የፖለቲካ አመራሮቹ ችሎት ያለ ተከላካይ ጠበቃ ሲታይ፤ቀጣይ ቀጠሯቸው ግልፅ አይደለም
ዛሬ መስከረም 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ፒያሳ አራዳ በሚገኘው የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ጉዳይ በዝግ ችከሎት ያለ ተከላካይ ጠበቃ ቀጠሮ መስጠቱ ተጠቆመ፡፡ የፖለቲካ አመራሮቹ አቶ ሀብታሙ አያሌው የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺ የአንድነት ፓርቲ ምክትል የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ፣ አቶ አብርሃ ደስታ የመቀሌ ዩኒቨርስቲ መምህርና የአረና ፓርቲ ምክትል የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ እንዲሁም አቶ የሺዋስ አሰፋ የሰማያዊ ፓርቲ ምክትል የምክር ቤቱ ሰብሳቢ ከተከላካይ ጠበቆቻቸው ጋር ሳይገናኙ ከቀጠሮ ሰዓታቸው አርፍደው ከቀኑ 10 እና 11 ሰዓት ፍርድ ቤት መቅረባቸውን ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡
በነበረው የፍርድ ቤት ችሎት ተከላካይ ጠበቃ ደንበኞቻቸውን ህጉ በሚፈቅደው መሰረት በማዕከላዊ ሄደው መጎብኘትና መነጋገር ቢፈልጉም፤ በፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ማዕከል “ማዕከላዊ” ፖሊስ ስላልተፈቀደላቸው ፍርድ ቤት መገኘቱ ለፕሮፖጋንዳ ካልሆነ ከህግ አግባብ ትርጉም ስለሌለው እንደማይገኙ አስቀድመው ማሳወቃቸው ተጠቁሟል፡፡ በችሎትም ቤተሰብ፣ ጋዜጠኛ፣ ዲፕሎማቶች እና ወዳጅ ዘመድ እንዳይከታተል መከልከሉም ታውቋል፡፡ የእስረኞቹ ቀጣይ ቀጠሮ መቼ እንደሆነ እስካሁን ከፍርድ ቤቱ ማግኘት ባይቻልም፤ እንደ ነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ ከሆነ የማዕከላዊ ምርመራ ኃላፊ አቶ ተክላይ ሹመት ተጠርጣሪዎቹ የተቀጠሩት ለጥቅምት 20 ቀን 2007 ዓ.ም. ሲሉ፤ ሌላ ፖሊስ ደግሞ ለጥቅምት 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ነው የሚል ጥቆማ መስጠታቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ እስረኞቹ እስካሁን በነበረው ምርመራ ፖሊስ ምንም ዓይነት ለወንጀል ክስ የሚያበቃ መረጃ ባለማግኘቱ፤ ወደ ኃይል እርምጃ በመሄድ ፖሊስ የሚፈልገውን ቃል እስረኞቹ ያልፈፀሙትን አስገድዶ የእምነት ቃል እንዳስፈረማቸው የማዕከላዊ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ ይሄም ለህዝቡና ለመገናኛ ብዙኃን እንዳይገለፅና ፍርድ ቤትም በቅሬታ መልክ እንዳይቀርብ ስለተፈለገ ነው ተከላካይ ጠበቆቹ እንዳይጎበኙ የተከለከሉት ሲሉ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በዚህም የዛሬው ችሎት ያለጠበቃ ጭምር በዝግ ችሎት መካሄዱ የተጠቆመ ሲሆን፤ የቀጠሯቸው ቀንም ከላይ ከተጠቀሰው ውጭ እስካሁን ትክክለኛውን ከፍርድ ቤቱ ማረጋገጥ እንዳልተቻለ መረጃዎእ አመልክተዋል፡፡ ችሎቱን ለመታደም ወደ ስፍራው ያቀኑ ሰዎችም ፍርድ ቤቱ ግቢ ሲገቡ ከወትሮ በተለየ በፖሊሶች ከፍተኛ ፍተሻ፣ እንግልትና ወከባ እንደተፈፀመባቸው የዓይን እማኞች ገልፀዋል፡፡
የደቡብ ሱዳን ቀውስ በቀጠናው ላይ ያለው ተፅዕኖ
Bisrat Woldemichael
afrosonb@gmail.com
ሱዳን በምስራቅ አፍሪካም ሆነ በአፍሪካ ካሉት ሰፊ ግዛቶች መካከል ቀዳሚዋ ነበረች፡፡ ሱዳን ለረጅም ጊዜ በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ስር የወደቀች ብትሆንም፤ ነፃነቷን ካገኘች በኋላ ግን የአረብ ሊግ አባል ሀገር ከመሆን በተጨማሪ በሼሪአ የእስልምና አስተምህሮ ህግ መተዳደር ጀመረች፡፡ ይሁን እንጂ በዜጎቿ መካከል እኩልነትንም ሆነ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል ማምጣት ባለመቻሏ ከ30 ዓመታት በላይ ለከፍተኛ የእርስ በርስ ግጭት ተዳርጋ መቆየቷ የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው፡፡
በተለይ ሱዳን የአረብ ሊግ አባል ሀገር እንደመሆኗ መጠን ኢትዮጵያን ከቀይ ባህር ማስወጣት እና ወደብ ማሳጣት ከየመን በስተቀር የግብፅና እና የሌሎች አረብ ሀገሮች የረጅም ጊዜ ዕቅድ እንድታስፈፅም ትልቅ ተልዕኮ ተሰጥቷት ነበር፡፡ በዚህም ተልዕኮ የኤርትራውን ህግአኤ (ሻዕብያ) እና የዛሬው ህወሓት/ኢህአዴግን ዋና ቢሮ በመከፍትና በተለያዩ የገንዘብና ቁሳቁስ በመደገፍ ሀገሪቱ እርስ በርስ እንድትታመስ ትልቅ ስራ ሰርታለች፡፡
ሱዳን ኢትዮጵያን ለመጉዳት እየወሰደች ያለችውን እርምጃ እንድታቆም እና እንደ ጥሩ ጎረቤት ሀገር በሰላም ተባብሮ መኖሩ እንደሚያዋጣ በቀድሞ የኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም ለሱዳን አመራሮች መልዕክት እና የቀጥታ ውይይት ተደረገ፡፡ ይሁን እንጂ ሱዳን ከአባይ ወንዝ ጋር በተያያዘ ግብፅ እና ሌሎች የአረብ ሀገሮች የሰጧትን ተልዕኮ በመደገፍ አጠናክራ ቀጠለችበት፡፡ በዚህም መንግስቱ ኃይለማርያምን ጨምሮ የወቅቱ የኢትዮጵያ መሪዎች ተደጋጋሚ ማሳሰቢያ እና ማስጠንቀቂያ ለሱዳን ከመስጠት አልቦዘኑም፤ ሱዳን ግን ቀጠለችበት፡፡
በድርጊቱ የተበሳጩት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም እና ሌሎች አመራሮቻቸው ለሱዳን የሚሆን አፀፋ ለመመለስ ተግባራዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ መውሰዱን የመጨረሻ አማራጭ አደረጉ፡፡ በዚህም በሱዳን ፈላጭ ቆራጭ የሆኑት እና እራሳቸውን አረብ ነን የሚሉት የሰሜን ሱዳን ተወላጆች በተፈጥሮ ሃብት የበለፀጉ የደቡብ ሱዳን ነዋሪዎችን መጨቆን እንደ ባህል መውሰዳቸው ለወቅቱ ኢትዮጵ መዎች እንደ አንድ የፖለቲካ ትርፍ ወሰዱት፡፡
