Monthly Archives: January, 2015

ምርጫ ቦርድ በሶስቱ የተፎካካሪ ፓርቲዎች ላይ ውሳኔ ማሳለፉን አስታወቀ

nebe

ዛሬ ጥር 5 ቀን 2007 ዓ.ም. ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በአንድነት፣ በመኢአድ እና ሰማያዊ ፓርቲዎች ላይ ውሳሳለፉን አስታውቋል፡፡ ቦርዱ ውሳኔ ብሎ ያስተላለፈው ፤ አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) እንዲሁም የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የውስጥ ችግራቸውን መፍታት አልቻሉም በሚል ለዛሬው ውሳኔ እሰጣለሁ ብሎ የነበረው ምርጫ ቦርድ ሁለቱ ፓርቲዎች በሁለት ሳምንት ውስጥ የውስጥ ችግራቸውን ፈትተው ሌላ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያደርጉ የመጨረሻ ጊዜ ሰጥቻቸዋለሁ ሲል ገልጾአል፡፡

ቦርዱ ዛሬ ከሰዓት በሰጠው መግለጫ በአንድነትና መኢአድ ስም የተለያዩ ጉባኤዎች በመደረጋቸው ሁለቱ ፓርቲዎች ጥር 3 ያደረጉትን ጠቅላላ ጉባኤ ላይ አለመገኘቱን፣ አንድነት የ2004 ዓ.ም እንዲሁም የመኢአድን የ2001 ዓ.ም ደንብን እንጅ ከዛ በኋላ ያሉትን የፓርቲውን ደንቦች እንደማያውቅ በመግለጽ በሁለት ሳምንት ውስጥ ጠቅላላ ጉባኤ አድርገው ችግራቸውን እንዲፈቱ የመጨረሻ ጊዜ ሰጥቻለሁ ብሏል፡፡

በሌላ በኩል መድረክ ረግጦ በመውጣት፣ ሌሎች ፓርቲዎች እንዲያድሙ በማድረግ፣ ቦርዱ የማያውቀው ትብብር በመመስረት በሚል በምርጫ ቦርድ ክስ የቀረበበትና ይቅርታ እንደማይጠይቅ በደብዳቤ ለገለጸው ሰማያዊ ፓርቲ የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ሰጥቻለሁ ብሏል፡፡ ማስጠንቀቂያውን የማያከብር ከሆነም ቦርዱ ህጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ ብሏል፡፡

የቦርዱ ባለስልጣናት ‹‹ሰማያዊ ፓርቲን ህገ ወጥ ትብብር በመመስረት ስትከሱ ሌሎቹን የትብብሩን አባል ፓርቲዎች ለምን አልከሰሳችሁም?›› በሚል ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና ‹‹ፓርቲዎቹ 9 መሆናቸውን የሰማሁት አሁን ነው፡፡›› ብለዋል፡፡ በተመሳሳይ ‹‹እስካሁን ሌሎች ትብብሮችን ምርጫ ቦርድ አያውቃቸውም ብላችሁ ከሳችሁ አታውቁም›› በሚል የ9ኙን ፓርቲዎች ትብብር ህገ ወጥ ነው ካሉ ገዠው ፓርቲ ከአጋሮቹ ጋር ያለውን ግንኙነትን ለምን ህገ ወጥ ነው እንደማይሉ ለቀረበላቸው ጥያቄም ፕሮፌሰር መርጋ በቃና ‹‹ኢህአዴግ እንደገዥ ፓርቲ አጋር ፓርቲዎች ሊኖሩት ይቻላል፡፡ እንደ ገዥ ፓርቲ ከአጋሮች ጋር መስራት ይችላል፡፡ እንዲህ አይነት ነገሮችን ቦርዱ አይመለከተውም›› ሲሉ መልሰዋል፡፡

