Monthly Archives: February, 2015

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ ትምህርት ክፍል ሊቀመንበር ከኃላፊነት መልቀቃቸውን ይፋ አደረጉ

ዶ/ር ካሳሁን ብርሃኑ

ዶ/ር ካሳሁን ብርሃኑ

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ማኀበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሊቀመንበር ዶ/ር ካሳሁን ብርሃኑ ራሳቸውን ከኃላፊነት ማንሳታቸውን የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ይፋ አደረገ፡፡ ዶ/ር ካሳሁን ከትምህርት ክፍሉ ሊቀመንበርነት ራሳቸውን ለማንሳት የተገደዱት፤ በትምህርት ክፍሉ ከ28 ዓመታት በላይ በፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና የስራ ውል በዩኒቨርስቲው አስተዳደር መቋረጡን ተከትሎ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

ዶ/ር ካሳሁን የዶ/ር መረራ የጡረታ ጊዜ እንዲራዘም ያስገቡት ጥያቄ በዩኒቨርስቲው አስተዳደር ውድቅ መደረጉ እና ከዚያም የትምህርት ክፍሉ ስለሚፈልጋቸው በራሱ የኮንትራት ውል አስፈርሞ ለሰባት ወራት ያሰራበት ክፍያ አለመፈፀሙን ተከትሎ ከመጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ራሳቸውን ከኃላፊነት ማንሳታቸውን የሚገልፅ ደብዳቤ ለዩኒቨርስቲው አስተዳደር ማስገባታቸው ታውቋል፡፡

በተለይ እንደ አሜሪካ ድምፅ ዘገባ ከሆነ፤ ዶ/ር ካሳሁን በዩኒቨርስቲው አስተዳደር በኩል በዶ/ር መረራ ጉዲና ላይ የተወሰደውን ርምጃ ተከትሎ “ የዩኒቨርስቲው አስተዳደር ለትምህርት ክፍሉ ጥያቄና ፍላጎት ምላሽ ባለመስጠቱ፤ የትምህርት ክፍሉን እያስተባበርኩ መቀጠል ከሞራልም አኳያ ተቀባይነት እንደሌለው ይሰማኛል፡፡” በማለት ከትምህርት ክፍሉ ሊቀመንበርነት ለመልቀቅ መወሰናቸውን የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘግቧል፡፡ ዶ/ር መረራ በበኩላቸው ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንደሚወስዱት አስታውቀዋል፡፡ በአሁን ወቅት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጡረታ ጊዜያቸው እንዲራዘም ጠይቀው የተፈቀደላቸውና እየሰሩ የሚገኙ በርካታ መምህራን እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ እስካሁን በዩኒቨርስቲው አስተዳደር ባልተገለፀ ምክንያት የዶ/ር መረራ ጉዲና የስራ ጥያቄ ብቻ ተቀባይነትን ሊያገኝ አለመቻሉ ታውቋል፡፡

ዶ/ር መረራ ጉዲና

ዶ/ር መረራ ጉዲና

ዶ/ር መረራ ከዚህ ቀደም ለሙሉ ፕሮፌሰርነት የሚያበቃ በርካታ ጥናቶችን አጠናቀው ማዕረጉን ለማግኘት ያቀረቡት ማመልከቻ በሚመለከተው የመንግሥት አካል ተቀባይነት እንዳላገኘ የሚታወቅ ነው፡፡ ዶ/ር መረራ ከዚህ ቀደምም ሆነ አሁን የተወሰደባቸው እርምጃ በተቃውሞ ፖለቲካ ባላቸው ተሳትፎ እንደሆነ የተጠቆመ ሲሆን፤ በአሁን ወቅትም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርነታቸው በተጨማሪ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ ሊቀመንበር እና የአራት ፓርቲዎች ግንባር የሆነው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) ምክትል ፕሬዘዳንት እና የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡

አትሌት ገንዘቤ ዲባባ አዲስ የዓለም ከብረ-ወሰን በማስመዝገብ አሸነፈች

ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ገንዘቤ ዲባባ በስዊድን ስቶኮሎም የ2015 ዓለም አቀፍ የ5,000 ሜትር የቤት ውስጥ ዓለም አቀፍ ውድድር አሸነፈች፡፡ አትሌት ገንዘቤ ውድድሩን ያሸነፈችው ከዚህ ቀደም ተመዝግቦ የነበረውን ክብረ-ወሰን በማሻሻል ነው፡፡