በነዳጅና በሌሎች የተፈጥሮ ሃብት የበለፀጉት ደቡብ ሱዳኖች እንደ ሰሜኑ ሱዳን ከእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ነፃ ቢወጡም በራሳቸው ሰሜን ሱዳኖች የባሰ ባርነት ውስጥ መውደቃቸውን አምርረው የሚቃወሙ በዶ/ር ጆን ጋራንግ የሚመራ ጥቂት የደቡብ ሱዳን ተወካዮች ወደ ኢትዮጵያ የግብዣ ጥሪ ተደረገላቸው፡፡ በዚህም ከወቅቱ የኢትዮጵያ አመራሮች ጋር ባደረጉት ውይይት ልኡካኑ ከሰሜን ሱዳን በመለየት የመብቶቻቸውና የተፈጥሮ ሃብቶቻቸው ተጠቃሚ ለመሆን ትግል ማድረግ እንደሚፈልጉ አረጋገጡ፡፡ ኮሎኔል መንግስቱም ኢትዮጵያ ለየትኛው ጭቁን የአፍሪካም ሆነ የዓለም ህዝብ ኢትዮጵያ ድጋፍ ማድረግ የተለመደ በጎ ዓላማዋ ስለሆነ፤ እናንተንም አቅም በፈቀደ እንረዳችኋለን ሲሉ አረጋገጡላቸው፡፡
እነ ዶ/ር ጆን ጋራንግም ወዲያው ወደ ሱዳን እንደተመለሱ ደቡብ ሱዳንን ከሱዳን ለመለየት በሚደረገው ትግል ለመሳተፍ ፈቃደኛ ለሆኑ ደቡብ ሱዳኖች በምስጢር ጥሪ አደረጉ፡፡ እጅግ በሚገርም ሁኔታ ወዲያውኑ ከ100 ሺህ በላይ ፈቃደኛ የደቡብ ሱዳን ወጣት እና ጎልማሳ ወንዶች ፈቃደኛነታቸውን አረጋገጡ፡፡ ያኔ የዛሬዋ ደቡብ ሱዳን ከሱዳን የመለየቷ ጥንስስ እውን ሆነ፡፡ ከዚያም የደቡብ ሱዳን ንቅናቄን የሚመሩት ልኡካን በአዲስ መልክ አመራር እንዲመረት ከላደረጉ በኋላ የበላይ መሪ እንዲሆኑ ዶ/ር ጆን ጋራንግ ከሌሎች አመራሮች ጋር ተመርጠው ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ጀመሩ፡፡ በወቅቱ ወደ ትግሉ ለመግባት ፈቃደኛ እንደሆነ የተነገረላቸው 100 ሺህ ደቡብ ሱዳናውያንን ለማስታጠቅም ሆነ ለማሰማራት ምቹ ሁኔታም ሆነ የአቅርቦት ዝግጅት አልነበረም፡፡
ውጥናቸው እንዲሳካ የተለያዩ ሀገሮችን በተለይም ምዕራብ እና ምስራቅ አውሮፓ ሀገሮችን ከመማፀን ጎን ለጎን በቅድሚያ ቃል የገባችላቸው ኢትዮጵያን ተግባራዊ ድጋፍ ጠየቁ፤ ደቡብ ሱዳኖች፡፡ ኢትዮጵያም ለእሷ ሱዳንን ለመበቀል እና ጥሩ ወዳጅ የሆነች ጎረቤት ሀገርን ለመፍጠር በሚደረገው እንቅስቃሴ የራሷን አሻራ ለማኖር የገባችውን ቃል በመጠበቅ ከ80 ሺህ የማያንሱ የደቡብ ሱዳን የትግል አባላት በተለያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ስልጠና እና ሌላ ሙያዊ ድጋፍ ከነ አስተዳደራዊ ቢሮ ድጋፍ አደረገች፡፡ ይሄ ደግሞ ለደቡብ ሱዳኖች ያልተጠበቅ ትልቅ ስጦታ መሆኑን በማመን ለትግሉ ፈቃደኛ የሆኑት በጋምቤላ እና ቤኒሻንጉል (ያኔ ኢሉባቦር እና ወለጋ በሚባለው ክፍለ ሀገር) በኩል ገብተው አስፈላጊው ድጋፍ ተደረገላቸው፡፡
ሱዳንም የራሷን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች እንዲሉ፤ ኢትዮጵያ ለመጉዳት ብዙ ስትደክም ባልጠበቀችው ሁኔታ የደቡብ ሱዳን ተዋጊዎች ተጠናክረው ሲቀጥሉ፤ ሌሎች እንደ ዳርፉር፣ ደቡብ ኮርዶፋ እና ብሉ ናይል በሚባሉ አካባቢዎች በርካታ ታጣቂዎች ትግል በማድረግ ሱዳንን ቁም ስቅል አሳዩ፡፡ በዚህም ሱዳን ከስህተቷ ሳትማር ኢትዮጵኝ ለመገነጣጠል ለሚደክሙት ድጋፏን መስጠት ቀጠለች፡፡ ኢትዮጵያም አፀፋውን አጠናክራ ቀጠለች፡፡
በመጨረሻም የደቡብ ሱዳን የትግል መሪው ዶ/ር ጆን ጋራንግ በሱዳን በመሪዎች ቅንብር በአውሮፕላን ከሱዳን ወደ ኬንያ አቅጣጫ ሲጓዙ ቢገደሉም፤ ትግሉ ግን ለፍሬ በቅቶ ከ3 ዓመት በፊት ደቡብ ሱዳን የአፍሪካ እና የዓለማችን አዲስ ሀገር ሆና ብቅ አለች፡፡ በዚህም ኢትዮጵያን እንደ ሁለተኛ ቤታቸው ከመቁጠር በተጨማሪ አዲስ አበባ እና ምዕራብ ኢትዮጵያ የራሳቸው ያሁል በነፃነት ተንቀሳቅሰው ህልማቸውን እውን አደረጉ፡፡
ሱዳንም ኢትዮጵያን ከታሪካዊ እና ተፈጥሯዊ የባህር በር በተጨማሪ ልጆቿ ኤርትራውያንን ከነ ምድሯ እንድታጣ ለሰራችው ነዳጅን ጨምሮ በተፈጥሮ ሃብት የበለፀገችውን ደቡብ ሱዳንን በማጣት የሰሜን በረሃን ይዛ ቀርታለች፡፡ በዱብ ሱዳኖች የተጀመረው የትጥቅ ትግል አሁንም ሳያበቃ ዳርፉር፣ ደቡብ ኮርዶፋ እና ብሉ ናይል የተሰኙ ግዛቶቿም ከደቡብ ሱዳን መገንጠል በኋላ አሁንም ከሱዳን ለመገንጠል እየታገሉ ይገኛሉ፡፡ ይሁን እንጂ ደቡብ ሱዳን ህልሟ እውን ሆኖ ራሷን የቻለች ሀገር ብትሆንም፤ የተመኘችውን ሰላም እና የተፈጥሮ ሃብቷ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ስትደክም፤ የስልጣን ጥም እና ሙስና ባናወዛቸው መሪዎቿ ከ2 ዓመት በላይ ሰላም ልትሆን አልቻለችም፡፡
በአሁን ሰዓት ገና ነፃነቷን ከተጎናፀፈች 3 ዓመታት ያላለፋት ደቡብ ሱዳን በፕሬዘዳንቷ ሳልቫ ኪር እና በምክትላቸው ዶ/ር ሬክ ማቻር መካከል በተፈጠረ አለመግባባት ከአንድ ሺህ በላይ ዜጎቿ ህይወት ሲያልፍ፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ደግሞ ተሰደዋል፡፡ በተለይ ሱዳን ነፃነቷ ባወጀች በአመቷ በቢሊዮን የሚቆጠር የአሜሪካን ዶላር በመሪዎቿ ከሀገሪቱ ካዝና በሙስና መዘረፉን ተከትሎ ፕሬዘዳንቷ ሳልቫ ኪር ሌቦቹ አመራሮች የወሰዱት የሀገርና የህዝብ ገንዘብ በአስቸኳይ እንዲመልሱ ማስጠንቀቃቸው አልቀረም፡፡ ይሁን እንጂ የተመለሰው ከተወሰደው ረብ ያህል እንኳ እንዳልሆነ በመገንዘብ ሚኒስትሮቻቸውን እና ምክትላቸውን ሙሉ ከሙሉ ከስልጣን በማባረር የሚኒስትሮቹ ምክትሎች ለተወሰነ ጊዜ እንዲሰሩ ተደርጓል፡፡
ከሙስናው መዘዝ በተጨማሪ የስልጣን መቀናቀን እና ውክልና በማየሉ በፕሬዘዳንት ሳልቫ ኪር እና በምክትላቸው ዶ/ር ሬክ ማቻር መካከል ሰፊ ቅራኔ በመፈጠሩ፤ የተወሰኑ የሬክ ማቻር ደጋፊዎች ታሰሩ፡፡ ይሄም በሀገሪቱ የበለጠ ውጥረት በመፍጠሩ አለመግባባት ከግልሰቦች ይልቅ ወደ አመራሮቹ ጎሳ አመራ፡፡ በዚህም ፕሬዘዳንት ሳልቫ ኪር የወጡበት ዲንቃ ጎሳ እና ምክትላቸው ሬክ ማቻር የወጡበት ኑዌር ጎሳ መካከል ከፍተኛ የእርስ በርስ የጎሳ ግጭት ተከሰተ፡፡ በዚህም በርካታ ደቡብ ሱዳናውያን ህይወታቸው ሲያልፍ፣ ሌሎች በርካቶች ደግሞ ቆስለዋል፣ ሀገር ጥለውም ተሰደዋል፡፡