አንድነትና መኢአድ በሁለት ሳምንት ውስጥ ችግራቸውን እንዲፈቱ ተጨማሪ ጊዜ ሰጥቻለሁ ያለው ምርጫ ቦርድ በሁለት ሳምንት ውስጥ ችግራቸውን ካልፈቱ ቦርዱ ተሰብስቦ ውሳኔውን አሳውቃለሁ ማለቱን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ ያመለክታል፡፡ አንድነት እና መኢአድ ምርጫ ቦርድ እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባዔ አድርጉ ባለው መሰረት ያለፈው እሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ባደረጉት ጠቅላላ ጉባኤ አንድነት ፓርቲ በድጋሚ አቶ በላይ ፈቃዱን ፕሬዘዳንት አድርጎ ሲመርጥ፤ መኢአድም እንዲሁ በተመሳሳይ ቀን ጠቅላላ ጉባዔ ያደረገ ሲሆን፤ በዕለቱ ምርጫ ቦርድ በህጉ መሰረት በሁለቱም ፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባኤ ላይ እንዲገኝ የጥሪ ደብዳቤ ቢደርሰውም በሁለቱም ጉባኤ ላይ የቦርዱ ተወካይ እንዳልተገኘ ታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ ቦርዱ አሁንም ለሶስተኛ ጊዜ ሁለቱም ፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባዔ እንዲያደርጉ የሁለት ሳምንት ጊዜ ሰጥቻቸዋለሁ ሲል ዛሬ በፅህፈት ቤቱ ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡

…….

የአንድነት ፓርቲ ሁለት አባላት ድብደባ ተፈፀመባቸው

ወይንሸት ስለሺ በህክምና ዕርዳታ ላይ

ወይንሸት ስለሺ በህክምና ዕርዳታ ላይ

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ (አንድነት) ፓርቲ የሴቶች ጉዳይ ምክትል ኃላፊ ወይንሸት  ስለሺ እና የፓርቲው አባል መሳይ ትኩ ባልታወቁ ሰዎች መደብደባቸው ተሰማ፡፡  ወጣት መሳይ ትኩ ባለፈው እሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. አንድነት ፓርቲ የጠራውን ጠቅላላ ጉባኤውን አጠናቆ ወደ ቤቱ ሲጓዝ አዲስ አበባ ራስ መኮንን ድልድይ አካባቢ ባልታወቁ ሰዎች ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈፀመበት ፓርቲው አስታውቋል፡፡

በተመሳሳይ ዜና በፓርቲው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የነበረችና በፓርቲው ንቁ ተሳትፎ እያደረገች የምትገኘው የሴቶች ጉዳይ ምክትል ኃላፊ ወይንሸት ስለሺ ጥር 6 ቀን 2007 ኣ.ም. ከረፋዱ 5፡30 ላይ አዲስ አበባ በተለምዶ ነፋስ ስልክ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ባልታወቁ ሁለት ሰዎች ከፍተኛ ድብደባ እንደደረሰባት የፍኖተ ነፃነት ዘገባ አመልክቷል፡፡ ወይንሸት ነፍሰጡር መሆኗንና ሆዷ ላይም ከፍተኛ ድብደባ በመፈፀሙ በአሁን ወቅት ራሷን ስታ ሆስፒታል የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላት መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

መሳይ ትኩ

መሳይ ትኩ

ሁለቱም የፓርቲው አባላት በፓርቲው እንቅስቃሴ ላይ ንቁ ተሳትፎ እንደነበራቸው በመግለፅ፤ በተለይ ወጣት መሳይ ምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ አንድነት መጪውን 2007 ኣ.ም. በሚደረገው ምርጫ እንዳይሳተፍ የሚደረገውን ሴራ ቀድሞ በማጋለጡ የተወሰደበት እርምጃ እንደሆነ የፍኖተ ነፃነት ዘገባ አመልክቷል፡፡ ወይንሸትም በፓርቲው ፕሬዘዳንታዊ ምርጫ አስመራጭ ኮሚቴ ሆና ከማገልገሏ በተጨማሪ በፓርቲው ላይ የሚደረጉ አፍራሽ እንቅስቃሴዎችን በማውገዝ አስተያየት መሰንዘሯ ለተፈፀመባት ድብደባ ምክንያት ሳይሆን እንዳልቀረ የፓርቲው ልሳን መረጃ አመልክቷል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ይቅርታ እንደማይጠይቅ አስታወቀ

