Monthly Archives: October, 2014

የዓለም ባንክ በቅርቡ ለኢትዮጵያ የሰጠው 600 ሚሊዮን ዶላር የገባበት አልታወቀም

በቅርቡ የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ 4ኛ ዙር የሴፍቲኔት መርሃ ግብር የሚውል 600 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር የሰጠው ብድር እስካሁን የገባበት አለመታወቁ ተሰማ፡፡ በተለይ የዓለም ባንክ ቦርድ ዋና ዳይሬክተሩ እ.አ.አ. መስከረም 30 ቀን 2014 ዓ.ም. የባንኩ ዓለም አቀፍ የልማት ማኀበር (IDA) ለኢትዮጵያ መንግስት ብድሩን መስጠቱን እና ሀገሪቱም በተፈቀደው ብድር ተጠቃሚ መሆኗን አረጋግጧል፡፡ ባንኩ ብድሩን የሰጠው 4ኛው ዙር የሴፍቲኔት መርሃ ግብር ውጤታማ ለማድረግ በሚል ሲሆን፤ ይህም በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ለሚኖሩ የሴፍቲኔትን ለማዳረስ፣ድርቅን ለመቋቋም የሚደረግ ስርዓትን ለማገዝ፣ የምግብ ዋስትና ላልተረጋገጠላቸው እና የገቢ መጠናቸው አነስተኛ የሆኑ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ታስቦ መሆኑን በመግለፅ፤ ባንኩ በቅርቡ እ.አ.አ መስከረም 30 ቀን 2014 ዓ.ም. በድህረ-ገፁ ላይ አስነብቧል፡፡

worldbank agreementባንኩ የሰጠውን ብድር አስመለክቶ የዓለም ባንክ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ዧንግ ዠ ቺን ቀደም ሲል በሀገሪቱ ይተገበር የነበረው የሴፍቲ ኔት መርሃ ግብር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና ዓለም አቀፉን የሚሊኒየሙን የልማት ግብ ለማገዝ ከሚደረገው ጥረት ውጭ የተራቆተ መሬትን መልሶ ማቋቋም አብሮ ተግባራዊ አለመደረጉን ገልፀዋል፡፡ ዳይሬክተሩ አሁን የተሰጠው 600 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር 10 ሚሊዮን የሚሆኑ የገጠር ነዋሪዎችን ተደራሽ በማድረግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ጎን ለጎን የተራቆተ መሬትን መልሶ ለማቋቋምም ታሳቢ መደረጉን ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት ጠቅላይ ሚኒስቴር አቶ ኃይለማርም ደሳለኝ ባለፈው ግንቦት 20 ቀን 2006 ዓ.ም. የኢህአዴግን 23ኛ ዓመት የድል በዓል አስመልክቶ ባደረጉት ንግግር ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናዋን አረጋግጣለች ሲሉ መናገራቸው አይዘነጋም፡፡ ይሁን እንጂ በአሁን ወቅት ከ10 ሚሊዮን የማያንሱ ኢትዮጵውን የምግብ ዋስትና ችግር ስለገጠማቸው ራሱ የኢትዮጵያ መንግስት በጠየቀው መሰረት የዓለም ባንክ የምግብ ዋስትናን ችግር ለመቅረፍ እንዲያግዝ የ600 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ብድር መሰጠቱን ባንኩ ይፋ አድርጓል፡፡

ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ መንግስት ገንዘብና ብድርን የሚመለከት ስምምነቶች በቀጥታ የሚመለከተው የገንዘብ፣ ኢኮኖሚና ልማት ሚኒስቴር የዓለም ባንክ የሰጠውን ብድር አስመልክቶ ለቀረበለት ጥያቄ ፤እንደማንኛውም ሰው ከሀገር ውስጥ ከዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ከመስማት ባለፈ የዓለም ባንክ ስለሰጠው የ600 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ብድር መንግስት የሚያውቀው ነገር እንደሌለ መናገሩን ድሬ ቲዩብ አስነብቧል፡፡ ይህ እስከተዘገበ ድረስ ባለፈው ወር መስከረም መጨረሻ 2007 ዓ.ም. የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ የሰጠው 600 ሚሊዮን ዶላር ብድር እስካሁን ያለበት አልታወቅም፡፡

የኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በአምስት ሺህ ብር ዋስ መለቀቁ ተሰማ

 