እስካሁን በይፋ ባይታወቅም ውስጥ ውስጡን ግን ኢትዮጵያ ውስጥ በስልጣን ያለው ኢህአዴግ ከግጭቱ ጀርባ ለኑዌር ተወላጁ ምክትል ፕሬዘዳንት ለነበሩት ሬክ ማቻር በተናጠል ድጋፍ እንደሚያደርግ መነገሩ ደግሞ ለቀጠናው አለመረጋጋት ትልቅ አስተዋፅዖ አድርጓል፡፡ በዚህም ፕሬዘዳንት ሳልቫ ኪር ሁለተኛ ቤታችን ከሚሏት ኢትዮጵያ ይልቅ ፊታቸውን ወደ ግብፅ በማድረግ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትራቸው አመካኝነት ደቡብ ሱዳን ከግብፅ ጋር የመከላከያ ጦር ስምምነት መፈራረማቸው ለኢትዮጵያ ትልቅ ስጋት መፍጠሩ አልቀረም፡፡ በተለይ በኢትዮጵያ በቋንቋ ዘር እና ጎሳ ከፋፍሎ የሚገዛው ኢህአዴግ ጎረቤት ሀገር ላይም ተመሳሳይ የተሳሳተ ‹ፖሊሲ መከተሉ ነገ ሀገሪቱን ትልቅ ዋጋ ሊያስከፍላት እንደሚችል ተገምቷል፡፡
በተለይ ኢትዮጵያ በአሁን ሰዓት የአባይ ወንዝን መገደቧ በግብፅ ዘንድ ከፍተኛ ተቃውሞና ጥርጣሬ ፈጥሮ ሳለ፤ የጎረቤት ሀገሮችን ማስቀየም ለግብፅ ጥሩ የፖለቲካ መጫወቻ መድረክ ሊፈጥር እንደሚችል የሰጉ አልታጡም፡፡ በተለይ የኢትዮጵያው ኢህአዴግ ለደቡብ ሱዳኑ የኑዌር ተወላጅ ለሆኑት ሪክ ማቻር ድጋፍ ያደርጋል ተብሎ የሚጠረጠረው፤ በሀገራችን ጋምቤላ በኑዌርና አኝዋክ መካከል ሆን ብሎ ግጭት በመፍጠር ሀገረ ውስጥ ኑዌሮች በአኝዋክ ጋምቤላዎች ላይ የበላይ እንዲሆኑ ማድረጉን በማውሳት የበለጠ ጥርጣሬው እንዲታመን አስችሎታል፡፡ በሌላ በኩል የለም! ኢህአዴግ ድጋፍ እያደረገ ያለው ለፕሬዘዳንቱ ጄነራል ሳልቫ ኪር ነው የሚሉም አልታጡም፤ ምንም እንኳ ጥርጣሬዎች በገሃድ የታዩ አሳማኝ እርምጃዎችን ዋቢ ያደረጉ ናቸው ባይባልም፡፡
በቅርቡ በሳልቫ ኪር እና በሬክ ማቻር መካከል የተፈጠረውን ግጭት ለማርገብ ኢትዮጵያ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረገች መሆኑ ደግሞ ጥርጣሬው በጥርጣሬ እንዲታይ ማድረጉ አልቀረም፡፡ በዚህም ግጭቱ እንዲበርድ እና መፍትሄ እንዲያገኝ ሁለቱም ተቀናቃኞች በቅርቡ አዲስ አበባ ላይ የተኩስ አቁም ስምምነት ቢፈራረሙም ወዲያው ተግባራዊ አላደረጉም ነበር፡፡ በተለይ የአማፂዓኑ መሪ ዶ/ር ሪክ ማቻር እና ሳልቫ ኪር ስምምነቱን ጨርሰው ወዲያው ሀገራቸው እንደገቡ፤ ዶ/ር ሪክ ማቻር ስምምነቱን የፈረሙት የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ አስፈራርተውኝ ነው የሚል መግለጫ ለአንድ የኬንያ ሚዲያ ሰጥተዋል መባሉ፤ግጭቱ በዘላቂነት ሊበርድ እንደማይችል አመላካች ነው፡፡
በአሁን ወቅት በምስራቅ አፍሪካ ባለው የፖለቲካ አለመረጋጋት፣ የደቡብ ሱዳን ግጭት የሚቀጥል ከሆነ በተለይ ለኢትዮጵያ እጅግ ፈታኝ አሉታዊ ተፅዕኖ ይኖረዋል፡፡ ተፅዕኖው ግብፅ እና የኢህአዴግም ሆነ የኢትዮጵያ ተቀናቃኞች አጋጣሚውን በመጠቀም ኢትዮጵያ ውስጥ አለመረጋጋት ሊፈጠር እንደሚችል የፖለቲካ ተንታኞች ያስረዳሉ፡፡ ስለዚህ በስልጣን ላይ ያለው ኢህአዴግ የደቡብ ሱዳን ግጭት እንዲበርድ ለየትኛውም አካል መወገን እንደሌለበት እና ሁለቱም ተቀናቃኞች በመተማመን ላይ የተመሰረተና ተግባራዊ መሆን የሚችል የሰላም ስምምነት በመፈራረም ለቀጠናው ሰላም የበኩላቸው ሊወጡ እንደሚገባ ይመከራል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ምስራቅ አፍሪካ በሶማሊያ፣ በሱዳን እና በኢትዮጵያ ካሉት የእርስ በርስ ግጭቶች በተጨማሪ የደቡብ ሱዳን መጨመር በቀጣይ ለአህጉሪቱ አፍሪካም ሆነ ለቀጠናው ሀገሮች ፖለቲካዊ፣ኢኮኖሚያዊ፣ ማኀበራዊና አካባቢያዊ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩ አይቀሬ ነው፡፡
በህይወት እስካለሁ ከመስራት ወደ ኋላ አልልም!
ብስራት ወልደሚካኤል
ሰሞኑን እንደፋሽን ይሁን በቂልነት ኢህአዴግዎች የተደናበሩ ይመስለኛል፡፡ በርግጥ ባዶ ሰው ሁሌም ደንባራ መሆኑ የሚጠበቅ ቢሆንም፡፡ ግን አንድ ነገር አለ፤ ያም የእኛን ባላገርነት(ኢትዮጵያዊነት) እንኳን እራሳቸውን መሆን ያልቻሉ ሆድ አምላኪዎች ቀርቶ ሰለጠንን ያሉ ምዕራባውያንም ለሰከንድ ተጠራጥረው አያውቁም፤ ጠንቅቀው በበቂ መረጃ ያውቁናልና፡፡ እራሳቸውን መሆን ያልቻሉ የኢህአዴግ ሰዎች ግን ይህንን ሐቅ የተረዱት አልመሰለኝም፡፡ ከእነሱ ውጭ ኢትዮጵያዊ እና ስለ ኢትዮጵያ የሚያውቅ ያለ አይመስላቸውም፡፡ ግን እንዲህ ባዶ አድርጎ የሚሞላቸው ማን ይሆን? ደግሞስ ማንበብና መፃፍ የሚችሉትስ ዝም ብለው ነው እንዴ የተነገራቸውን ብቻ የሚጋቱት? ይገርማል ኸረ ማንበብ ሙሉ ሰው ያደርጋል ባካችሁ፤ አንብቡ፣ መርምሩ፣ጠይቁ፣ እወቁ፡፡ ያኔ እራሳችሁን እንጂ ሮኆቦት አትመስሉም፡፡
ደግሞም አለማቅ ወንጀል አይደለም፤ ለማወቅ አለመፈለግና አለመሞከር ግን ለእኔ ድንቁርና ነው የሚመስለኝ፡፡ ምክንያቱም ሰው የመሆን አንዱ ተፈጥሯዊ ምስጢር ሁሌም ለማወቅ መሯሯጥ፣ መዘጋጀትና በተሻለ መንገድ ለመለወጥ መሞከር ብልህነት ነው ብዬ አምናለሁና፤ ካልሆነ ግን ከሌሎች እንሰሳት በምንም አንለይማ፡፡ ይህንን እንድል ያስቻለኝ ሰሞኑን የታዘብኩትና በራሴ ላይ የደረሰው እንዲሁም እየደረሰ ያለው ነገር አስገርሞኝ ነው፤ ግን ፈርቼ አይደለም፣ ለእውነት እና ላመንኩበት ነገር ከመቆም በስተቀር ፍርሃትን ቀድሞውንም አልፈጠረብኝምና፡፡
ባለፈው እንደወትሮ ከጓደኞቼ ጋር 4 ኪሎ አካባቢ የወጉን ተጫውተን ከተለያየን በኋላ በዕለቱ ሰኞ ነሐሴ 20 ቀን 2005 ዓ.ም. ከምሽቱ 2፡10 ሰዓት ላይ ታክሲ ቀጥታ ወደ እኔ መኖሪያ ሰፈር ስለሌለ እንደ አማራጭ አንበሳ የከተማ አውቶቡስ እጠቀማለሁ፡፡ ያኔ እንደ አማራጭ የተጠቀምኩትም ከሽሮ ሜዳ በ4 ኪሎ ቄራ የምትሄደውን 75 ቁጥር የከተማ አውቶቡስ ነበር፡፡
