቀሩ፣ የታሰሩ ለምሳሌ ዶ/ር መራራ ጉዲና፣ ሁለት ጋዜጠኞች ኤልያስ ገብሩና አናንያ ሶሪ ሌሎችም መፈታት እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡ ድርድሩ ሙሉ የሚሆነውም ይኼ በተግባር ከተፈተጸመ እንደሆነም አክለዋል፡፡
አሁን ገና ድርድር እንዳልተጀመረና በቀረቡት አጀንዳዎችም ላይ መስማማት እንዳልተቻለ የገለጹት አቶ የሺዋስ፣ አደራዳሪ ማን ይሁን? ታዛቢ ማን ይሁን? የአጀንዳዎች ቅደም ተከተል እንዴት ይሁን? እና ድርድሩ ለየትኛው ሚዲያ ክፍት ይሁን? የሚለው ጥያቄ የካቲት 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ምላሽ ሊያገኝ ባለመቻሉ እሳቸውን ጨምሮ ሰባት አባላት ያሉበት ኮሚቴ ተመርጦ፣ የተጠጋጋ ሐሳብ እንዲያቀርብ ለየካቲት 17 ቀን 2009 ዓ.ም. ቀጠሮ መያዙን አሳውቀዋል፡፡
ውጤታማ ድርድር ለማድረግና የፖለቲካ ለውጥ ለማምጣት የሕዝብ፣ የተፎካካሪ ፓርቲዎችና በተቃውሞ ጎራ በያለበት ተሠልፈው የሚገኙ አካላትንና የመንግሥትን ፈቃደኝነት ማግኘት አስፈላጊ መሆኑን አቶ የሺዋስ አስረድተዋል፡፡ ዘገባው የሪፖርተር ነው።
በቂሊንጦ ለደረሰው ቃጠሎ ተጠያቂዎች ናችሁ በሚል በሽብር የተከሰሱት እስረኞች ላይ የሚደርሰው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት ቀጥሏል
*ለፍርድ ቤት አቤቱታ ማሰማታቸውን ተከትሎ ጨለማ ቤት እንዲታሰሩ ተደርገዋል

ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ ፎቶ ከሲውድን ሬዲዮ
ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም በአዲስ አበባ ቂሊንጦ እስር ቤት የደረሰውን የእሳት ቃጠሎ ተከትሎ ለጠፋው የሰው ህይወትና ለደረሰው የንብረት ውድመት ተጠያቂዎች ናችሁ በሚል የፌደራል አቃቤ ህግ በፍይደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት የሽብር ክስ መስርቶባቸው በእስር ላይ የሚገኙት 38 ተከሳሾች ላይ የሚፈጸምባቸው የሰብዓዊ መብት ጥሰት ቀጥሏል፡፡
ተከሳሾች ታህሳስ 14 ቀን 2009 ዓ.ም በነበረው የችሎት ውሎ ወቅት በእስር ቤት እየደረሰብን ነው ያሉትን ኢ-ሰብዓዊ አያያዝ በተመለከተ አቤቱታ ማሰማታቸውን ተከትሎ ወደ እስር ቤቱ ሲመለሱ ጨለማ ክፍል፣ በጠባብ ቤት ውስጥ ታጭቀው እንዲታሰሩ መደረጋቸውንም ለማወቅ ተችሏል፡፡
በህክምና ላይ የሚገኙት የ66 ዓመቱ ኢትዮ- ሲውድናዊው የልብ ህክምና ባለሙያ እና የ “አዲስ የልብ ህክምና ሆስፒታል” መስራች ዶ/ር ፍቅሩ ማሩን ጨምሮ በእነ ማስረሻ ሰጤ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ የቀረበባቸው 38 ተከሳሾች፣ የጸረ-ሽብር ህጉን አንቀጽ 3 (1፣ 2፣ 4 እና 6) ስር የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት ተላልፈዋል በሚል አቃቤ ህግ በህዳር 13 ቀን 2009 ዓ.ም በይፋ ክስ እንደመሰረተባቸው ይታወሳል፡፡ ከዚህ ክስ በተጨማሪም ሌሎች 131 ሰዎች ላይ በተመሳሳይ ክስ መከፈቱ ለመንግስት ቅርበት ባላቸው መገናኛ ብዙሃን ተዘግቦም ነበር፡፡