አትሌት ገንዘቤ ዲባባ

አትሌት ገንዘቤ ዲባባ

ገንዘቤ ውድድሩን ያሸነፈችው 14 ደቂቃ ከ18 ሰከንድ ከ86 ማይክሮ ሰከንድ በመግባት ነው፡፡ በውድድሩ ከዚህ ቀደም የነበረው የዓለም ክብረወሰን 14 ደቂቃ ከ24 ሰከንድ ከ37 ማይክሮ ሰከንድ ሲሆን፤ ይህም በኢትዮጵያዊቷ አትሌት መሰረት ደፋር ተይዞ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ አትሌት ገነዝቤ ዲባባ የአትሌት ጥሩነሽ እና የአትሌት እጅጋየሁ ዲባባ ታናሽ እህት ስትሆን፤ በተለይ ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች ላይ አዳዲስ የዓለም ክብረወሰን እያስመዘገበች ማሸነፏ ይታወቃል፡፡

ምርጫ ቦርድ ከ200 በላይ የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎችን ሰረዘ

  • “ምርጫ ቦርድ ሰማያዊ በምርጫ ሂደቱ እንዲቆይ አይፈልግም” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት

ELEC

ሰማያዊ ፓርቲ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ከ200 በላይ ዕጩዎቹ በምርጫ ቦርድ ትዕዛዝ እንደተሰረዙበት የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በመላ አገሪቱ በተለይም በደቡብ ወሎ፣ በሰሜን ሸዋ፣ በወላይታ፣ በቤንች ማጅ፣ በምዕራብ ጎጃም፣ በሲዳማ፣ በከምባታ፣ በጋሞጎፋ፣ አዲስ አበባ፣ በደቡብ ጎንደርና ጉጅን ጨምሮ በሌሎችም የአገሪቱ ክፍሎች ከ200 በላይ ዕጩዎቹ አንድን ዕጩ ለመሰረዝ የሚያበቃ ምንም አይነት ህጋዊ ምክንያት ሳይኖር “ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደብዳቤ ታዘናል” በማለት ለህዝብ ተወካዮች ምክርቤትና ለክልል ምክር ቤቶች ያስመዘገብናቸው ዕጩ ተወዳዳሪዎቹን በመሰረዝ ከምርጫው ውድድር ውጪ እንዲሆኑ እየተደረገ እንደሆነ ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት አስረድተዋል፡፡

በየክፍለ ሀገሩ የተሰረዙት ዕጩዎች “ፓርቲው ትብብር የሚባል ህገ ወጥ አደረጃጀት መስርቷል፣ የሌሎች ፓርቲዎች አባላት ናችሁ” የመሳሰሉ ምክንያቶችና ደብዳቤ የተሰጣቸው ሲሆን በአንጻሩ በአዲስ አበባ የተሰረዙት ዕጩዎች ከምርጫ አስፈጻሚዎች ምንም አይነት ምክንያትና ደብዳቤ እንዳልተሰጣቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ዕጩዎቹ “የተሰረዝንበትን ምክንያት ንገሩን፣ ደብዳቤ ልትሰጡን ይገባል” ቢሉም የምርጫ አስፈጻሚዎቹ “እኛ እናንተን ለመመዝገብ ችግር የለብንም፡፡ ግን ከበላይ አካል እንዳንመዘግብ ተነግሮናል፡፡ ደብዳቤም ልንሰጣችሁ አንችልም፡፡” የሚል መልስ እንደሰጧቸው ገልፀዋል፡፡

Semayawi-Party

በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎች መሰረዛቸውን ተከትሎ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች የቦርዱን ሰብሳቢ ፕ/ር መርጋ በቃናን ለማግኘት ቢጥሩም “ከከተማ ውጭ ናቸው፡፡ አሁን አታገኟቸውም” የተባሉ ሲሆን ፕ/ር መርጋ የህወሓትን 40ኛ አመት ለማክበር መቀሌ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በትናንትናው ዕለት በጉዳዩ ላይ ከቦርዱ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ነጋ ዱፌሳ ጋር የተነጋገሩ ሲሆን አቶ ነጋ “ማመልከቻ አስገቡ” ከማለት ውጭ ዕጩዎቹ ለመሰረዛቸው ተጨባጭ ምክንያት መስጠት እንዳልቻሉ  ኢ/ር ይልቃል ገልጸውልናል፡፡

“የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎችን ያለ አግባብ የሚሰርዙት ሰማያዊ በምርጫ ሂደቱ ጫና መፍጠር ስለሚችል በሂደቱ እንዲቆ ስለማይፈልጉ ነው” ያሉት ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት፤ ሆኖም ይህ የምርጫ ቦርድ ውሳኔ ለነጻነት የሚያደርጉትን ትግል ትክክለኛ እንደሆነ እንዳስረገጠላቸው፣ ይህን የነፃነት ትግልም አጠናክረው እንደሚቀጥሉና የካቲት 22 ፓርቲያቸው ከትብብሩ ፓርቲዎች ጋር በ15 ከተሞች በተመሳሳይ ጊዜ በ15 ከተሞች የሚያደርገው ሰልፍ የዚሁ የነጻነት ትግል አካል እንደሆነ መግለፃቸውን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ እስራኤላውያን ሴቶች የወሊድ መከላከያ እንዲወስዱ ተገደዋል መባሉን እስራኤል አመነች

ከኢትዮጵያ የተወሰዱ ቤተ እስራኤላውያን ሴቶች ለረዥም ጊዜ የሚያገለግለውን ዴፖ ፕሮቬራ የተባለ የወሊድ መቆጣጠሪያ መድሃኒት ለመወጋት ካልተስማሙ ወደ እስራኤል ሊገቡ እንደማይችሉ ይነገራቸው እንደነበር ይታወቃል።

ክሊኒኩን ያስተድድር የነበረው “Joint Distribution Committee” እና የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ውንጀላውን ማስተባበላቸው የሚታወስ ቢሆንም ዛሬ በወጣው ሪፓርት የእስራኤል መንግስት ውንጀላውን አምኗል።

ethio-jewish

በርካታ ሴቶች፣ በኢትዮጵያ ጊዜያዊ መጠለያ ውስጥ ሳሉ በክትባት መልክ የሚሰጠውን የወሊድ መቆጣጠሪያ መድኃኒት እንዲወስዱ እንዴት ያግባቧቸውና ያስፈራሯቸው እንደነበር ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያውያን ቤተ-እስራኤላውያኑ ሲገልፁ “የማትወስዱ ከሆነ ወደ እስራኤል አትሄዱም፤ እርዳታና ህክምናም አታገኙ ተባልን፡፡ ይሄኔ ፈራን፤ ምንም ምርጫ አልነበረንም፡፡ ያለ እነሱ እርዳታ መውጣት አንችልም ነበር፡፡ ስለዚህ ክትባቱን ለመወጋት ተስማማን፡፡” ሲሉ ቤተ-እስራኤላውያን መናገራቸውን የሀገሪቱ መገናኛ ብዙኃን በመጥቀስ ዎርልድ ቡሌቲን ዘግቧል፡፡ ቤተ-እስራኤላውያኑ ከዚህ ቀደም በእስራኤል መንግሥትና ቀድመው እስራኤል በገቡ ዜጎች ከተለያዩ ማኀበራዊ የመንግሥት አገልግሎቶች ጭምር ይገለሉ እንደነበር መዘገቡ አይዘነጋም፡፡

የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር በ15 ከተሞች የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጠራ

“ነፃነት ለፍትሃዊ ምርጫ” በሚልመርህ የሚካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ የካቲት 22 ቀን 2007 ዓም በ15 ከተሞች እንደሚካሄድ ትብብሩ አስታውቋል።

ከግራ ወደ ቀኝ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ከ(ሰማያዊ) እና አቶ ግርማ በቀለ ከ(ኦህዴህ)

ከግራ ወደ ቀኝ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ከ(ሰማያዊ) እና አቶ ግርማ በቀለ ከ(ኦህዴህ)

