Tag Archives: Bekele Gerba

አቶ በቀለ ገርባ በድጋሚ ታሰሩ

የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ/መድረክ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበር እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር አቶ በቀለ ገርባ ዛሬ በድጋሚ መታሰራቸው ተገለፀ፡፡ አቶ በቀለ ዛሬ የታሰሩት አዳማ/ናዝሬት ከሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው በ14 የደህንነት አባላት ለሰባት ሰዓታት ያህል ፍተሻ ከተደረገ በኋላ ተይዘው ወደ አዲስ አበባ መምጣታቸውን የኢሳት ዘገባ አመልክቷል፡፡

Bekele Gerbaባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. ከተቀጣጠለው የኦሮሚያ ክልል ህዝብ ተቃውሞን ተከትሎ የፌደራል ፖሊስ፣ የአጋዚ ልዩ ኃይል እና መከላከያ ሰራዊት በክልል በተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ ከ86 በላይ ሰዎች መገደላችን፣ በርካታ ሰዎች መቁሰላቸውን እና መታሰራቸውን ተከትሎ አቶ በቀለ በፓርቲያቸው ኦፌኮ/መድረክ አማካኝነት ከፍተኛ ተቃውሞ ሲያሰሙ ከነበሩ አመራሮች አንዱ መሆናቸው ይታወቃል፡፡

አቶ በቀለ ከዚህ በፊት በሰኔ 2003 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል በመንግሥት ስለሚፈፀሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በተመለከተ ለአምንስቲ ኢንተርናሽናል ጋር ያደረጉትን አጭር ቆይታ ተከትሎ መንግሥት በሽብር ወንጀል ፈርዶ ለ3 ዓመት ከ7 ወር በኋላ የእስር ፍርድ ጊዜያቸውን ጨርሰው ባለፈው መጋቢት 2007 ዓ.ም. መፈታታቸው አይዘነጋም፡፡ አቶ በቀለ ዛሬ ከመኖሪያ ቤታቸው ተይዘው የታሰሩበት ምክንያት እስካሁን እንዳልተገለፀላቸው ታውቋል፡፡

በተያያዘ ዜና ከአቶ በቀለ ገርባ በተጨማሪ ቀደም ሲል ከኦፌኮ/መድረክ ከፍተኛ አመራሮች አቶ ደጀኔ ጣፋ እና የተለየዩ የፓርቲው አባላትና የዞን አመራሮችም መታሰራቸው ታውቋል፡፡
ለለአንድ ወር የዘለቀው የኦሮሚያ ህዝባዊ ተቃውሞ አዲሱን የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላንን በመቃወም መነሻ ቢሆንም በተጨማሪ የተለያዩ የመብት ጥያቄዎችን ያካተተ እንደነበር አይዘነጋም፡፡

የመድረክ ከፍተኛ አመራርና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህሩ አቶ በቀለ ገርባ ከእስር ተለቀቁ

አቶ በቀለ ገርባ

አቶ በቀለ ገርባ

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርና የቀድሞው የኦሮሞ ፌደራሊስት ንቅናቄ፣ የአሁኑ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ/መድረክ ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት አቶ በቀለ ገርባ ከነሐሴ 2003 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ከቆዩ በኋላ መጋቢት 21 ቀን 2007 ዓ.ም. ተለቀዋል፡፡ አቶ በቀለ ገርባ መንግሥት በዜጎች ላይ በፈፀማቸውና እየፈፀማቸው ባሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ጉዳይ ከአምንስቲ ኢንተርናል ጋር ቃለ መጠይቅ ካደረጉ በኋላ የኦነግ አባል ናቸው በሚል በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ ወንጀል ችሎት 8 ዓመት ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸው ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ተከላካይ ጠበቆቻቸውና አቶ በቀለ የታሰሩት ያለምንም ወንጀል እንደሆነ፣መንግሥት የኦነግ አባል ብሎ የመሰረተባቸው ክስ እንደማይመለከታቸው፣ እሳቸው በወቅቱ በሀገር ውስጥ በሰላማዊ መንገድ እየታገለ ያለው የኦፌዲን/መድረክ አመራር መሆናቸውን በማስረጃ ቢከራከሩም ፍርድ ቤቱ ሳይቀበለው በመቅረቱ ለፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ መጠየቃቸው ይታወሳል፡፡