ተከሳሾቹ በምርመራ ወቅት እጅግ የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈጸምባቸው እንደነበር በተደጋጋሚ ይፋ መደረጉ የሚታወስ ሲሆን፣ ይህንኑ የተፈጸመባቸውን ድርጊት ለችሎት ለማስረዳት መሞከራቸውን ተከትሎ ደግሞ አሁን ላይ በጨለማ ክፍል እንዲታሰሩ ተደርገዋል፡፡
በታህሳስ 14 ቀን 2009 ዓ.ም በነበረው የችሎት ውሎ ዳኞቹ ወደ ችሎት ሲገቡ ሁሉም ተከሳሾች ከመቀመጫቸው በመነሳት፣ ‹‹በእሳት ቃጠሎው ወቅት ህይወታቸውን ላጡ በእስር ላይ የነበሩ ወንድሞቻችን የህሊና ጸሎት እናደርጋለን›› በማለት ጸሎት አድርገው መቀመጣቸውና በወቅቱ ለደረሰው ቃጠሎም ተጠያቂው ያሰራቸው አካል መሆኑን መናገራቸው አሁን ላይ በጨለማ ክፍል ለመታጎር እንደዳረጋቸው ቤተሰቦቻቸው እምነታቸውን ይገልጻሉ፡፡
የተከሳሽ ቤተሰቦች በተከሳሾች ላይ እየደረሰ ያለው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት እንዲቆም የከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንትን ቢያነጋግሩም፣ ‹‹ጉዳያችሁን ወደ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ውሰዱ›› የሚል መልስ እንዳገኙ ታውቋል፡፡ በዚህም የተከሳሽ ቤተሰቦች ጠቅላይ አቃቤ ህግ በማምራት ዋና ጠቅላይ አቃቤ ህግ አቶ ጌታቸው አምባየንና ምክትል ዋና ጠቅላይ አቃቤ ህግ አቶ ብርሃኑ ወ/አገኝን አነጋግረዋል፡፡ አቶ ጌታቸው ለተከሳሽ ቤተሰቦች ‹‹ጉዳያችሁን በጽሁፍ አቅርቡ›› በማለት አቤቱታቸውን በጽሁፍ የተቀበሉ ሲሆን፣ በጉዳዩ ላይ ታህሳስ 21 ቀን 2009 ዓ.ም ምላሽ ለመስጠት ቀጠሮ ሰጥተው ነበር ፡፡ ነገር ግን ከቀናት በኋላም ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የሚሰጥበት ጉዳይ ነው የሚል ሰበብ ምላሽ እንዳላገኙ ተናግረዋል፡፡
ለፍርድ ቤቱ የቀረበው የተከሳሾችን አቤቱታ ከታች ይመልከቱ


ምንጭ፦ ኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት
ኢትዮጵያ- የአማራ ህዝብ የመብት ጥያቄና ( #AmharaProtests) በመንግስት የተወሰደው የኃይል እርምጃ
በአማራ የተቃውሞ ድምጽ በሚያሰሙ ዜጎች ላይ የሚደርሰው የመብት ጥሰት ግድያ፣ የእስርና ደብዛ መጥፋት መጠኑ ይለያይ እንጂ አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡ በተለይም አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ አሁንም ድረስ በጎንደር፣ በባህር ዳርና በምዕራብ ጎጃም ዞኖች ዜጎችን በገፍ የማሰሩ እርምጃ ቀጥሏል፡፡

ወጣት ንግስት ይርጋ በጎንደር ህዝባዊ ተቃውሞ ላይ
በተቃውሞ ሰልፎች የተሳተፉ ወጣቶችን በተለያዩ ፖሊስ ጣቢያዎች በገፍ ማሰሩ ተቃውሞዎች በበረቱባቸው ከተሞች ከፍተኛ ነው ፡፡ ለምሳሌ በጎንደር ከተማ በሚገኙ 1ኛ፣ 2ኛ፣ 3ኛ፣ 4ኛ፣ 5ኛ እና 6ኛ ፖሊስ ጣቢያዎች በጠባብ ክፍሎች ውስጥ በአንድ ጣቢያ በአማካይ እስከ 140 ሰዎች እንደሚታሰሩ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡
ጎንደር ከተማ ውስጥ 5ኛ ፖሊስ ጣቢያ ለሁለት ሳምንታት ታስሮ የነበረ ወጣት ደረጀ ጌቱ (ስሙ የተቀየረ) እንደሚናገረው በጣቢያው ውስጥ አብረውት ታስረው የነበሩት አብዛኞቹ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ መሳተፋችሁ በፎቶ ተረጋግጧል በሚል ለእስር ተዳርገው የነበሩ ናቸው፡፡
በተመሳሳይ በባህር ዳር ከተማ በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች እንዲሁ በከተማዋ ተደርጎ በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት በተሳተፉ ወጣቶች በገፍ እየታሰሩ ነው፡፡ እነዚህ ወጣቶች አንዳንዶቹ በአጭር ጊዜ ሲታሰሩ እና ሲፈቱ ሌሎች ደግሞ በተደጋጋሚ መታርና መፈተታ እንደሚገጥማቸው ማየት ተችሏል፡፡
በእነዚህ ፖሊስ ጣቢያዎች የሚታሰሩትን ማን እንደታሰረና፣ የት እንደታሰረ ቤተሰብና ዘመድ የማወቅ እድል ቢኖረውም ሌሎች የት እንደታሰሩ ሳይታወቅ ለቀናት፣ ለሳምንታትና ለወራትም የሚከርሙ መኖራቸውም ታውቋል፡፡ እነዚህ የእስር ስፍራዎች በይፋ የማይታወቁና በተቃውሞ እንቅስቃሴው እጃቸው በሰፊው አለበት በሚል መንግስት የጠረጠራቸውን “የሚመረምርባቸው” ናቸው፡፡
ከእነዚህ ድብቅ የእስር ቦታዎች መካከል ለምሳሌ ባህር ዳር አባይ ማዶ ከብአዴን ጽ/ቤት ጀርባ የሚገኝ ቀድሞ የመሳሪያ መጋዘን የነበረ ስፍራ ይገኝበታል፡፡ በዚህ ቦታ የሚታጎሩ ወጣቶችን ቤተሰቦቻቸው ለመጠየቅም ሆነ በዚያ ስፍራ ስለመኖር አለመኖራቸው ለማወቅ እንደማይችሉ ታስረው የተፈቱና፣ ታስረው እንደነበርም እንዳይናገሩ ማስፈራሪያ ደርሷቸው የወጡ ይመሰክራሉ፡፡ አበበ አስረስ (ስሙ የተቀየረ) በዚህ ድብቅ የእስር ቦታ ለ17 ቀናት ሲሰቃይ ቆይቶ መለቀቁን ይናገራል፡፡
‹‹ቦታው የሆነ መጋዘን ነገር ነው፤ ሰፊ አዳራሽ ነው፡፡ በዚህ አዳራሽ ውስጥ በጣም ብዙ ሰዎች አብረውኝ ታስረው ነበር፡፡ የእስራችን ምክንያት ብለው የነገሩን ባህር ዳር ነሐሴ 01/2008 ዓ.ም በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ሰልፉን አደራጅታችኋል የሚል ነው፡፡ በእስራችን ጊዜ ቤተሰቦቻችን አንድም ቀን አላገኙንም፡፡ በኋላ ብዙዎችን ወደ ብርሸለቆ ሲወስዷቸው እኔን ድጋሜ ሰልፍ ላይ ካገኘንህ እንገድልሃለን ብለው ዝተውብኝ የሆነ ወረቀት ላይ አስፈርመው ለቀውኛል፡፡ ማታ ላይ ነው በመኪና ከሌሎች ሦስት ልጆች ጋር ጥለውኝ የሄዱት›› ሲል ያስታውሳል አበበ፡፡
አበበ አስረስ ከድብቅ እስር ቤቱ መፈታቱን ተከትሎ ዘመድ ለመጠየቅ በሚል ከአካባቢው ዞር ለማለት አስቦ የቤተሰቦቹን ምክር ተቀብሎ ወደ አዲስ አበባ ዘመድ ጋር ሳምንታትን አሳልፏል፡፡ ‹‹በጣም ከባድ ጊዜ ነበር እስር ላይ ሆኜ ያሳለፍኩት›› የሚለው አበበ፣ ከሳምንታት የአዲስ አበባ ቆይታ በኋላ የገና በዓልን ከቤተሰቦቹ ጋር ለማሳለፍ ወደ ባህር ዳር በተመለሰበት ወቅት፣ ‹‹የት ጠፍተህ ከርመህ እንደመጣህ እናውቃለን!›› በሚል በድጋሜ ለእስር እንደተዳረገ ታውቋል፡፡
