Daily Archives: January 25th, 2015

አዲስ አበባ በሚገኝ ትምህርት ቤት አጥር በመደርመሱ ከተጎዱት መካከል የአንዲት ተማሪ ህይወት አለፈ

በአደጋው ህይወቷ ያለፈው ተማሪ ፅዮን ንጉሴ

በአደጋው ህይወቷ ያለፈው ተማሪ ፅዮን ንጉሴ

ባለፈው ሳምንት በአዲስ አበባ ሳሪስ አካባቢ በሚገኘው ፍሬህይወት አጠቃላይ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አጠገብ ከባቡር መንገድ ስራ ጋር በተያያዘ በተደረገ ቁፋሮ የትምህርት ቤቱ አጥር ተደርምሶ 11 ተማሪዎች ላይ ጉዳት አድርሶ የነበረ ሲሆን፤ ከተጎዱት መካከል ተማሪ ፅዮን ንጉሴ ሆስፒታል ውስጥ የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላት በደረሰባት ከባድ ጉዳት ምክንያት ህይወቷ ማለፉ ተሰምቷል፡፡ የተማሪ ፅዮን ንጉሴ የቀብር ስነስርዓትም ዛሬ ሳሪስ አካባቢ በሚገኘው ብሔረ ፅጌ ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን መፈፀሙን የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡

የትምህርት ቤቱ አጥር የተደረመሰው ቻይናዎች ጥንቃቄ በጎደለው መልኩ አጥሩ ጥግ ቁፋሮ በሚያደርጉበት ወቅት ተማሪዎች ዕረፍት ላይ ስለነበሩ አንዳንዶቹ ሲጫወቱ ሌሎች ደግሞ በአጥሩ ጥቅ ሲያጠኑ አደጋው መድረሱን በወቅቱ የነበሩ የዓይን እማኞች ተናግራዋል፡፡ በወቅቱ በቻይናዎቹ ድርጊት የተበሳጩ ተማሪዎቹ ቁጣቸውን ሲገልፁ በስፍራው በነበሩ ቻይናዎችና የአዲስ አበባ ፖሊሶች በርካታ ተማሪዎች መደብደባቸውም ተጠቁሟል፡፡ ስለተፈጠረው አደጋም ሆነ ስለተማሪዎቹ ጉዳት የመንግስት አካላት እስካሁን ምንም ያሉት ነገር የለም፡፡

ሁለት ታዋቂ የአውሮፓ ኩባንያዎች በኦሞ ሸለቆ ጥጥ የተሠሩ ምርቶች አንገዛም አሉ

ዮሐንስ አንበርብር

 ታዋቂዎቹ የአውሮፓ ጨርቃ ጨርቅ ኩባንያዎች የጀርመኑ ቼቦና የስዊድኑ ኤችኤንድኤም በኢትዮጵያ ኦሞ ሸለቆ ውስጥ የተመረተ የጥጥ ምርትን የሚጠቀም የጨርቃ ጨርቅ ምርቶች እንደማይገዙ መግለጻቸው ተሰማ፡፡

omo1

 የኢትዮጵያን የልማት እንቅስቃሴ ለመገደብና ጥላሸት ለመቀባት የሚደረግ የሰብዓዊ መብት አቀንቃኞች ዘመቻ መሆኑን፣ የኢትዮጵያ ጨርቃ ጨርቅ ልማት ኢንስቲትዩት በመግለጽ አጣጥሎታል፡፡

ሁለቱ ታዋቂ የጨርቃ ጨርቅ ኩባንያዎች በበርካታ የዓለም አገሮች ሰፊ ቅርንጫፍ መደብሮች እንዳሏቸው የሚታወቅ ሲሆን፣ በኦሞ ሸለቆ ከሚመረት ጥጥ ጋር ግንኙነት እንደሌላቸው ማሳወቅ የጀመሩት ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የምዕራብ የሰብዓዊ መብት አቀንቃኝ ተቋማት የኦሞ ሸለቆ ነዋሪዎች ከመሬታቸው በመንግሥት እንዲፈናቀሉ ተደርገው መሬቱ ለጥጥ ምርት መዋሉ፣ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ነው በሚል ባናፈሱት መረጃ ነው፡፡ ሁለቱ ታዋቂ ኩባንያዎች ደግሞ የሰው ልጆችን ሰብዓዊ መብትና የአካባቢ ጥበቃ እንደሚያስከብሩ የሚያሳውቁ በመሆናቸው ነው፡፡

