ሰበር ዜና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዕቃ ጫኝ አውሮፕላን ተከሰከሰ
ዛሬ ቅዳሜ ጥር 2 ቀን 2007 ዓ.ም. ከረፋዱ 5 ሰዓት ላይ ከቶጎ ሎሜ ተነስቶ ጋና አክራ ይጓዝ የነበረው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 737-400F ዕቃ ጫኝ አውሮፕላን ተከሰከሰ፡፡ አውሮፕላኑ አደጋ የደረሰበት በመጥፎ የአየር ፀባይ መሆኑን በመጥቀስ አብራሪው በጋና ኮቶካ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ በሰላም ለማሳረፍ ጥረት በሚያደርግበት ወቅት መሆኑ የጋና አየር ማረፊያ ኮሚኒኬሽን ኦፊሰር ኒውማን ኳርቴይ ተናግረዋል፡፡
ኦፊሰሩ እንደተናገሩት ከሆነ የበረራ ቁጥር ET –AQV46 መሆኑን ጠቅሰው፤ የአውሮፕላኑ አብራሪን ጨምሮ በውስጡ የነበሩ 3 ሰራተኞች ከአደጋው ህይወታቸው መትረፉንና በጋና 37 ሚሊተሪ ሆስፒታል የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በአደጋውም 3ቱ ሰረተኞች የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው እንደሆነ ከመግለፅ በስተቀር ከአውሮፕላኑ መከስከስ በስተቀር በሌላ የሰው ሕይወት ላይ ያስከተለው ጉዳት ስለመኖሩ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ የተገለፀ ነገር የለም፡፡
አደጋው የደረሰበት የጋና አክራ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያም የሀገሪቱ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች የጦር ኃይል፣ፖሊስ፣ የደህንነትና የአቭየሽን ባለስልጣን በአካባቢው ተገኝተው ከሚያደርጉት ማጣራት በስተቀር መደበኛው ስራ መቀጠሉን ማረጋገጣቸውን የተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል፡፡
በምርጫ 2007 ዓ.ም. ኢህአዴግ የፈራውን ህዝባዊ አብዮት እየጠራ ነው
ብስራት ወልደሚካኤል
ከዚህ በፊት ኢህአዴግ ጠንካራ የሰላማዊ የፖለቲካ ታጋይ አመራሮችንና አባላቱን አሰረ፡፡ በመቀጠልም ጋዜጠኞችና የዞን 9 ብሎገሮችን አሰረ፡፡ ይህም አልበቃ ሲለው አሁን ደግሞ በራሱ ምርጫ ቦርድ ተወዳድረን እናሸንፍሃለን ብለው የቆረጡ ተፎካካሪዎችን ከምርጫ ለማስወጣት ባትሏል፡፡ ለዚህም ማሳያ አንድነት ፓርቲን አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባዔ ጥሩ ምናም…መኢአድን ደግሞ እናንተም ችግር የውስጥ ችግራችሁን ፍቱ፣…ሰማያዊ ፓርቲን ደግሞ ምርቻ ቦረድ በጠራው ስብሰባ ላይ ረግጣችሁ ጥታችኋልና ይቅርታ ካልጠየቃችሁኝ፣…ኃይማኖታዊ በዓል በሆነውና ከጥር 10-12 በሚከበረው የጥምቀት በዓል ዋዜማና ስነስርኣት ሰማያዊ ልብስ እንዳይለበስ የሚል ትዕዛዝ መስጠት፣…ዛሬ ደግሞ ለነገ ጠቅላላ ጉባኤ የጠራውን አንድነት ፓርቲ ላይ ለመሳተፍ የተንቀሳቀሰውን የአንድነት ፓርቲ የምስራቅ ቀጠና አደራጅ አዳማ/ናዝሬት ላይ ማገት፣…እያለ ጠንካራ የተባሉ የተፎካካሪ ፖለቲካ አባላትንና አመራሮችን ማገትና ማሰሩን ቀጥሏል፡፡ ከዚህ በፊት ከ200 ያላነሱ ጠንካራ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣አባላት፣ጋዜጠኞች፣ብሎገሮችንና አክቲቪስቶችን በግፍ ማሰሩ አይዘነጋም፡፡