እነ አቶ በቀለ ገርባ የከፍተኛው ፍርድ ቤት ውሳኔ በመቃወም ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ካሉ በኋላ የ8 ዓመቱ ፅኑ እስራት ወደ 3 ዓመት ከ7 ወር የተቀነሰ ሲሆን፤ ይሄንንም ይግባኝ ብለው ወደ ፌደራሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ቢሄዱም የ3 ዓመት ከ7 ወር ፍርድ በመፅናቱ በእስር ቆይተዋል፡፡ አቶ በቀለ ገርባ በህጉ መሰረት በአመክሮ ከእስር መፈታት የነበረባቸው ከአንድ ዓመት በፊት ጥር 2006 ዓ.ም. ቢሆንም፤ ዝዋይ የሚገኘውም ሆነ አቃቂ ቂሊንጦ የሚገኘው ወህኒ ቤት ፈቃደኛ ባለመሆናቸው 4ኛ ዓመት ድረስ በእስር ሊቆዩ ችለዋል፡፡ መረጃዎች እንደጠቆሙት ከሆነ አቶ በቀለ ገርባ የተለቀቁት ከነበሩበት እስር ቤት ከተለቀቁ በኋላ ከባለቤታቸው ወ/ሮ ሐና ጋር እየተጓዙ ከእስር ቤቱ ብዙም ሳይርቁ፤ በወህኒ ቤቱ ጠባቂዎች ቆይ ሌላ የሚጣራ ጉዳይ አለ በሚል ተመልሰው እስር ቤት ካስገቧቸው በኋላ በጭለማ ሞጆ ከተማ አካባቢ ተወስደው መለቀቃቸው ተጠቁሟል፡፡ አቶ በቀለ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ከማስተማራቸው በተጨማሪ የዶክተሬት ዲግሪ ማጠናቀቂያቸው ላይ መታሰራቸው አይዘነጋም፡፡ በአሁን ወቅት የኦፌኮ/መድረክ አመራር አቶ ኦልባና ሊሊሳን፣ የአድነት ከፍተኛ አመራር አቶ አንዱዓለም አራጌ እና ጋዜጠኛ እስንክንድር ነጋን ጨምሮ በርካታ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮችና አክቲቪስቶች በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡

አመክሮና በቀለ ገርባ

Zelalem Kibret

የኦሮሞ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኦፌዴን) ምክትል ሊቀመንበርና የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ መድረክ ስራ አስፈፃሚ የነበሩት “ህጋዊ የፖለቲካ ፓርቲን ሽፋን በማድረግ  የአሸባሪ ቡድን የሆነው ኦነግ አባል ሆነዋል” በሚል ክስ ተመስርቶባቸው የ8 ዓመት እሥር የተበየነባቸው ሲሆን፤ ይግባኝ ጠይቀው እስሩ ወደ 3 ዓመት ከ7 ወር ዝቅ ተደርጎላቸዋል፡፡

bekele-gerbaከ3 ዓመት ከ7 ወር የእስር ጊዜ ውስጥም 3ቱን ዓመት በመጨረሳቸው በአመክሮ ይፈቱ ዘንድ ለማረሚያ ቤቱ ያመለከቱ ሲሆን ማረሚያ ቤቱም ‹አመክሮ መስጠትም አለመስጠትም መብታችን ነው›  በማለት እስከአሁን ሊፈታቸው አልቻለም፡፡ ይህም ብዙ ጥያቄዎችን አስነስቷል፡፡

አንዳንድ ህጋዊ ሁኔታዎች ስለጉዳዩ፡

አመክሮ ምንደር ነው?
ሌላውን ትርጉም ትተን የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ‹በተወሰነ ጊዜ በአመክሮ መፈታት› በሚለው ክፍል በተለይም በአንቀፅ 202 እንደደነገገው፡
“ተቀጭው ከተወሰነበት የእስራት ጊዜ ከሶስት እጅ ሁለቱን እጅ ወይም ፍርዱ የእድሜ ልክ እስራት ሲሆን ሀያ ዓመት በፈፀመ ጊዜ አግባብ ባለው አካል ወይም በጥፋተኛው አሳሳቢነት ጥፋተኛውን ከቅጣቱ ነፃ ያወጣዋል፡፡” ይህም ማለት አመክሮ 2/3ኛውን የቅጣት ጊዜውን የጨረሰ ታራሚ ከእስር የሚፈታበት አሰራር ነው፡፡

አመክሮ ለማግኝት ምን መስፈርት ማሟላት ያስፈልጋል?

የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ከላይ በጠቀስነው አንቀፅ 202 ላይ አመክሮ ለማግኝት አንድ እስረኛ ማሟላት የሚያስፈልገውን መስፈርቶች ይዘረዝራል፡፡ ይህም፡

– ‹ታራሚው በስራ ጠባዩ የተረጋገጠ መሻሻል አሳይቶ እንደሆነ…›

– ‹ካሳ የመክፈል ግዴታ ተጥሎበት ከነበረና ካሳውን መክፈሉ የተረጋገጠ እንደሆነ…›

– ‹አመሉና ጠባዩ መልካም አኗኗር ለመኖር የሚያስችለውና በአመክሮ መፈታቱ መልካም ውጤት ሊያስገኝ ይችላል ተብሎ የታመነ እንደሆነ..›

ነው ብሎ ይደነግጋል፡፡

ማረሚያ ቤት ወይስ ፍርድ ቤት?

