Category Archives: Politics

ማሰርና ማሳደድ መፍትሄ ይሆናል?

ብስራት ወልደሚካኤል
afrosonb@gmail.com

በቀድሞ ታጣቂዎች እንደ ጭራቅና አውሬ ይሳል የነበረው የደርግ ስርዓት ወድቆ ስልጣን በአማፂዓን እጅ ከገባ 23 ዓመታት አልፈዋል፡፡ ነገር ግን የታሰበው ለውጥ ዛሬም ቢሆን መናፈቁን አልተወም፡፡ ምክኔቱም ያኔ ማሰር ነበር፤ ዛሬም ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ያኔም መወንጀልና መፈረጅ ነበር ዛሬ ግን ተባብሷል፡፡ ለእኔ ከድሮ የተለየ ተቀይሮ ያገኘሁት በዋናነት የመሪዎች ስምና ልብሳቸው እንጂ ስራቸው ያው ነው፡፡

በዘመነ ደርግ ጠባብነትና ዘረኝነትን እንዲሁም ኢትዮጵያ ላይ ጥላቻ ያላቸውን በሙሉ ስልጣኑን ሊቀናቀኑ ካሰቡት እኩል በጠላትነት ይፈረጃሉ፡፡ በዘመነ ኢህአዴግ ደግሞ ኢትዮጵያዊነትን ማስቀደምና ለኢትዮጵያውያን በእኩል ዓይን መቆምና መቆርቆር እንደ ወንጀል ይታያል፡፡ሁለቱም ወደ ስልጣን ሲወጡ በጠብመንጃ ሲሆን፤ ስልጣናቸውንም ያስጠበቁትን የሚያስጠብቁት እንዲ በጦር መሳሪያ ነው፡፡ምን አለፋችሁ፤ ልዩነቱን “…ጃሃ ያስተሰርያል” የሚለው የአርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (የቴዲ አፍሮ) ሙዚቃ በደንብ ይገልፀዋል፡፡

sssበሁለቱ መካከል ያለው መሰረታዊ ልዩነት ደርግ የማይፈልገውን ነገር በግልፅ በአዋጅ ይደነግጋል፤ከአዋጅ ወይም ህግ ውጭ ይቀጣል፡፡ ኢህአዴግ ደግሞ የሚፈልገውንም ሆነ የማይፈልገውን በህገ መንግስት እውቅና ሰጥቶ የማይፈልገውን በሌላ አዋጅ ይቀጣል፣ያስራል፡፡ ልዩነታቸው የመሪዎች ስም፣ የለበሱት ልብስና አካሄዳቸው እንጂ መሰረታዊ የልዩነት ባህርይ አይታይባቸውም፡፡ ለዚህም አሁን በስልጣን ላይ ያለው ኢህአዴግ ከደርግ በባሰ ያከናወናቸውን እና እያከናወናቸው ካሉት አሉታዊ ተግባራት መካከል በዋናነት የእስር ዘመቻውን ማንሳቱ በቂ ነው፡፡

በተለይ በምርጫ 1997 ዓ.ም. ኢህአዴግ በአደባባይ መሸነፉን እና የህዝብን ድምፅ መቀማቱን የሚያሳብ በርካታ ተግባራትን ሲያከናውን ዋናው ገመናውን የሚያጋልጡና በአብዛኛው ህዝብ ዘንድ ተቀባይነትና ተወዳጅነት ያላቸውን በሰበብ አስባቡ አስሮ ማሰቃየትን እንደ ትልቅ አማራጭ መጠቀም ጀመረ፡፡ ለዚህ በምርጫው ያሸነፉት የቀድሞ ቅንጅት አመራሮችን ከወነጀለበት በኢትዮጵያ 2000 ዓ.ም. ዋዜማ ከእስር ከፈታ በኋላ አዲሱ ቀዳሚ እስረኛ አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ነበር፤ የእስርዓ ምዕት ኢትዮጵያ ጅማሮ እስረኛ፡፡ ይህም አዲስ አበባና አስመራን ጨምሮበመላው ዓለም ጥያቄና ተቃውሞ ከማስነሳቱ በተጨማሪ ከእስር ሲፈታም የህዝብ ድጋፍ በመላው ዓለም ተጠናክሮ እስከዛሬም ድረስ ዘልቋል፡፡

ከዚህ በኋላ የኢህአዴግ ጥላቻ እየተባባሰ፣ ለስልጣን ያለው ጥማት ሰርክ እንደ አዲስ ወይን እየጣመው ይሄድ ጀመር፡፡ ከስልጣናቸው በዕድሜ ይፍታህ የተሰናበቱት ሟቹ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ በስልጣናቸው እስከ መቃብር አፋፍ ዋስትና ይሆናል ያሏቸውን አፋኝ ህጎች ፀድቀው ተግባር ላይ እንዲውሉ ቀን ከሌት ኳተኑ፡፡ በዚህም የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኀበራት አዋጅ፣ የፕሬስ አዋጅ፣ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ፣…ይገኙበታል፡፡

በተለይ በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች እና የነፃ ጋዜጠኞች ከፍተኛ ተቃውሞ የገጠመው የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ ሰኔ 30 ቀን 2001 ዓ.ም. ፀድቆ ለምርጫ 2002 ዓ.ም. ማፈኛ ተዘጋጀ፡፡ የዚህም ገፈት የዴሞክራሲ እንቅስቃሴዎችን ገድቦ የነበረውን ተስፋ መቀመቅ ውስጥ ከተተው፡፡ ከዚህ በኋላ በየካቲት 2003 ዓ.ም. በቱኒዚያ መሐመድ ቡዓዚዝ የተጀመረው የአረቡ ፀደይ አብዮት በሰሜን አፍሪካን እና መካከለኛ ምስራቅ አረብ ሀገሮች መቀጣጠሉን የተመለከቱት አቶ መለስና ተከታዮቻቸውና አጋሮቻቸው በኢትዮጵያም ይከሰታል በሚል የአስር አደኑንን አጣደፉት፡፡

የአረቡን አብዮት ተከትሎ በኢትዮጵያ የእስር ሰንሰለቱን የጀመሩት እንደ ታሰበው ጋዜጠኞች እና የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ናቸው፡፡ በቀዳሚነትም በወርሃ ሰኔ 12 ቀን 2004 ዓ.ም. ከፖለቲከኛ አቶ ዘሪሁን ገ/እግዚአብሔር፣ ሰኔ 14 ቀን 2003 ዓ.ም. ደግሞ ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ፣ ርዕዮት አለሙ፤ ከዚያም በክረምት 2003 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህርና የኦፌኮ/መድረክ አመራር አቶ በቀለ ገርባና አቶ ኦልባና ሌሊሳ የእስር ሰለባ ሆኑ፡፡

andሌላው ከኢትዮጵያውያን በተጨማሪ ሁለት ሲውድናውያን ጋዜጠኞች ማርቲን ሸብይ እና ጆሃን ፐርሰን ሽብርተኝነትን ደግፈዋል በሚል በዚሁ የፀረ-ሽብርተኝነት ሰለባ በመሆን ከ14 ወራት የሰቆቃ እስር በኋላ በዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ጫና መስከረም 1 ቀን 2004 ዓ.ም.ተለቀዋል፡፡ በመቀጠል መስከረም 3 ቀን 2004 ዓ.ም. ደግሞ ታዋቂው የፖለቲካ ተንታኝ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣በብዙ ወጣቶች ዘንድ በቅንነቱና ፍቅርን በመስጠት እንዲሁም ሰላማዊ የፖለቲካ ትግልን አጥብቆ በመደገፍ የሚከራከረው የአንድነት/መድረክ አመራር አቶ አንዱዓለም አራጌ እና ሌሎች የአንድነት ፓርቲ አመራሮች አቶ ናትናኤል መኮንን፣አቶ ዮሐንስ ተረፈና ሻምበል የሺዋስ ይሁንዓለምንና አቶ አንዱዓለም አያሌውን ጨምሮ አቶ ክንፈ ሚካኤል ደበበና ሌሎች ሰዎችም በሽብርተኝነት ስም ወደ ወህኒ ወረዱ፡፡ በዚህም አፍቃሬ መንበር አቶ መለስ የፈሩትን የአረቡን አብዮት በዚህ ያለፉ ይመስል ጀብደኝነት ተሰምቷቸው፤ ተጠርጣሪዎቹ ገና በፍርድ ቤት ብይን ሳይሰጥባቸው አሸባሪዎች ናቸው ሲሉ ለተወካዮቻቸው አረጋገጡ፡፡
ያሰሯቸው ላይ ቀድመው ወንጀለኛ በማለት ፍርድ በመስጠት መከራን የደገሱት አቶ መለስ ባልጠበቁት ሁኔታ በጠና ታመው በአውሮፓ ቤልጄየም ብራሰልስ አንድ የዩኒቨርስቲ ሪፈራል ሆስፒታል ተኙ፡፡ በመጨረሻም እንደ ሆስፒታሉ ምንጮች ከሆነ ሐምሌ 13 ቀን 2004 ዓ.ም. እንደወጡ ላይለመሱ ብዙ ለመኖር ያሰቡበትን በ21 ዓመታት የስልጣን ዘመናቸው እንደ ግል ርስታቸው ያስቡት የነበረውን ቤተመንግስት ጥለው እስከወዲያኛው ተሰናበቱ፡፡

bekይሁን እንጂ አጋሮቻቸውና የቅርብ የኢህአዴግ አመራሮች መታመማቸውን እንኳ ለህዝብ ሳይገልፁ በድንገት የሞቱትን ሰውዬ ከጋዜጠኞች ጥያቄ ቢበረታባቸው በቅርቡ ተመልሰው ስራ ይጀምራሉ የሚል መልስ ሰጡ፡፡ በኋላም የተባለው ሳይሆን ፈጣሪ የወሰነው ሞት እርግጥ መሆኑ እና ነሐሴ 14 ቀን 2004 ዓ.ም. ሌሊት እንዳረፉ ተደርጎ ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም. ማለዳ አንድ ለእናቱ በሆነው ሀገሪቱ ቴሌቪዥን ኢቴቭ ይፋ ተደረገ፡፡ ከዚያም ነሐሴ 27 ቀን 2004 ዓ.ም. ግብዓተ መሬታቸው እንደ ተከናወነ በግብረ-አበሮቻቸውና በመንግስት ሹማምንት ከተገለፀ በኋላ “…የመለስን ራዕይ እናስቀጥላለን!” የሚል መፈክር መሰማት ጀመረ፤የተባለው ራዕይ ኑዛዜ አሁንም ባያበቃም፡፡