በርግጥ ኢህአዴግ ድሮም ፈሪ ነው፡፡ የሚፈራው የኢትዮጵያን ህዝብ ብቻ ሳይሆን፤ ሐሳብን በራሱ ይፈራል፡፡ ለዚህም ነው ከእስክሪብቶና ወረቀት ውጭ በእጃቸው ምንም የሌላቸውን ንፁሃንን አሸባሪ እያለ ሚያስረው፡፡ አምባገነንቱና ጨካጭነጹ ከፍርሃትና ከድንቁርና የመኘጨ እንጂ የፖለቲካ ስትራቴጂ ሆኖ አይደለም፡፡ ይህ ግን በስልጣን ለመቆየት ዋስትና ሊሆን አይችልም፤ሆኖም አያውቅም፡፡ ይልቅ ጭቂና እና ጭካኔ በገዥዎች በተበራከተ ቁጥር ገና ወደፊት ይመጣል ተብሎ የተፈራውን ህዝባዊ አብዮት ራሱ ኢህአዴግ እያቀረበ ያለ ይመስለኛል፡፡ ምንም እንኳ የምርጫ እንቅስቃሴ መኖሩና ተፊካካሪዎች ወደ ውድድሩ ቢገቡ እንደ አንድ መልካም ነገር ቢታይም፤ ምርጫው ላይ ከበፊቱ የተለየ ውጤት ይኖራል ተብሎ ላይጠበቅ ይችላል፡፡ የምርቻ ሂደቱ በራሱ ግን ህዝቡን የፖለቲካ መብቱን እንዲጠይቅና እንዲጠቀም ከማድረግ አኳይ አዎንታዊ ሚና መኖሩ እሙን ነው፡፡
ህዝባዊ አብዮት ምንጊዜም የሚፈጠረው በገዥዎች ምክንያት ድንገት እንጂ በህዝቡ ታቅዶና ተፈልጎ አይደለም፡፡ ህዝቡ የአብዮቱ ምክንያት በሆኑ ገዥዎች ህዝባዊ እምቢተኝነት አንዱ አፀፋ ምላሽ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ ኢህአዴግ በርካታ የጦር መሳሪያ አለኝ ብሎ በአፈሙዝ አስቦና ተመክቶ ህዝባዊ አብዮትን ቢፈራም በራሱ ጊዜ እያፈጠነውና እየጠራው ያለ ይመስለኛል፡፡
አሁን ግን ኢህአዴግ ምርጫ ቦርድን፣ ፍርድ ቤትን፣ ደህንነትን፣ ፖሊስን፣ መከላከያን፣ሚዲያውን እና ኢኮኖሚውንም ይዞ ሊረጋጋ አልቻለም፡፡ የሚገርመው ህዝባዊ ደጀን ከጀርባቸው እንዳለ በማመን እስክሪብቶ፣ወረቀትና ሐሳብ የያዙትን ከጦር በላይ መፍራቱ እርግጥ ነው፡፡ ግን በመፍራት፣ ጭካኔና ኃላፊነት በጎደለው ስሜት የሚወሰዱ እርምጃዎችን ከፈሩት ነገር ለማምለጥ ዋስትና ከመሆን ይልቅ የፈሩትን ነገር የማምጣት ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡
ኢህአዴግ አሁን እያደረገ ያለው የእውር ድንብር ተግባሩ በራሱ ጊዜ የፈራውን ህዝባዊ አብዮት ከምን ጊዜውም በላቀ ሁኔታ እየጠራው ነው፡፡ ይሄም በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች፣አባላትና አመራሮች፣ በአክቲቪስቶችና ጋዜጠኞች ሳይሆን በራሱ በኢህአዴግ የከበረ ጥሪ እየተደረገለት ነው፡፡ በርግጥ ህዝባዊ አብዮት ድንገት የሚፈጠር ህዝባዊ አመፅ/እምቢተኝነት በመሆኑ አምባገነኖችን ድንገት ሳያስቡ ከስልጣን በማውረድ በበጎ ጎኑ ቢታይም የጦርነት ውጊያን ያህል ባይሆንም የሰው ህይወትና ንብረት ላይ ጉዳት ማድረሱ አይቀርም፡፡ ነገር ግን ራሳቸው አምባገነኖች በሚፈጥሩት ቅጥ ያጣ ጭቆና የሚመጣ በመሆኑ በፀጋ ከመቀበል ውጭ ሌላ አማራጭ ያለ አይመስለኝም፡፡ እነደ ሌሎቹ ስልጡናን የመንግስት ስርዓት ከጦርነት ክህዝባዊ አብዮት ይልቅ በሰለጠነው ነፃና ፍትሃዊ በሆነ የህዝብ ምርጫ ቢሆን መልካም ነበር፡፡ ነገር ግን የዚህ ሁሉ ዕድል ከተዘጋ የታፈነ ህዝብ ነገ ባልታሰበ ጊዜ ህዝባዊ እምቢተኝነት ወይም አመፅ ውስጥ መግባት አይቀሬ ነው፡፡ ለዚህ ተጠያቂ ደግሞ ራሱ ኢህአዴግና የበኩር ልጁ ምርጫ ቦርድ መሆናቸውን ማወቅ አለባቸው፡፡
አሁን አብዮቱን እየጠራ ያለው ኢህአዴግ ብቻ ሳይሆን ልጁ ታማኝ ልጁ ምርጫ ቦርድ በመሆናቸው በሀገሪቱና በህዝቡ ላይ ለሚፈጠሩ ጥፋቶች ተጠያቂዎቹ ተቋማቱ ብቻ ሳይሆኑ የኢህአዴግ አመራሮችና የምርጫ ቦርድ ዋና አመራሮችና እንደ የደረጃቸው ሌሎች የቦርዱና የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚዎች እንደየስራቸው ከተጠያቂነት ማምለጥ እንደማይችሉ ከወዲሁ ራሳቸውን መመርመርና የዓለማችንና የህዝባንን ነባራዊ ሁኔታ መገንዘብ ያለባቸው ይመስለኛል፡፡ አለበለዚያ እንደ ከዚህ ቀደሙ በንፁሃን ደም ነግዶ መኖርና ማላገጥ፣ ሀገርና ትውልድ አጥፍቶ አመልጣለሁ ማለት የማይቻልበት ጊዜ ላይ መድረሳችንንም ሊረሳ አይገባም፡፡ ስለዚህ በሀገሪቱ ላይ እስካሁን ከፈፀሙት በደል በተጨማሪ አሁንም ለመፈፀም ለተዘጋጁ ጥፋቶች ምርጫ ቦርና ኢህአዴግ ከነተባባሪዎቻቸው መቼም ቢሆን ከተጠያቂነት እንደማያመልጡ መረዳት አለባቸው፡፡ ምንክንያቱም እንደከዚህ ከቀደሙ በዝምታም ሆነ በፍራቻ የሚታለፍበት ጊዜ አልፏልና፡፡ ምናልባት ለመተንበይ አስቸጋሪ ቢሆንም በኢትዮጵያ የፖለቲካ ስርዓት ለውጡ የማይቀር እውነት ነው፡፡