ኩባንያዎቹ ከሁለት ዓመት በፊት ቢሯቸውን በአዲስ አበባ ከፍተው በኢትዮጵያ ጨርቃ ጨርቅ ኩባንያዎች የተመረቱ ጨርቆችን በጥሩ ዋጋ መግዛት መጀመራቸው ይታወሳል፡፡ በመጀመርያ የጀርመኑ ኩባንያ ቼቦ ነው በኦሞ ሸለቆ የሚመረት የጥጥ ምርቶች መቀበል ማቆሙን የገለጸው፡፡ በዚህ ሳምንት ኤኮ ቴክስታይል በተባለው ድረ ገጽ በጉዳዩ ላይ መረጃ የሰጠው ኤችኤንድኤም መሬት መቀራመትን (ላንድ ግራቢንግ) እንደ ሰብዓዊ መብት ጥሰት ስለሚወስድ እንደሚቃወም ገልጿል፡፡ ድርጊቱ በተጨማሪም የተባበሩት መንግሥታትን የሰብዓዊ መብት መርህና የኤችኤንድኤም ድርጅትን የሰብዓዊ መብት ፖሊሲ እንደሚጥስ አክሏል፡፡ በመሆኑም በዋናነት የጨርቃ ጨርቅ ምርት ለሚያቀርብለት የቱርኩ አይካ አዲስ በዚህ አካባቢ የተመረተ ጥጥ ተጠቅሞ የሚያመርተውን ጨርቅ እንዳያቀርብለት ማሳወቁን ገልጿል፡፡

Cotton field near Weita. Omo Valley. Ethiopia.

የኢትዮጵያ ጨርቃ ጨርቅ ልማት ኢንስቲትዩት ጨርቃ ጨርቅ ኩባንያዎችንና ልማቱን የሚደግፍ፣ ገበያና አዲስ ቴክኖሎጂዎችን ወደ አገር የሚያቀርብ የመንግሥት ተቋም ነው፡፡ የተቋሙ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ባንተይሁን ገሠሠ በጉዳዩ ላይ ተጠይቀው፣ የዚህ ዓይነቱ ዘመቻ የሰብዓዊ መብት አቀንቃኝ ነን ባዮች ተግባር መሆኑን ጠቅሰው፣ የጥጥ ልማት በሚከናወንበት አካባቢ መንግሥት እንኳን ሰው ሊያፈናቅል ቀርቶ እያሰባሰበ የልማት ተጠቃሚ እያደረገ ነው ብለዋል፡፡

በአካባቢው በጣም ጥቂት አርብቶ አደሮች ብቻ የሚኖሩበት ለእርሻ የሚመች በጣም ግዙፍ መሬት መኖሩን የጠቀሱት ኃላፊው፣ ‹‹አርብቶ አደሮቹ ሳር ካለ በአካባቢው ይቆያሉ፡፡ ከሌለ አካባቢውን ለቀው ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ከዚህ ውጪ ሰው ያልሠፈረበት አካባቢ ነው፤›› ብለዋል፡፡ አርብቶ አደሮቹ በአካባቢው ረግተው እንዲቆዩና ቋሚ የእርሻ መሬት ማረስ እንዲለምዱ መንግሥት እያስተባበረ እንደሚገኝና በአሁኑ ወቅትም 80 ሔክታር መሬት ላይ አርብቶ አደሮቹን በማስለመድ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

ለጥጥ እርሻ የተዘጋጀ 116,859 ሔክታር መሬት በአካባቢው በአሁኑ ወቅት መኖሩንና ከዚህ ውስጥ የለማው 70,867 ሔክታር ብቻ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በአካባቢው ጥጥ በማምረት ላይ የሚገኙ 22 ኩባንያዎች መኖራቸውንና በአሁኑ ወቅት ከተዘጋጀው 116 ሺሕ ሔክታር መሬት በላይ ማስተናገድ እንደሚችልም ጠቁመዋል፡፡ ‹‹የሰብዓዊ መብት አቀንቃኞቹን ዘመቻ መንግሥትም፣ እኛም፣ ኤችኤንድኤምና ቼቦም ያውቁታል፡፡ እኔ እስከማውቀው ድረስ አሁንም እነዚህ ኩባንያዎች ከኢትዮጵያ እየገዙ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ጉዳዩን በተመለከተ የአይካ አዲስ የሥራ ኃላፊዎች ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆናቸውን ጨምሮ ሪፖርተር ጋዜጣ ዘግቧል፡፡