በርግጥ አቶ መለስ ራዕይ ነበራቸው ከተባለ፤ እስከ ህልፈታቸው ድረስ የትኛውንም መንገድ ተጠቅመው ከቤተመንግስት ሳይወጡ ተቀናቃኞቻቸውን በማሰርና በማጥፋት በስልጣን መቆየት ነው፡፡ ነበራቸው የተባለው ራዕይ አሳቸው ሲሞቱ አብሮ ሞቷል፡፡ ይህ ደግሞ ራዕይ ሳይሆን የስልጣን ጥም እንጂ ህዝባዊና ሀገራዊ አይደለም፡፡ ተከታዮቻቸውም እናስቀጥላለን ያሉት ይህንኑ በመሆኑ ልክ እንደሳቸው ተመሳሳይ ድርጊት መፈፀሙትን እንደ ትክክለኛ እና ቅዱስ ተግባር ማከናወን ጀመሩ፡፡ ለአብነትም መጪውን ምርጫ 2007 ዓ.ም. ተከትሎ ለኢህአዴግና አመራሮቹ ስልጣን ማክተሚያ ምክንያት ይሆናሉ ብለው ያሰቧቸውን ማጥመድ፣ ማሰርና መፈረጁን ተያያዙት፡፡ የዚህ ሰለባ ከሆኑት መካከል በሚያዝያ 2006 ዓ.ም. መጨረሻ አካባቢ ጋዜጠኛ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ፣ ጋዜጠኛ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬና ጋዜጠኛ አዚዛ መሐመድ፤ እንዲሁም የኢትዮጵያው ዞን 9 ብሎገሮች በፈቃዱ ኃይሉ፣ዘለዓለም ክብረት፣ አቤል ዋበላ፣ ማህሌት ፋንታሁን፣አጥናፍ ብርሃኔ እና ናትናኤል ፈለቀ ቀዳሚዎቹ ናቸው፡፡

mesበ2004ዓ.ም. ዛሬም ድረስ ምላሽ እንዳላገኘ የሚነገርለት የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ጥያቄ ጋር በተያያዘ የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት፣ጋዜጠኛ ዩሱፍ ጌታቸውና ጋዜጠኛ ሰለሞን ከበደ ታስረው እስካሁን በወህኒ ቤት ይገኛሉ፡፡ ምንም እንኳ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት የተያዘ ቢሆንም እስካሁን ብይንም ሆነ እልባት አላገኘም፡፡ ይሄ ሁሉ በአቶ መለስ አገዛዝ ዘመን የተጀመረ እስር ነው፡፡
በመቀጠልም በሀገር ውስጥ የኢህአዴግ መንግስት እውቅና ያልተቸረውና በሽብርተኝነት የተፈረጀው የግንቦት 7 የፖለቲካ ማኀበር ዋና ፀሐፊ የነበሩት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ በየመን ፀጥታ ኃይሎች ታግተው ለኢትዮጵያው ገዥ ተላልፈው ተሰጥተዋል፡፡ አቶ አንዳርጋቸው ቀደም ሲል የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ አድርጋችኋል በሚል በነ ጄነራል ተፈራ ማሞ ክስ መዝገብ ከነ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ጋር በሌሉበት የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸውል፡፡ የሞት ፍርድ ተፍርዶባቸው የነበሩት አቶ አንዳርጋቸው እንደገና በ2005 ዓ.ም. ደግሞ በነ አንዱኣለም አራጌና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ክስ በሌሉበት የዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት ተፈርዶባቸዋል፡፡ ይሁን አንጂ ወደፊት ትናው ክስ ተፈፃሚ እንደሚሆንና በቀጣይ ስለሚኖረው የፍርድ ሂደት ዕድሜ ከሰጠን አብረን የምናየው ነው ሚሆነው፡፡

ከላይ የተጠቀሰው እንዳለ እስሩ ተጠናክሮ በመቀጠል በሀገር ውስጥ በገዥው ስርዓት ህጋዊ እውቅና ተችሯቸው የሚንቀሳቀሱየፖለቲካ ፓርቲ ወጣት አመራሮች ተለቅመው ታሰሩ፡፡ እነኚህም መካከል በማኀበራዊ ሚዲያ የተለያዩ በሳል ፅሑፎችን በመፃፍ የሚታወቀው፣ የመቀሌ ዩኒቨርስቲ መምህርና የዓረና ትግራይ/መድረክ አመራር አቶ አብርሃ ደስታ፤ ከአንድነት ፓርቲ አመራሮች አቶ ሀብታሙ አያሌውና አቶ ዳንኤል ሺበሺ እንዲሁም ከሰማያዊ ፓርቲ አቶ የሺዋስ አሰፋ ይገኙበታል፡፡አራቱም ወጣት ፖለቲከኞች በፓርቲያቸውም ይሁን በሀገሪቱ ሰለማዊ የፖለቲካ ትግል በጎ ተፅዕኖ ፈጣሪዎች መሆናቸው ይነገርላቸዋል፡፡
ሌላው እየተወሰደ ያለውን እስር በመሸሽ ከምርጫ 1997 ዓ.ም. ወዲህ ከ2005 ዓ.ም.ጀምሮ እስከ ያዝነው 2006 ዓ.ም. ድረስ ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞች ተሰደዋል፡፡ ለዚህም በዋነኝነት እንደ አስረጂ ሊጠቀስ የሚችለው በአሁን ሰዓት በጅምላ እየተፈፀመ ያለው እስር ነው፡፡ በአቶ መለስ ዜናዊ የስልጣን ዘመን የተጀመረው የጋዜጠኞችና ብሎገሮች እስር በአሁን ወቅት ሶስት የውጭ ዜጎችን ጨምሮ 20 የደረሰ ሲሆን፤ ከላይ በስም ከተጠቀሱት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች በተጨማሪ በርካታ የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ ማኀበር አባላትም በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ዴሞክራሲያዊ መብቶች ዝግ ከነበሩበት የደርግ ጊዜ ጋር ሲነፃፀር፤ በኢህአዴግ ጊዜ 20 ጋዜጠኞችና ብሎገሮችን በማሰር በሀገሪቱ ታሪክ ቀዳሚውን አሉታዊ ስፍራ እንድይዝ ያደርገዋል፡፡ በዚህም በፀታ ኃይሉና በፍትህ ተቋማቱ ላይ ተጨማሪ የስራ ጫና ከመፍጠር በዘለለ የታሰበውን የፖለቲካ ትርፍ ያስገኛል ተብሎ አይጠበቅም፡፡

እንደ ገዥው ስርዓት አመራሮች፣ ደጋፊዎችና የፀጥታ ኃይሎች ገለፃ ከሆነ እስሩ የሚቆም አይደለም፡፡ በቀጣይ የዚህ ሰለባ ማን እንደሚሆን ባይታወቅም፤ እንደተባለው የሚተገበር ከሆነ በድጋሚ ቀሪ ጋዜጠኞች እና ፖለቲካኖች የእስር ስለባው ሊሆኑ እንደሚችሉ አያጠያይቅም፡፡ ምክንያቱም ከሌላው በተሻለ መብቶቻቸውን እየተገበሩና እየተጠቀሙ ማኀበረሰቡ ላይ በጎ ተፅዕኖ በመፍጠር የስርዓቱ ስልጣን ፈተና ይተረጎማሉና፡፡ አቶ መለስ ከመሞታቸው በፊት ምርጫ ሲደርስና ለስልጣናቸው የሚያሰጋቸው ነገር ብልጭ ሲልባቸው የሚወስዷቸው ርምጃዎች አሁን በስልጣን ላይ ባሉ ተከታዮቻቸው ተጠናክረው መቀጠላቸው አንዱ የመለስ ራዕይ ነው ሊያስብል ይችላል፡፡ ይህም አመራሮቹ እናስቀጥለዋለን ያሉት የአቶ መለስ ራዕይ አንዱ አካል ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ምክንያቱም ያኔ በሳቸው ዘመን የተጀመረው ዛሬም በቃ ሊባልና መቋጫ ሊበጅለት አልቻለምና፡፡

አሁን በመንግስት አመራሮች ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮችና ፖለቲካኞች ላይ ትኩረት ያደረገ የእስር ዘመቻ ከዚህ በፊት እንደ ተወዳጅ ነጠላ ዜማ ሲዜም የነበረውን “የመለስን ራዕይ እናስቀጥላለን” አባባል የሚታየው የእስር ዘመቻ መሆኑን በማሳበቅ በደጋፊዎቻቸው እንደ ሊቀ ሊቃውንትና ባለራዕይ የተወሰዱት ሟቹ ሰውዬ እንዲኮነኑ ማድረጉ አይቀርም፡፡ በየትኛውም ዓለም እንደሚታየው የፖለቲካ ርምጃና ተሞክሮ ሰዎችን ያውም ዜጎችን አሸባሪ ብሎ ማሰር በስልጣን ለመቆየትም ሆነ ለመረጋጋት መፍትሄ ሊሆን አይችልም፡፡ እንዲህ ዓይነት ርምጅ መፍትሔ ቢሆን ኖሮ የሊቢያው መሪ ኮሎኔል ሙዓመር ጋዳፊ፣ የግብፁ ሆስኒ ሙባረክ፣የየመኑ ዓሊ አብደላ ሳላህ በስልጣን ላይ መቆየት በቻሉ ነበር፤ግን አልሆነም፡፡