ታራሚን በአመክሮ የመልቀቅ የመጨረሻው ስልጣን የፍርድ ቤት፡፡ ነገር ግን ጉዳዩን ማረሚያ ቤቱ በራሱ ተነሳሽነት ወይም በታራሚው አሳሳቢነት ለፍርድ ቤት ሲያቀርብ ነው ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የሚሰጠው፡፡ እዚህ ላይ ማረሚያ ቤቱ ትልቁን ስልጣን ይዞ እናገኛለን፡፡ ማረሚያ ቤቱ ለፍርድ ቤት ማቅረብ ካልፈለገ ሊተወው የሚችልበት አግባብ አለ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ማረሚያ ቤቱ በሕግ ስር ያለ አካል እንደመሆኑ መጠን በወንጀል ሕጉ አንቀፅ 202 ላይ የተቀመጡ መስፈርቶችን ላሟላ ታራሚ አመክሮ ሊከለክል አይችልም – የታራሚው መብት ነውና!

በቀለ ገርባስ?

አቶ በቀለ ገርባ ከተፈረደባቸው የአምስት ዓመት እስር ውስጥ 2/3ኛውን ወይም 3 ዓመት የሚሆነውን ጨርሰው የአመክሮ ጥያቄያቸው በማረሚያ ቤቱ በኩል ለፍርድ ቤት እንዲቀርብላቸው ቢጠይቁም ማረሚያ ቤቱ  ‹አመክሮ መስጠትም አለመስጠትም መብታችን ነው› የሚል መልስ እንደሰጣቸው ተሰምቷል፡፡
1ኛ. አመክሮ መስጠት የማረሚያ ቤት መብት ሳይሆን ግዴታም ጭምር ነው፡፡ መስፈርቱን ያሟላ ታራሚ አመክሮ የማግኝት መብት ያለው መሆኑ በሌላ በኩል አመክሮ ሰጭውን አካል ላይ ግዴታ ይጥላልና፡፡
2ኛ ሌላው አቶ በቀለ ገርባ መስፈርቱን አሟልተዋል ወይስ አላሟሉም የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ 2/3ኛውን የእስር ጊዜ መጨረስ የሚለውን Objective መስፈርት እንዳሟሉ ግልፅ ሲሆን፡፡ ችግሩ የተፈጠረው Subjective መስፈርቱ ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ይህም ማለት በእስር ወቅት መልካም ፀባይ አሳይተዋል ወይስ አላሳዩም የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ አንድ ታራሚ በእስር ወቅት ለመልካም ፀባይ ተቃራኒ የሆኑ ነገሮችን ካሳየ የቅጣት ማስጠንቀቂያ ከመፃፍ እስከ ብቻውን ማሰር (Solitary Confinement) ድረስ ያሉ እርምጃዎች በማረሚያ ቤቱ ሊወሰዱበት ይችላሉ፡፡

አቶ በቀለ ገርባ ከፀባያቸው ጋር በተያያዘ ምንም አይነት ቅጣት ያልተወሰደባቸው ከመሆኑም ሌላ መልካም ፀባይ እንዳሳዩ ከማረሚያ ቤቱ እንደተነገራቸው ራሳቸው ገልፀዋል፡፡ በቀለ ገርባ ምም መስፈር አሟልተዋል ማለት ነው፡፡ ታዲያ ምን ይሆን አቶ በቀለን በአመክሮ ከመፈታት ያገዳቸው?

አንዳንድ ነገሮች

ባለው አካሄድ አብዛኛው ታራሚዎች በአመክሮ ይፈታል፡፡ ከሌባ እስከ ሙሰኛ፡፡ High Profile በሆኑ ክሶች የተከሰሱ ሰዎች ሳይቀሩ በአመክሮ ሲፈቱ እንደነበር እናስታውሳለን ለምሳሌ ቴዲ አፍሮ 24 ወራት ተፈርዶበት 16 ወራትን ጨርሶ በአመክሮ ተፈቷል፡፡ አቶ አሰፋ አብርሃ 9 ዓመት ተፈርዶባቸው ሰባት ዓመታት ታስረው ከብዙ ውዝግብ በኋላ በአመክሮ ተፈተዋል፡፡ በሌላ በኩል በቅንጅት ክስ ስር ተከሰው የነበሩት አቶ ዳንኤል በቀለና አቶ ነፃነት ደምሴ 30 ወራት የተፈረደባቸው ሲሆን 20 ወራትን በእስር አሳልፈው አመክሮ ቢጠይቁም ማረሚያ ቤቱ ‹ፍርዳችሁን ጨርሳችሁ ውጡ› በሚል ምክንያት አመክሮ ከልክሏቸው ነበር፡፡

እንግዲህ አቶ በቀለ ገርባ በሕጉ የተቀመጠውን መስፈርት አሟልተው እያለ በአመክሮ የመፈታት መብታቸው አልተከበረም ወይም ማረሚያ ቤቱ ግዴታውን ሊወጣ አልፈለገም!

ምክንያት: በጉልበተኞች የምትተዳደር ሀገር ዜጋ ስለሆኑ!

ልዩ ማስታወሻ፡-ይህ ባለፈው ጥር  16 ቀን 2006 ዓ.ም. የዞን 9 ብሎገርና የአምቦ ዩኒቨርስቲ የህግ መምህር ዘለዓለም ክብረት ከመታሰሩ በፊት የፃፈው ቢሆንም፤በአሁን ሰዓት እሱ ራሱ በግፍ እስር አቃቂ ቂሊንጦ ወህኒ ቤት ይገኛል፡፡

#‎FreeBekeleGerba

ማሰርና ማሳደድ መፍትሄ ይሆናል?