የሰማያዊ ፓርቲ ዓርማ

የሰማያዊ ፓርቲ ዓርማ

ሰማያዊ ፓርቲ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጽሕፈት ቤትን እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ በጽሑፍ ይቅርታ ይጠይቅ በማለት የተላለፈው ውሳኔ ከሕግ አግባብ ውጪ ስለሆነ ተቃውሞውን በመግለጽ ይቅርታ እንደማይጠይቅ አስታወቀ፡፡

የቦርዱ የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ደምሰው በንቲ ባለፈው ሐሙስ በጽሕፈት ቤታቸው በሰጡት መግለጫ፣ ሰማያዊ ፓርቲ የምርጫ ቦርድን ስም አጥፍቷል ብለዋል፡፡ ‹‹በተሻሻለው የምርጫ ሕግ አንቀጽ 102 (4)ሀ፣ ለ እና ሠ እንዲሁም 102 (6) ሐ መሠረት የፖለቲካ ፓርቲዎች የቦርዱን ሥልጣን መቀበል፣ ሕጋዊ ትዕዛዙንና መመርያውን የማክበር ግዴታ እንዳለባቸው፣ እንዲሁም ቦርዱ በሚያዘጋጃቸው የጋራ የምክክር መድረኮች ወይም ሌሎች መድረኮች ላይ ወኪል የመላክ ኃላፊነት እንዳለባቸውና በሐሰት ስም ከማጥፋት መቆጠብ እንዳለባቸው ያመለክታሉ፤›› ብለዋል፡፡

‹‹ሰማያዊ ፓርቲ ግን ቦርዱ በተለያዩ ጊዜያት ያዘጋጃቸውን የጋራ ምክክሮች እንዲበተኑ ሙከራ አድርጓል፣ እየረገጠ ወጥቷል፣ በሐሰት ቦርዱን ወንጅሏል፡፡ እንዲሁም የስም ማጥፋት ዘመቻ አድርጓል፤›› በማለት ፓርቲው በጽሑፍ ይቅርታ እንዲጠይቅ ቦርዱ ወስኗል በማለት አስታውቀዋል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ውሳኔውን አስመልክቶ፣ ‹‹እኛ ይህን የምንረዳው የምርጫ ቦርድ የራሱ አቋም ሳይሆን ኢሕአዴግ በቦርዱ ውስጥ ምን ያህል ሚና እንዳለው ያጋለጠ ውሳኔ መሆኑን ነው፤›› በማለት ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡

‹‹ቀደም ባሉት ጊዜያት የሰጠነው አስተያየትና ስብሰባ ረግጠን መውጣታችን ዘለፋ መስሎ ከተሰማቸው አትዝለፉን እንነጋገር ማለት መልካም ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ ጊዜ ውስጥ ይቅርታ ጠይቁኝ ብሎ ማስፈራራት አገራችንን አሳፋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚከት ነው፡፡ ይቅርታ መቀለጃ አይደለም፡፡ እኛም በዚህ ምክንያት አናስተናግደውም፤›› ብለዋል፡፡

‹‹በተጨማሪም በመሠረቱ እኛ አንድ ድርጅት ነን፡፡ ምርጫ ቦርድም እንዲሁ አንድ ድርጅት ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ድርጅቶች ሊግባቡ የሚችሉት ደግሞ በሕግና በደንብ ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ካጠፋ ወይ ወደ ፍርድ ቤት ይሄዳል፣ ወይም ቦርዱ ባለው ሥልጣን ችግሩ ይፈታል፡፡ ቦርዱም ካጠፋ እንዲሁ፡፡ ከዚህ ውጪ ይቅርታ ጠይቀኝ ብሎ መጠየቅ ፍፁም ተቋማዊ አሠራር አይደለም፤›› በማለት ውሳኔውን ፓርቲያቸው እንደሚቃወም አስታውቀዋል፡፡