በድብቅ እስር ቤቶችም ሆነ በፖሊስ ጣቢያዎች የሚታሰሩ ሰዎች የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደሚፈጸም ለማረጋገጥ የተቻለ ሲሆን፣ በተለይ ድብደባ በብዙዎቹ ላይ በምርመራ ወቅት የሚፈጸም የሰብአዊ መብት ጥሰት ነው፡፡ በባህር ዳር ከተማ 9ኛ ፖሊስ ጣቢያ የሚታሰሩ የፖለቲካ እስረኞች በምርመራ ወቅት ጥፍርን እስከመንቀል የሚደርስ ኢ-ሰብዓዊ የሆነ ድርጊት ይፈጸምባቸዋል፡፡
ብዙዎች በፖሊስ ጣቢያ ለሳምንታት እንዲቆዩ ከተደረገ በኋላ ወደ ብርሸለቆ የወታደራዊ ማሰልጠኛ ተቋም ለ‹ተሃድሶ ስልጠኛ› ተግዘዋል፡፡ በማሰልጠኛ ተቋሙ በሚኖራቸው ቆይታም ቢሆን ተመሳሳይ፣ አንዳንዴም የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈጸምባቸዋል፡፡ (በተሃድሶ ማሰልጠኛ ስፍራዎች ስለሚፈጸም የሰብዓዊ መብት ጥሰት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት በቅርቡ ለማሳያነት ይፋ ያደረገውን ሪፖርት መመልከት ይቻላል፡፡)
በአማራ ክልል የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ መንግስት በዋናነት ቀድሞውንም በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ በሚታገሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ላይ ያነጣጠረ የእስር እርምጃ ሲወስድ ታይቷል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት ‹የጸረ-ሽብር ግብረ-ኃይል› በሽብር ጠርጥሬያቸዋለሁ በሚል 2008 ዓ.ም ሐምሌ ወር መግቢያ ላይ በጎንደር በነበሩ የወልቃይት አማራ ማንነት ጠያቂ የህዝብ ተወካይ (ኮሚቴ) አባላትን ለማሰር በተደረገ እንቅስቃሴ በሁዋላ በአማራ ክልል የተለያዩ ዞኖች ህዝባዊ ተቃውሞዎች በተደጋጋሚ መከሰታቸው ይታወሳል፡፡ የህዝባዊ ተቃውሞዎቹም መነሻ ከመስፋፋታቸው በፊት ጎንደር ላይ ብዙ ነዋሪዎች የተሳተፉበት ትልቅ እና ሰላማዊ ሰልፍም ተካሄዷል፡፡
ከጎንደር በማስከተል በሐምሌ 29 ቀን 2008 ዓ.ም የተከናወነው የባህር ዳር ሰልፍ ግን በተለየ መልኩ በአሳዝኝ ሁኔታ የተጠናቀቀ ነበር፡፡ ሰልፉ ሲጀምር ሰላማዊ የነበር ቢሆንም ዘግይቶ የመንግስት ታጣቂዎች በወሰዱት እርምጃ በአንድ ቀን ብቻ ከ50 በላይ የሚገመቱ ንጹሃን መገደላቸው የሚታወስ ነው፡፡
እስካሁን ባለው መረጃ መሰረት አማራ ክልል ከሚገኙት በአጠቃላይ 11 ዞኖች በስድስቱ ዞኖች የጎላ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ተደርጎባቸዋል፡፡ እነዚህም ሰሜን ጎንደር፣ ደቡብ ጎንደር፣ ባህር ዳር ልዩ ዞን፣ አዊ ዞን፣ ምዕራብ ጎጃም እና ምስራቅ ጎጃም ዞኖች ናቸው፡፡ በስድስቱ ዞኖች የሚገኙ አብዛኞቹ የዞንና የወረዳ ከተሞች (አንዳንድ ቦታዎች ላይ ገጠር ቀበሌዎችንም ጨምሮ) መንግስትን የሚቃወሙ ሰላማዊ ሰልፎችንና የቤት ውስጥ አድማዎችን አስተናግደዋል፡፡ የሰሜን ጎንደር ዞን ዋና ከተማና የቱሪስት መናሃሪያዋ ጎንደር ላይ የተጀመረው