ብስራት ወልደሚካኤል
afrosonb@gmail.com

በቀድሞ ታጣቂዎች እንደ ጭራቅና አውሬ ይሳል የነበረው የደርግ ስርዓት ወድቆ ስልጣን በአማፂዓን እጅ ከገባ 23 ዓመታት አልፈዋል፡፡ ነገር ግን የታሰበው ለውጥ ዛሬም ቢሆን መናፈቁን አልተወም፡፡ ምክኔቱም ያኔ ማሰር ነበር፤ ዛሬም ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ያኔም መወንጀልና መፈረጅ ነበር ዛሬ ግን ተባብሷል፡፡ ለእኔ ከድሮ የተለየ ተቀይሮ ያገኘሁት በዋናነት የመሪዎች ስምና ልብሳቸው እንጂ ስራቸው ያው ነው፡፡

በዘመነ ደርግ ጠባብነትና ዘረኝነትን እንዲሁም ኢትዮጵያ ላይ ጥላቻ ያላቸውን በሙሉ ስልጣኑን ሊቀናቀኑ ካሰቡት እኩል በጠላትነት ይፈረጃሉ፡፡ በዘመነ ኢህአዴግ ደግሞ ኢትዮጵያዊነትን ማስቀደምና ለኢትዮጵያውያን በእኩል ዓይን መቆምና መቆርቆር እንደ ወንጀል ይታያል፡፡ሁለቱም ወደ ስልጣን ሲወጡ በጠብመንጃ ሲሆን፤ ስልጣናቸውንም ያስጠበቁትን የሚያስጠብቁት እንዲ በጦር መሳሪያ ነው፡፡ምን አለፋችሁ፤ ልዩነቱን “…ጃሃ ያስተሰርያል” የሚለው የአርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (የቴዲ አፍሮ) ሙዚቃ በደንብ ይገልፀዋል፡፡

sssበሁለቱ መካከል ያለው መሰረታዊ ልዩነት ደርግ የማይፈልገውን ነገር በግልፅ በአዋጅ ይደነግጋል፤ከአዋጅ ወይም ህግ ውጭ ይቀጣል፡፡ ኢህአዴግ ደግሞ የሚፈልገውንም ሆነ የማይፈልገውን በህገ መንግስት እውቅና ሰጥቶ የማይፈልገውን በሌላ አዋጅ ይቀጣል፣ያስራል፡፡ ልዩነታቸው የመሪዎች ስም፣ የለበሱት ልብስና አካሄዳቸው እንጂ መሰረታዊ የልዩነት ባህርይ አይታይባቸውም፡፡ ለዚህም አሁን በስልጣን ላይ ያለው ኢህአዴግ ከደርግ በባሰ ያከናወናቸውን እና እያከናወናቸው ካሉት አሉታዊ ተግባራት መካከል በዋናነት የእስር ዘመቻውን ማንሳቱ በቂ ነው፡፡

በተለይ በምርጫ 1997 ዓ.ም. ኢህአዴግ በአደባባይ መሸነፉን እና የህዝብን ድምፅ መቀማቱን የሚያሳብ በርካታ ተግባራትን ሲያከናውን ዋናው ገመናውን የሚያጋልጡና በአብዛኛው ህዝብ ዘንድ ተቀባይነትና ተወዳጅነት ያላቸውን በሰበብ አስባቡ አስሮ ማሰቃየትን እንደ ትልቅ አማራጭ መጠቀም ጀመረ፡፡ ለዚህ በምርጫው ያሸነፉት የቀድሞ ቅንጅት አመራሮችን ከወነጀለበት በኢትዮጵያ 2000 ዓ.ም. ዋዜማ ከእስር ከፈታ በኋላ አዲሱ ቀዳሚ እስረኛ አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ነበር፤ የእስርዓ ምዕት ኢትዮጵያ ጅማሮ እስረኛ፡፡ ይህም አዲስ አበባና አስመራን ጨምሮበመላው ዓለም ጥያቄና ተቃውሞ ከማስነሳቱ በተጨማሪ ከእስር ሲፈታም የህዝብ ድጋፍ በመላው ዓለም ተጠናክሮ እስከዛሬም ድረስ ዘልቋል፡፡

ከዚህ በኋላ የኢህአዴግ ጥላቻ እየተባባሰ፣ ለስልጣን ያለው ጥማት ሰርክ እንደ አዲስ ወይን እየጣመው ይሄድ ጀመር፡፡ ከስልጣናቸው በዕድሜ ይፍታህ የተሰናበቱት ሟቹ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ በስልጣናቸው እስከ መቃብር አፋፍ ዋስትና ይሆናል ያሏቸውን አፋኝ ህጎች ፀድቀው ተግባር ላይ እንዲውሉ ቀን ከሌት ኳተኑ፡፡ በዚህም የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኀበራት አዋጅ፣ የፕሬስ አዋጅ፣ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ፣…ይገኙበታል፡፡