እኔም እንደከዚ ቀደሙ ተራ ነገር ካልሆነ ሀገር አማን ነው ብዬ በመሳፈር በዕለቱ ልክ ከምሽቱ 2፡35 ሰዓት ላይ ለመዳረሻዬ በሚቀርበኝ ጎተራ ሞሐ የለስላሳ መጠጥ ፋብሪካ ጋ ባለው ፌርማታ ወረድሁ፡፡ እንደአጋጣሚ በቦታው ከእኔ ጋር መዳረሻቸው ሆኖ የወረዱት ከ5 ሰዎች አንበልጥም፡፡ ከዛም ወደሳሪስ ታክሲ ለመያዝ የተሻለ አማራጭ ወዳለው ሼል ነዳጅ ማደያው ጋ በጎተራ ማሳለጫ የእግረኛ መንገድ ዘና ብዬ እየተጓዝኩ ሳለሁ ወደ ሙገር ሲሚንቶ አቅጣጫ ባለው የቀድሞው ባቡር ሐዲድ አማካይ ጎተራ ማሳለጫ ጋ ስደርስ ማንነታቸውን የማላውቃቸው 3 ሰዎች (2ቱ ጥቁር ጃኬት፣መነፅርና ኬፕ፣ አንዱ ግራጫ ሱሪና ሹራብ ለብሰዋል፤ ሹራብ የለበሰውን ልደታ ፍርድ ቤት የነ አንዱዓለም አራጌን፣ የነ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን፣ የነ በቀለ ገርባን፣…የችሎት ጉዳይ ለመዘገብ ስሄድ በአካል በደንብ አውቀዋለሁ፤ እዛ አይጠፋም ) “ይቅርታ ወንድም ትተባበረናለህ?” አሉኝ፡፡
እኔም ምናልባት አቅጣጫ ጠፍቶባቸው፣ መንገድ ስተው አሊያም የታክሲ ጎድሏቸው ሊሆን ይችላል ብዬ በመገመት የምችለው ከሆነ ችግር የለውም፤ እና ምን ልተባበራችሁ? ስል ጥያቄያቸውን በጥያቄ መለስኩ፡፡ ወዲያው ከእኔ ጋር ከ75 ቁጥር አውቶቡስ የወረደ ቆዳሞኝ ከኋላዬ በመምጣት ተቀላቀለ፤ ለካ ከእነሱ ጋር ትውውቅና ግብብነት ነበረው፡፡ ስለዚህ 4 ሆኑ ማለት ነው፡፡እዛ አካባቢ ያለው የመንገድ መብራት(ፓውዛ) በፊት ይጠፋል፣አይኖርም ነበር፤ የዛን ቀን ግን ወገግ ብሎ በርቷል ደስ ይላል፤ ሰው ይተላለፍበታልና፡፡
ከዛም በቅርብ ርቀት እያናገሩኝ የነበሩ ሰዎች በቁጥር 4 ሆነው ይበልጥ ወደ እኔ ተጠጉ፡፡ ኬፕ ና መነፅር ካደረጉት 2ቱ መካከል አንዱ ከመቅፅበት ሴንጢ አወጣና ሆዴ ላይ ደግኖ አሁን ምንም ትንፍሽ እንዳትል፣ ለትንሽ ደቂቃ ለጥያቄ ስለምንፈልግህ ከመንገድ ላይ ትንሽ ወረድ እንበል አለኝ፡፡ እኔም እንዴ አታውቁኝ አላውቃችሁ ምን ዓይነት ጥያቄ ነው የምትጠይቁኝ? ደግሞስ ለማላውቀው ሰው ጥያቄ ለመመለስ እንዲህ ዓይነት ነገር ተገቢ ነው? ምናልባት ከእኔ ጋር የተመሳሰለ ሰው ፈልጋችሁ እንዳይሆን በቅድሚያ ማንነቴን አውቃችኋል ስል ደገምኩላቸው፡፡
እነሱም የምንፈልገው አንተን ነው፣አሁን ጊዜያችንን አትግደል፣ ከዚህ በኋላ የተባልከውን ብቻ ማድረግ ነው አለበለዚያ ላንተ ጥሩ አይሂንም አለኝ ሴንጢውን የደገነው፡፡ ግብር አበሩ ባለኬፕ ደግሞ ወገቡ ላይ የታጠቀውን ሽጉጥ እንዳይለት ከፈት አድርጎ በግርምት ይመለከተኝ ጀመር፡፡ እውነት ለመናገር ገንዘብና ስልክ የሚዘርፉ ሌቦች መስለውኝ ደነገጥኩ፤ ያልጠበኩተ ነውና፡፡ ምክንያቱም የሚረባ ስልክም ሆነ ገንዘብ ስለሌለኝ ካላገኙ አይለቁኝም በሚል ዘዴ ወደማሰላሰሉ ገባሁ፤ ግን በ4 ሰው ያውም አንድ ሽጉጥና አንድ ሴንጢ ይዞ በምሽት ባይሞከርም፡፡
ከዛም እንዳሉት ወረድ አልን፤ አካባቢው ላይ ሁለት ኮንቴይነሮች አሉ፡፡ አንዱ ላይ መብራት ይታያል ሰዎችም እንዳሉ በኋላ አረጋግጫለሁ፡፡ ከነበርንበት የእግረኛ መንገድ ከኮንቴይነሩ ጀርባ ከወሰዱኝ በኋላ የመንገድ ላይ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ይመስል በርካታ ጥያቄዎችን ከበርካታ ፀያፍ ስድብና ዘለፋ ጋር ውርጅብኝ አስተናገድኩ፡፡ ያኔ ከነፃነትና ዜግነት ክብር በስተቀር የገንዘብ ዘራፊ ወይም ሌቦች አለመሆናቸውን አረጋገጥኩ፡፡ እዚህ ላይ ዘለፋና ስድቦቻቸውን አልነግራችሁም፣ በጥሩ ማኀበረሰብና ቤተሰብ አድጌያለሁና ይቅርባችሁ፡፡
ካነሷቸው ጥያቄዎች መካከል በቅርቡ ከግንቦት 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በኢቦኒ መፅሔት ላይ ዋና አዘጋጅ ሆኜ መስራት ከጀመርኩበት ጊዜ ጀምሮ ከወጡ ፅሑፎች መካከል የአቶ መለስ ዜናዊ 3 ቢሊዮን ዶላር፣ የልጃቸው ሰመሃል መለስ 5 ቢሊዮን ዶላር ጉዳይ እንዲሁም የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጁ እንዴት ከህገ መንግስቱ ጋር ፍፁም እንደሚጋጩ የተወሰኑ አንቀፆችን ቃል በቃል በማስቀመጥ ስለተፃፈው ጉዳይ በዋናነት ደጋግመው ያነሱ ሲሆን ስለ ስጀኳር ፕሮጀክትና ስለመብራት ጉዳይም ጣል አድርገዋል፡፡ እነሱንም በተመለከተ አንተ ማን ነህ በማያገባህና በማይመለከትህ ነገር ትዘበዝባለህ፣ ደግሞስ የመለስንም ሆነ የሰመሃልን ገንዘብ አንተ ነህ ያስቀመጥከው? በሚል ተናደው ሲናገሩ አደመጥኳቸው፡፡
ከዛም የተፃፉ ነገሮች በሙሉ መረጃና ምንጭ ተጠቅሶባቸው እንጂ በስማ በለው የተፃፈ አንዳች ነገር የለም፤ ቢኖር እንኳ መብቴ ተነካ የሚል አካል በህግ ሊጠይቀኝ ይችላል ስል፤ ሴንጢ የደገነው በግራ ጉንጬ አንድ ጥፊ አላሰኝ፡፡ የበለጠ ተናደድኩና ለምን ትመታኛለህ? ስል ጉረኛው ባለሽጉጥ “ከዚህ በኋላ እናንተን መክሰስና ማሰር አያስፈልግም ከፈለግን እዚሁ እንጨርስሃለን፤ እኛ ግን እስከዛሬ ዝም እያስጠነቀቅንህ ዝም ያልንህ ትመለሳለህ ብለን ነው እንጂ” አለኝ፡፡
እኔም ወስጤ በጣም እየበገነ እኔ ጋዜጠኝነትን ወድጄና ፈልጌ የተማርኩበት፣ አሁንም ሆነ በህይወት እስካለሁ ወደፊትም የምሰራበት ሙያ እንጂ ተገድጄና ተመድቤ የማከናውነው አይደለም፣ በስራዬም ሙያው ከሚጠይቀው ውጭ አልሰራሁም አልሰራምም፣ በስራዬም ሀገራችንና እኔን ጨምሮ ህዝባችንን የሚጎዳ ተግባር ካገኘው እንደማኝኛውም ጋዜጠኛ እና ሀገር ወዳድ ዜጋ ከመዘገብ ወደ ኋላ አልልም፡፡ ስለዚህ ምን አድርግ ነው ምትሉኝ? አልኳቸው:: በዚህ ንግግሬ የተናደደው ባለሽጉጥ ጉረኛ በካልቾ ሊመታኝ እግሩን ሲሰነዝር መጀመሪያ አንድ ጥፊ ያቀመሰኝ ባለሴንጢው ከለከለው፤ ገረመኝም፡፡