ነገርን ግን የህዝቡን ቁጣ በመቀስቀስ በውርደት ከስልጣን እንዲወርዱ አስገደዳቸው እንጂ መፍትሄ አልሆናቸውም፡፡ ስለዚህ በስልጣን ለመቆየት ጉጉቱ ካለ እንኳ የዜጎችን መብት፣ፍላጎትና ጥቅም ማክበርና ማስጠበቅ የተሻለ አማራጭ ነው፡፡ መፍትሔውን ልክ እንደ ጥሎ ማለፍና ፍፃሜ የአትሌቲክስ ውድድር ዜጎችን በማሰርና እንዲሰደዱ በማድረግ ዙሩን ማክረር ታምቆ የቆየውን የህዝብን ስሜት ባልተጠበቀ ሰዓት እንዲፈነዳ በማድረግ ሌላ ችግር ሊወልድ ይችላል፡፡የሚፈራው ችግር የሚከሰት ከሆነ ደግሞ የበለጠ ለገዥዎችም፣ ለህቡም ሆነ ለሀገሪቱ አሉታዊ ተፅዕኖ ማስከተሉ እሙን ነው፡፡

የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት በጋዜጠኞችና ብሎገሮች ጉዳይ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጠ

የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ ሐምሌ 28 ቀን 2006 ዓ.ም. በዋለው ችሎት የፌደራሉ አቃቤ ህግ በሽብርተኝነት በሶሊያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ክስ የመሰረተባቸው ዘጠኝ ጋዜጠኞችና የኢትዮጵያ ዞን 9 ብሎገሮች ለነሐሴ 14 ቀን 2006 ዓ.ም. ከጠዋቱ 3 ሰዓት ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ሰጠ፡፡ ጋዜጠኛ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ፣ ተስፋዓለም ወልደየስ እና ኤዶም ካሳዬ እንዲሁም የኢትዮጵያ ዞን 9 ድህረ-ገፅ ብሎገሮች በፈቃዱ ኃይሉ፣ ዘለዓለም ክብረት፣ማህሌት ፋንታሁን፣ አጥናፍ ብርሃኔ፣ አቤል ዋበላ እና ናትናኤል ፈለቀ በአካል ፍርድ ቤት የቀረቡ ሲሆን፤ 1ኛ ተከሳሽ ሶሊያና ሽመልስ በአካል ልትቀርብ ስላልቻለች በኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ጋዜጣ ጥሪ እንዲደረግ የተሰጠው ትዕዛዝ አቃቤ ህጉ ማስፈፀም ባለመቻሉ ዛሬ ክሳቸው ሊታይ ባለመቻሉ ፍርድ ቤቱ ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ሰጥቷል፡:

zonይህ በእንዲህ እንዳለ ተከላካይ ጠበቆች በአቃቤ ህግ የተመሰረተው ክስ የህገ መንግስት ጉዳይ ስለሆነ ፤ለህግ መንግስት አጣሪ ጉባዔ እንዲመራ፣አቃቤ ህግ ያቀረበው ክስ የህግ ስነስርዓቱን ባለመከተሉና ግልፅ ባለመሆኑ መቃወሚያ በማቅረብ ተከሳሾች በነፃ እንዲሰናበቱ አሊያም የዋስትና መብታቸው እንዲከበር በሚል ያቀረቡት ክርክር ከፍርድ ቤቱ መቅረፀ- ድምፅ ተገልብጦ አልቀረበም በሚል ፍርድ ቤቱ ብይን ሳይሰጥ ቀርቷል፡፡

ጉዳያቸው ክስ ሳይመሰረት ከ10 ወራት በላይ እንደፈጀ የሚነገርላቸውና እስካሁን ለህዝብ ይፋ ያልተደረገ የበርካታ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ጉዳይም በዕለቱ ችሎት ውሎ ነበር፡፡ በዚህም 8ቱ ከአዲስ አበባ ወደ ወልቂጤ፣ ያለፈው ጥቅምት 2006 ዓ.ም.ለአረፋ በዓል ሲሄዱ፣8ቱ ደግሞ አዲስ አበባ እያሉ በፀጥታ ኃይሎች ተይዘው በቁጥጥር ስር የዋሉት የነ ኤልያስ ከድር የክስ መዝገብ የሚገኙ 15 ወንዶችና አንዲት ሴት በአጠቃላይ 16 ወጣቶች ጉዳይ ለነሐሴ 5 ቀን 2006 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡
በተያያዘ ወቅት እንደታሰሩ የሚነገርላቸውና ከአዳማ 4 ወንድ እና አንዲት ሴት በአጠቃላይ 5 ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች በፀጥታ ኃሎች በቁጥጥር ስር የዋሉት ለነሐሴ 12 ቀን 2006 ዓ..ም. ተለዋጭ ቀነቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡ በዚህ ጉዳይ ከተከላካይ ጠበቃ በተለይም በአንድ ወንድ እና በአንዲት ሴት ተጠርጣሪ ላይ በማረሚያ ቤቱ አያያዝ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ተፈፅሟል በሚል ቅሬታ ቢቀርብም፤ ፍርድ ቤቱ በቀጠሮ ቀን መርምሮ ውሳኔ እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡ ፍርድ ቤቱም መቼ እንደሚጀመር ባይገልፅም ከነሐሴ 14 ቀን 2006 ዓ.ም. በኋላ ዝግ እንደሚሆን አስታውቋል፡፡

ኢትዮጵያ፣ ጅቡቲ እና ወደብ

ብስራት ወልደሚካኤል
Afrosonb@gmail.com

አንድ መንግስት ዛሬ በሚሰራው ሁሉ ነገንም ያስባል፤ኢትዮጵያ ግን ለዚህ የታደለች አትመስልም፡፡ ለዚህም አሁን በስልጣን ላይ ባለው ስርዓት ላለፉት 23 ዓመታት ከተከናወኑ በርካታ ዘመን እና ታሪክ አይሽሬ ስህተቶች መካከል የሰሞኑን የኢትዮጵያ እና ጅቡቲ ስምምነትን ማየት በቂ ነው፡፡ ስምምነቱ በየትኛውም ዓለም ያሉ ሀገሮች ያልተፈፀመ እና ሊፈፀም የማይችል በኢትዮጵያ ግን እውን ሆኗል፤እስካሁን ምክንያቱ በግልፅ ባይታወቅም፡፡

ገዥው ስርዓት ለህዝቡ ቃል የገባውን ላለመፈፀሙ በተደጋጋሚ ከሚገልፃቸው ቃላቶች እና ምክንያቶች መካከል የአፈፃፀም እንጂ የፖሊሲ ችግር የለብኝም የሚለው ነው፡፡ እውነታው ግን ከሚናገረው በተቃራኒ የፖሊሲ እና የአፈፃፀም ችግር ይስተዋልበታል፡፡ በመጀመሪያ ፖሊሲ ሲነደፍ የሀገሪቱን አቅም፣ ፍላጎት፣ ነባራዊ ሁኔታ፣ የህዝቡ ፍላጎትና አኗኗር እንዲሁም ዓለም አቀፍ ሁኔታን ከግምት በማስገባት የዜጎችን እነ የሀገሪቱን ቁሳዊና ስነልቦናዊ አዎንታዊ ውጤት ታስቦ የሚዘጋጅ የተግባር ሰነድ ነው፡፡ በርግጥ ፖሊሲን ከየትኛውም ሀገር መኮረጅ ይቻል ይሆናል፤ ነገር ግን ውጤታማነቱ የሚለካው የፖሊሲው ትግበራ አፈፃፀም ነው፡፡

ፖሊሲ በራሱ ከሌሎች የተለየ ሙያዊ ስነምግባር የሚጠይቅ በመሆኑ የአስፈፃሚውንም አካል አቅምና ብቃት እንዲሁም የፖለቲካ ቁርጠኝነት የሚፈተሽበት ነው፡፡ ስለሆነም የፖሊሲ ችግር የለም፤የአፈፃፀም እንጂ ሚባል ከሆነ ፖሊሲውን ሊያስፈፅም የሚችል ብቃት ያለው አካል የለም ማለት ነው፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ ችግሩን ለማረም ከሁለቱ አማራጮች አንዱን መውሰድ ግድ ይላል፡፡ ይህም ሚነደፈው ፖሊሲ ከገሪቱ አቅምና ፍላጎት ጋር ሳይሆን ከስራ አስፈፃሚው(ከገዥው ፓርቲ አመራሮች) አቅምና ብቃት ጋር በሚስማማ መልኩ መንደፍ፤ አሊያም ፖሊሲ የማስፈፀም ችግር አለብኝ ብሎ ያለው አካል ፖሊሲ የማስፈፀም አቅምና ብቃት ላለው አካል በሰላም ስልጣን መልቀቅ ብቸኛው መንገድ ነው፡፡ አለበለዚያ በፖሊሲ ንድፍና አፈፃፀም ችግር ምክንያት የሚፈጠሩ ችግሮችን በዘፈቀደ ወዲያው ለማረም መሞከር የበለጠ ሀገርን እና ትውልድን ሊያጠፋ የሚችል ከባድ ስህተት እንዲፈፀም በር ሊከፍት ይችላል፡፡