መቼም በአሁን ጊዜ እንደቀድሞ በተጭበረረበር ምርጫና በካድሬ ውዳሴ ከንቱ ዳንኪራ ምርጫ አድርጌ አሸንፊያለሁ ማለት ለምርጫው የወጣውን ወጪ ከየትኛውም የኢኮኖሚ ኪሳራ በላቀ አጉልቶ ከማሳየት በስተቀር በስልጣን ለመቆየት ዋስትና ሊሆን አይችልም፡፡ ምርጫ አንዱ የዴሞክራሲያዊ የመነግስት ስርዓት ሽግግር መገለጫ እንጂ ብቸኛው ህዝብን የስልጣን ባለቤት ማድረጊያና አምባገነኖችን ከሚንደላቀቁበት ስልጣን ማስወገጃ መንገድ አይደለም፡፡ ይሄ ደግሞ ከማንም የሚሰወር አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም የተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ባይኖሩ እንኳ በርካታ የሰላማዊ ትግል ስልቶች እንደየወቅቱ፣እንደየሀገሩና ህዝቡ የሚተገበሩ አሉና፡፡ ስለሆነም መጪውን ጊዜ ስለሀገራችን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ በተለይም የፊታችን ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ለሚደረገው ምርጫ ሂደትና ሰኔ 15 ቀን 2007 ዓ.ም ይፋ ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ውጤት ከወዲሁ በጉጉት እንድንጠብቀው ግድ ብሎናል፡፡
ኦኬሎ አኳይ እጅና እግራቸውን ታስረው ጨለማ ክፍል መታሰራቸው ተገለፀ
-ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ከቤተሰብ ውጭ ጠያቂ ተከልክሏል
የቀድሞው የጋንቤላ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ኦኬሎ አኳይ እጅና እግራቸው ታስሮ ጨለማ ክፍል መታሰራቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ገለጹ፡፡
አቶ ኦኬሎ ቂሊንጦ በእስር ላይ እንደሚገኙ የሚታወስ ሲሆን፣ ሰውዬው ከሰሞኑ የርሃብ አድማ ማድረጋቸውን ተከትሎ በእስር በሚገኙበት እስር ቤት እጅና እግራቸውን ታስረው ብቻቸውን ጨለማ ክፍል እንዲገቡ እንደተደረጉ ምንጮች ተናግረዋል፡፡
ዛሬ ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም ወደ ቂሊጦ ማረሚያ ቤት እስረኞችን ሊጠይቁ ሄደው እንደነበር የገለጹት ምንጮች፣ እዚያው በእስር ላይ ካሉ ሰዎች አቶ ኦኬሎ ያሉበትን ሁኔታ መረዳታቸውን አክለው ገልፀዋል፡፡
በሌላ በኩል የ18 አመት እስር ፍርደኛው ታዋቂው ጋዜጠኛና የፖለቲካ ተንታኝ እስክንድር ነጋ ከቤተሰብ ውጭ ሌላ ሰው መጠየቅ እንደተከለከለ የነገረ-ኢትዮጵ ዘገባ አመልክቷል፡፡
አንድነት ፓርቲ በአንድ ወር ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ አስቸኳይ ልዩ ጠቅላላ ጉባዔ ጠራ
የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ ጠራ፡፡ ፓርቲው ነገ እሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤ በድጋሚ እንዲጠራ የተገደደው ገለልተኛ እንዳልሆነ ተደጋጋሚ ቅሬታዎች የቀረቡበትና እየቀረቡበት ያለው ምርጫ ቦርድ ባደረገበት ጫና መሆኑን በመግለጫው አስታውቋል፡፡