እንቅስቃሴ፣ ደባርቅ፣ ደብረታቦር፣ መተማ፣ አምባ ጊዮርጊስ፣ ወረታ፣ ስማዳ፣ ጋይንት፣ ባህር ዳር፣ ፍኖተ ሰላም፣ ቡሬ፣ እንጅባራ፣ ዳንግላ፣ ቻግኒ፣ ቲሊሊ፣ ብርሸለቆ፣ ቋሪት፣ ደምበጫ፣ አማኑኤል፣ ደብረ ማርቆስና ሌሎች በርካታ ከተሞችን አዳርሷል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት አድማሱን እያሰፋ የሄደውን የተቃውሞ እንቅስቃሴ ለመግታት የኃይል እርምጃ መውሰዱን በተግባር ከማሳየቱም በላይ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የመንግስት ጦር ተቃውሞውን ለመግታት ‹ማንኛውንም እርምጃ እንዲወስድ› ማዘዛቸው የሚታወስ ነው፡፡ በዚህም በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል፡፡ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች እንደ ብርሸለቆ የመሰሉ የጦር ማሰልጠኛዎች ውስጥ ሳይቀር በተለያዩ ቦታዎች ታስረዋል፤ በርካቶች ደግሞ የደረሱበት አልታወቀም፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት ባለፉት ወራት በተደረጉት የአማራ ህዝብ የተቃውሞ እንቅስቃሴዎች ወቅት ለጊዜው ያሰባሰበው መረጃም ብዙ ዜጎች በመንግስት ኃይሎች እንደተገደሉ ያሳያል፡፡ ከዚህ በታች ያለው ዝርዝር ለጊዜው ተለይተው የታወቁ የሟቾችን ስምና አድራሻ አካትቶ ለማሳያነት የቀረበ ነው፡፡
የተገደሉ ሰዎች ስም አድራሻ
1. ይሻል ከበደ ……………………………ጎንደር
2. ሲሳይ ታከለ ……………………………ጎንደር
3. አበበ ገረመው…………………………ባህር ዳር
4. ተፈሪ ባዬ ………………………………ባህር ዳር
5. እድሜዓለም ዘውዱ ……………………ባህር ዳር
6. አደራጀው ደሳለኝ …………………… ባህር ዳር (ዩኒቨርሲቲ)
7. ይበልጣል…………………………………ደብረ ታቦር
8. ግዛቸው ከተማ …………………………ጎንደር
9. አዳነ አየነው ………………………………ጎንደር
10. ማንደፍሮ አስረስ………………………ባህር ዳር
11. ቁምላቸው ቃሉ …………………………ባህር ዳር
12. አወቀ ጥበቡ ……………………………ፍኖተ ሰላም
13. ሲሳይ ከበደ ……………………………ጎንደር
14. ሰጠኝ …………………………………ጎንደር (የወልቃይት ተወላጅ)
15. እቴነሽ ሽፈራው ……………………ም/ጎጃም፣ ጂጋ
16. እንዳለው መኮነን …………………ጎንድር፣ ጋይንት
17. እሸቴ ……………………………… ባህር ዳር (ቀበሌ 16)
18. ሰለሞን አስቻለ ………………………ባህር ዳር
19. ሙሉቀን ተፈራ ………………………ባህር ዳር
20. አደራጀው ኃይሉ ………………………ባህር ዳር
21. አስማማው በየነ ……………………… ባህር ዳር
22. ታዘበው ጫኔ …………………………ባህር ዳር
23. አስራት ካሳሁን …………………………ባህር ዳር
24. የሺዋስ ወርቁ ……………………………ባህር ዳር
25. ብርሃን አቡሃይ ………………………… ባህር ዳር
26. ሽመልስ ታየ ………………………………ባህር ዳር
27. አዛናው ማሙ …………………………… ባህር ዳር
28. ሲሳይ አማረ ………………………………ባህር ዳር
29. ሞላልኝ አታላይ ………………………… ባህር ዳር