በተለይ የአንዲት ሀገር የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ተወደደም ተጠላ መሰረታዊ የሚባሉ ሶስት ነገሮችን ፖለቲካዊ፣ ማኀበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታን ታሳቢ በማድረግ የሁለትዮሽ ተጠቃሚነት ላይ መሰረት ያደረገ ነው፡፡ ይህም አንዲት ሀገር ፍላጎቷን፣መብትና ጥቅሟን ለማስፈፀም የምትንቀሳቀስባቸው በመሆኑ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ የሀገሪቱ ሁሉ-አቀፍ ፖሊሲ ግልባጭ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ለየት የሚያደርገው ፖሊሲው ከሀገር ውጭ ትኩረት ማድረጉ ብቻ ነው፡፡
dddበኢትዮጵያ እየተተገበረ ነው የሚባለው የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ በሐሳብ ደረጃ ከላይ ካለው በተቃራኒ ትኩረቱ ኢኮኖሚ ላይመሰረት ያደረገ ነው መባሉ ነው፡፡ ስለዚህ የትኛውም ዓለም ሀገርም ሆነ ዓለም አቀፍ ግንኙነት ሳይንስ ንድፈ ሐሳብና ትግበራ አንፃር እጅግ ጎዶሎ መሆኑን ያሳያል፡፡ ምክንያቱም ኢኮኖሚ በባህርይው ዛሬን እንጂ ነገን የማይል መሆኑ፣ስለአለውም ሆነ መጪው ጊዜ ፖለቲካዊና ማኀበራዊ ዓለም አቀፍ ሁኔታ እና ግንኙነት ቦታ በጥልቀት ከመገንዘብ ይልቅ ፋይናንስ ላይ የሚያተኩር ነውና፡፡ ከውጭ የሚገኝ የኢኮኖሚ ትብብር በራሱ ደግሞ ያለ ፖለቲካዊ ስራ እና ግንኙነት ሊሆን የማይችል ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ገዥው እና አስፈፃሚው ስርዓት አርቆ የማሰብም ሆነ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ምንነት ትርጓሜና ተግባር ላይ ምን ያህል የአቅምና የፖለቲካ ቁርጠኝነት ችግር እንዳለ አመላካች ነው፡፡ የዚህ ውጤት ደግሞ ሀገሪቱንም ሆነ ህዝቡን ለአላስፈላጊ ከፍተኛ መስዋዕትነት መዳረጉ አይቀርም፤ ዳርጓልም፡፡

በቅርቡ 90 ሚሊዮን ከሚሆነው የኢትዮጵያ ህዝብመካከል 4.5 ሚሊዮን የሚሆነው የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልልህዝብ ከራሱ የከርሰ ምድር103 ሺህ ሜትር ኪዩብ ውሃ 800 ሺህ ለሚሆነው የጅቡቲ ነዋሪ ንፁህ የመጠጥ ውሃ በኢትዮጵያ ወጭ ሊቀርብ ነው፡፡ ይህም እ.አ.አ ባለፈው መስከረም 3 ቀን 2012 ዓ.ም. ስምምነት ከተፈፀመ የሰነበተውን ለወጉ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባለፈው ግንቦት 26 ቀን 2006 ዓ.ም. መፅደቁ በብዙዎች ዘንድ አግራሞት ፈጥሯል፤ሊፈጥርም ይገባል፡፡ ምክንያቱም ጉዳዩ ለኢትዮጵያ የሚያስገኘው ፖለቲካዊ፣ ማኀበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጥቅም መኖሩን የሚያመላክት ነገር አለ ወይ የሚለውን ጥያቄ እስካሁን በደፈናው ፖለቲካዊ ጥቅም ከሚል በስተቀር ኢኮኖሚያዊ ጥቅም የለም መባሉ በራሱ፤ ስርዓት እከተለዋለሁ ከሚለው ኢኮኖሚያዊ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ጋር ይጋጫል፡፡

በርግጥ እንኳን ቀጥተኛ ትስስር ካላት ከጎረቤት ሀገር ጅቡቲ ቀርቶ ከማንኛውም የውጭ ሀገር መልካም ግንኙነትና ጉርብትና መፍጠር ጠቃሚም ተገቢም ነው፡፡ ይበልጥ ጠቀሜታ ሊኖረው የሚችለው ግን የሁለቱንም ሀገራት ከጥርጣሬ የፀዳ የጋራ ተጠቃሚነት ላይ መሰረት ካደረገ ብቻ ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ተለመደና ጤናማ ግንኙነትና ጉርብትና ነው፡፡ ከዚህ ውጭ የራስን ፖለቲካዊ፣ ተፈጥራዊና እና ኢኮኖሚያዊ ጥቅም አሳልፎ በመስጠት የሚመሰረት ወዳጅነት በሀገሮቹ መካከል የነበረውን ግንኙነት በማሻከር በጥርጣሬ እንዲመሰረት በማድረግ ያልታሰበ ችግር የመፍጠር አጋጣሚ ይኖረዋል፡፡እስኪ ሰሞኑን በኢትዮጵያ እና ጅቡቲ መካከል በተደረገው ስምምነት አለ የተባለው ፖለቲካዊ ጥቅምስ እውን አለን? የሚለውን እና ነገ በኢትዮጵያ ላይ የሚኖረውንፖለቲካዊ፣ማኀበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተፅዕኖ በአጭሩ እንመልከት፡፡

ፖለቲካዊ ፋይዳ

በሁለት ሉዓላዊ ሀገሮች መካከል የሚደረግ ማንኛውም ስምምነት ሁለቱንም የጋራ ተጠቃሚነት ታሳቢ ያደረገ ማንኛውም ስምምነት በቀዳሚነት ፖለቲካዊ ፋይዳው ነው የሚታየው፡፡ ጅቡቲ ከኢትዮጵያ የሶማሌ ክልል አካል አንዱ፤በድሬዳዋ እና ጅቡቲ አዋሳኝ ከሆነው ሽንሌ ዞን ለ30 ዓመታት በ100 ኪሎ ሜትር የድንበር ርቀት ያለውን 20 ሄክታር መሬት ጨምሮ 4ሺህ ሄክታር የከርሰ ምድር ውሃ ያለበትን የተፈጥሮ ሃብት በነፃ እንድታገኝ ተደርጓል፡፡ ይህም ጅቡቲ ለዓመታት ፈተና የሆነባትን የንፁህ ውሃ አገልግሎት ከኢትዮጵያ ያለምንም ውጭ ማግኘቷ ከወደብ ጋር በተያያዘ በፖለቲካው ያላትን የበላይነት የሚያመላክት ነው፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያ ከድህነት ወለል በታች ካሉ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎቿ በንፁህ የመጠጥ ውሃ አገልግሎት እጥረት እየተሰቃዩ ባሉበት ሰዓት ከ800 ሺህ ለማይበልጥ ጎረቤት ሀገር ሚዛናዊ ያልሆነ ወጪ እንድታደርግ አስገዳጅ ነገር መፍጠሯ እና እየፈጠረች መሆኗ ስምምነቱ አሉታዊ የፖለቲካ ፋይዳ እንዲኖረው አስችሏል፡፡

ሌላው የውሃ ቁፋሮው የሚካሄድበት የሽንሌ ዞን ነዋሪዎች እስካሁን ለ23 ዓመታት ንፁህ የመጠጥ ውሃ አገልግሎት በአግባቡ ሳያገኙ ዛሬ በአንድ ጊዜ ለጅቡቲ ህዝብ ጥቅም ሲባል ጭራሽ ነዋሪው እንዲፈናቀል መደረጉ በሶማሌ ክልልም ሆነ በሌላው ኢትዮጵያዊ ዘንድ ስርዓቱ የሀገርና የህዝብን ጥቅም የማስጠበቅ ፖለቲካዊ ቁርጠኝነቱ ጥያቄ ምልክት ውስጥ እንዲገባ ያደርገዋል፡፡ ይሄ ደግሞ በአካባቢው ሌላ ቅራኔ በመፍጠር በቀጠናው ለእስኩኑ በባሰ የፖለቲካ አለመረጋጋት የመፍጠር ዕድል ይኖረዋል፡፡ በርግጥ ገዥው ኢህአዴግ ፖለቲካዊ ጥቅም ይኖረዋል በሚል የጅቡቲ ወደብን በቀጣይነት በተረጋጋ ሁኔታ በዓመት እስከ 1 ቢሊዮን በሚጠጋ የአሜሪካን ዶላር ለመጠቀም ለመደለል ማሰቡ መጭውን ጊዜ ያለማገናዘቡን ከማመልከት በስተቀር በቀጣይ ጅቡቲ ውሳኔ ላይ ያን ያህል የጎላ ፖለቲካዊ ተፅዕኖ ይኖረዋል ተብሎ አይታሰብም፡፡ እዚህ ላይ ኢህአዴግ ያለህዝቡ ፈቃድ ላለፉት 23 ዓመታት የኢትዮጵያን ተፈጥሯዊና ታሪካዊ የሆነውን የአሰብ ወደብን በአሁኑ ለጅቡቲ የሀገሪቱን የተፈጥሮሃብት ከክፍያ ነፃ በሆነ መንገድ እንደሰጠ ያኔ ለኤርትራ መስጠቱ ያመጣውን አሉታዊ ተፅዕኖ ዛሬም መድገሙ ገዥዎቹ አሁንም ከስህተት ፖለቲካዊ ውሳኔ ለመማርዝግጁ አለመሆናቸውን ያሳያል፡፡