ቀደም ሲል መስከረም 23 ቀን 2007 ዓ.ም. ለምሳ ሲወጡ ቢሯቸው ታሽጎ ሰኞ መስከረም 26 ቀን 2007 ዓ.ም. የተከፈተው እና ለሰባት ሳምንታት ህትመቷ የተቋረጠው የኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጌታቸው ወርቁ በፌደራል የወንጀል ምርመራ ማዕከል ማዕከላዊ ፖሊስ ቃሉን እንዲሰጥ በተደረገለት ጥሪ መሰረት ማክሰኞ መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ማዕከላዊ መቅረቡ ታውቋል፡፡ ጋዜጠኛው ማዕከላዊ የተጠራው የቀድሞው መኢአድ አመራር የነበረው አቶ ማሙሸት አማረ ክስ መሰረት ቃሉን እንዲሰጥ የነበረ ቢሆንም፤ ማዕከላዊ ምርመራ ክፍልም የጋዜጠኛውን ቃል ከተቀበለ በኋላ ጉዳዩ አስፈላጊ ሲሆን እንደሚቀርብ በመጠቆም በ5,000.00 (አምስት ሺህ ) ብር ዋስ መለቀቁ ተጠቁሟል፡፡

Getachew workuኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ መንግስት በጋዜጠኞች፣ በመፅሔቶች እና ጋዜጦች ላይ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የሚወነጅል ዘጋቢ ፊልም በተደጋጋሚ መስራቱን ተከትሎ አታሚ ቤቶች የነፃ ጋዜጦችን እና መፅሔቶችን እንዳያትሙ በተለያዩ የመንግስት አካላት ጫና በማሳደሩ ለ7 ሳምንታት ከህትመት መቋረጧን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የጋዜጣው አዘጋጆች በተደጋጋሚ ስራውን አጠናቀው ቀድም ሲል የሚያትምላቸው አታሚ ድርጅትና ሌሎች አታሚዎች ጋር በተደጋጋሚ ቢኬድም እስካሁን ለማተም ፈቃደኛ እንዳልሆኑ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ መንግስት የነፃ መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞችን፣ ጋዜጦችን እና መፅሔቶችን በተደጋጋሚ መወንጀሉ እና መክሰሱን ተከትሎ የተለያዩ በርካታ ነፃ ጋዜጦችና መፅሔቶች ከህትምት እና አንባቢ ውጭ እንዲሆኑ መደረጉ ይታወቃል፡፡ ይህንንም ተከትሎ ከሚያዝያ 2006 ዓ.ም.  እስከ ነሐሴ 2006 ዓ.ም. መጨረሻ ድረስ ከ25 ያላነሱ የነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞች የግፍ እስርና ስቃዩን በመሸሽ መሰደዳቸው ይታወቃል፡፡ በአሁን ወቅት ኢትዮጵያ ውስጥ 3 የውጭ ዜጎችን ጨምሮ ከ17 ያላነሱ ጋዜጠኞች እና ብሎገሮች በግፍ ታስረው ይገኛሉ፡፡

 

 

 

 

 

 

 

የኢትዮ ምህዳር ጋዜጣ ቢሮ ታሸገ

ethi-mihedarየኢትዮ ምህዳር ጋዜጣ ዛሬ መስከረም 23 ቀን 2007 ዓ.ም ለምሳ ከቢሮ እንደወጡ መታሸጉን ዋና አዘጋጁ አቶ ጌታቸው ወርቁ ለፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል ገለጹ፡፡ እንደ አቶ ጌታቸው ገለፃ ህትመት ካቋረጥንበት ነሐሴ 14 ቀን ጀምሮ ወደ ተለያዩ ማተሚያ ቤቶች ሄደን ለማተም ጥረት ብናደርግም ሊሳካልን አልቻለም፡፡ ነገር ግን ከ2 ሳምንት በፊት ማተሚያ ቤት አግኝተን ዝግጅታችንን ካጠናቀቅን በኋላ ወደ ህትመት ልንገባ ስንል ፊውዝ ተቃጠለ በሚል ሰበብ ልትታተም አልቻለችም፡፡ አሁንም ወደ ሌላ ማተሚያ ቤት በመሄድ ለማተም ተስማምተው ዝግጅት በምናደርግበት ሰዓት ከማዕከላዊ ተደውሎ ትፈለጋላችሁ እንድትመጡ የሚል የስልክ መልዕክት እንደደረሳቸው አቶ ጌታቸው ገልጸው፣ ለምን እንደተፈለጉ ቢጠይቁም በስልክ አልነግርክም ማዕከላዊ ቢሮ ቁጥር 75 አቶ አለበል ብለህ እንድትመጣ እንደተባሉ እሳቸውም ሰኞ እንደሚመጡ ለደዋዩ እንደገለጹላቸው ነገር ግን በዛሬው ዕለት ለምሳ እንደወጡ ቢሮዋቸው እንደታሸገ ለፍኖተ ነፃነት ገልጸዋል፡፡