በተለይ በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች እና የነፃ ጋዜጠኞች ከፍተኛ ተቃውሞ የገጠመው የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ ሰኔ 30 ቀን 2001 ዓ.ም. ፀድቆ ለምርጫ 2002 ዓ.ም. ማፈኛ ተዘጋጀ፡፡ የዚህም ገፈት የዴሞክራሲ እንቅስቃሴዎችን ገድቦ የነበረውን ተስፋ መቀመቅ ውስጥ ከተተው፡፡ ከዚህ በኋላ በየካቲት 2003 ዓ.ም. በቱኒዚያ መሐመድ ቡዓዚዝ የተጀመረው የአረቡ ፀደይ አብዮት በሰሜን አፍሪካን እና መካከለኛ ምስራቅ አረብ ሀገሮች መቀጣጠሉን የተመለከቱት አቶ መለስና ተከታዮቻቸውና አጋሮቻቸው በኢትዮጵያም ይከሰታል በሚል የአስር አደኑንን አጣደፉት፡፡

የአረቡን አብዮት ተከትሎ በኢትዮጵያ የእስር ሰንሰለቱን የጀመሩት እንደ ታሰበው ጋዜጠኞች እና የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ናቸው፡፡ በቀዳሚነትም በወርሃ ሰኔ 12 ቀን 2004 ዓ.ም. ከፖለቲከኛ አቶ ዘሪሁን ገ/እግዚአብሔር፣ ሰኔ 14 ቀን 2003 ዓ.ም. ደግሞ ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ፣ ርዕዮት አለሙ፤ ከዚያም በክረምት 2003 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርና የኦፌኮ/መድረክ አመራር አቶ በቀለ ገርባና አቶ ኦልባና ሌሊሳ የእስር ሰለባ ሆኑ፡፡

andሌላው ከኢትዮጵያውያን በተጨማሪ ሁለት ሲውድናውያን ጋዜጠኞች ማርቲን ሸብይ እና ጆሃን ፐርሰን ሽብርተኝነትን ደግፈዋል በሚል በዚሁ የፀረ-ሽብርተኝነት ሰለባ በመሆን ከ14 ወራት የሰቆቃ እስር በኋላ በዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ጫና መስከረም 1 ቀን 2004 ዓ.ም.ተለቀዋል፡፡ በመቀጠል መስከረም 3 ቀን 2004 ዓ.ም. ደግሞ ታዋቂው የፖለቲካ ተንታኝ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣በብዙ ወጣቶች ዘንድ በቅንነቱና ፍቅርን በመስጠት እንዲሁም ሰላማዊ የፖለቲካ ትግልን አጥብቆ በመደገፍ የሚከራከረው የአንድነት/መድረክ አመራር አቶ አንዱዓለም አራጌ እና ሌሎች የአንድነት ፓርቲ አመራሮች አቶ ናትናኤል መኮንን፣አቶ ዮሐንስ ተረፈና ሻምበል የሺዋስ ይሁንዓለምንና አቶ አንዱዓለም አያሌውን ጨምሮ አቶ ክንፈ ሚካኤል ደበበና ሌሎች ሰዎችም በሽብርተኝነት ስም ወደ ወህኒ ወረዱ፡፡ በዚህም አፍቃሬ መንበር አቶ መለስ የፈሩትን የአረቡን አብዮት በዚህ ያለፉ ይመስል ጀብደኝነት ተሰምቷቸው፤ ተጠርጣሪዎቹ ገና በፍርድ ቤት ብይን ሳይሰጥባቸው አሸባሪዎች ናቸው ሲሉ ለተወካዮቻቸው አረጋገጡ፡፡
ያሰሯቸው ላይ ቀድመው ወንጀለኛ በማለት ፍርድ በመስጠት መከራን የደገሱት አቶ መለስ ባልጠበቁት ሁኔታ በጠና ታመው በአውሮፓ ቤልጄየም ብራሰልስ አንድ የዩኒቨርስቲ ሪፈራል ሆስፒታል ተኙ፡፡ በመጨረሻም እንደ ሆስፒታሉ ምንጮች ከሆነ ሐምሌ 13 ቀን 2004 ዓ.ም. እንደወጡ ላይለመሱ ብዙ ለመኖር ያሰቡበትን በ21 ዓመታት የስልጣን ዘመናቸው እንደ ግል ርስታቸው ያስቡት የነበረውን ቤተመንግስት ጥለው እስከወዲያኛው ተሰናበቱ፡፡

bekይሁን እንጂ አጋሮቻቸውና የቅርብ የኢህአዴግ አመራሮች መታመማቸውን እንኳ ለህዝብ ሳይገልፁ በድንገት የሞቱትን ሰውዬ ከጋዜጠኞች ጥያቄ ቢበረታባቸው በቅርቡ ተመልሰው ስራ ይጀምራሉ የሚል መልስ ሰጡ፡፡ በኋላም የተባለው ሳይሆን ፈጣሪ የወሰነው ሞት እርግጥ መሆኑ እና ነሐሴ 14 ቀን 2004 ዓ.ም. ሌሊት እንዳረፉ ተደርጎ ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም. ማለዳ አንድ ለእናቱ በሆነው ሀገሪቱ ቴሌቪዥን ኢቴቭ ይፋ ተደረገ፡፡ ከዚያም ነሐሴ 27 ቀን 2004 ዓ.ም. ግብዓተ መሬታቸው እንደ ተከናወነ በግብረ-አበሮቻቸውና በመንግስት ሹማምንት ከተገለፀ በኋላ “…የመለስን ራዕይ እናስቀጥላለን!” የሚል መፈክር መሰማት ጀመረ፤የተባለው ራዕይ ኑዛዜ አሁንም ባያበቃም፡፡