ሌላው ኢህአዴግ ህዝብ ሳይመክርበትና ሳይወያይበት እንዲሁም ሳይፈቅድ የሀገሪቱን መሬት ከነተፈጥሮ ሃብቱ በነፃ አሳልፎ መስጠቱ ነገ በሁለቱ ሀገሮች መካከል በሚኖረው ጉርብትና እና ወንድማማችነት መካከል ችግር መፍጠሩ አይቀርም፡፡ ምክንያቱም ነገ በኢትዮጵያ የፖለቲክ መንግስት ስርዓት ለውጥ ቢፈጠርና ይህ ስምምነት አዲስ በሚመሰረተው የመንግስት ቢሻር፤ ለኢትዮጵያ ሌላ አዲስ የጎረቤት ሀገር በጠላትነት የመፍጠር ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡ ምክንያቱም የተደረገው ስምምነት ሁለቱንም ሀገሮችና ህዝብ ተጠቃሚ ያደረገ ሚዛናኑን የጠበቀ ስምምነት አልተፈፀመምና፡፡ በርግጥ ኢህአዴግ በአንድ መነፅር ብቻ በመመልከት ለጅቡቲ የኃይል አቅርቦት መብራት እጅግ በቅናሽ ዋጋ ማቅረቡ እና ይህን ውሃ በነፃ መፍቀዱ በቀጣይ ለሚጠቀምበት የወደብ ኪራይ ማረጋጊያ እንደ ማታለያ ለመጠቀም አስቦ ሊሆን ይችላል፡፡ ይሄ ደግሞ ሌላው የዋህነትና ድፍረት ነው፡፡

ጅቡቲ በቀጠናው ካላት መልካዓ ምድራዊ ፖለቲካ አቀማመጥ አንፃር በአሁን ሰዓት ሁሉ ነገሯን በራሷ ትወስናለች ማለት ዘበት ነው፡፡ ቀጠናው በቀይባህርና እና ህንድ ውቅያኖስ ዓለም አቀፍ የንግድ መስመር ላይ እንደመገኘቷ፣ የቀጠናው ፖለቲካዊ አለመረጋጋት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ምዕራባውያንንም ሆነ እንደ ቻይና እና ኢራን ያሉ እስያ ሀገሮችንም መሳቧ እርግጥ ነው፡፡ በተለይ ፈረንሳይ እና አሜሪካ በቀጠናው ሽብርተኝነትን ለመዋጋት በሚል ከአረብ ሀገራት ለሚያጓጉዙት ግዙፍ የቶታል፣ሞቢል እና የመሳሰሉ የነዳጅ ኩባንያዎቻቸው ደህንነት ጅቡቲን በእጅ አዙር መጠበቅና መንከባከብ ስለማይቦዝኑ፤ኢትዮጵያ አሁን ባደረገቸውና ለወደፊቱም ለማድረግ ባሰበችው የማታለል ተግባር ፈረንሳይና አሜሪካንም ጭምር መሆኑን ልታጤን ይገባል፤ይህ ደግሞ የላጭን ልጅ ቅማል በላት ዓይነት ተረት መሆኑ ነው፡፡
ስለዚህ ሚዛኑን ያልጠበቀውና ነገን ታሳቢ ያላደረገው የጅቡቲ ብቻ ተጠቃሚነት የውጭ ጉዳይ ስምምነት ለኢትዮጵያ አሉታዊ የፖለቲካ ፋይዳ እንጂ ከአጭር ጊዜም ሆነ ከረጅም ጊዜ አኳያ ሲሰላ ትርጉም አልባ ይሆናል፡፡ ስለሆነም ስምምነቱ ሙሉ ለሙሉ ከመተግበሩ በፊት ውሃ የሚቆፈርበት ቦታ ግልፅና ገለልተኛ በሆነ አካል የአካባቢ ተፅዕኖ ግምገማ በማካሄድ ራስን ከአላስፈላጊ ፖለቲካዊ ኪሳራ ማዳኑ የተሸለ ነው፡፡

ማኀበራዊ ፋይዳ

እንደማዕከላዊ መረጃ ኤጀንሲ ከሆነ ከኢትዮጵያ በህዝብ ብዛት ከኦሮሞ እና አማራ ክልል ነዋሪ ቀጥሎ በ3ኛ ደረጃ የሚገኘው እና 4.5 ሚሊዮን ነዋሪ ያለው የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ህዝብ በቂ ንፁህ የመጠጥ ውሃ ሳያገኝራሷን ለቻለች ሉዓላዊ ጎረቤት ሀገር በኢትዮጵያ ወጪ መደረጉ ስርዓቱ ገዥነት ለጅቡቲ ነው ወይስ ለኢትዮጵያ ያስብላል፡፡ የሶማሌ ክልል ነዋሪ በ 5.6 እጥፍ ከጅቡቲ ህዝብ ይበልጣል፡፡ ይሁን እንጂ ኢህአዴግ መራሹ መንግስት እመራዋለሁ የሚለውን ህዝብ ፍላጎትና ፍጆታ ሳያሟላ፤በኢትዮጵያ ወጭ ለጅቡቲ ማኀበራዊ አገልግሎት የሚውል፤ ውሃ ከሚቆፈርበት የሶማሌ ክልል ሽንሌ ዞን ለድሬዳዋ እና ሐረር በቅርብ ርቀት ቢገኝም የሀብቱ ባለቤት የሆኑት የአከባቢው ኢትዮጵያውያን ነዋሪዎች በንፁህ የመጠጥ ውሃ አገልግሎት ችግር ሲሰቃዩ እስካሁን መፍትሄ ያላቸው የመንግስት አካል የለም፡፡

በአንፃሩ አዲስ አበባን ጨምሮ በአራቱም የሀገሪቱ አቅጣጫዎች ለሚገኙ ነዋሪዎችም ቢሆን ያለው የንፁህ የመጠጥ ውሃ አገልግሎት ችግር ከዕለት ወደ ዕለት እየተባባሰ ነው፡፡ በሌላ በኩል በመንግስት ይህን የማኀበራዊ አገልግሎት ችግር ለመፍታት ከቃላት ባለፈ በተግባር የተሰጠ መፍትሄ ሳይኖር በአሁን ወቅት የኢትዮጵያ አካል ላልሆነቸው ጅቡቲ አብዝቶ መጨነቅና ከድሃ ህዝብ ጉሮሮ በጀት ተነጥቆ መመደቡ ትልቅ የሞራል ኪሳራ ነው፡፡ ይህም የሚያሳየው የኢትዮጵያ መንግስት ለዜጎቹ ያለው ተቆርቋሪናትና ማኀራዊ አገልግሎት ያለው ተነሳሽነት ዝቅተኛ መሆኑን ነው፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ነገ የውሃ ጉድጓድ ቁፋሮውን ተከትሎ የሚፈናቀሉ ዜጎች ለማን ተጠቃሚነት በሚል ከቀያቸው ሊነሱ ነው? እኚህ ዜጎች የነሱ ችግር ሳይፈታ አላቂ የሆነውን የተፈጥሮ ሃብታቸውን ያለፈቃዳቸው ተነጥቀው ለተጨማሪ የማኀበራዊ ቀውስ መዳረጋቸው በጅቡቲና በአዋሳኝ ድንበር ባሉ ኢትዮጵያውን መካከል ቅሬታ መፍጠሩ አይቀርም፡፡ የዚህ ቅሬታ ደግሞ ወደ ግጭት በማምራት ለተጨማሪ ማበራዊ ቀውስ መዳረጉ ከወዲሁ መጤን ያለበት ጉዳይ ቢሆንም፤ በማን አለብኝነት ሊታለፍ መሆኑ ማጣፊያው የሚቸግር ሌላ መዘዝ ይዞ መምጣቱን ካለፉ ስህተቶች መማር ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያ በራሷ ወጭ ለጅቡቲ በነፃ በምትሰጠው የንፁህ የመጠጥ ውሃ አገልግሎት ሀገሪቱም ሆነች ዜጎቿ ከማኀበራዊዘርፍ ከሚያገኙት ጉዳት በስተቀር ምንም ጥቅም የለም፡፡

                    ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ

በስምምነቱ መሰረት ኢትዮጵያ ያላትን የተፈጥሮ ሃብት ከመስጠቷ በተጨማሪ ሌላ የፋይናንስ ወጪ ለማድረግ መፈራረሟ ሊላ የኢኮኖሚ ኪሳራን ያስከትላል፡፡ ይህ መደረጉ በራሱ ሀገሪቱ እከተለዋለሁ፤ እየተከተልኩ ነው የሚለው የኢኮኖሚ ተኮር የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ጋር በእጅጉ ይቃረናል፡፡ ምክንያቱም ሀገሪቱ በኢኮኖሚ ለተጨማሪ ኪሳራ ከመዳረጓ በስተቀር የሚያስገኝላት አንዳች ጥቅምም የለምና፡፡
ኢትዮጵያ ይህን በማድረጓም ጅቡቲ ለኢትዮጵያ እየሰጠች ባለችው የወደብ ኪራይ

ላይ ተጨማሪ ክፍያ እንዳትጠይቅ የሚከለክል ነገር እንኳ ባለመኖሩ፤ነገ በቅናሽ የቀረበላትን የመብራት ኃይል አገልግሎት እና የጫት ንግድ በነፃ ማግኘት አለብን የሚል ሌላ ኢኮኖሚያዊ ጥያቄንም ይዞ ሊመጣ ይችላል፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያ ሙሉ 90 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ኢትዮጵያ 800 ሺህ ባላት ጅቡቲ ላይ ጥገኛ መሆኗን ሳትገነዘብ አትቀርም፤በኢህአዴግ የስልጣን አገዛዝ ሌላ የተሻለ አማራጭ የላትምና፡፡