አንድነት ፓርቲ የምርጫ ቦርድን እና የኢህአዴግን ህገወጥ አሰራር አሰራር ለመቃወም በተጠራው ሰልፍ በርካታ ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል

እሁድ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. አንድነት ፓርቲ በጠራው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ አዲስ አበባ ላይ በፖሊስ ድብደባ ድብደባ ከ26 በላይ ሰዎች ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡

የሰላማዊ ሰልፉ ጅማሮና ፖሊስ ለድብደባ ሲሄድ የሚያሳይ እና በፖሊስ ድብደባው ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች በከፊል፡-

ud

udj8

udj demon1

udj4

ujd

udj2

udj11

udj9

udj12

udj7

meski

“የስርዓቱን አረመኔያዊ እርምጃ እናወግዛለን!”- የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ጥምረት

በተቃውሞ ሰልፉ በአንድነት ፓርቲ አመራርና አባላት እንዲሁም ሌሎች ዜጎች ላይ በፖሊስ የተፈፀመውን ድብደባ የ9ኙ ትብብር ፓርቲዎች ጥምረት አውግዟል፡፡ የ9ኙ የትብብር ፖለቲካ ድርጅት መኢአድ፣ሰማያዊ፣የኦሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት፣ የከንባታ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅትና ሌሎች አባላትን ያቀፈ የፖለቲካ ጥምረት ድብደባውን በፅኑ አውግዟል፡፡ ሙሉ መግለጫውን ከዚህ በታች ይገኛሉ፡-

pressrelease

የስርዓቱን አረመኔያዊ እርምጃ እናወግዛለን!

9 ፓርቲዎች ትብብር የተሰጠ መግለጫ

የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር አብሮ ስለመስራትና ሌሎቹም ትብብሩን እንዲቀላቀሉ በየጊዜው የሚወተውተው አገራችን በዚህ ዘመን በማይመጥን አምባገነንና የጭካኔ ስርዓት ውስጥ የምትገኝ መሆኑን በመረዳቱ ነው፡፡ ይህ የህወሓት/ኢህአዴግ አምባገነንና ጨካኝ ስርዓት ህዳሩ 27/28 2007 ዓ.ም የአዳር ሰላማዊ ሰልፍ ላይ በወጡት አመራሮቻችን፣ አባላቶቻችን፣ ደጋፊዎቻችንና በየጎዳናው የተገኙት ንፁሃን ላይ ከፍተኛ ድብደባና የጅምላ እስር በመፈፀም ስርዓቱን ለመታገል የተነሳነበትን አላማ ትክክለኝነት አረጋግጦልናል፡፡

በዛሬው ዕለትም ገዥው ፓርቲ በፓርቲያቸው የውስጥ ጉዳይ ገብቶ የሚፈፅመውን ደባ፣ ምርጫ ቦርድንና የህዝብ ሚዲያን ተጠቅሞ ፓርቲውን ለመከፋፈልና አሳንሶ ለማሳየት የሚያደርገውን እኩይ ተግባር በመቃወም ሰልፍ የወጡ የአንድነት አመራሮች፣ አባላት፣ ደጋፊዎችና የፓርቲው ጽ/ቤት ፊት ለፊት የሚገኘው ቤተ ክርስትያን አካባቢ የነበሩ አዛውንት ምዕመናንን ሳይቀር በመደብደብ ጭካኔውን ዳግመኛ አሳይቶናል፡፡ ፖሊስ በትዕዛዝ በአንድነት አባላት ላይ ከፍተኛ የጭካኔ እርምጃ ወስዷል፡፡ አብዛኛዎቹንም በጅምላ አስሯል፡፡

ስርዓቱ በእነዚህ ሰላማዊ ዜጎች ላይ አሁንም የጭካኔ እርምጃውን መድገሙ ስልጣኑን የማጣት ከፍተኛ ስጋት ውስጥ እንዳለ እና ከይስሙላ ያለፈ ለሰላማዊ ትግሉ ዝግጁ አለመሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ ትብብራችን የስርዓቱን ጨካኝነት እያወቁም ቢሆን በሰላማዊ መንገድ ጥያቄያቸውን ለማቅረብ በስርዓቱ የማይከበረውን ህገ መንግስታዊ መርህ ተከትለው ሰልፍ ለወጡ ቆራጥ የአንድነት አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች አድናቆቱን መግለጽ ይወዳል፡፡ መስዋዕትነታችሁ ለነገ ድላችን ስንቅ በመሆኑ ይበልጡን ተጠናክራችሁ በጋራ ትግላችን እንደምናጠናክርም እምነታችን ነው፡፡