አንድነት ፓርቲ በድጋሚ በጠራው አስቸኳይ ልዩ ጠቅላላ ጉባዔ ፕሬዘዳንቱን በመምረጥ ተጠናቀቀ

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዓርማ

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዓርማ

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በመጪው ምርጫ ግንቦት 2007 ዓ.ም. ለመሳተፍ መወሰኑን እና ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚወዳደሩ 450 ዕጩዎቹን በአራቱም የሀገሪቱ አቅጣጫ ማቅረቡን ይፋ ካደረገ በኋላ ምርጫ ቦርድ ፓርቲው እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ በድጋሚ ጠቅላላ ጉባዔ አድርጎ የፓርቲውን ፕሬዘዳንቱን ካለተመረጠ ምርጫው ላይ እንዳይሳተፍ አደርጋለሁ ባለው መሰረት ዛሬ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. አዲስ አበባ ቀበና በሚገኘው የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት አዳራሽ ጠቅላላ ጉባዔው መካሄዱ ታውቋል፡፡ ፓርቲውን ለመምራት በዕጩነት ቀርበው የተወዳደሩት አቶ በላይ ፈቃዱ፣ አቶ አለነ ማህፀንቱ እና አቶ ዳግማዊ ተሰማ መሆናቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ከተደረገው የአንድነት ጠቅላላ ጉባዔ በከፊል

ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ከተደረገው የአንድነት ጠቅላላ ጉባዔ በከፊል

ለፕሬዘዳንትነት የተወዳደሩት ሶስቱም ዕጩዎች በወጣትነት የዕድሜ ክልል ላይ የሚገኙ ሲሆን፤ በትምህርታቸው የማስተርስ ድግሪ፣ በፖለቲካ ተሳትፎ ሶስቱም በአንድነት ፓርቲ በተለያየ ከፍተኛ አመራርነት ያገለገሉ ሲሆን፣ በሙያቸውም የተለያዩ ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ተቋማት ላይ ማገልገላቸው ተጠቁሟል፡፡ በመጨረሻም በነበረው ውድድር አቶ አለነ ማህፀንቱ ራሳቸውን በገዛ ፈቃዳቸው ከውድድሩ ውጭ በማድረግ በአቶ በላይ ፈቃዱና በአቶ ዳግማዊ ተሰማ መካከል በተደረገ የምረጡኝ ቅስቀሳና ውድድር የጠቅላላ ጉባዔው አባላት ባደረጉት የምስጢር ድምፅ አሰጣጥ መሰረት አቶ በላይ 183 ድምፅ በማግኘት የአንድነት ፕሬዘዳንት ሆነው ተመርጠዋል፡፡ አንድነት መተዳደሪያ ደንብ መሰረት የጠቅላላ ጉባዔው አባላት 320 ሲሆን፤አቶ በላይም የአባላቱን 57.2 በመቶ ድምፅ በማግኘት አሸንፈዋል፡፡

ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ከተደረገው የአንድነት ጠቅላላ ጉባዔ በከፊል

ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ከተደረገው የአንድነት ጠቅላላ ጉባዔ በከፊል

ውጤቱን ተከትሎም ተፎካካሪያቸው የነበሩት አቶ ዳግማዊ ተሰማ ለአቶ በላይ ፈቃዱ የእንኳን ደስ ያሎት መልዕክት በማስተላለፍ መጪውን ምርጫ አንድነት ፓርቲ አሸናፊ ሆኖ እንዲወጣ በጋራ ጠንክረው መስራት እንዳለባቸውና ለዚህም በፓርቲው የሚሰጣቸውን የስራ ድርሸና ተልዕኮ ለመወጣት ዝግጁ እንደሆኑ መግለፃቸውን ከስፍራው የአዲስሚዲያ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በመጨረሻም አቶ በላይ ፈቃዱ ፓርቲውን በፕሬዘዳንትነት ለመምራት ቃለ መሐላ መፈፃማቸው ታውቋል፡፡