ማንነቱንና በስም የማላውቀው ግን ልደታ ፍርድ ቤት በተደጋጋሚ የማየው ሹራብ ለባሹ ንግግሩን ቀጠለ ከዚህ በኋላ በየትኛውም ጋዜጣ፣ መፅሔትም ሆነ ብሎግ ላይ ብትሰራ በህይወትህ ፍረድ፣ ከእንግዲህ እናንተን(ኢህአዴግን የሚያበሳጩ ጋዜጠኞችን ማለቱ መሰለኝ) ማሰር አያስፈልግም፡፡ በህይወት መኖር ከፈለክ በቅርቡ መልዕክት ይመጣልሃል፤ ከዛም ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ድርጅት ጉዳይ ሲል ከባስ አብሮኝ የወረደው የህዝብ አደረጃጀት ሲል አረመውና ትሄድና የመጨረሻ ውሳኔህንና ምርጫህን ታሳውቀናለህ፤ ከዛ እንተያያለን አለ፡፡
የአማርኛ አነጋገር ዘይቤው ወደ ትግርኛ የሚመራው ጉረኛው ባለ ሽጉጥ ቀጠል አደረገና ከዚህ በኋላ ድጋሚ ላንተ የሚነገርህ የለም፤ እንደውም አላርፍም ብለህ ብትሰራ(ብትፅፍ ለማለት ነው) ባንተ ብቻ ሳይሆን በቤተሰቦችህ በተለይም በምስኪን አባትህ እንጀራና ህይወት ላይ ነው የምትፈርደው ሲል(ውስጤን ሳቅ አፈነው) አስጠነቀቀኝ፡፡ ባለሴንጢው አጋች ደግሞ ይሄንን ነገር ለማንም እንዳትናገር፣ ብትናገር በራስህ ላይ ነው የምትፈርደው፤ ደግሞም አራዳ አይደለሽ ይገባሻል ብለን እናስባለን ሲል ዛቻን በቂልነት አወረደው፡፡ ወይ ማባበል፡፡ ለካ እንዲህ ተራ መሐይሞች ኖረዋል ጎበዝ፡፡ የእኔ አባት ከዚህ ዓለም በሞት የተለየው ገና ተማሪ ሳለሁ ገና የ7ኛ ክፍል ተማሪ ሳለሁ ነሐሴ 13 ቀን 1989 ዓ.ም. ሲሆን አሁን 16 ዓመታት አልፎታል፡፡ ይሄ አነጋገሩ ሀገራችንን ምን ዓይነት ደህንነት እየጠበቃት እንዳለ የበለጠ ስጋጥ ውስጥ ከተተኝ፤ ምክንያቱም ስለ ደህንነት ስራ ካነበብኳቸው የስለላ መፅሐፎች በጥቂቱም ቢሆን አውቃለሁና፡፡ የማያውቁትን መረጃ መዘላበድስ ምን አመጣው? እንዲህም ማስፈራራት የለ፡፡
በመጨረሻም ከ50 ደቂቃ በላይ ከወሰደው እገታ፣ጥያቄ፣ ማስፈራሪያና ዛቻ በኋላ ሳልፈ፤ጋቸውና ሳልከፍላቸው ጊዜያዊ አጃቢዎቼ(አጋቼ) ጋር ወደ ሼል ማደያው በእነሱ ፊትና ኋላ መሪነት አብረን ሄድን፡፡ ከዛም የታክሲ መያዣው ጋር ስንደርስ አራቱም መንገዱን አቋርጠው ጎተራ ተዋበች(አቦኝ) ህንፃ ጋር ባለችው መንገድ ሲገቡ ተመለከትኩ፡፡ በርግጥ ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ ከተመሰረተ ጀምሮ አዘጋጅ ሆኜ በሰራሁበት ወቅት በርካታ ማስፈራሪያዎችና ዛቻዎች ከመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣን እስከ ተራው የኢህአዴግ ካድሬ ደርሶኛል፡፡ እንደውም ነሐሴ 24 ቀን 2004 ዓ.ም. የችሎት መረጃ ይዤ ወደቢሮ ስሄድ ልደታና ባምቢስ አካባቢ በጠራራ ፀሐይ በማላውቃቸው ተመሳሳይ ሰዎች ሁለቴ መታገቴን አልረሳሁትም፡፡ ይሁን እንጂ እኔ ህዝብና ሀገርን የሚጎዳ አንዳች ነገር እስካልፈፀምኩና ህግ እስካልተላለፉ በስተቀር እውነት ያልኩትንና ያመንኩበትን ከመስራት ወደ ኋላ እንደማልል ያኔም በተደጋጋሚ ተናግሬያለሁ፤ ባይሰሙኝም፡፡
እኔም ታክሲ አግኝቼ ቀጥታ ወደ ሳሪስ በመሄድ ሳሪስ ፖሊስ ጣቢያ ገባሁ፡፡ በወቅቱ የሚተባበረኝ ፖሊስ ቢኖር ኖሮ(ለወጉም ቢሆን) የገቡበትን ስለማውቅ በራሴ የኮንትራት ታክሲ ይዤም ቢሆን ብንሄድ አጋቾቹን እናገኛቸው ነበር፤ ግን አልሆነም፡፡ በዕለቱ በፖሊስ ጣቢያው የነበረው ቃል ተቀባይና ወንጀል ምርመራ ክፍል የነበረው ኮንስታብል ጥላሁን ታዴ ሁኔታውን በደንብ ከጠየቀኝ በኋላ አንድም ቃል ሳይፅፍና መፍትሄ ያለውን ሳይጠቁመኝ ያንተን ጉዳይ ነገ ጠዋት(ነሐሴ 21 ቀን 2005 ዓ.ም.) የጣቢያው ዋና ኢንስፔክተር አበበ ሲመጡ ትነግራቸውና እሳቸው ያዩልሃል አለኝና አሰናበተኝ፡፡ ያኔ ይበልጥ ተናደድኩ፡፡ ከዛም በተነገረኝ ሰዓት ጠዋት ወደ ጣቢያው ስሄድ ዋና ኢንስፔክተሩ ለስብሰባ ስለሄዱ ከሰዓት እንድመለስ በሌላ ፖሊስ ተነገረኝ፡፡ የሚገርመው የእኔን ጉዳዩ ቀድሞንም እንደ ሰማ የማክሰኞ ተረኛው ፖሊስ ሲነግረኝ የምርመራ ቢሮ የነበረው ሌላው ተረኛ ፖሊስ ደግሞ የአንተ ጉዳይ ተራ ስለሆን ምን እንዲደረግለህ ትፈልጋለህ፣ ስለማይሆን ነውና ቤትህ ብትሄድ ይሻላል፤ጨረስን ሲል አመናጨቀኝ ፤ ይሄ ደግሞ እኔ ያልነገርኩት ጉዳዩን የሰማ ፖሊስ መሆኑ ነው፡፡
ቀናው ፖሊስ በነገረኝ መሰረት ዋና ኢንስፔክተሩ ከሰዓት ስሄድ አሁንም ከስብሰባ እንዳልመጡና ነገ ረቡዕ ነሐሴ 22 ቀን 2005ዓ.ም. ጠዋት እንድመለስ ነገረኝ፡፡ በድጋሚ በተነገረኝ መሰረት ነሐሴ 22 ቀን 2005 ዓ.ም. ጠዋት ወደፖሊስ ጣቢያው ስሄድ ዋና ኢንስፔክተሩ አሉ፤ ግን ከቢሮ ውጭ ግቢ ውስጥ ናቸው፡፡ በአካል ስለማላውቃቸው ያኔ ሰኞ ሁኔታውን የነገርኩት ፖሊስ በርቀት አይቶኝ ወደ እኔ በመምጣት “ዋና ኢንስፔክተር አበበ አያሌው እሳቸው ናቸው፣ አናግራቸው” አለኝ፡፡ እኔም ቀርቤ ስለ ሁኔታው በሙሉ ነገርኳቸው፡፡
እሳቸውም “ይህ ጉዳይ ከባድ ስለሆነ ኢንስፔክተር አበበ ነው የላከኝ በልና ጉዳዩን ቀድመህ እዚህ ማሳወቅህን ንገራቸውና ወደ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መመሪያ ዋና የወንጀል ምርመራ ክፍል ኃላፊ ወደ ሆኑት ምክትል ኮማንደር ስዩም አስፍሃ ጋር ሂድና ንገራቸው አሉኝ፡፡” ከዛም ጥንቃቄ እንዳደርግና “በየትኛውም ቦታ ሆነህ የምትጠራጠረው ተመሳሳይ ድርጊትም ሆነ ሰዎቹን ካገኘሃቸውና ካስታወስካቸው ወዲያውኑ ደውልልኝ፣አይዞህ ብለው ተንቀሳቃሽ ስልካቸውን ሰጡኝ፣ በሳቸው ሁኔታም ከምር ፖሊስ ናቸው ስል ተደሰትኩ፡፡
ረቡዕ ዕለት ወዲያው ኢንስፔክተሩ እንዳዘዙኝ ወደ ክፍለከተማው ፖሊስ መመሪያ ዋና የወንጀል ክፍል ኃላፊ ምክትል ኮማንደር ስዩም ጋር ሄድኩና ሁኔታውን በሙሉ ነገርኳቸው፡፡ እሳቸውም “ድርጊቱ ሲፈፀም ምስክር የሚሆንህ ሰው ካለ አሁኑኑ ክስ መስርተህ ልንከታተላቸው እንችላለን፤ ምስክር ከሌለ ግን አስቸጋሪ ነው፡፡ በእርግጥ በአካል አውቀዋለሁ የምትለውን ሰው በደንብ ተከታተለው፤ ሲከታተልህም ሆነ አንድ ነገር ለማድረግ በምትጠራጠርበት ጊዜ ወዲያው በጣቢያው ስልክ ደውልልንና ፖሊስ እናዛለን፤ እስከዚያ ግን ድርጊቱን በዕለት ሁኔታ በዝርዝር አስመዝግብና ይቀመጥ፣ ነገ ሰዎቹንም ሆነ ከጉዳዩ ጋር የተያያዘ ድርጊት ለመፈፀም የሚሞክሩ ካሉ አንዱ እንኳ ቢያዝ ሊሎችን መያዝና አስፈላጊውን ማድረግ ይቻላል፤ አንተም ለእራስህ ጥንቃቄ አድርግ አሉኝ፡፡” እኔ በኮማንደሩ በተባልኩት መሰረት ረቡዕ ነሐሴ 22 ቀን 2005ዓ.ም. በፖሊስ መመሪያው የእለት ሁኔታ ቁጥር 3 ላይ አስመዝግቤ አጋቾቹ በቅርቡ መልዕክት ይመጣልሃል ያሉትን እየጠበቅሁ ነው፡፡