በርግጥ አቶ መለስ ራዕይ ነበራቸው ከተባለ፤ እስከ ህልፈታቸው ድረስ የትኛውንም መንገድ ተጠቅመው ከቤተመንግስት ሳይወጡ ተቀናቃኞቻቸውን በማሰርና በማጥፋት በስልጣን መቆየት ነው፡፡ ነበራቸው የተባለው ራዕይ አሳቸው ሲሞቱ አብሮ ሞቷል፡፡ ይህ ደግሞ ራዕይ ሳይሆን የስልጣን ጥም እንጂ ህዝባዊና ሀገራዊ አይደለም፡፡ ተከታዮቻቸውም እናስቀጥላለን ያሉት ይህንኑ በመሆኑ ልክ እንደሳቸው ተመሳሳይ ድርጊት መፈፀሙትን እንደ ትክክለኛ እና ቅዱስ ተግባር ማከናወን ጀመሩ፡፡ ለአብነትም መጪውን ምርጫ 2007 ዓ.ም. ተከትሎ ለኢህአዴግና አመራሮቹ ስልጣን ማክተሚያ ምክንያት ይሆናሉ ብለው ያሰቧቸውን ማጥመድ፣ ማሰርና መፈረጁን ተያያዙት፡፡ የዚህ ሰለባ ከሆኑት መካከል በሚያዝያ 2006 ዓ.ም. መጨረሻ አካባቢ ጋዜጠኛ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ፣ ጋዜጠኛ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬና ጋዜጠኛ አዚዛ መሐመድ፤ እንዲሁም የኢትዮጵያው ዞን 9 ብሎገሮች በፈቃዱ ኃይሉ፣ዘለዓለም ክብረት፣ አቤል ዋበላ፣ ማህሌት ፋንታሁን፣አጥናፍ ብርሃኔ እና ናትናኤል ፈለቀ ቀዳሚዎቹ ናቸው፡፡

mesበ2004ዓ.ም. ዛሬም ድረስ ምላሽ እንዳላገኘ የሚነገርለት የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ጥያቄ ጋር በተያያዘ የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት፣ጋዜጠኛ ዩሱፍ ጌታቸውና ጋዜጠኛ ሰለሞን ከበደ ታስረው እስካሁን በወህኒ ቤት ይገኛሉ፡፡ ምንም እንኳ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት የተያዘ ቢሆንም እስካሁን ብይንም ሆነ እልባት አላገኘም፡፡ ይሄ ሁሉ በአቶ መለስ አገዛዝ ዘመን የተጀመረ እስር ነው፡፡
በመቀጠልም በሀገር ውስጥ የኢህአዴግ መንግስት እውቅና ያልተቸረውና በሽብርተኝነት የተፈረጀው የግንቦት 7 የፖለቲካ ማኀበር ዋና ፀሐፊ የነበሩት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ በየመን ፀጥታ ኃይሎች ታግተው ለኢትዮጵያው ገዥ ተላልፈው ተሰጥተዋል፡፡ አቶ አንዳርጋቸው ቀደም ሲል የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ አድርጋችኋል በሚል በነ ጄነራል ተፈራ ማሞ ክስ መዝገብ ከነ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ጋር በሌሉበት የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸውል፡፡ የሞት ፍርድ ተፍርዶባቸው የነበሩት አቶ አንዳርጋቸው እንደገና በ2005 ዓ.ም. ደግሞ በነ አንዱኣለም አራጌና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ክስ በሌሉበት የዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸዋል፡፡ ይሁን አንጂ ወደፊት ትናው ክስ ተፈፃሚ እንደሚሆንና በቀጣይ ስለሚኖረው የፍርድ ሂደት ዕድሜ ከሰጠን አብረን የምናየው ነው ሚሆነው፡፡