በተለይ በአሁን ወቅት በርካታ አመራሮቹና አባሎች የታሰሩበት አንድነት ፓርቲ፤ የፊታችን ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በሚደረገው ምርጫ ላይ ለመሳተፍ መወሰኑን እና በመላ ሀገሪቱም ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚወዳደሩ 450 ዕጩዎቹን ማዘጋጀቱንና ምርጫውንም በአሸናፊነት ለመወጣት ህዝቡን “2007 ለለውጥ ተደራጅ” በሚል መርህ ሰፊ ሀገራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡ ይህንንም ተከትሎ አንድነት ፓርቲ፣ ከኢህአዴግና ከምርጫ ቦርድ ጋር ባለው የፖለቲካ እንቅስቃሴ ከቀድሞ በበለጠ እየተካረረ መሄዱን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡ ይህንንም በተመለከተ ፓርቲው መግለጫ አውጥቷል፡፡ የፓርቲውን ሙሉ መግለጫ ከታች ይመልከቱ፡-
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ፖለቲካዊ ደባ አንድነት ከመስመር አይወጣም!
*******************************************************************************
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ መግለጫ
በየትኛውም የአለም ክፍል በተለያየ አጣራርና ስያሜ ቢሰጣቸውም ምርጫን ለማስፈፀም በሕግ የሚቋቋሙ ተቋማት ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ተቋማት በአንድ ሀገር ዘላቂ ለሆነ ሠላምና መረጋጋት ብሎም ለዴሞክራሲዊ ስርዓት ግንባታ ከፍተኛ ሚና ይጫወታሉ፡፡ እንደ ኢትዮጵያ በአንባገነን ስርዓት ውስጥ ላሉ ሀገሮች ደግሞ ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ያላቸው ሚና ከምንም በላይ ከፍተኛ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራው ምርጫ ቦርድ ይህን የመሰለ ግዙፍ ተግባር እንዲያከናውን፣ የሕዝብ እና የሀገር አደራ እንዲወጣ ኃላፊነት የተሰጠው ተቋም ነው፡፡ የዚህ ተቋም አሰራር በተቋቋመለት ዓላማ፣ ሕግ እና አለም አቀፍ መስፈርት መሠረት ነፃ፣ ገለልተኛ፣ ዴሞክራሲያዊ እና በህዝብ ዘንድ ተአማኒነት ያለው መሆን ይጠበቅበታል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቀደሙት አሠራሮችና ውሳኔ አሰጣጦች በበርካታ ኢትዮጵያውያን እና አለም አቀፍ ታዛቢዎች በአሉታዊ ጎኑ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የ2ዐዐ7 ሀገር አቀፍ ምርጫን ‹‹የኢህአዴግ መጨረሻ›› እናደርገዋልን ብሎ ፖለቲካዊ አቋም ወስዶ እንቅስቃሴ ሲጀምር የምርጫ ቦርድን ቀደምት አሉታዊ ተግባሩን ዘንግቶ አይደለም፡፡ ይህ ተቋም መልካም ስም እንዲገነባ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር በመሆን እድል ለመስጠት ነበር፡፡ በዚህ ስትራቴጂ መሠረት ቦርዱን በተግባር ፈተና ላይ ጥለነዋል፣ ማንነቱንም ለኢትዮጵያ ሕዝብ እና ለዓለም ማህበረሰብ በማጋለጥ ላይ እንገኛለን፣ ዛሬ ለሁለም የሚዲያ አካላት ያካሄድናቸውን የደብዳቤ ልውውጦች በይፋ አንሰጣለን፣ ሁሉም ዜጋ እንዲደርሰውም እናደርጋለን፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አንድነት ፓርቲን ከ2ዐዐ7 አጠቃላይ ምርጫ ገፍቶ ለማስወጣት ካልተሳካለትም በተዳከመ የአባላትና ደጋፊ ስሜት ውስጥ ገብተን እንድንጫወት የፈለገ ይመስላል፡፡ ይህ ደግሞ ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ የአንድነት ፓርቲ በ2ዐዐ7 ዓም ሀገራዊ ምርጫ ከጅምሩ በሁሉም ሂደቶች በንቁ ለመሳተፍ የያዘው አቋም እንዳስደነገጠው፤ ከዚያም አልፎ ከምንም በላይ ቅድሚያ የሚሰጠውን ስልጣን አጣለሁ በሚል መሸበሩን የሚያጋልጥ ነው፡፡ ይህን ፍርሃቱን በህዝብ ፊት በሚደረግ ትግል ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ የመረጠው ሜዳ በብሔራዊ ምርጫ ቦርደ በኩል እንዲሆን ነው፡፡ የቦርዱ ኃላፊዎች ተቋማዊ በሆነ መልክ ደብዳቤ ሲሰጣቸው፣ በደብዳቤ መልስ ከመስጠት ይልቅ በመገናኛ ብዙሃን ምላሻቸውን ቀድመው መናገር ጀምረዋል፡፡ ለዚህም ማሳያው ታህሣሥ 27 ቀን 2ዐዐ7 ዓም የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ የሆኑት ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዝአብሔር ከቦርዱ ስብሰባ በፊት በሚዲያ ወጥተው ውሳኔ በመገናኛ ብዙሃን ተናግረዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው ቦርዱ እንደተቋም ሳይሆን በግለሰብ ውሳኔ የሚመራ መሆኑን ነው፡፡ ለዚህም መገለጫው በታህሳስ 30/2007 የደረሰን ደብዳቤ የቦርዱን ምክትል ስብሳቢ ከሚዲያ መግለጫ ጋር ተመሳሳይ መሆኑ ነው፡፡ ከምርጫ ቦርድ ባልተናነሰ ሁኔታ በኢትዮጵያ በህግ የተቋቋሙት እና በህዝብ ሀብት የሚንቀሳቀሱት የመገናኛ ብዙሃንም በፍጥነት ተቀብለው ማስተጋባታቸው በውዥንብር ፈጠራ ላይ ተሳታፊነታቸውን ያሳያል፡፡ ዓላማው በአባላት፣ በደጋፊና በህዝቡ ውስጥ ውዥንብር ለመፍጠር ታሰቦ የሚካሄድ ፖለቲካዊ ደባ ነው፡፡
በሀገራችን አስተማማኝ ሠላም እና ዘላቂነት ያለው ደህንነት የሚያረጋግጠው እንደ ምርጫ ቦርድ ያሉ ተቋሞች ነፃ፣ ገለልተኛ እና በህዝብ ዘንድ አመኔታ ሲጣልባቸው ነው፡፡ ይህ ተቋም አሁን በያዘው ሁኔታ ከቀጠለ ከታሪክ ተጠያቂነት አይድንም፡፡ ገዢው ፓርቲም ጧት ማታ የሚያባንነው ሕዝባዊ እምቢተኝነት መምጣቱ አይቀሬ ነው፡፡ በመሆኑም አሁን ፓርቲያችንን ለመታደግ እና የቦርዱን የመጨረሻ ካርድ ለማስጣል አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለ2ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርተናል፡፡ ይህ ማለት የትግሉ መጨረሻ አይደለም፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያደረሰብንን የሕግ ጥሰት ይዘን በፍርድ ቤት ክስ እንመሰርታለን፡፡ እስከ አሁን ያለውን ሂደት ስናየው የቦርዱ ፖለቲካዊ ደባ ቀጣይ እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡ ስለሆነም መላው አባሎቻችን፣ ደጋፊዎቻችን እና የኢትዮጵያ ሕዝብ ለምንወስዳቸው ተከታታይ ፖለቲካው ውሳኔዎች እና እርምጃዎች ከጎናችን እንዲቆም ጥሪያችንን በአክብሮት እናስተላልፋለን፡፡
ድል የሕዝብ ነው
ጥር 1 ቀን 2ዐዐ7 ዓም
አዲስ አበባ
አባቶችና ምእመናን ‹‹ሸኚው ሸኚ ሲያጣ›› እስኪሉ ድረስ በመጣደፉ በእጅጉ ያዘኑበት የ106 ዓመት አረጋዊው የአቡነ አረጋዊ ሥርዐተ ቀብር ተፈጸመ
ዜና ሕይወቱ ወዕረፍቱ ለብፁዕ አቡነ አረጋዊ ሊቀ ጳጳስ
ብፁዕ አቡነ አረጋዊ በ1901 ዓ.ም. በፀለምት (ሰሜን ጎንደር) ተወልደው ዕድሜአቸው ለትምህርት ሲደርስ ትምህርት ቤት ገብተው ንባብና ዳዊት እንዲኹም ፀዋትወ ዜማ አጠናቅቀው ከብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ግብፃዊ ማዕርገ ዲቁናና ማዕርገ ቅስና ተቀብለዋል፡፡