ትሄዳለህ የተባልኩበት ቦታ ኃላፊ ስምም ተጠቅሶልኛል(ጅሎች አይደሉ)፣ መልዕክት ሲመጣልህ ትሄዳለህ የተባልኩበት ሰው በተጠቀሰው ኃላፊነት ደረጃ ሳይሆን ከዛ አነስ ባለ የኢህአዴግ ማዕረግ እየሰራ መሆኑን አጣርቼ ደርሼበታለሁ፤መልዕክቱ ሲመጣም ቀድሜ ለፖሊስ ስላስመዘገብኩ ያኔ ፖሊስም ይፈተንበታል ብዬ ተዘጋጅቻለሁ፡፡ ግን እስካሁን የተባለው መልዕክት ሳይመጣ ሳምንት ቢያልፈውም ትናንት ደግሞ በሌላ ሁለት የወጣት ሸበቶዎች ነገር ፍለጋ ሲሞከር መልስም ሳልሰጣቸው ጥያቸው ሄድኩ፡፡ ምክንያቱም አጠገቤ በርካታ ሰዎች ስለነበሩ ምንም ደፍረው እንደማያደርጉ በመገመትና ሆን ብለው ጥል በመፍጠር ለሌላ ዘዴ መዘጋጀታቸው ሌላኛው ስልት መሆኑን ከሌላ የሙያ ባልደረባዬ የተማርኩ ስለሆነ ነቄ ብዬ ሸወድኳቸው፤ ነገር እንዳላበዛ እንጂ እሱም ቀላል አልነበረም፡፡ ከዛም አንዱ ትንሽ እራቅ ካሉ በኋላ ወደ ኋላ በመዞር የማትገኝ መስሎህ ነው አይደል? እናገኝሃለን ብሎ የሚመጥናቸውን የለመዱትን ተራ ስድብ ጣል አድርጎ ያሰቡት እንዳልተሳካ ገብቷቸው ነኩት፡፡
በጡንቻ ለሚያስቡ ፤ እውነት ነው፣ ለሀገራችንና ለወገናችን ይጠቅማል ያልኩትንና ሙያዊ ስነምግባርና ህግን ሳልጥስ መቼም ቢሆን ከመፃፍና በምችለው ሁሉ ከመስራት ወደ ኋላ እንደማልል አረጋግጥላችኋለሁ፡፡ ያውም በሀገሬ! በቻልኩት መጠን ሁሉ መብቴን አሳልፌ እንደማልሰጥና ሁሌም ቢሆን ህገወጥ ድርጊትን አጥብቄ እንደምቃወም መግለፅ እወዳለሁ፡፡ ምንም እንኳ http://www.addismedia.wordpress.com ድህረ-ገፄ (ብሎጌ) ከሰኔ 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በሀገር ውስጥ እንዳይነበብ ቢደረግም እድሜ ለቴክኖሎጂ መፃፌንና ፖስት ማድረጌን አላቆምም፡፡ በምችለው መጠንና ባለኝ ጊዜ ሁሉ ባገኘሁት ጋዜጣና መፅሔትም ቢሆን ከመስራት ወደ ኋላ አልልም፤ መኖርን ብፈልግም የእናንተን የሞት ማስፈራሪያና ዛቻ ፈርቼ የፈፀማችሁትን እንዳልናገር ብታስጠነቅቁኝም፤ድርጊታችሁንም ቢሆን ከቅደም ተከተሉ ያስቀመጥቁት ፍርሃት ስለሌለብኝ እንደሆነ የሚገባችሁ ይመስለኛል፡፡
እስካሁን ግን የሚጠበቅብኝን ያህል እስካሁን እንዳልሰራሁ እንጂ እንዲህ በትንሹ መደናበራችሁን ከወቅሁማ ኸረ ገና ብዙ ይሰራል፡፡ ስለዚህ መሰማትና ማስተዋል ከቻላችሁ(ማኀበራዊ ሚዲያዎች ላይ በብዛት እንዳሉ ስለማውቅ ነው) ከምር ነው የምላችሁ ህሊናዬን በሆዴ ስለማልሸጥና ስለማልፈራ ብዙ ባትለፉ ይሻላል ስል ወንድማዊ ምክሬን ጀባ ብያለሁ፡፡ ባይሆን እናንተም ቢያንስ ሰው ሁኑ እና እንደ ሰው በማሰብ እራሳችሁን ነፃ ብታደርጉ እንዲሁም ክፉ ሲያዟችሁ መልካሙን በማድረግ መልካም እንዲሰሩ ብታደርጉ የሚሻል ይመስለኛል፡፡ በተረፈ ወደ ዓይነ ህሊናችሁ እንድትመለሱና መልካም እንድትሆኑ እና መልካሙ እንዲገጥማችሁ መልካሙን ሁሉ እመኝላኋለሁ፤ችርስ፡፡
የመከነው የአፍሪካ ራዕይ
ልክ የዛሬ 5ዐ ዓመት እ.አ.አ. በ1963 ዓ.ም የአፍሪካ ጥቁሮች ከባርነት ቅኝ ግዛት ለመውጣት የተወሰኑ መሪዎቿ ሽር ጉድ እያሉ ነበር፡፡ ሽርጉዱም የአፍሪካ ምድር በአውሮፓውያን ጨካኝ አገዛዝ መዳፍ ውስጥ የወደቁትን ሀገሮች ነፃ ለማውጣት በጥቂት ጥቁር መሪዎች ምክክር ሊካሄድ ነው፡፡
ይሄን የሰሙት ገዥዎች በተለይም እንግሊዝ፣ ፈረንሳይ፣ ፖርቹጋልና፣ ጣሊያን ይበልጥ በጥቁሮች ላይ በደል መፈፀምን ተያያዙት፡፡ ይህን የተመለከቱት የአፍሪካ የአብራክ ልጆች በቁጭት በመንገብገብ ወገኖቻቸውን ከጭቆና ቀንበር ለማላቀቅ መዘየድ ጀመሩ፡፡ ያኔ ግን የተለያዩ ሀገሮች በተለይም ጋና፣ ናይጄሪያና ደቡብ አፍሪካውያነ በየሀገሮቻቸው የተናጥል ትግል ያደርጉ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ትግሉ ፈቀቅ አላለም፡፡ ምክንያቱም ብቻቸውን ነበሩና፡፡
በወቅቱ ፈረንሳይ የሰሜን አፍሪካ ሀገሮችን በተለይም ግብፅ፣ ቱኒዚያ፣ አልጄሪያ፣ ሞሮኮን እንዲሁም በምዕራብ እንደ ማሊና ኮትዲቫርን በምስራቅ ጅቡቲን ይዛ ነበር፡፡ እንግሊዝ በበኩሏ በምስራቅ አፍሪካ ሱዳን፣ ኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ሯንዳ፣ ክፊል ሱማሊያ በምዕራብ ናይጄሪያ፣ ጋና በደቡብ የቀድሞ ሮዴዥያ (ዙምባቤና ዛምቢያ)፣ደቡብ አፍሪካ የመሳሰሉ ሀገሮችን በቅኝ ግዛት ይዛ ነበር፡፡ ፖርቹጋል ደግሞ በደቡብ ምዕራብ አንጐላን ስትቆጣጠር ጣሊያንም እንዳቅሟ ሊቢያንና ምስራቅ ሶማሊያን ተቆጣጥራ ነበር፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ለናሙና እንጂ በአውሮፓውያን ቅኝ ግዛት የወደቁ ሌሎችም በርካታ የአፍሪካ ሀገሮች ነበሩ፡፡
ነፃ ሀገር
በተፈጥሮ የበለፀገችዋ እማማ አፍሪካ ምንም እንኳ በልጆቿ ስቃይ ማቅ ብትለብስም በወቅቱ እንደሀገር ሉዓላዊነት ያላቸው ሁለት ሀገሮች ነበሯት፡፡ እነኚህም በስተምስራቅ ታሪካዊቷ ኢትዮጵያ እና በምዕራብ የአልማዝ ምድር የሆነችው ላይቤሪያ ናቸው፡፡ በርግጥ ላይቤሪያ እንደሀገር ብትታይም ከነ ሰንደቅዓላማዋ ከአሜሪካ ቁጥጥር ስር ውጭ ነበረች ማለት አልነበረም፡፡ ምክንያቱም እንደ ሀገር ከመመስረቷ በፊት የማንም ያልነበረች በኋላ ግን አሜሪካ በባርነት ከአፍሪካ ተወስደው በሀገሯ እየተባዙ የመጡትን የጥቁሮች ቁጥር ስጋት ላይ እንዳይጥላት በማሰብ ወደዛሬዋ ላይቤሪያ አብዛኞቹን ጭና በማራገፍ የዛሬዎቹ ላይበሪያውያን መኖሪያ አድርጋለች፡፡