ከላይ የተጠቀሰው እንዳለ እስሩ ተጠናክሮ በመቀጠል በሀገር ውስጥ በገዥው ስርዓት ህጋዊ እውቅና ተችሯቸው የሚንቀሳቀሱየፖለቲካ ፓርቲ ወጣት አመራሮች ተለቅመው ታሰሩ፡፡ እነኚህም መካከል በማኀበራዊ ሚዲያ የተለያዩ በሳል ፅሑፎችን በመፃፍ የሚታወቀው፣ የመቀሌ ዩኒቨርስቲ መምህርና የዓረና ትግራይ/መድረክ አመራር አቶ አብርሃ ደስታ፤ ከአንድነት ፓርቲ አመራሮች አቶ ሀብታሙ አያሌውና አቶ ዳንኤል ሺበሺ እንዲሁም ከሰማያዊ ፓርቲ አቶ የሺዋስ አሰፋ ይገኙበታል፡፡አራቱም ወጣት ፖለቲከኞች በፓርቲያቸውም ይሁን በሀገሪቱ ሰለማዊ የፖለቲካ ትግል በጎ ተፅዕኖ ፈጣሪዎች መሆናቸው ይነገርላቸዋል፡፡
ሌላው እየተወሰደ ያለውን እስር በመሸሽ ከምርጫ 1997 ዓ.ም. ወዲህ ከ2005 ዓ.ም.ጀምሮ እስከ ያዝነው 2006 ዓ.ም. ድረስ ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞች ተሰደዋል፡፡ ለዚህም በዋነኝነት እንደ አስረጂ ሊጠቀስ የሚችለው በአሁን ሰዓት በጅምላ እየተፈፀመ ያለው እስር ነው፡፡ በአቶ መለስ ዜናዊ የስልጣን ዘመን የተጀመረው የጋዜጠኞችና ብሎገሮች እስር በአሁን ወቅት ሶስት የውጭ ዜጎችን ጨምሮ 20 የደረሰ ሲሆን፤ ከላይ በስም ከተጠቀሱት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በተጨማሪ በርካታ የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ ማኀበር አባላትም በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ዴሞክራሲያዊ መብቶች ዝግ ከነበሩበት የደርግ ጊዜ ጋር ሲነፃፀር፤ በኢህአዴግ ጊዜ 20 ጋዜጠኞችና ብሎገሮችን በማሰር በሀገሪቱ ታሪክ ቀዳሚውን አሉታዊ ስፍራ እንድይዝ ያደርገዋል፡፡ በዚህም በፀታ ኃይሉና በፍትህ ተቋማቱ ላይ ተጨማሪ የስራ ጫና ከመፍጠር በዘለለ የታሰበውን የፖለቲካ ትርፍ ያስገኛል ተብሎ አይጠበቅም፡፡

እንደ ገዥው ስርዓት አመራሮች፣ ደጋፊዎችና የፀጥታ ኃይሎች ገለፃ ከሆነ እስሩ የሚቆም አይደለም፡፡ በቀጣይ የዚህ ሰለባ ማን እንደሚሆን ባይታወቅም፤ እንደተባለው የሚተገበር ከሆነ በድጋሚ ቀሪ ጋዜጠኞች እና ፖለቲካኖች የእስር ስለባው ሊሆኑ እንደሚችሉ አያጠያይቅም፡፡ ምክንያቱም ከሌላው በተሻለ መብቶቻቸውን እየተገበሩና እየተጠቀሙ ማኀበረሰቡ ላይ በጎ ተፅዕኖ በመፍጠር የስርዓቱ ስልጣን ፈተና ይተረጎማሉና፡፡ አቶ መለስ ከመሞታቸው በፊት ምርጫ ሲደርስና ለስልጣናቸው የሚያሰጋቸው ነገር ብልጭ ሲልባቸው የሚወስዷቸው ርምጃዎች አሁን በስልጣን ላይ ባሉ ተከታዮቻቸው ተጠናክረው መቀጠላቸው አንዱ የመለስ ራዕይ ነው ሊያስብል ይችላል፡፡ ይህም አመራሮቹ እናስቀጥለዋለን ያሉት የአቶ መለስ ራዕይ አንዱ አካል ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ምክንያቱም ያኔ በሳቸው ዘመን የተጀመረው ዛሬም በቃ ሊባልና መቋጫ ሊበጅለት አልቻለምና፡፡

አሁን በመንግስት አመራሮች ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮችና ፖለቲካኞች ላይ ትኩረት ያደረገ የእስር ዘመቻ ከዚህ በፊት እንደ ተወዳጅ ነጠላ ዜማ ሲዜም የነበረውን “የመለስን ራዕይ እናስቀጥላለን” አባባል የሚታየው የእስር ዘመቻ መሆኑን በማሳበቅ በደጋፊዎቻቸው እንደ ሊቀ ሊቃውንትና ባለራዕይ የተወሰዱት ሟቹ ሰውዬ እንዲኮነኑ ማድረጉ አይቀርም፡፡ በየትኛውም ዓለም እንደሚታየው የፖለቲካ ርምጃና ተሞክሮ ሰዎችን ያውም ዜጎችን አሸባሪ ብሎ ማሰር በስልጣን ለመቆየትም ሆነ ለመረጋጋት መፍትሄ ሊሆን አይችልም፡፡ እንዲህ ዓይነት ርምጅ መፍትሔ ቢሆን ኖሮ የሊቢያው መሪ ኮሎኔል ሙዓመር ጋዳፊ፣ የግብፁ ሆስኒ ሙባረክ፣የየመኑ ዓሊ አብደላ ሳላህ በስልጣን ላይ መቆየት በቻሉ ነበር፤ግን አልሆነም፡፡