የፖለቲካ አመራሮቹ ችሎት ያለ ተከላካይ ጠበቃ ሲታይ፤ቀጣይ ቀጠሯቸው ግልፅ አይደለም

ዛሬ መስከረም 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ፒያሳ አራዳ በሚገኘው የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት የፖለቲካ  ፓርቲ አመራሮች ጉዳይ በዝግ ችከሎት ያለ ተከላካይ ጠበቃ ቀጠሮ መስጠቱ ተጠቆመ፡፡ የፖለቲካ አመራሮቹ አቶ ሀብታሙ አያሌው የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ፣ አቶ ዳንኤል ሺበሺ የአንድነት ፓርቲ ምክትል የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ፣ አቶ አብርሃ ደስታ የመቀሌ ዩኒቨርስቲ መምህርና የአረና ፓርቲ ምክትል የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ እንዲሁም አቶ የሺዋስ አሰፋ የሰማያዊ ፓርቲ ምክትል የምክር ቤቱ ሰብሳቢ ከተከላካይ ጠበቆቻቸው ጋር ሳይገናኙ ከቀጠሮ ሰዓታቸው አርፍደው ከቀኑ 10 እና 11 ሰዓት ፍርድ ቤት መቅረባቸውን ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡

detained politiciansበነበረው የፍርድ ቤት ችሎት ተከላካይ ጠበቃ ደንበኞቻቸውን ህጉ በሚፈቅደው መሰረት በማዕከላዊ ሄደው መጎብኘትና መነጋገር ቢፈልጉም፤ በፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ማዕከል “ማዕከላዊ” ፖሊስ ስላልተፈቀደላቸው ፍርድ ቤት መገኘቱ ለፕሮፖጋንዳ ካልሆነ ከህግ አግባብ ትርጉም ስለሌለው እንደማይገኙ አስቀድመው ማሳወቃቸው ተጠቁሟል፡፡ በችሎትም ቤተሰብ፣ ጋዜጠኛ፣ ዲፕሎማቶች እና ወዳጅ ዘመድ እንዳይከታተል መከልከሉም ታውቋል፡፡ የእስረኞቹ ቀጣይ ቀጠሮ መቼ እንደሆነ እስካሁን ከፍርድ ቤቱ ማግኘት ባይቻልም፤ እንደ ነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ ከሆነ የማዕከላዊ ምርመራ ኃላፊ አቶ ተክላይ ሹመት ተጠርጣሪዎቹ የተቀጠሩት ለጥቅምት 20 ቀን 2007 ዓ.ም. ሲሉ፤ ሌላ ፖሊስ ደግሞ ለጥቅምት 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ነው የሚል ጥቆማ መስጠታቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ እስረኞቹ እስካሁን በነበረው ምርመራ ፖሊስ ምንም ዓይነት ለወንጀል ክስ የሚያበቃ መረጃ ባለማግኘቱ፤ ወደ ኃይል እርምጃ በመሄድ ፖሊስ የሚፈልገውን ቃል እስረኞቹ ያልፈፀሙትን አስገድዶ የእምነት ቃል እንዳስፈረማቸው የማዕከላዊ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ ይሄም ለህዝቡና ለመገናኛ ብዙኃን እንዳይገለፅና ፍርድ ቤትም በቅሬታ መልክ እንዳይቀርብ ስለተፈለገ ነው ተከላካይ ጠበቆቹ እንዳይጎበኙ የተከለከሉት ሲሉ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡  በዚህም የዛሬው ችሎት ያለጠበቃ ጭምር በዝግ ችሎት መካሄዱ የተጠቆመ ሲሆን፤ የቀጠሯቸው ቀንም ከላይ ከተጠቀሰው ውጭ እስካሁን ትክክለኛውን ከፍርድ ቤቱ ማረጋገጥ እንዳልተቻለ መረጃዎእ አመልክተዋል፡፡ ችሎቱን ለመታደም ወደ ስፍራው ያቀኑ ሰዎችም ፍርድ ቤቱ ግቢ ሲገቡ ከወትሮ በተለየ በፖሊሶች ከፍተኛ ፍተሻ፣ እንግልትና ወከባ እንደተፈፀመባቸው  የዓይን እማኞች ገልፀዋል፡፡