የመገርመው ኢትዮጵያ ለጅቡቲ ከፍተኛ የወደብ ኪራይ ከመክፈሏ በተጨማሪ ለኢትዮጵያውያን ያልተሰጠው ከክፍያ ነፃ የኢንቨስትመንት መሬት እና በወደቡ አካባቢ ተገነቡ ከፍተኛ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች በኢትዮጵያ ወጪ መከናወኑ ራሱ ሌላው ያልተመለሰ የኢኮኖሚ ኪሳራ ነው፡፡ ይሄ ደግሞ መቼም ከጅቡቲ ጋር ለሚኖረን ወዳጅነት ጥሩ መፍትሄ ሊሆን አይችልም፡፡ ምክንያቱም በዓለም አቀፍ ፖለቲካ ኢኮኖሚ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መሰረት ዘላቂ ወዳጅ እና ዘላቂ ጠላት የሚባል የለምና፡፡ ያውም የዓለም የፖለቲካ ስርዓት በፍጥነት እየተቀያየረ ባለበት ሰዓት፤ እንዲህ ዓይነት ውሳኔ መወሰን እና መስማማት አሁን ከወጣውና ሊወጣ ከታሰበው በወጪ በላይ ተጨማሪ የገንዘብ ኢኮኖሚ ጥያቄን ይዞ መምጣቱ የተገመተ አይመስልም፡፡

                መፍትሄ

የኢትዮጵያ መንግስት አሁን የተፈራረመው (የውሃ ጉድጓድ ቁፋሮው መጀመሩ ቢነገርም) ሙሉ ለሙሉ ተጋባራዊ ከመሆኑ በፊት የሚኖረውን ፖለቲካዊ፣ማበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ማጤን አለበት፡፡ ሌላው የሁለት ሀገሮችን ጠጋራ ተጠቃሚነት የማያረጋግጥ ማንኛውም ሰምምነት ነገ ማጣፊያው የሚቸግር ሌላ ችግር ማስከተሉ ከወዲሁ በመገንዘብ ወደ ዘላቂ መፍትሄ መሄዱ ብልህነት ነው፡፡ ለዚህም ኢህአዴግ ያኔ ያለ ህዝብ ፈቃድ ታሪካዊና ተፈጥሯዊ የሆነውን የባህር በር (አሰብ ወደብን) ራሱ አሳልፎ እንደሰጠ በማመን በዓለም አቀፍ ህግ መሰረት ለማስመለስ ግልፅ ውይይት እና ጥረት ማድረግ አለበት፡፡

ሌላው ከህግ አኳያ ስምምነቱ የህገ መንግስት ጥሰትም አለበት፡፡ እዚህ ላይ የሚያሳፍረው የሀገሪቱንና ህዝቧን ጥቅም በህግ ያስጠብቃሉ የተባሉት እንደራሴዎች በግልፅ ገዥ የሆነውን የሀገሪቱን ህግ ከአስፈፃሚው እኩል ጥሰው ስምምነቱን ማፅደቃቸው ነው፡፡ ይህም በህገመንግስቱ አንቀፅ 86(3) ላይ የውጭ ግንኙነት መርሆች በሚለው ስር “የሀገሪቱ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ በጋራ ጥቅምና በእኩልነት ላይ የተመሰረተ መሆኑን እንዲሁም በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚደረጉ ስምምነቶች የኢትዮጵያን ጥቅም የሚያስከብሩ መሆናቸውን ማረጋገጥ::” ይላል፡፡ ነገር ግን ስምምነቱ የማኀበራዊ እሴት መጠበቂያ የሆነው ህገ መንገስት በግልፅ በዚህ መልክ ተጥሶ የጅቡቲን ጥቅም ማስጠበቁን አስፈፃሚዎችም አልካዱትም፡፡ ይሁን እንጂ ፓርላማው ራሱ የህገመንግስት ጥሰትን በመፈፀም ተባባሪ መሆኑን አሳይቷል፡፡ ስለዚህ የፀደቀው አዋጅ ተፈፃሚ ከመሆኑ በፊት የሀገሪቱንም ሆነ የሁለቱን ሀገሮች የጋራ ጥቅም በሚያስጠብቅ መልኩ ሊሻሻል አሊያም ሊሻር ይገባዋል፡፡ አለበለዚያ ህግ ተርጓሚዎች እና አስከባሪዎች ጉዳዩን ወደ ህግ በመውሰድ ተገቢው እርምት እንዲወሰድ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

የገዥው ፓርቲ ወገንተኝነትን ትቶ የሀገሪቱን እና የህዝቡን ጥቅም ሊያስጠብቁ የሚችሉ ዓለም አቀፍ ኢትዮጵያውያን ዲፕሎማቶችን፣ የታሪክና የህግ ባለሙያዎችን፣ ሀገር ሽማግሌዎችን፣ የኃይማኖት አባቶችን እና ፖለቲከኞችን ያካተተ ግብረ ኃይል በማቋቋም ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩ የሚያዋጣ መንገድ ነው፡፡ ኢህአዴግ ይሄን ማድረግ ፍላጎትና አቅም የለኝም የሚል ከሆነ ስልጣኑን በፈቃዱ ለቆ ለሰላማዊ የስልጣን ሽግግር በር መክፈት አሊያም ሌሎች ኢትዮጵያውያን ተከታትለው እንዲያስፈፅሙ አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ የተሻለና የሰለጠነ አማራጭ መፍትሄ ነው፡፡ ለዚህም ሁሉም ዜጋና እና በቀጥታ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ትኩረት ሊሰጡት ይገባል፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ አሁን ካለው 90 ሚሊዮን ከአስርና ሃያ ዓመታት በኋላ ቁጥሩ በከፍተኛ ደረጃ ጨምሮ ከ120-150 ሚሊዮን ሲደርስ ችግሩ ከአሁኑ እጅግ የባሰ ይሆናል፡፡ ያኔ የጅቡቲን ወደብ በኪራይመጠቀም ቀርቶ፤ ጅቡቲ በፈቃዷ የኢትዮጵያ መንግስት አንዷ ፌደራላዊ አካል ብትሆን እንኳ ችግሩን መቅረፍ አይቻልም፡፡ ስለዚህ በየዓመቱ በተለያየ መንገድ የኢትዮጵያን ጥቅምና ፍላጎት ለጅቡቲ አሳልፎ እየሰጡ እሽሩሩ ማለቱ ለሌላ ተጨማሪ ችግር በር ከመክፈቱ በስተቀር ለአጭርም ሆነ ለረጅም ጊዜ መፍትሄ ሊሆን አይችልም፡፡

በተደጋጋሚ ተጨማሪ ወጭና ስጋት የማይፈጥር ዘላቂ መፍትው ግልፅና አጭር፤ያም ሀገሪቱ በህገ ወጥ መንገድ ያጣችውን ታሪካዊና ተፈጥሯዊ የሆነውን የአሰብ ወደብንማስመለስ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ እንደ ኬኒያ፣ ሶማሊ ላንድ እና ሱዳን ወደቡን በአማራጭነት ማሰቡ ደግሞ ከጅቡቲ የባሰ ፖለቲካዊ፣ ማኀበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር ይዞ መምጣቱ የማይቀር ስለሆነ፤መፍትሄው ኢትዮጵያ የራሷን የባህር በር በዓለም አቀፍ ህግ መሰረት በማስመለስ የወደብ ባለቤት መሆን ብቻ ነው፡፡

የደቡብ ሱዳን ቀውስ በቀጠናው ላይ ያለው ተፅዕኖ

Bisrat Woldemichael
afrosonb@gmail.com

ሱዳን በምስራቅ አፍሪካም ሆነ በአፍሪካ ካሉት ሰፊ ግዛቶች መካከል ቀዳሚዋ ነበረች፡፡ ሱዳን ለረጅም ጊዜ በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ስር የወደቀች ብትሆንም፤ ነፃነቷን ካገኘች በኋላ ግን የአረብ ሊግ አባል ሀገር ከመሆን በተጨማሪ በሼሪአ የእስልምና አስተምህሮ ህግ መተዳደር ጀመረች፡፡ ይሁን እንጂ በዜጎቿ መካከል እኩልነትንም ሆነ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል ማምጣት ባለመቻሏ ከ30 ዓመታት በላይ ለከፍተኛ የእርስ በርስ ግጭት ተዳርጋ መቆየቷ የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው፡፡

በተለይ ሱዳን የአረብ ሊግ አባል ሀገር እንደመሆኗ መጠን ኢትዮጵያን ከቀይ ባህር ማስወጣት እና ወደብ ማሳጣት ከየመን በስተቀር የግብፅና እና የሌሎች አረብ ሀገሮች የረጅም ጊዜ ዕቅድ እንድታስፈፅም ትልቅ ተልዕኮ ተሰጥቷት ነበር፡፡ በዚህም ተልዕኮ የኤርትራውን ህግአኤ (ሻዕብያ) እና የዛሬው ህወሓት/ኢህአዴግን ዋና ቢሮ በመከፍትና በተለያዩ የገንዘብና ቁሳቁስ በመደገፍ ሀገሪቱ እርስ በርስ እንድትታመስ ትልቅ ስራ ሰርታለች፡፡