በአንፃሩ ደግሞ ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1888 እና በ1928 ዓ.ም በጣሊያን የቅኝ ግዛት ሙከራ ቢደረግም በጥቁር አናብስት ትግል ሳይሳካ በመቅረቱ ከአፍሪካ ብቸኛዋ ነፃ ሀገር ሆና ቆይታለች፡፡ በዚህም ምክንያት በተለይ በዳግማዊ አጼ ምኒሊክ መሪነት የጥቁር አናብስት በጣሊያን ላይ በተቀዳጁት ድል ለሌሎችም ፋና ወጊ በመሆን የነፃነት ትግል እንዲቀጣጠል ፈር ቀዷል፡፡
የነፃነት ናፍቆት ህብር
አፍሪካውያን የነፃነት ናፍቆት ቢያንገበግባቸውም ትግሉ በተናጥል ስለሆነ በተፈለገው ፍጥነት ውጤታማ ሊሆን አልቻለም፡፡ ለዚህም የናይጄሪያውን ኢቦ ኢቢቦ፣ የጋናው አሻንቲ እና የደቡብ አፍሪካውን የነ ባሱቶ ዙሉ ትግልን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ስለሆነም ትግሉ እንዲሰምር በገዥዎች ሀገር ይኖሩ የነበሩ የጥቁሮች የአብራክ ክፋይ እነ ኩዋሜ ኑኩሩማ፣ ጆሞ ኬንያታ የመሳሰሉት በጋራ መታገሉ የተሻለ እንደሆነ በማሰብ በነፃይቱ የጥቁር አናብስት ምድር ንጉስ ከሆኑት ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃ/ስላሴ ጋር መከሩ፡፡
ምክክራቸውንም በማጧጧፍ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የአፍሪካ ሀገሮች ገፉበት፡፡ በዚህም ጥቁሮች ሲነቃቁ ቅኝ ገዥ አውሮፓውያን ግን ድንጋጤ ወሯቸው ነበር፡፡ በተቃራኒው ጥቁሮች ደግሞ ከፍተኛ የአሸናፊነት ወኔን ተላብሰው ለልጆቻቸው ከጭቆና ነፃ የሆነ ምድር ለማውረሰና ለራሳቸውም ነፃነት ተግተው ተፋለሙ፡፡
ይሄን የተረዱት የትግሉ ውጤት ናፋቂዎች እነ አፄ ኃ/ስላሴና ኩዋሜ ኑኩርማን ጨምሮ ሌሎች የወቅቱ የአፍሪካ የቁርጥ ቀን ልጆች አፍሪካውያን ከቅኝ ግዛት ይላቀቁ ዘንድ አፍሪካውያን በአንድ ስም ተጠርተው የሚጠለሉበትን ተቋም መመስረት እንዳለባቸው ወሰኑ፡፡ የዚህም ተቋም ዋነኛ ዓላማ አፍሪካውያንን ከቅኝ ግዛት ነፃ ማውጣት ነበር፡፡
የአፍሪካ አንድነት ድርጅት
አፍሪካውያንን የነፃነት ድል ለማቀዳጀት ሲባል የዛሬ 5ዐ ዓመት እ.አ.አ ግንቦት 1963 ዓ.ም በነፃይቱ ታሪካዊት ሀገር አዲስ አበባ ኢትዮጵያ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ተመሰረተ፡፡ ድርጅቱ ሲመሰረትም ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡት ኢትዮጵያው ንጉስ አጼ ኃ/ስላሴ ነበሩ፡፡
በወቅቱ ተቋሙ ምንም እንኳ ቢመሰረትም ወዲያው የራሱን ቢሮና ለምክክር የሚሆን አዳራሽ መገንባት የማይቻል ቢሆንም ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃ/ስላሴ መንግስታቸውና መላው የሀገራቸው ህዝብ አፍሪካውያን ወገኖቹ ነፃ እንዲወጡ እንደሚሻ ተናገሩ፡፡ በዚህም ሳያበቁ በመንግስታቸውና በህዝባቸው ስም ዛሬ የህብረቱ አሮጌው ህንፃ ለፖሊስ ጽህፈት ቤት ተብሎ የተሰራውን ከነሙሉ ግቢው በነፃ ለድርጅቱ አስረከቡ፡፡ ድርጅቱም በነፃይቱ ምድር ያለማንም ከልካይ በነፃነት በመምከር የአፍሪካውያንን መፃኢ ተስፋ ብሩህ ለማድረግ ተግቶ ይሰራ ጀመር፡፡
በድርጅቱ ያላሰለሰ ጥረትም ጋና ቀድማ ከእንግሊዞች ቅኝ ግዛት ነፃ ስትወጣ ሌሎችም ተከታትለው ነፃ ወጥተዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ግን ከአሰቃቂው የአፓርታይድ ዘረኝነት አገዛዝ ነፃ የወጣችው ዘግይታ ነበር፡፡
ያኔ በአዲስ አበባ የተመሰረተው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዋነኛ ዓላማ አፍሪካውያንን ከባርነት ቅኝ አገዛዝ ነፃ ማውጣት በተጨማሪ የአህጉሪቱ ሃብት በአውሮፓውያን ተወስደው ዜጐቿ እንዳይራቆቱ ነበር፡፡ የአፍሪካ አንጡራ ሃብት በቅኝ ገዥዎች ከልጆቿ ጉሮሮ ተነጥቆ እንዳይወሰድና ልጆቿ በእናት ምድራቸው በነፃነት እንዲቦርቁ ታስቦ በቀድሞው አባቶች መልካም ፈቃድ የተቋቋመው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት /አ.አ.ድ/ ዛሬ ስሙ ተቀይሯል፡፡ ይህም የሆነበት ምከንያት ድርጅቱ የተቋቋመለትን አፍሪካውያንን ከባርነትና ጭቆና ነፃ ማውጣት የሚለውን አሳክቶ ጨርሷል በሚል ነው፡፡
የጨነገፈው ፅንስ
የቀድሞ የአፍሪካ መሪዎች ያነገቡት ወገኖቻቸውን ነፃ የማውጣት መልካም ራዕይ በአሁኖቹ የአስተሳሰብ አድማስ እሳቤ ተሳክቷል በሚል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የዛሬ 12 ዓመት ግንቦት 2ዐዐ1 (እ.አ.አ) ደቡብ አፍሪካ በተወሰነው ውሳኔ መሰረት ወደ አፍሪካ ህብረት ተቀይሯል፡፡ እውነት ለመናገር ዛሬም ድረስ አፍሪካውያን ነፃ ወጥተዋል ማለት አይቻልም፤ ነፃ የነበሩትም በአብራኮቻቸው ክፋይ ቅኝ ግዛት ውስጥ ገብተዋልና፡፡
በተለይ በዛሬዎቹ መሪዎች ድርጅቱ ዓላማውን አሳክቷል፤ ግቡን መቷል በሚል የአህጉሪቱን ልማት መሰረት በማድረግ የአፍሪካ ህብረት ተቋቁሞ መቀመጫውንም እዚሁ አዲስ አበባ አድርጓል፡፡
ያኔ ቅኝ ገዥዎች ባላገሮቹን በግፍ ይጨቁኑ ነበር፣ ህዝቡ በስርዓቱ ላይ ያለውን ተቃውሞ ሲያቀርብ በጥይት እሩምታ በመረሸን የቀሩትን ወደ አሰቃቂ እስር ቤት ይከቱ ነበር፡፡ ይህ ግን ነፃዋን ኢትዮጵያን አይመለከትም ነበር፡፡ ምክንያቱም ንጉሷም መሪዋም ባዕድ ሳይሆኑ ያው ያብራኳ ክፋይ አፄ ኃ/ስላሴና ኢትዮጵያውያን ናቸውና በመካከል የቅኝ ገዥነት እሳቤ የለም፡፡
በወቅቱ ኢትዮጵያውያን በንጉሱ ስርዓት ቅሬታ ሲሰማቸው በነፃነት ሰላማዊ ሰልፍ በመውጣት ተቃውሟቸውን ያሰሙ ነበር፡፡ ለዚህም እ.አ.አ በ197ዐ ዎቹ መጀመሪያ ላይ የነበረውን የነዳጅ ጭማሪ ዋጋ በመቃወም የነበረውን ማስታወሱ በቂ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የነዳጅ ዋጋ ቀንሷል፡፡ ከዛም በፊት ወጣቶች መሬት ላራሹ ተቃውሞን በነፃነት አሰምተዋል፡፡ በሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች ግን የማይቻል ነው፤ ቅኝ ገዥዎች ናቸውና፡፡