በዋልድባ አብረንታንት ገዳም ገብተው ለዘጠኝ ዓመታት ያኽል (ከ1933 – 1942 ዓ.ም.) ሥርዓተ ገዳሙን ከአጠኑና በግብዝና ከአገለገሉ በኋላ በዚኹ ገዳም መዓርገ ምንኵስናን ተቀብለዋል፡፡ ትምህርታቸውን በመቀጠል በሰሜን ምዕራብ ትግራይ በሚገኘው በደብረ ዓባይ ገዳም የደብረ ዓባይ መዝገበ ቅዳሴ ዜማ ተምረው በመምህርነት ተመርቀዋል፡፡
በ1943 ዓ.ም. በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ባስልዮስ ፈቃድና ትእዛዝ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትን እንዲያገለግሉ ተልከው ለአራት ዓመታት ያኽል አገልግለዋል፡፡ አኹንም በቅዱስ ፓትርያርኩ ፈቃድ ወደ ግብጽ ሔደው ለ16 ዓመታት ያኽል ነገረ መለኰትን በዓረብኛ ቋንቋ አጥንተው ተመርቀዋል፡፡
ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሱ በኋላ በሱዳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በሓላፊነት ለማገልገል ተልከው ለስድስት ዓመታት ያኽል በአስተዳዳሪነት ሠርተዋል፡፡ በዚኹ ሓላፊነት ሳሉም በ1968 ዓ.ም. ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የኢትዮጵያ ፓትርያርክ ኹነው በተሾሙ ጊዜ በሱዳን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ወክለው በመምጣት ለበዓሉ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርገዋል፡፡
በ1972 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው በቅዱስ ፓትርያርኩ ፈቃድ የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሊቀ ሥልጣናት በመኾን አገልግለዋል፡፡
በጥቅምት ወር 1983 ዓ.ም. በሱዳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ኾነው በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አንብሮተ እድ ተሾመዋል፡፡
ከመጋቢት 1985 ዓ.ም. ጀምሮ የኢሉባቦርና የጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ኾነው ለአንድ ዓመት ያኽል ሠርተዋል፡፡
ከየካቲት 1986 ዓ.ም. ጀምሮ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳምና ት/ቤት የበላይ ሓላፊ ኾነው አገልግለዋል፡፡
ከሐምሌ 1968 ዓ.ም. ጀምሮ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ኾነው አገልግለዋል፡፡
ከግንቦት 1992 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ አዲስ አበባ ተዛውረው የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ሓላፊ ኾነው ሲሠሩ ቆይተዋል፡፡
በመጨረሻም በዚኹ ሥራ ላይ ሳሉ ባደረባቸው ድንገተኛ ሕመም ምክንያት በሕክምና ሲረዱ ቆይተው ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም. በተወለዱ በ106 ዓመታቸው ከዚኽ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል፡፡
የቀብራቸው ሥነ ሥርዓትም በዚኹ ዕለት፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ባሉበትና የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች በተገኙበት ሥርዓተ ጸሎተ ፍትሐቱ ከተፈጸመ በኋላ በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡
ምንጭ፡- ሐራ ተዋህዶ