በተቃራኒው ገዥው ፓርቲ ህግ የማክበርና የማስከበር ሚናውን ረስቶ ፖሊስ፣ ደህንነትንና ሌሎች ተቋማትን ለራሱ ስልጣን ማስጠበቂያ በማዋል በአንድነት አመራሮች፣ አባላት፣ ደጋፊዎች ላይ የፈፀመውን ለዘመኑ የማይመጥንና በሰላማዊ መንገድ መብታቸውን ለጠየቁት ኢትዮጵያውያንም የማይገባ የጭካኔ እርምጃ በጥብቅ እናወግዛለን፡፡

ኢትዮጵያውያንን የማስተዳደር አቅምና ሞራል ያጣው ገዥው ፓርቲ የዜጎችን ጥያቄ በኃይል ማዳፈን የማይቻል መሆኑንና አገራችን ወደባሰ ችግር እንደሚከታት ተረድቶ ከዚህ የጭካኔ እርምጃው እንዲቆጠብ፣ እርምጃውን የወሰዱትን አካላት በህግ ተጠያቂ እንዲሆኑና የታሰሩትን በአስቸኳይ እንዲፈታ እናሳስባለን፡፡ ፖሊስ፣ ደህንነት፣ መከላከያና ሌሎች ተቋማት ገዥው ፓርቲ አላፊ መሆኑን በመገንዘብና ከገዥው ፓርቲ ታዛዥነት በመውጣት ወገኖቻቸሁ ላይ እንዲህ አይነት የጭካኔና አሳፋሪ እርምጃ ከመውሰድ ተቆጥባችሁ ከህዝብ ጎን እንድትቆሙ ጥሪያችን እናቀርባለን፡፡

ያለ መስዋዕትነት ድል የለም!

ጥር 17/2007 ዓ.ም

አዲስ አበባ

አንድነት ፓርቲ የጠራው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ በፖሊስ ድብደባ ሲጠናቀቅ፤በርካታ ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል

-“የፍትህና የነፃነት ጥያቄያችን ደም በማፍሰስ አይቀለበስም!”- አንድነት

-በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞችም ተከታታይ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች እንዲቀጥሉ ተወስኗል

ud

 አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዛሬ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ አራት የክልል ከተሞች የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ በፖሊስ ድብደባ ተጠናቀቀ፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ የነበረው የተቃውሞ ሰልፍ መነሻውን ቀበና ከሚገኘው የፓርቲው ዋና ጽህፈት ቤት በማድረግ መዳረሻውን ጥቁር አንበሳ አካባቢ በሚገኘው ኢትዮ-ኩባ አደባባይ ሲንቀሳቀስ የነበረው ሰልፍ በፅህፈት ቤቱ አካባቢ በተፈፀመ የፖሊስ ድብደባና እገታ ሊቋረጥ ችሏል፡፡

udj demon1

የተቃውሞ ሰልፉ ዋነኛ ዓላማም ምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ አንድነት ወደ ምርጫው መግባቱን በመወሰን በመላ ሀገሪቱ ከ450 በላይ ዕጩዎቹን ማቅረቡን ይፋ ማድረጉን ተክትሎ ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ፓርቲው ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ በሚል ፓርቲውን ከምርጫ ውድድር ለማስወጣት የሚደረገውን ተግባር ለመቃወም መሆኑን ቀደም ሲል ይፋ ማድረጉ ይታወቃል፡፡ ከተጠቀሰው ዓላመ በተጨማሪ በዜጎች ላይ የሚደርስ ህገወጥ እና የግፍ እስር እንዲቆም፣ የታሰሩ የህሊና እስረኞች እንዲፈጡ፣ ነፃና ገለልተኛ ምርጫ ቦርድ እንዲኖር፣…የሚሉ ጥያቄዎች ይገኙበታል፡፡