ዛሬ ግን ምናልባት አንፃራዊ ዴሞክራሲያዊ የመንግስት አስተዳደር ያላቸው ጋና እና ደቡብ አፍሪካ ካልሆነ በስተቀር አፍሪካውያን በራሳቸው ጥቁር ገዥዎች የጭቆና ቀንበር ስር ወድቀዋል፡፡ ለዚህም በግብፅ፣ በሊቢያ፣ በኮትዲቫር፣ በቱኒዚያ፣ በሞሮኮና በአልጄሪያ ያሉትን ጨቋኝ አስተዳደሮች በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ የወጡት ከቅኝ ገዥዎች በባሰ በአሽከሮቻቸው ታጣቂዎች በአደባባይ የጥይት እራት ሆነዋል፡፡
በምስራቅ አፍሪካ ኢትዮጵያም የተመለከትን እንደሆነ አፍሪካውያን ነፃ ወጥተዋል በሚል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ወደ ህብረት ከተቀየረ በኋላ በቅኝ ያልተገዙት ኢትዮጵያውያን የመንግስት ገዥዎች በርካታ እኩይ ተግባራትን ለመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ቢፈልጉም ለመጨረሻ ጊዜ በሚል ይመስላል እ.አ.አ በ2ዐዐ5 (በ1997 ዓ.ም) በምርጫ ወቅት ነበር የተደረገው፡፡ ከዚያም የምርጨውን ውጤት ተከትሎ በተፈጠረ ተቃውሞ አሁን በስልጣን ላይ ባለው ገዥው ቡድን መሪ በነበሩት በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ትዕዛዝ ጨቅላ ህፃናትን ጨምሮ ከ86ዐ በላይ ዜጐች የጥይት ናዳ አርፎባቸው እስከወዲያኛው አሸልበዋል፡፡
በኬንያና በሱዳንም ሆነ በአብዛኛው የአፍሪካ ሀገሮች በተመሳሳይ መልኩ ገዥዎችን ለመደገፍ ካልሆነ ለተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ለሞት ይዳርጋል፡፡ ይህንን ደግሞ ቅኝ ገዥዎች ያደርጉት የነበረው አስከፊ ድርጊት በጥቁር ቆዳ ካባ በለበሱ አምባገነን መሪዎች መደገፍ አፍሪካውያንም ሆኑ አፍሪካ ነፃ ወጥተዋል ማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም የድጋፍ የድጋፍማ ቅኝ ገዥዎችም አሳምረው በመፍቀድ መፈክር እና ሌላ ወጭ በመሸፈን ይከናወን ነበር፤ ተቃውሞ ባይቻለም፡፡
ሌላው ያኔ በቅኝ ገዥዎች ወቅት የአፍሪካ አንጡራ ሃብት ተዝቆና ተሸጦ ወደ አውሮፓ ካዝና ይገባ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ በእራሳቸው በአፍሪካውያን መሪዎች ከአህጉሪቱ ህዝብ ጉሮሮ ተነጥቀው አንጡራ ሃብቷን ዝቀውና ሸጠው ወደ አውሮፓና እስያ ሀገሮች ካዝና ያስገባሉ፤ አፍሪካውያን ግን ዛሬም ይራባሉ፣ይታሰራሉ፣ ይገረፋሉ፣ ይጨቆናሉ፣ይሰደዳሉ፣ይገደላሉ፣ይዘረፋሉ፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የተቋቋመለትን ዜጐቿን ነፃ የማውጣት ራዕይ ግቡን ሳይመታና ሳያሳካ የነፃነት ፅንሱ በዚህ መልክ ጨንግፏል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የእስያዎቹ ቻይና፣ ህንድና የአረብ ሀገራትን ጨምሮ አሜሪካና አውሮፓ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ እጃቸውን አላወጡም፣ ዛሬም በዘመናዊው እጅ አዙር ቅኝ ጋዛት ቀፍድደው ይዘዋልና፡፡ ስለዚህ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዓላማ ተጨናግፋል እንጂ ተሳክቷል ማለት አይቻልም፡፡
በትረ ከረባት ነዳያን
የቀድሞ ለነፃነት ቀናዒ የሆኑ የአባቶቻችንን ዓላማ ተሳክቷል በሚል ክህደት የዛሬዎቹ በትረ ከረባት ነዳያን የአፍሪካ ህብረትን አቋቁመዋል፡፡ የህብረቱም ዓላማ በአፍሪካ ልማትን ማምጣትና ማፋጠን እንዲሁም ማስተሳሰር የሚል ነው፡፡ በዚህም ስም በስልጣን ላይ ያሉት የአህጉሪቱ መሪዎች የራሳቸውን ሆድና ስልጣን ታሳቢ በማድረግ በአህጉሪቱ ህዝብ ስም ከረባት አስረው ለምነው የሚያመጡትን ገንዘብ በሌላ መንገድ በስማቸው ወደ ለጋሽ ሀገሮች ካዝና ይቋጥራሉ፡፡
ለዚህም የሊቢያ፣ የግብፅ፣ የቱኒዚያና የኢትዮጵያ መሪዎችን ጨምሮ አብዛኞቹ የዚህ ባለሟል ናቸው፡፡ አብዛኞቹ መሪዎችም እጃቸው ከዜጐቻቸው የግፍ ደምና የህዝቡ አንጡራ ሃብት ዝርፍያ የፀዳ አይደለም፡፡ በዚህም ምክንያት ዛሬም ድረስ ዜጐቻቸውን እጅግ ከቅኝ ገዥዎች በባሰ መልኩ በመጨቆን አንዳንዶቹ በወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ሌሎቹ ደግሞ በምርጫ ስም ህዝብን በማጭበርበር በትረስልጣናቸውን እያደላደሉ ይገኛሉ፡፡
አሁን በስልጣን ላይ ያሉት የአፍሪካ ማሪዎች የእነሱ የስልጣን ዕድሜ እስከረዘመና ዝርፊያውን እስኳጧጧፉ ድረስ የአህጉሪቱን አንጡራ ሃብት ጥቅም በማዘረፍ ተወዳዳሪ የላቸውም፡፡ በዚህም ለዜጐቻቸው ያላቸው ቀናዒነትና ተቆርቋሪነት ከቀድሞዎቹ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መስራቾች ጋር ሲነፃፀር እጅግ አናሳ ነው፡፡ ምክንያቱም አብዛኞቹ የበትረ ከረባት ነዳይ ሆነው የአህጉሪቱን ሃብት እያዘረፉ የዜጐቻቸውን ነፃ አስተሳሰብና ነፃ ሚዲያን በማፈን ከፍተኛ ጭቆና እያደረጉ ስለመሆኑ የህብረቱ ዋና መቀመጫ የሆነችውን ኢትዮጵያን ጨምሮ አብዛኛው አፍሪካ ሀገሮችን ማየት በቂ ነው፡፡
በአጠቃላይ አሁን እ.አ.አ. በያዝነው ግንቦት 2ዐ13 የአፍሪካ ህብረት ምስረታ 5ዐኛ ዓመት ክብረ በዓል ለመሪዎቹ ብቻ ካልሆነ በቀር ለአህጉሪቱ ህዝብ ይሄ ነው የሚባል የፈየደው ነገር አለ ለማለት አያስደፍርም፡፡ ምክንያቱም እየተሰሩ ያሉት መሰረተ ልማቶችና ሌሎች የህዝብ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት ግንባታ ሰብዓዊ ልማትን ወደጐን በመተው እየተደረገ ያለው ቅኝ ገዥዎች በጊዜያቸው ሲያደርጉት ከነበረው እምብዛም የተለየ አይደለምና፡፡ በዚህም አፍሪካ ቀድሞ የነበራት ራዕይ በአሁኖቹ በትረ ከረባት ነዳይ መክኖ ቀርቷል ማለት ይቻላል፡፡ ያኔ ቅኝ ገዥዎች ሰብዓዊ መብትን በመርገጥ በቁሳዊ ልማት ህዝቡን ለመደለል ይሹ እንደነበረው ዛሬም እንዲሁ ነው፡፡