ሱዳን ኢትዮጵያን ለመጉዳት እየወሰደች ያለችውን እርምጃ እንድታቆም እና እንደ ጥሩ ጎረቤት ሀገር በሰላም ተባብሮ መኖሩ እንደሚያዋጣ በቀድሞ የኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም ለሱዳን አመራሮች መልዕክት እና የቀጥታ ውይይት ተደረገ፡፡ ይሁን እንጂ ሱዳን ከአባይ ወንዝ ጋር በተያያዘ ግብፅ እና ሌሎች የአረብ ሀገሮች የሰጧትን ተልዕኮ በመደገፍ አጠናክራ ቀጠለችበት፡፡ በዚህም መንግስቱ ኃይለማርያምን ጨምሮ የወቅቱ የኢትዮጵያ መሪዎች ተደጋጋሚ ማሳሰቢያ እና ማስጠንቀቂያ ለሱዳን ከመስጠት አልቦዘኑም፤ ሱዳን ግን ቀጠለችበት፡፡
በድርጊቱ የተበሳጩት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም እና ሌሎች አመራሮቻቸው ለሱዳን የሚሆን አፀፋ ለመመለስ ተግባራዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ መውሰዱን የመጨረሻ አማራጭ አደረጉ፡፡ በዚህም በሱዳን ፈላጭ ቆራጭ የሆኑት እና እራሳቸውን አረብ ነን የሚሉት የሰሜን ሱዳን ተወላጆች በተፈጥሮ ሃብት የበለፀጉ የደቡብ ሱዳን ነዋሪዎችን መጨቆን እንደ ባህል መውሰዳቸው ለወቅቱ ኢትዮጵ መዎች እንደ አንድ የፖለቲካ ትርፍ ወሰዱት፡፡

sed በነዳጅና በሌሎች የተፈጥሮ ሃብት የበለፀጉት ደቡብ ሱዳኖች እንደ ሰሜኑ ሱዳን ከእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ነፃ ቢወጡም በራሳቸው ሰሜን ሱዳኖች የባሰ ባርነት ውስጥ መውደቃቸውን አምርረው የሚቃወሙ በዶ/ር ጆን ጋራንግ የሚመራ ጥቂት የደቡብ ሱዳን ተወካዮች ወደ ኢትዮጵያ የግብዣ ጥሪ ተደረገላቸው፡፡ በዚህም ከወቅቱ የኢትዮጵያ አመራሮች ጋር ባደረጉት ውይይት ልኡካኑ ከሰሜን ሱዳን በመለየት የመብቶቻቸውና የተፈጥሮ ሃብቶቻቸው ተጠቃሚ ለመሆን ትግል ማድረግ እንደሚፈልጉ አረጋገጡ፡፡ ኮሎኔል መንግስቱም ኢትዮጵያ ለየትኛው ጭቁን የአፍሪካም ሆነ የዓለም ህዝብ ኢትዮጵያ ድጋፍ ማድረግ የተለመደ በጎ ዓላማዋ ስለሆነ፤ እናንተንም አቅም በፈቀደ እንረዳችኋለን ሲሉ አረጋገጡላቸው፡፡

እነ ዶ/ር ጆን ጋራንግም ወዲያው ወደ ሱዳን እንደተመለሱ ደቡብ ሱዳንን ከሱዳን ለመለየት በሚደረገው ትግል ለመሳተፍ ፈቃደኛ ለሆኑ ደቡብ ሱዳኖች በምስጢር ጥሪ አደረጉ፡፡ እጅግ በሚገርም ሁኔታ ወዲያውኑ ከ100 ሺህ በላይ ፈቃደኛ የደቡብ ሱዳን ወጣት እና ጎልማሳ ወንዶች ፈቃደኛነታቸውን አረጋገጡ፡፡ ያኔ የዛሬዋ ደቡብ ሱዳን ከሱዳን የመለየቷ ጥንስስ እውን ሆነ፡፡ ከዚያም የደቡብ ሱዳን ንቅናቄን የሚመሩት ልኡካን በአዲስ መልክ አመራር እንዲመረት ከላደረጉ በኋላ የበላይ መሪ እንዲሆኑ ዶ/ር ጆን ጋራንግ ከሌሎች አመራሮች ጋር ተመርጠው ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ጀመሩ፡፡ በወቅቱ ወደ ትግሉ ለመግባት ፈቃደኛ እንደሆነ የተነገረላቸው 100 ሺህ ደቡብ ሱዳናውያንን ለማስታጠቅም ሆነ ለማሰማራት ምቹ ሁኔታም ሆነ የአቅርቦት ዝግጅት አልነበረም፡፡

ውጥናቸው እንዲሳካ የተለያዩ ሀገሮችን በተለይም ምዕራብ እና ምስራቅ አውሮፓ ሀገሮችን ከመማፀን ጎን ለጎን በቅድሚያ ቃል የገባችላቸው ኢትዮጵያን ተግባራዊ ድጋፍ ጠየቁ፤ ደቡብ ሱዳኖች፡፡ ኢትዮጵያም ለእሷ ሱዳንን ለመበቀል እና ጥሩ ወዳጅ የሆነች ጎረቤት ሀገርን ለመፍጠር በሚደረገው እንቅስቃሴ የራሷን አሻራ ለማኖር የገባችውን ቃል በመጠበቅ ከ80 ሺህ የማያንሱ የደቡብ ሱዳን የትግል አባላት በተለያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ስልጠና እና ሌላ ሙያዊ ድጋፍ ከነ አስተዳደራዊ ቢሮ ድጋፍ አደረገች፡፡ ይሄ ደግሞ ለደቡብ ሱዳኖች ያልተጠበቅ ትልቅ ስጦታ መሆኑን በማመን ለትግሉ ፈቃደኛ የሆኑት በጋምቤላ እና ቤኒሻንጉል (ያኔ ኢሉባቦር እና ወለጋ በሚባለው ክፍለ ሀገር) በኩል ገብተው አስፈላጊው ድጋፍ ተደረገላቸው፡፡

ሱዳንም የራሷን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች እንዲሉ፤ ኢትዮጵያ ለመጉዳት ብዙ ስትደክም ባልጠበቀችው ሁኔታ የደቡብ ሱዳን ተዋጊዎች ተጠናክረው ሲቀጥሉ፤ ሌሎች እንደ ዳርፉር፣ ደቡብ ኮርዶፋ እና ብሉ ናይል በሚባሉ አካባቢዎች በርካታ ታጣቂዎች ትግል በማድረግ ሱዳንን ቁም ስቅል አሳዩ፡፡ በዚህም ሱዳን ከስህተቷ ሳትማር ኢትዮጵኝ ለመገነጣጠል ለሚደክሙት ድጋፏን መስጠት ቀጠለች፡፡ ኢትዮጵያም አፀፋውን አጠናክራ ቀጠለች፡፡

በመጨረሻም የደቡብ ሱዳን የትግል መሪው ዶ/ር ጆን ጋራንግ በሱዳን በመሪዎች ቅንብር በአውሮፕላን ከሱዳን ወደ ኬንያ አቅጣጫ ሲጓዙ ቢገደሉም፤ ትግሉ ግን ለፍሬ በቅቶ ከ3 ዓመት በፊት ደቡብ ሱዳን የአፍሪካ እና የዓለማችን አዲስ ሀገር ሆና ብቅ አለች፡፡ በዚህም ኢትዮጵያን እንደ ሁለተኛ ቤታቸው ከመቁጠር በተጨማሪ አዲስ አበባ እና ምዕራብ ኢትዮጵያ የራሳቸው ያሁል በነፃነት ተንቀሳቅሰው ህልማቸውን እውን አደረጉ፡፡

ሱዳንም ኢትዮጵያን ከታሪካዊ እና ተፈጥሯዊ የባህር በር በተጨማሪ ልጆቿ ኤርትራውያንን ከነ ምድሯ እንድታጣ ለሰራችው ነዳጅን ጨምሮ በተፈጥሮ ሃብት የበለፀገችውን ደቡብ ሱዳንን በማጣት የሰሜን በረሃን ይዛ ቀርታለች፡፡ በዱብ ሱዳኖች የተጀመረው የትጥቅ ትግል አሁንም ሳያበቃ ዳርፉር፣ ደቡብ ኮርዶፋ እና ብሉ ናይል የተሰኙ ግዛቶቿም ከደቡብ ሱዳን መገንጠል በኋላ አሁንም ከሱዳን ለመገንጠል እየታገሉ ይገኛሉ፡፡ ይሁን እንጂ ደቡብ ሱዳን ህልሟ እውን ሆኖ ራሷን የቻለች ሀገር ብትሆንም፤ የተመኘችውን ሰላም እና የተፈጥሮ ሃብቷ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ስትደክም፤ የስልጣን ጥም እና ሙስና ባናወዛቸው መሪዎቿ ከ2 ዓመት በላይ ሰላም ልትሆን አልቻለችም፡፡
በአሁን ሰዓት ገና ነፃነቷን ከተጎናፀፈች 3 ዓመታት ያላለፋት ደቡብ ሱዳን በፕሬዘዳንቷ ሳልቫ ኪር እና በምክትላቸው ዶ/ር ሬክ ማቻር መካከል በተፈጠረ አለመግባባት ከአንድ ሺህ በላይ ዜጎቿ ህይወት ሲያልፍ፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ደግሞ ተሰደዋል፡፡ በተለይ ሱዳን ነፃነቷ ባወጀች በአመቷ በቢሊዮን የሚቆጠር የአሜሪካን ዶላር በመሪዎቿ ከሀገሪቱ ካዝና በሙስና መዘረፉን ተከትሎ ፕሬዘዳንቷ ሳልቫ ኪር ሌቦቹ አመራሮች የወሰዱት የሀገርና የህዝብ ገንዘብ በአስቸኳይ እንዲመልሱ ማስጠንቀቃቸው አልቀረም፡፡ ይሁን እንጂ የተመለሰው ከተወሰደው ረብ ያህል እንኳ እንዳልሆነ በመገንዘብ ሚኒስትሮቻቸውን እና ምክትላቸውን ሙሉ ከሙሉ ከስልጣን በማባረር የሚኒስትሮቹ ምክትሎች ለተወሰነ ጊዜ እንዲሰሩ ተደርጓል፡፡

ከሙስናው መዘዝ በተጨማሪ የስልጣን መቀናቀን እና ውክልና በማየሉ በፕሬዘዳንት ሳልቫ ኪር እና በምክትላቸው ዶ/ር ሬክ ማቻር መካከል ሰፊ ቅራኔ በመፈጠሩ፤ የተወሰኑ የሬክ ማቻር ደጋፊዎች ታሰሩ፡፡ ይሄም በሀገሪቱ የበለጠ ውጥረት በመፍጠሩ አለመግባባት ከግልሰቦች ይልቅ ወደ አመራሮቹ ጎሳ አመራ፡፡ በዚህም ፕሬዘዳንት ሳልቫ ኪር የወጡበት ዲንቃ ጎሳ እና ምክትላቸው ሬክ ማቻር የወጡበት ኑዌር ጎሳ መካከል ከፍተኛ የእርስ በርስ የጎሳ ግጭት ተከሰተ፡፡ በዚህም በርካታ ደቡብ ሱዳናውያን ህይወታቸው ሲያልፍ፣ ሌሎች በርካቶች ደግሞ ቆስለዋል፣ ሀገር ጥለውም ተሰደዋል፡፡