30. መሳፍንት ………………………………………ጎንደር፣ እስቴ
31. እንግዳው ዘሩ ………………………………… ባህር ዳር
32. ዝናው ተሰማ ………………………………… ባህር ዳር
33. ሞገስ ሞላ ………………………………………ባህር ዳር
34. ሞላልኝ ታደሰ …………………………………ባህር ዳር
35. ይታያል ካሴ ………………………………………ባህር ዳር
36. እሸቴ ብርቁ …………………………………… ባህር ዳር
37. ሞገስ………………………………………………ባህር ዳር
38. ገረመው አበባው ………………………………ባህር ዳር
39. ማህሌት…….…………………………………… ባህር ዳር
40. ተስፋየ ብርሃኑ …………………………………ባህር ዳር
41. ፈንታሁን………………………………………… ባህር ዳር
42. ሰጠኝ ካሴ ……………………………………… ባህር ዳር
43. ባበይ ግርማ ………………………………………ባህር ዳር
44. አለበል ዓይናለም ……………………………… ደብረ ማርቆስ
45. አብዮት ዘሪሁን …………………………………ባህር ዳር
46. አበጀ ተዘራ ………………………………………ወረታ
47. ደሞዜ ዘለቀ ……………………………………ወረታ
48. አለበል ሀይማኖት ………………………………ባህር ዳር
49. እስቲበል አስረስ …………………………………አዴት
50. ዓይናዲስ ለዓለም ……………………………… ደብረወርቅ
51. ሽመልስ ወንድሙ ……………………………… ቡሬ
52. ታደሰ ዘመኑ ………………………………………አዴት
53. ሀብታሙ ታምራት ……………………………ባህር ዳር
54. ይበልጣል እውነቱ …………………………ባህር ዳር፣ ጭስ አባይ
55. ይህነው ሽመልስ ………………………………ደብረታቦር
56. በለጠ ካሴ ………………………………………ደብረታቦር
57. አዳነ እንየው ……………………………………ጎንደር፣ ቀበሌ 16
58. አለማየሁ ይበልጣል ……………………………ዳንግላ
59. ያየህ በላቸው …………………………………… ዳንግላ
60. በረከት አለማየሁ …………………………………ዳንግላ
61. ተመስገን ……………………………………………ዳንግላ
62. ቅዱስ ሀብታሙ ………………………………… ባህር ዳር
63. ፍስሃ ጥላሁን ………………………………………ባህር ዳር
64. ሰለሞን ጥበቡ …………………………………… ቻግኒ
65. እስቲበል አስረስ …………………………………አዴት
66. ዘሪሁን ገደብዬ …………………………………ጎንደር
67. ሲሳይ ባብል ………………………………………ጎንደር
68. ባየሁ ጎንደር ………………………………………ጎንደር
69. በለጡ መሃመድ …………………………………አዘዞ፣ ጎንደር
70. እንጀራ ባዬ ………………………………………አዘዞ፣ ጎንደር
71. ወንድም ……………………………………………ጎንደር
72. ግርማቸው ከተማ ………………………… ላይ አርማጭሆ
73. ሊሻን ከበደ ………………………………………አይባ
74. መሌ አይምባ …………………………………… አይባ
75. አዛነው ደሴ ………………………………………አርማጭሆ
76. አራገው መለስ ……………………………………አርማጭሆ
77. ሰጠኝ አድማሱ ……………………………………ደልጊ
78. ታረቀኝ ተሾመ ……………………………………ደልጊ
79. ሄኖክ አታሎ ………………………………………ደልጊ
80. ደሴ ደረሰ …………………………………………ሻውራ
81. ግርማቸው ሞገስ …………………………………ሻውራ