“የሙስሊም ማህበረሰቡ ታህሳስ 10 ቀን 2007 ዓም በኑር መስጂድ ፣ የካቲት 6 ቀን 2007 ዓም ደግሞ በአንዋር መስኪድ ያደረገው ተቃውሞ እንዲሁም የባህርዳር ከተማ ህዝብ ታህሳስ 10 ቀን 2007 ዓም ያሳየው ህዝባዊ እምቢተኝነት ትግል በሃይል ሊዳፈን ቢችልም እንደማይጠፋ ትምህርት ሰጥቷል” ሲል በመግለጫው አስታውቋል፡፡ ትብብሩ፣ ገዢው ፓርቲ እያደረሰ ያለው የመብት ረገጣ፣ የሙስና መስፋፋትና የመልካም አስተዳደር እጦት የህዝቡን የለውጥ ፍላጎትና የትግል ተነሳሽነት እንዳሳደገው ገልጿል።

ትብብሩ ገዢው ፓርቲ ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ከቃላት ያለፈ እምነትም ሆነ ቁርጠኝነት እንደሌለው በመግለጽ፣ ምርጫ ቦርድን በቁጥጥር ስር በማዋል ጠንካራ ፓርቲዎችን ከመጪው ምርጫ ለማግለል እየሰራ መሆኑን የአንድነትና መኢአድን ጉዳይ በመግለፅ አብራርተዋል።

ከሰሞኑ ኢቢሲ ያቀረበው የተቃዋሚ ፓርቲዎችን የመኖር ትርጉም ዋጋ የሚያሳጣው ‹‹መንግስትንና የመንግስት አስፈጻሚዎችን ከተቻችሁ፣ ካላከበራችሁ ወይም ጸጥ ለጥ ብላችሁ የምርጫ አጃቢ ካልሆናችሁ እስከ 15 ዓመት ትታሰራላችሁ›› የሚል አንድምታ ያለው በ ‹‹ባለሙያዎች ትንታኔ ›› ሥም የተላከው የማስፈራሪያ መልዕክትና የሌሉ የፈጠራ ክሶችን ለመፈብረክ በአባል ፓርቲዎቻችን ላይ ‹‹የሞተ ጉዳይን ከመቃብር በመቀስቀስ›› እና በአዲስ መልክ የተጀመረው የሚዲያ የፕሮፖጋንዳ ዘመቻ በግልጽ ያስተላለፈው ገዢው ፓርቲ የመድብለ ፓርቲ ስርአት እንዳይኖር መፈለጉን ነው ሲል አክሏል።

የእኛ፣ የአገራችንና ዜጓቿ ቀጣይ ዕጣ ፈንታ በሁለት አማራጮች ላይ የተንጠለጠለ ነው የሚለው ትብብሩ አንድም ያለውን አምባገነናዊ ሥርዓት ተቀብለን፣የአገራችን ሉዓላዊነት በጥያቄ ውስጥ ባለበት፣ የጭቆና ቀንበር ተሸክመን በከፋ ውርደት ሥር ሰጥ ለጥ ብሎ መገዛት፤ አሊያም አምባገነንነትና ጭቆናን “በቃ” በማለት በሕዝባዊ የተቀናጀ ሰላማዊ ትግል ለአገራችን ሉዓላዊነትና የዜግነት ክብራችንን ለማስመለስ በህገ መንግስታዊ መብታችን ተጠቅመን ትግላችንን እስከማይቀረው ለውጥ/ ድል ደጃፍ ድረስ በቆራጥነት መቀጠል፣ ናቸው ብሏል፡፡

ሁሉን አቀፍ የነፃነትና ክብርን የማስመለስ ሰላማዊ ትግል ለ9ኙ ፓርቲዎች ብቸኛ አማራጭ መሆኑም ትብብሩ አስምሮበታል፡፡

ፓርቲዎቹ በመጨረሻም በሚደረገው አገራዊ፣ ሰላማዊና ሕዝባዊ ትግል በማይቀረው የሥርዓት ለውጥ ለሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር በአንድነትና በቆራጥነት ህዝቡ እንዲነሳና በየካቲት 22 የተቃውሞ ሰልፍ ላይ እንዲገኝ በመግለጫቸው ጥሪ አቅርበዋል።