ነገርን ግን የህዝቡን ቁጣ በመቀስቀስ በውርደት ከስልጣን እንዲወርዱ አስገደዳቸው እንጂ መፍትሄ አልሆናቸውም፡፡ ስለዚህ በስልጣን ለመቆየት ጉጉቱ ካለ እንኳ የዜጎችን መብት፣ፍላጎትና ጥቅም ማክበርና ማስጠበቅ የተሻለ አማራጭ ነው፡፡ መፍትሔውን ልክ እንደ ጥሎ ማለፍና ፍፃሜ የአትሌቲክስ ውድድር ዜጎችን በማሰርና እንዲሰደዱ በማድረግ ዙሩን ማክረር ታምቆ የቆየውን የህዝብን ስሜት ባልተጠበቀ ሰዓት እንዲፈነዳ በማድረግ ሌላ ችግር ሊወልድ ይችላል፡፡የሚፈራው ችግር የሚከሰት ከሆነ ደግሞ የበለጠ ለገዥዎችም፣ ለህቡም ሆነ ለሀገሪቱ አሉታዊ ተፅዕኖ ማስከተሉ እሙን ነው፡፡

ሰበር ሰሚ ችሎት የነ አቶ በቀለ ገርባን ይግባኝን እንደማያይ አስታወቀ -እነ አንዱዓለም አራጌም የፊታችን ሰኞ ሰበር ሰሚ ችሎት እንደሚቀርቡ ይጠበቃል

የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የኦፌኮ-መድረክ ምክትል ሊቀመንበር እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር የሆኑት አቶ በቀለ ገርባ ላይ እና የኦፌኮ ሌላው አመመራር ወጣት ኦልባና ሌሊሳ የጠየቁትን ይግባኝ ዛሬ ጥቅምት 21 ቀን 2006 ዓ.ም. በዋለው ችሎት የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የህግ ስህተት የለውም በሚል ሰበር ሰሚ ችሎቱ ይግባኙን ውድቅ አድርጎታል፡፡ አቶ በቀለ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ ወንጀል ችሎት በፌደራሉ አቃቤ ህግ በተከሰሱበት የሽብር ወንጀል 8 ዓመት ፅኑ እስራት የተፈረደባቸው ሲሆን ፤ ይህን በመቃወምፈደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ጠይቀው ነበር፡፡

ጠቅላይ ፍርድ ቤቱም በከፍተኛው ፍርድ ቤት የተወሰነውን የ8 ዓመት እስራት ወደ 3 ዓመት ከ7 ወር ዝቅ ማድረጉይታወቃል፡፡ አቶ ኦልባና ሌሊሳም በከፍተኛው ፍርድ ቤት 13 ዓመት ፅኑ እስራት የተፈረደባቸውን በይግባኝ ጠቅላይፍርድ ቤቱ ወደ 11 ዝቅ እንዲል አድርጓል፡፡ ይሁን እንጂ እነ አቶ በቀለ ገርባ የተከሰስነው በሐሰት የፈጠራወንጀል እንጂ ምንም የፈፀምነው ወንጀል ስለሌለ፤ አቃቤ ህግም በከሰሰን ወንጀል ያቀረበው ማስረጃ እርስ በርሱየሚጣረስ በመሆኑ ሰበር ሰሚ ችሎቱ በነፃ ሊያሰናብተን ይገባል ሲሉ ይግባኝ ቢሉም ፤ሰበር ሰሚ ችሎቱ በዛሬውጥቅምት 21 ቀን 2006 ዓ.ም. ውሎው የይግባኝ ጥያቄያቸውን ውድቅ አድርጎታል፡፡

በተያያዘ ዜና የአንድነት ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር እና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የሆኑት አቶ አንዱዓለም አራጌ ፣ሌላው የፓርቲው ምክር ቤት አባል አቶ ናትናኤል መኮንን፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ፣ አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ እናሌሎች የአንድነት ፓርቲ አመራርና አባላት በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት እና ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተወሰነባቸውንየጥፋተኝነት ውሳኔ በመቃወም ለሰበር ሰሚ ችሎት ይግባኝ ብለዋል፡፡ በዚሁ መሰረት የፊታችን ሰኞ ጥቅምት 25 ቀን 2006 ዓ.ም. ከቀኑ 8 ሰዓት 6 ኪሎ በሚገኘው ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ቀነ ቀጠሮ መሰጠቱንጠበቃው አቶ አበበ ጉታ አስታውቀዋል፡፡

ይህም ለነ አቶ አንዱዓለም ቀጠሮ የመጀመሪያው የሰበር ሰሚ ችሎት ቀነ ቀጠሮ መሆኑ ታውቋል፡፡ አቶ አንዱዓለምአራጌ በከፍተኛው እና በጠቅላይ ፍርድ ቤት ዕድሜ ልከል ፅኑ እስራት ሲፈረድበት ጋዜጠና እስክንድ ነጋ ደግሞ 18 ፅኑ እስራት ፍርድ በጠቅላይ ፍርድ ቤቱ መፅናቱ ሲታወቅ የሌሎችም እንዲሁ መሆኑም አይዘነጋም፡፡