82. ወርቁ ጠቁሳ ………………………………………ሻውራ
83. ማማዬ አንጋው …………………………………ዳንሻ
84. ፈንታ አህመድ ……………………………………ዳንሻ
85. ክንፌ ቸኮል ………………………………………በአከር
86. ሲሳይ ታከለ ……………………………………… አርማጭሆ
87. ማዕረግ ብርሃን …………………………………ደብረታቦር
88. መምህር ተስፋየ ብርሃን ……………… ደብረታቦር ቀበሌ 01
89. ይበልጣል ደሴ ………………………… ደብረታቦር ቀበሌ 01
90. አራጋው መለሰ …………………………… አርማጭሆ
91. አዳነ አያሌው ………………………… አርማጭሆ
92. አያናው ደሴ ………………………… አርማጭሆ
93. ትርፌ አጣናው ……………………… አርማጭሆ
94. መምህር ብርሃኑ አየለ …………… ሰሜን ሸዋ፣ ማጀቴ
95. አብራራው አለማየሁ ………………ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
96. ተመስገን ሲሳይ …………………… ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
97. ጋሻው ሲራጅ ……………………… ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
98. ፈንታ ሞገስ ……………………… ደቡብ ጎንደር፣ ስማዳ
99. ታደለ ያየህ ……………………………ምዕራብ ጎጃም፣ ቡሬ
(*ማስታወሻ፡- መንግስት ህዝባዊ ተቃውሞዎች በበረቱባቸው አካባቢዎች የኢንተርኔትና የስልክ ግንኙነቶችን በሙሉና በከፊል መዝጋቱ በእነዚህ አካባቢዎች ስለተከሰቱ ጉዳዮች መረጃ የማግኘት ስራውን አዳጋች በማድረጉ ይህ ዝርዝር ሁሉንም የመብት ጥሰት የደረሰባቸው ዜጎችን ያሳያል ተብሎ አይጠበቅም፡፡)
*ሌላው ከአማራ ህዝባዊ ተቃውሞ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ ለእስር ተዳርገው የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው
1. ንግስት ይርጋ………የመብት ተሟጋች፣ አድራሻ ሳንጃ ሰሜን ጎንደር…. ቃሊቲ እስር ቤት ታስራ ትገኛለች
2. አለምነው ዋሴ የመኢአድ አባል አድራሻ ጎንደር ቂሊንጦ በእስር ላይ ያለ
3. ቴዎድሮስ ተላይ……….አድራሻ ጎንደር
4. አወቀ አባተ……………….የመኢአድ አባል
5. በላይነህ አለምነህ…የሰማያዊ ፓርቲ አባል፣ አድራሻ ባህር ዳር
6. ያሬድ ግርማ…………………. የመኢአድ አባል
7. አታላይ ዛፌ…የወልቃይት አማራ ማንነት መብት ኮሚቴ አባል
*ክስ ሳይመሰረትባቸው በእስር ላይ የሚገኙ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት
7. ማሩ ዳኛው
8. ቢሆን
9. መልካሙ ታደለ
10. ሲሳይ ታፈረ
11. ወርቁ ጥላሁን
12. ድንቁ
13. ስማቸው ማዘንጊያ
14. እያዩ መጣ
15. ድርሳን ብርሃኔ
16. አንዳርጌ አባይ
17. ዮናስ ሰለሞን
18. መሃመድ ኑርየ
19. መምህር መሃመድ አሊ
20. መንግስቴ ብርሃኔ
21. ጌታነህ ደምሴ
22. ታደለ እንዳልፈራ
23. መምህር ለወየሁ ጌቱ
24. እሸቴ ደረሰ
25. ጌጤ ላሽተው
26. ሰይዒድ እንድሪስ
27. አህመድ በዛብህ
28. ጀማል ኡመር
29. አብደላ መሃመድ
30. አዲሱ ጌታነህ