udj8

መረጃዎች ከስፍራው እንደጠቆሙት ከሆነ፤ የተቃውሞ ሰልፉ ቀበና ከሚገኘው የአንድነት ፓርቲ ጽ/ቤት የተነሳው ከ 150 በላይ የሚሆን ሰልፈኛ ከጽህፈት ቤቱ 100 ሜትር ርቀት ላይ ከሚጠብቁ ከ500 በላይ ሰልፈኞች ጋር ከመቀላቀላቀላቸው አስቀድሞ ፖሊሶች ቆርጠው በመግባት ከባድ ድብደባ አድርሰዋል፡፡ አራት ኪሎ፣ በፒያሳና የሰልፉ ማጠናቀቂያ በሆነው ኢቲዮ -ኩባ አደባባይ ይጠባበቅ የነበረው ሰልፈኛ ሊበተን መቻሉንም ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

ujd

በተፈፀመው የፖሊስ ድብደባም ከ26 በላይ የፓርቲው አባላትና አመራሮች ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን፤ ከሰልፉ ጋር ምንም ንክኪ ያልነበራቸውና ቀበና መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን የነበሩ የ70 ዓመት አዛውንትም ከፍተና ጉዳት ደርሶባቸው በአቅራቢያው በሚገኝ የጤና ተቋም የህክምና ዕርዳታ ሲደረግላቸው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት በክልል ከተደረጉት የተቃውሞ ሰልፎች መካከል ፓርቲው በደብረማርቆስ፣ በሸዋሮቢት እና በጋሞጎፋ ከምባ የተሳካ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መደረጉ ተጠቁሟል፡፡

በአዲስ አበባው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጉዳት ከደረሰባቸው የአንድነት አባላት መካከል የሚሊዮኖች ድምፅ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ስለሺ ሐጎስና የፓርቲው ኦዲትና ኢንስፔክሽን ኃላፊ ዳግማዊ ተሰማ ከፍተኛ ጉዳት ስለደረሰባቸው ራሳቸውን ስተው እንደነበርና ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው እንደነበር የዓይን እማኞች ከስፍራው አስታውቀዋል፡፡ በተመሳሳይም ……የተባሉ ነፍሰጡር በፖሊስ ድብደባ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው የተጠቆመ ሲሆን፤በፖሊስ ድብደባ ከተፈፀመባቸውና ጉዳት ከደረሰባቸው የፓርቲው ስራ አስፈፃሚና አባላት መካከል፡-

  1. አቶ አስራት አብርሃም (የህዝብ ግንኙነት ተጠባባቂ ሃላፊ)
    2. አቶ ዳንኤል ተፈራ (የውጭ ጉዳይ ሃላፊ)
    3. አቶ ብሩ ብርመጅ (የፖለቲካ ጉዳይ ሃላፊ)
    4. አቶ ፀጋየ አላምረው (ምክትል አፈ-ጉባኤ)
    5. አቶ አሻግሬ መሸሻ (የሰሜን ቀጠና ሃላፊ)
    6. አቶ ሰለሞን ስዩም (የኤዲቶሪያል ቦርድ ሰብሳቢ)
    7. ወ/ት ልዕልና ጉግሳ (የም/ቤት አባል)
    8. አቶ ዳግማዊ ተሰማ (የም/ቤት አባል)
    9. ጋዜጠኛ ስለሺ ሀጎስ (የም/ቤት አባል)
    10. አቶ ስንታየሁ ቸኮል (የአዲስ አበባ የወጣቶች ጉዳይ ሃላፊ)
    11. አቶ አሸናፊ አሳምረው (የወረዳ አመራር)
    12. አቶ ኢሳያስ ቱሉ (አባል)
    13. ወ/ት መስከረም ያረጋል (አባል)
    14. አቶ ሃይሉ ግዛው (የወረዳ ሰብሳቢ)
    15. አቶ አዲሱ መኮንን (የወረዳ ሰብሳቢ)
    16. አቶ ሲሳይ ካሴ (አባል)
    17. አቶ ወጋየሁ አድማሴ (አባል)
    18. አቶ ክብረት ሃይሉ (የም/ቤት አባል)
    19. አቶ ስለሺ ደቻሳ (አባል)
    20. አቶ ማሩ አካሉ (አባል)
    21. አቶ ክፍሉ በዳኔ (አባል)
    22. አቶ ፋሲካ አዱኛ (የወረዳ አመራር)
    23. ወ/ሮ ገነት ሞገስ (የወረዳ አመራር)
    24. ተስፋየ ብዙነህ (አባል)
    25. ሙሉጌታ ተፈራ
    26.ኤፍሬም ሰለሞን(የአዲስ አበባ ስራ አስፈፃሚ)