እስካሁን በይፋ ባይታወቅም ውስጥ ውስጡን ግን ኢትዮጵያ ውስጥ በስልጣን ያለው ኢህአዴግ ከግጭቱ ጀርባ ለኑዌር ተወላጁ ምክትል ፕሬዘዳንት ለነበሩት ሬክ ማቻር በተናጠል ድጋፍ እንደሚያደርግ መነገሩ ደግሞ ለቀጠናው አለመረጋጋት ትልቅ አስተዋፅዖ አድርጓል፡፡ በዚህም ፕሬዘዳንት ሳልቫ ኪር ሁለተኛ ቤታችን ከሚሏት ኢትዮጵያ ይልቅ ፊታቸውን ወደ ግብፅ በማድረግ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትራቸው አመካኝነት ደቡብ ሱዳን ከግብፅ ጋር የመከላከያ ጦር ስምምነት መፈራረማቸው ለኢትዮጵያ ትልቅ ስጋት መፍጠሩ አልቀረም፡፡ በተለይ በኢትዮጵያ በቋንቋ ዘር እና ጎሳ ከፋፍሎ የሚገዛው ኢህአዴግ ጎረቤት ሀገር ላይም ተመሳሳይ የተሳሳተ ‹ፖሊሲ መከተሉ ነገ ሀገሪቱን ትልቅ ዋጋ ሊያስከፍላት እንደሚችል ተገምቷል፡፡
በተለይ ኢትዮጵያ በአሁን ሰዓት የአባይ ወንዝን መገደቧ በግብፅ ዘንድ ከፍተኛ ተቃውሞና ጥርጣሬ ፈጥሮ ሳለ፤ የጎረቤት ሀገሮችን ማስቀየም ለግብፅ ጥሩ የፖለቲካ መጫወቻ መድረክ ሊፈጥር እንደሚችል የሰጉ አልታጡም፡፡ በተለይ የኢትዮጵያው ኢህአዴግ ለደቡብ ሱዳኑ የኑዌር ተወላጅ ለሆኑት ሪክ ማቻር ድጋፍ ያደርጋል ተብሎ የሚጠረጠረው፤ በሀገራችን ጋምቤላ በኑዌርና አኝዋክ መካከል ሆን ብሎ ግጭት በመፍጠር ሀገረ ውስጥ ኑዌሮች በአኝዋክ ጋምቤላዎች ላይ የበላይ እንዲሆኑ ማድረጉን በማውሳት የበለጠ ጥርጣሬው እንዲታመን አስችሎታል፡፡ በሌላ በኩል የለም! ኢህአዴግ ድጋፍ እያደረገ ያለው ለፕሬዘዳንቱ ጄነራል ሳልቫ ኪር ነው የሚሉም አልታጡም፤ ምንም እንኳ ጥርጣሬዎች በገሃድ የታዩ አሳማኝ እርምጃዎችን ዋቢ ያደረጉ ናቸው ባይባልም፡፡

sudaበቅርቡ በሳልቫ ኪር እና በሬክ ማቻር መካከል የተፈጠረውን ግጭት ለማርገብ ኢትዮጵያ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረገች መሆኑ ደግሞ ጥርጣሬው በጥርጣሬ እንዲታይ ማድረጉ አልቀረም፡፡ በዚህም ግጭቱ እንዲበርድ እና መፍትሄ እንዲያገኝ ሁለቱም ተቀናቃኞች በቅርቡ አዲስ አበባ ላይ የተኩስ አቁም ስምምነት ቢፈራረሙም ወዲያው ተግባራዊ አላደረጉም ነበር፡፡ በተለይ የአማፂዓኑ መሪ ዶ/ር ሪክ ማቻር እና ሳልቫ ኪር ስምምነቱን ጨርሰው ወዲያው ሀገራቸው እንደገቡ፤ ዶ/ር ሪክ ማቻር ስምምነቱን የፈረሙት የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ አስፈራርተውኝ ነው የሚል መግለጫ ለአንድ የኬንያ ሚዲያ ሰጥተዋል መባሉ፤ግጭቱ በዘላቂነት ሊበርድ እንደማይችል አመላካች ነው፡፡

በአሁን ወቅት በምስራቅ አፍሪካ ባለው የፖለቲካ አለመረጋጋት፣ የደቡብ ሱዳን ግጭት የሚቀጥል ከሆነ በተለይ ለኢትዮጵያ እጅግ ፈታኝ አሉታዊ ተፅዕኖ ይኖረዋል፡፡ ተፅዕኖው ግብፅ እና የኢህአዴግም ሆነ የኢትዮጵያ ተቀናቃኞች አጋጣሚውን በመጠቀም ኢትዮጵያ ውስጥ አለመረጋጋት ሊፈጠር እንደሚችል የፖለቲካ ተንታኞች ያስረዳሉ፡፡ ስለዚህ በስልጣን ላይ ያለው ኢህአዴግ የደቡብ ሱዳን ግጭት እንዲበርድ ለየትኛውም አካል መወገን እንደሌለበት እና ሁለቱም ተቀናቃኞች በመተማመን ላይ የተመሰረተና ተግባራዊ መሆን የሚችል የሰላም ስምምነት በመፈራረም ለቀጠናው ሰላም የበኩላቸው ሊወጡ እንደሚገባ ይመከራል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ምስራቅ አፍሪካ በሶማሊያ፣ በሱዳን እና በኢትዮጵያ ካሉት የእርስ በርስ ግጭቶች በተጨማሪ የደቡብ ሱዳን መጨመር በቀጣይ ለአህጉሪቱ አፍሪካም ሆነ ለቀጠናው ሀገሮች ፖለቲካዊ፣ኢኮኖሚያዊ፣ ማኀበራዊና አካባቢያዊ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩ አይቀሬ ነው፡፡

ዞን 9 ብሎገሮች ሌላ ቀጠሮ ተጠየቀባቸው፤ የፖሊስየ28 ተጨማሪ ቀናት ጥያቄ ውድቅ ተደርጓል

የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጠረጠርኳቸው ያላቸውን 9 ጋዜጠኞች እና ብሎገሮች ሚያዝያ 2006 ዓ.ም.ቢያስርም እስካሁን ምንም ዓይነት ህጋዊ ክስ ሳይመሰርት፤ ዛሬ ሰኔ 22 ቀን 2006ዓ.ም. በድጋሚ ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ጠይቋል፡፡ ፖሊስ ለፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ ቀጠሮ የነበራቸውን እና በማዕከላዊ ያሰራቸውን የዞን 9 ብሎገሮች መካከል በፍቃዱ ኃይሉ፣ ማህሌት ፋንታሁን እና አቤል ዋበላን ይዞ ቢቀርብም፤ እንደተለመደው የቴክኒክ ምርመራዬን አልጨረስኩም፣ ከተሰከሳሾች የተገኙ መረጃዎች ተተርጉመው አላለቁም፣…የሚሉ ምክንያቶችን በመጥቀስ ተጨማሪ የ28 ቀናት ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ እንዲሰጠው መጠየቁ ተሰምቷል፡፡

hgtፍርድ ቤቱ እስካሁን የተሰጠው ጊዜ በቂ ነው በማለት የተጠየቀውን የ28 ቀናት ውድቅ ቢያደርግም፤ ፖሊስ ምርመራው አጠናቆ እንዲቀርብ የ14 ቀናት ጊዜ በመስጠት ለሐምሌ 6 ቀን 2006ዓ.ም.ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ይሁን እንጂ ዕለቱ እሁድ ቀን የሚውል በመሆኑ እና መዝገቡ ከእንግዲህ በተዘዋዋሪ ተረኛ ዳኛ ሳይሆን በመደበኛ ችሎት መታየት ስላለበት ለሰኞ ሐምሌ 7 ቀን 2006 ዓ.ም. ከቀኑ 8፡00ሰዓት ተለዋጭ ቀነ ቀጠሮ መሰጠቱን ከተከላካይ ጠበቃቸው አቶ አምሃ መኮንን መረዳት ተችሏል፡፡ ጉዳዩ ሲታይ የነበረው ከሌሎች ቀናት በተለየ ዛሬ ቤተሰብም በችሎቱ ላይ እንዳይታደም ተከልክሏል፡፡

በፍርድ ቤቱ ግቢ በርካታ የእስረኞቹ ቤተሰቦች፣ ወዳጅ ዘመዶች፣ ዓለም አቀፍ ዲፕሎማቶች እና ጋዜጠኞች ቢገኙም አንዳቸውም ችሎቱን እንዲከታተሉ አልተፈቀደም ነበር፡፡ ፖሊስ ያሰራቸውን ተጠርጣሪዎች ይዞ ወደ ችሎት ሲገባ በፍርድ ቤቱ ግቢ ችሎቱን ለመታደም ከመጡት መካከል ዮናታን ተስፋዬ እና ምኞት የሚባሉ ወጣቶችን በሞባይል ፎቶ ለማንሳት ሞክራችኋል በሚል ወደ ማዕከላዊ ይዟቸው የሄዱ ሲሆን፤ ከሰዓታት በኋላ መለቀቃቸው ታውቋል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ እስካሁን ምንም ክስ ሳይመሰረትባቸው በእስር ላይ የሚገኙት ቀሪዎቹ 6ቱ ጋዜጠኞች እና ብሎገሮች የፊታችን ሐምሌ 5 ቀን 2006 ዓ.ም. ጠዋት ቀነ ቀጠሮ እንዳላቸው ይታወቃል፡፡