31. ዘሪሁን እሸቱ
32. ጀማል ይመር
33. አበበ ጥላሁን
34. ተሻገር ወልደሚካኤል
35. እያሱ ሁሴን
36. በላቸው አወቀ
37. ዘውዱ ነጋ
38. ወልደመስቀል ማማየ
*የህዝቡን የመብት ጥያቄ (ህዝባዊ ተቃውሞ) ደግፋችኋል በሚል ከታሰሩት መካከል፡-
39. ገድፍ ጌታነህ……ሰሜን ጎንደር በለሳ ወረዳ
40. ሊቀሊቃውንት እዝራ (ቤተ-ክርስቲያንን ሽፋን አድርገው የህዝቡን ተቃውሞ ይደግፋሉ በሚል የታሰሩ)
41. ቀለመወርቅ ዓለሙ (በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የጎንደር ሀገረ ስብከት ጳጳስ ኃላፊ)
42. ሂሪያኮስ አበበ…..ጎንደር ከተማ
43. ዶክተር ጋሹ ክንዱ
(ዶክተር ጋሹ ክንዱ የቡሬ ዳሞት ሆስፒታል ሜዲካል ዳሬክተር ናቸው፡፡ ታህሳስ 27 ቀን 2009 ዓ.ም ለገና በዓል ወደ ቤተሰቦቻቸው ባመሩበት ጊዜ ባህር ዳር ከተማ ለእስር ተዳርገው ወደ አዲስ አበባ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እንዲዛወሩ ተደርገው በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡
ምንጭ፦ ኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ፕሮጀክት (ኢሰመፕ) የተዘጋጀ
የመብት አራማጅ ንግስት ይርጋ የሽብር ክስ ተመሰረተባት
በአማራ ክልል የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ጎንድር ውስጥ ለእስር ተዳርጋ ወደ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ተዛውራ ከአራት ወራት በላይ ያሳለፈችው አክቲቪስት ንግስት ይርጋና ሌሎች አምስት ሰዎች የሽብር ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡

ንግስት ይርጋ
የፌደራል አቃቤ ህግ ታህሳስ 28 ቀን 2009 ዓ.ም. በጻፈውና ለተከሳሾች ጥር 1 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲደርሳቸው በተደረገው የክስ ቻርጅ ላይ እንደተመለከተው ንግስት ይርጋ ‹‹ከአርበኞች ግንቦት ሰባት የሽብር ድርጅት ጋር ግንኙነት በመፍጠር፣ በሰሜን ጎንደርና በሌሎች የአማራ ክልል አካባቢዎች አመጽ በማስነሳት፣ አመጹን በበላይነት በመምራትና በማስቀጠል…›› የሽብር ወንጀል ድርጊት ተሳታፊ በመሆን ክስ ቀርቦባታል፡፡
ንግስት ይርጋ 1ኛ ተከሳሽ በተደረገችበት የክስ ዝርዝር ላይ እንደተመለከተው፣ ተከሳሾች በ2001 ዓ.ም የወጣውን የጸረ ሽብር አዋጅ አንቀጽ 3/4/6ን በመተላለፍ ተከሰዋል፡፡
የመብት አራማጅ ንግስት ይርጋ ነሐሴ ወር ላይ በጎንደር ከተማ በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ‹‹የአማራ ህዝብ አሸባሪ አይደለም›› የሚል ጽሁፍ የሰፈረበት ቲሸርት ለብሳ በሰልፉ ላይ መታየቷ ይታወሳል፡፡
ክሱ የቀረበለት የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት የቀረበውን ክስ በንባብ ለማሰማት ለጥር 10 ቀን 2009 ዓ.ም ቀጠሮ ይዟል፡፡
ምንጭ፦ EHRP