አዲሱ የአንድነት ፓርቲ ተመራጭ ፕሬዘዳንት አቶ በላይ ፈቃዱ ቃለ መሐላ ሲፈፅሙ

አዲሱ የአንድነት ፓርቲ ተመራጭ ፕሬዘዳንት አቶ በላይ ፈቃዱ ቃለ መሐላ ሲፈፅሙ

በጉባዔው ላይ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ዲፕሎማቶችና ጋዜጠኞች እንዲሁም ሌሎች ተጋባዦች የተገኙ ሲሆን፤ በሀገሪቱ የምርጫ ቦርድ ህግ መሰረት ሂደቱን መታዘብ የነበረበት ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሂደቱን ለመታዘብ እንደማይገኝና ወኪልም እንደማይልክ ቀደም ሲል ከፓርቲው ለተደረገለት ጥሪ በደብዳቤ ማሳወቁ ተጠቁሟል፡፡ ቀደም ሲል ታህሳስ 2006 ዓ.ም. የፓርቲው ፕሬዘዳንት የነበሩት ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው ስልጣናቸውን በገዛ ፈቃዳቸው በመልቀቅ ለፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት ካስረከቡ በኋላ አቶ በላይ ፈቃዱ ያለፉት 3 ወራት የፓርቲው ፕሬዘዳንት ሆነው ማገልገላቸው አይዘነጋም፡፡

በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ታሪካዊ የሆነው ጣይቱ ሆቴል የእሳት አደጋ ደረሰበት

አዲስ አበባ ፒያሳ የሚገኘው ጣይቱ ሆቴል በእሳት ሲቃጠል

አዲስ አበባ ፒያሳ የሚገኘው ጣይቱ ሆቴል በእሳት ሲቃጠል

ዛሬ እሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ከረፋዱ 5 ሰዓት አካባቢ በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመሪያው ዘመናዊ ሆቴል የሆነው ጣይቱ ሆቴል የእሳት አደጋ ቃጠሎ ደርሶበታል፡፡ ሆቴሉ ነሐሴ1898 ዓ.ም. በንጉሱ ዳግማዊ አጼ ምኒልክ ባለቤት እቴጌ ጣይቱ ብጡል አማካኝነት ጣይቱ ሆቴል በሚል በአዲስ አበባ መሐል ፒያሳ ተመስርቶ ኢህአዴግ ስልጣን እስኪይዝ ድረስ በመንግስት ስር የሚተዳደር ሆቴል የነበረ ሲሆን ፤ ህወሓት/ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ በኋላ ግን ወደ ግል በማዞር አቶ ፍፁምዘዓብ አስገዶም ለተባሉ ግለሰብ መሸጡ ይታወሳል፡፡

በወቅቱ በርካታ የታሪክ ባለሙያዎችና የተፎካካሪ ፖለቲካ ድርጅት አባላትና አመራሮች የሀገሪቱ ታሪክ ቅርስ አካል ተደርጎ የተመዘገበን ሆቴል በርካሽም ሆነ በውድ መሸጥ ተገቢ እንዳልሆነ አጥብቀው ቢከራከሩም በኢህአዴግ ተቀባይነት ሳያገኝ ቢቀርም ዛሬ ከባድ የሚባል የእሳት አደጋ ቃጠሎ ደርሶበታል፡፡ የአዲስ አበባ እሳትና ድንገተኛ አደጋ ከሆቴሉ ያለው ርቀት ከ1 ኪሎ ሜትር የማይበልጥ ቢሆንም በፍጥነት መጥቶ መከላከል ባለመቻሉ ሆቴሉን ጨምሮ ከአደጋው መትረፍ የሚችሉ በርካታ ንብረቶች መውደማቸውን ከስፍራው የዓይን እማኞች ገልፀዋል፡፡

በአሁን ወቅት የጣይቱ ሆቴል ባለቤት የሆኑት አቶ ፍፁምዘዓብ አስገዶም የቀድሞ የህወሃት ከፍተኛ አመራር የነበሩት አቶ ስየ አብርሃ ታናሽ ወንድም የአቶ አሰፋ አብርሃ ባለቤት ወንድም ሲሆኑ፤ ከአቶ አሰፋ አብርሃ ጋር በተያያዘ ሆቴሉን ሲገዙ ሙስና ፈፅመዋል በሚል ለ6 ዓመታት ታስረው መለቀቃቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ በሆቴሉ ላይ ከባድ የሚባል የእሳት አደጋ መድረሱ የታወቀ ቢሆንም፤የአደጋው መንስኤ፣በአደጋው የወደመው ንብረት በአሀዝም ሆነ በዓይነት ምን ያህል እንደሆነ ለማወቅ አልተቻለም፡፡