በተቃውሞ ሰልፉ ፖሊሶች ያደረሱትን ጉዳት በቅርብ ሲከታተሉ የነበሩት የተለያዩ ሀገራት ዲፕሎማቶች የአንድነት አመራሮችን እና ጉዳት ደርሶባቸው በየሆስፒታሉ የሚገኙ የአንድነት አባላትና ደጋፊዎችን አነጋግረዋል፡፡ የፓርቲው አመራሮች ከአባላትና ከደጋፊዎች ጋር ውይይት ያደረጉ ሲሆን አንድነት በአዲስ አበባ ተከታታይ የተቃውሞ ሰልፎችን እንደሚያደርግ ይፋ ተደርጓል፡፡ ይህንንም በተመለከተ ፓርቲው መግለጫ ያወጣ ሲሆን፤ ሙሉ መግለጫውን ከዚህ በታች ይመልከቱ፡-

udj

የፍትህና የነፃነት ጥያቄያችን ደም በማፍሰስ አይቀለበስም!!!

ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ

ፓርቲያችን አንድነት ገዥው ፓርቲ፣ ምርጫ ቦርድና የገዥው ፓርቲ ልሳን በመሆን እያገለገሉ ያሉ ሚዲያዎች በመተባበር ከምርጫ ለማስወጣትና ተለጣፊ አንድነት ለመፍጠር የሚደረገውን ጥረት በመቃወም የተቃውሞ ሰልፍ መጥራቱ የሚታወቅ ነው፡፡

የተቃውሞ ሰልፉን ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም እንደምናከናውን ለአዲስ አበባ መስተዳድር ብናሳውቅም መስተዳድሩ በ12 ሰዓት ውስጥ በፅሁፍ ምላሽ መስጠት ባለመቻሉ ሰልፉ እውቅና አለው፡፡ መስተዳድሩ ግን የተጣለበትን ሃላፊነት ከመወጣት ይልቅ ወደ ጎን በመግፋት የተወሰኑና የማይታወቁ ግለሰቦች ፔቲሽን ተፈራርመው አምጥተዋል በማለት ብዥታ ለመፍጠር ሞክሯል፡፡ ፓርቲያችን ህጉን ጠብቆ ህጋዊ የሆነ ሰልፍ ለማካሄድ ቢሞክርም አሁንም ሃላፊነት በጎደለው ሁኔታ የፓርቲያችን ከፍተኛ አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ጭካኔ በተመላበት ሁኔታ ከፍተኛ ድብደባ ተፈፅሞባቸዋል፡፡ በተደጋጋሚ እንዳየነው ፖሊስ ደንብ ማስከበር ሲገባው አድሎ ለፈፀመው አካል በመወገን ድብደባ መፈፀሙ ከወገንተኝነት ያልፀዳ መሆኑን እንድናረጋግጥ አድርጎናል፡፡

ጥያቄያችን አሁንም የፍትህ፣ የእኩልነትና ህግ እንዲጠበቅ የማድረግ ነው፡፡ ገዥው ፓርቲ የመንግስትነት ስልጣኑን በመጠቀም የስልጣን ዘመኑን ለማስረዘም እየከወነ ያለውን ሴራ ማስቆም ነው፡፡ ጥያቄያችን የነፃነትና ያልተሸራረፈ ዴሞክራሲ ይረጋገጥ የሚል ነው፡፡ ጥቄያችን ምርጫ ቦርድ የገዥው ፓርቲ አጋር መሆኑ ቀርቶ ገለልተኛ ሚናውን ይወጣ የሚል ነው፡፡ እነዚህ ጥያቄዎቻችን ደግሞ ደም በማሰስ፤ በድብደባም ሆነ በእስር ፈፅሞ አይቆሙም፡፡

በሚቀጥለው ሳምንትም በተለያዩ ከተሞችና በአዲስ አበባ የሰላማዊ ተቃውሞ ድምፃችንን ከፍ አድርገን እናሰማለን፡፡ ትግሉ ይቀጥላል፡፡
ድል የህዝብ ነው!!

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)

ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም.

አዲስ አበባ

%d bloggers like this: